በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የመታሰቢያው እራት

የመታሰቢያው እራት

ምዕራፍ 114

የመታሰቢያው እራት

ኢየሱስ የሐዋርያቱን እግር ካጠበ በኋላ “እንጀራዬን የሚበላ በእኔ ላይ ተረከዙን አነሣብኝ” በማለት በመዝሙር 41:​9 ላይ ያለውን ጥቅስ ጠቀሰ። ከዚያም መንፈሱ ተረበሸ፤ “ከእናንተ አንዱ አሳልፎ ይሰጠኛል” አላቸው።

ሐዋርያቱ አዘኑና እያንዳንዳቸው ኢየሱስን “እኔ እሆንን?” እያሉ ይጠይቁት ጀመር። የአስቆሮቱ ይሁዳ እንኳን ሳይቀር ጠየቀው። በማዕዱ ከኢየሱስ አጠገብ ጋደም ያለው ዮሐንስ ወደ ኢየሱስ ደረት ጠጋ ብሎ “ጌታ ሆይ፣ ማን ነው?” ብሎ ጠየቀው።

ኢየሱስ “ከአሥራ ሁለቱ አንዱ ከእኔ ጋር ወደ ወጭቱ እጁን የሚያጠልቀው ነው” ሲል መለሰ። “የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል፤ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት፤ ያ ሰው ባልተወለደ ይሻለው ነበር።” ከዚያ በኋላ ክፉ በሆነው ልቡ ውስጥ ያለውን ክፍተት በመጠቀም ሰይጣን እንደገና ይሁዳ ውስጥ ገባበት። ኢየሱስ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ በዚያው ምሽት ይሁዳን የ“ጥፋት ልጅ” ብሎ መጥራቱ ትክክል ነበር።

አሁን ኢየሱስ ይሁዳን “የምታደርገውን ቶሎ ብለህ አድርግ” አለው። ሌሎቹ ሐዋርያት ኢየሱስ ምን ማለቱ እንደሆነ አልገባቸውም። አንዳንዶቹ የገንዘብ ከረጢቱን የሚይዘው ይሁዳ ስለነበረ ኢየሱስ “ለበዓሉ የሚያስፈልገንን ግዛ” ወይም ደግሞ ሄደህ ለድሆች ምጽዋት ስጥ ያለው መሰላቸው።

ይሁዳ ከሄደ በኋላ ኢየሱስ ከታማኝ ሐዋርያቱ ጋር ሙሉ በሙሉ አዲስ የሆነ በዓል ወይም መታሰቢያ አቋቋመ። አንድ ቂጣ ወስዶ አመሰገነና ቆራርሶ “እንካችሁ ብሉ” ብሎ ሰጣቸው። “ስለ እናንተ የሚሰጠው ሥጋዬ ይህ ነው፤ ይህን ለመታሰቢያዬ አድርጉት” ሲል ገለጸ።

እያንዳንዳቸው ቂጣውን ከበሉ በኋላ ኢየሱስ ወይን የያዘ ጽዋ አነሳ፤ ይኸኛው ጽዋ በማለፍ በዓሉ ሥርዓት ላይ የተጠቀሙበት አራተኛው ጽዋ እንደሆነ ከሁኔታው መረዳት ይቻላል። አሁንም አመስግኖ ከጽዋው ጠጡ አላቸው። “ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን አዲስ ኪዳን ነው” ሲል ገለጸ።

ስለዚህ ይህ የኢየሱስ ሞት መታሰቢያ ነው። ኢየሱስ ባዘዘው መሠረት ይህ በዓል በየዓመቱ ኒሳን 14 ለእሱ መታሰቢያነት ይከበራል። የበዓሉ አክባሪዎች ኢየሱስና ሰማያዊ አባቱ የሰው ዘር ሞት ካመጣበት ኩነኔ እንዲላቀቅ ለማድረግ ያከናወኗቸውን ነገሮች እንዲያስታውሱ ያደርጋቸዋል። በዓሉ የክርስቶስ ተከታዮች ለሆኑት አይሁዶች የማለፍ በዓል ምትክ ይሆንላቸዋል።

በፈሰሰው የኢየሱስ ደም ሥራ ላይ የዋለው አዲሱ ቃል ኪዳን አሮጌውን የሕግ ቃል ኪዳን ተክቷል። ይህ ቃል ኪዳን በኢየሱስ ክርስቶስ አስታራቂነት በሁለት ወገኖች መካከል ማለትም በይሖዋ አምላክና በመንፈስ በተ​ወለዱት 144,000 ክርስቲያኖች መካከል የተካሄደ ነው። ይህ ቃል ኪዳን የኃጢአት ይቅርታ ከማስገኘቱም በላይ ነገሥታትና ካህናት የሆኑ ሰዎችን ያቀፈ ሰማያዊ ብሔር እንዲቋቋም ያደርጋል። ማቴዎስ 26:​21-29፤ ማርቆስ 14:​18-25፤ ሉቃስ 22:​19-23፤ ዮሐንስ 13:​18-30፤ 17:​12፤ 1 ቆሮንቶስ 5:​7

▪ ኢየሱስ ጓደኛን የሚመለከት ምን የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት ጠቅሷል? ትንቢቱን የተጠቀመበትስ እንዴት ነው?

▪ ሐዋርያቱ በጣም ያዘኑት ለምን ነበር? እያንዳንዳቸውስ ምን ጥያቄ አቅርበዋል?

▪ ኢየሱስ ይሁዳን ምን እንዲያደርግ ነገረው? ሆኖም ሌሎቹ ሐዋርያት እነዚህን መመሪያዎች የተረዷቸው እንዴት ነው?

▪ ኢየሱስ፣ ይሁዳ ከሄደ በኋላ ምን በዓል አቋቋመ? ይህስ ለምን ዓላማ ያገለግላል?

▪ በአዲሱ ቃል ኪዳን ውስጥ የታቀፉት ወገኖች እነማን ናቸው? ቃል ኪዳኑስ ምን ዓላማ ያከናውናል?