በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አልዓዛር ከሞት ሲነሣ

አልዓዛር ከሞት ሲነሣ

ምዕራፍ 91

አልዓዛር ከሞት ሲነሣ

ኢየሱስ አብረውት ካሉት ሰዎች ጋር ሆኖ የአልዓዛር የመታሰቢያ መቃብር ወዳለበት ቦታ ደረሰ። መቃብሩ መግቢያው በድንጋይ የተዘጋ ዋሻ ነበር። ኢየሱስ “ድንጋዩን አንሡ” አላቸው።

ማርታ አሁን ኢየሱስ ምን ለማድረግ እንዳሰበ ስላልገባት ሐሳቡን ተቃወመች። “ጌታ ሆይ፣ ከሞተ አራት ቀን ሆኖታልና አሁን ይሸታል” አለችው።

ሆኖም ኢየሱስ “ብታምኚስ የእግዚአብሔርን ክብር እንድታዪ አልነገርሁሽምን?” አላት።

ስለዚህ ድንጋዩን አነሱት። ከዚያም ኢየሱስ ዓይኖቹን ወደ ላይ አንስቶ እንዲህ ሲል ጸለየ:- “አባት ሆይ፣ ስለ ሰማኸኝ አመሰግንሃለሁ። ሁልጊዜም እንድትሰማኝ አወቅሁ፤ ነገር ግን አንተ እንደ ላክኸኝ ያምኑ ዘንድ በዚህ ዙሪያ ስለ ቆሙት ሕዝብ ተናገርሁ።” ኢየሱስ ቀጥሎ የሚያከናውነው ነገር ከአምላክ ባገኘው ኃይል አማካኝነት የሚፈጸም መሆኑን ሕዝቡ እንዲያውቁ ሲል የጸለየው በሕዝብ ፊት ነበር። ከዚያም በታላቅ ድምፅ “አልዓዛር ሆይ፣ ወደ ውጭ ና” ብሎ ጮኸ።

በዚህ ጊዜ አልዓዛር ወጣ። እጆቹና እግሮቹ በመግነዝ እንደተገነዙ ነበር፤ ፊቱም በጨርቅ ተሸፍኖ ነበር። ኢየሱስ “ፍቱትና ይሂድ ተዉት” አላቸው።

ይህን ተአምር ሲመለከቱ ማርያምንና ማርታን ለማጽናናት መጥተው ከነበሩት አይሁዶች መካከል ብዙዎቹ በኢየሱስ አመኑ። ሌሎቹ ግን የተፈጸመውን ነገር ለፈሪሳውያን ለመንገር ሄዱ። ፈሪሳውያንና የካህናት አለቆቹ ወዲያውኑ ሳንሄድሪን የተባለው የአይሁድ ከፍተኛ የፍርድ ሸንጎ እንዲሰበሰብ ጥሪ አደረጉ።

ሳንሄድሪን የተባለው የፍርድ ሸንጎ የወቅቱ ሊቀ ካህናት የሆነውን ቀያፋን እንዲሁም ፈሪሳውያንንና ሰዱቃውያንን፣ የካህናት አለቆችንና የቀድሞ ሊቃነ ካህናትን በአባልነት ያቀፈ ነበር። እነዚህ ሰዎች “ምን እናድርግ? ይህ ሰው ብዙ ምልክቶች ያደርጋልና። እንዲሁ ብንተወው ሁሉ በእርሱ ያምናሉ፤ የሮሜም ሰዎች መጥተው አገራችንን ወገናችንንም ይወስዳሉ” በማለት በምሬት ተናገሩ።

ምንም እንኳ የሃይማኖት መሪዎቹ ኢየሱስ “ብዙ ምልክቶች” እንደሚፈጽም አምነው ለመቀበል ቢገደዱም እነሱን ያሳሰባቸው ነገር የራሳቸው ቦታና ሥልጣን ብቻ ነበር። ሰዱቃውያን በትንሣኤ የማያምኑ ሰዎች ስለነበሩ የአልዓዛር ትንሣኤ በተለይ ለእነሱ ታላቅ ሽንፈት ነበር።

ቀያፋ (ሰዱቃዊ ሳይሆን አይቀርም) በዚህ ጊዜ እንዲህ አለ:- “እናንተ ምንም አታውቁም፤ ሕዝቡም ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው ስለ ሕዝቡ ይሞት ዘንድ እንዲሻለን አታስቡም።”

ሐዋርያው ዮሐንስ ከጊዜ በኋላ “[ቀያፋ] ይህንም የተናገረ ከራሱ አይደለም” በማለት ጽፏል፤ ስለዚህ ቀያፋ ይህን እንዲናገር የገፋፋው አምላክ ነበር። ቀያፋ ይህን ሲናገር የሥልጣንና የአመራር ቦታቸውን ይበልጥ እንዳያዳክምባቸው ለመከላከል ኢየሱስ መገደል እንዳለበት መናገሩ ነበር። ሆኖም ዮሐንስ እንደገለጸው ‘ቀያፋ ትንቢት የተናገረው ኢየሱስ ለሕዝቡ ብቻ ሳይሆን የአምላክ ልጆች አንድ ላይ መሰብሰብ እንዲችሉ ጭምር የሚሞት መሆኑን ነው።’ በእርግጥም አምላክ ልጁ ለሁሉም ቤዛ ሆኖ እንዲሞት ዓላማው ነው።

አሁን ቀያፋ የሳንሄድሪን ሸንጎ ኢየሱስን ለመግደል እንዲወስን ለማግባባት ቻለ። ሆኖም ኢየሱስ ይህን ሴራ ወዳጁና የሳንሄድሪን ሸንጎ አባል ከሆነው ከኒቆዲሞስ ሳይሰማ አይቀርም። ስለዚህ አካባቢውን ለቆ ሄደ። ዮሐንስ 11:​38-54

▪ ኢየሱስ አልዓዛርን ከማስነሣቱ በፊት በሕዝብ ፊት የጸለየው ለምንድን ነው?

▪ ይህን ትንሣኤ የተመለከቱ ሰዎች ምን ተሰማቸው?

▪ የሳንሄድሪን ሸንጎ አባላትን ክፋት የሚያሳየው ምንድን ነው?

▪ የቀያፋ ዓላማ ምን ነበር? ሆኖም አምላክ ምን ትንቢት እንዲናገር ተጠቅሞበታል?