በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ኢየሱስና ኮከብ ቆጣሪዎቹ

ኢየሱስና ኮከብ ቆጣሪዎቹ

ምዕራፍ 7

ኢየሱስና ኮከብ ቆጣሪዎቹ

በርከት ያሉ ሰዎች ከምሥራቅ መጡ። እነዚህ ሰዎች የከዋክብትን አቀማመጥ ትርጉም እናውቃለን የሚሉ ኮከብ ቆጣሪዎች ነበሩ። በምሥራቅ በኩል አገራቸው ሳሉ አንድ አዲስ ኮከብ ተመለከቱ። ከዚያም እሱን ተከትለው በመቶዎች የሚቆጠሩ ኪሎ ሜትሮች ከተጓዙ በኋላ ኢየሩሳሌም ደረሱ።

ኮከብ ቆጣሪዎቹ ኢየሩሳሌም ሲደርሱ እንዲህ ሲሉ ጠየቁ:- “የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው? ኮከቡን በምሥራቅ አይተን ልንሰግድለት መጥተናል።”

በኢየሩሳሌም የነበረው ንጉሥ ሄሮድስ ይህን ሲሰማ ደነገጠ። ስለዚህ የካህናት አለቆችን ጠርቶ ክርስቶስ የሚወለደው የት እንደሆነ ጠየቃቸው። በ“ቤተ ልሔም ነው” ብለው በቅዱሳን ጽሑፎች ላይ የተመሠረተ መልስ ሰጡት። በዚህ ጊዜ ሄሮድስ ኮከብ ቆጣሪዎቹን አስጠርቶ “ሂዱ፣ ስለ ሕፃኑ በጥንቃቄ መርምሩ፤ ባገኛችሁትም ጊዜ እኔ ደግሞ መጥቼ እንድሰግድለት ንገሩኝ አላቸው።” ሆኖም ሄሮድስ ልጁን ለማግኘት የፈለገው ሊገድለው አስቦ ነበር!

ኮከብ ቆጣሪዎቹ ከሄዱ በኋላ አንድ አስገራሚ ነገር ተፈጸመ። በምሥራቅ ሳሉ የተመለከቱት ኮከብ ከፊት ከፊታቸው ይሄድ ጀመር። ይህ ኮከብ እነሱን ለመምራት ሆን ተብሎ የተዘጋጀ እንጂ ተራ ኮከብ እንዳልሆነ ግልጽ ነው። ኮከብ ቆጣሪዎቹ ኮከቡ ዮሴፍና ማርያም ካሉበት ቤት በላይ እስኪቆም ድረስ ተከተሉት።

ኮከብ ቆጣሪዎቹ ቤቱ ውስጥ ሲገቡ ማርያምን ከትንሹ ልጅዋ ከኢየሱስ ጋር አገኟት። በዚህ ጊዜ ሁሉም ሰገዱለት። ከረጢታቸውንም ከፍተው ወርቅ፣ ዕጣንና ከርቤ በስጦታ አበረከቱለት። ከዚያ በኋላ ሕፃኑ የት እንዳለ ለሄሮድስ ለመንገር ሊመለሱ ሲሉ አምላክ ሄደው እንዳይነግሩት በሕልም አስጠነቀቃቸው። ስለዚህ በሌላ መንገድ አድርገው ወደ አገራቸው ተመለሱ።

በሰማይ ላይ እየሄደ ኮከብ ቆጣሪዎቹን ሲመራ የነበረውን ኮከብ ያዘጋጀው ማን ይመስልሃል? ኮከቡ በቀጥታ በቤተ ልሔም ወደነበረው ወደ ኢየሱስ እንዳልመራቸው አስታውስ። ከዚህ ይልቅ ኮከቡ የመራቸው ከንጉሥ ሄሮድስ ጋር ወደ ተገናኙበት ወደ ኢየሩሳሌም ነበር። ሄሮድስም ይህን ሲሰማ ኢየሱስን ለመግደል ፈለገ። ደግሞም አምላክ ጣልቃ ገብቶ ኮከብ ቆጣሪዎቹ ኢየሱስ የት እንዳለ ለሄሮድስ እንዳይነግሩት ባያስጠነቅቃቸው ኖሮ ሄሮድስ ከመግደል አይመለስም ነበር። ኢየሱስ እንዲገደል ይፈልግ የነበረው የአምላክ ጠላት የሆነው ሰይጣን ዲያብሎስ ነበር። ይህን ዓላማውን ለማሳካትም ኮከቡን መሣሪያ አድርጎ ተጠቅሞበታል። ማቴዎስ 2:​1-12፤ ሚክያስ 5:​2

▪ ኮከብ ቆጣሪዎቹ የተመለከቱት ኮከብ ተራ ኮከብ እንዳልሆነ የሚያሳየው ምንድን ነው?

▪ ኮከብ ቆጣሪዎቹ ኢየሱስን ያገኙት የት ነበር?

▪ ኮከብ ቆጣሪዎቹን ለመምራት ኮከቡን ያዘጋጀው ሰይጣን ነው የምንለው ለምንድን ነው?