በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 57

ይሖዋ ኤርምያስን እንዲሰብክ ላከው

ይሖዋ ኤርምያስን እንዲሰብክ ላከው

ይሖዋ በይሁዳ ምድር ነቢይ ሆኖ እንዲያገለግል ኤርምያስን ሾመው። ለሕዝቡ እንዲሰብክና መጥፎ ነገር ማድረጋቸውን እንዲያቆሙ እንዲያስጠነቅቃቸው አዘዘው። ኤርምያስ ግን እንዲህ አለ፦ ‘ይሖዋ፣ እኔ እኮ ገና ልጅ ነኝ። ለሕዝቡ ምን ብዬ መናገር እንዳለብኝ እንኳ አላውቅም።’ ይሖዋም እንዲህ አለው፦ ‘አትፍራ። ምን ብለህ መናገር እንዳለብህ እኔ እነግርሃለሁ። ደግሞም እረዳሃለሁ።’

ይሖዋ ኤርምያስን የሕዝቡን ሽማግሌዎች እንዲሰበስብና በፊታቸው የሸክላ ገንቦ ወስዶ እንዲሰብር ነገረው፤ ከዚያም ‘ኢየሩሳሌም ልክ እንደዚህ ገንቦ ትሰባበራለች’ ብሎ እንዲነግራቸው አዘዘው። ኤርምያስ ይሖዋ እንዳዘዘው ሲያደርግ ሽማግሌዎቹ በጣም ተናደዱ። ጳስኮር የተባለ አንድ ካህን ኤርምያስን ከመታው በኋላ እጆቹንና እግሮቹን በእግር ግንድ አሰራቸው። ኤርምያስ ሌሊቱን ሙሉ ምንም መንቀሳቀስ አልቻለም ነበር። ጳስኮር በቀጣዩ ቀን ጠዋት ኤርምያስን ፈታው። ኤርምያስም ‘አሁንስ በቃኝ። ከዚህ በኋላ አልሰብክም’ ብሎ ነበር። ታዲያ ኤርምያስ በእርግጥ መስበኩን አቆመ? አላቆመም። እንዲያውም ሲያስብበት ከቆየ በኋላ እንዲህ አለ፦ ‘የይሖዋ መልእክት በውስጤ እንዳለ እሳት ነው። መስበኬን ማቆም አልችልም።’ በመሆኑም ኤርምያስ ሕዝቡን ማስጠንቀቁን ቀጠለ።

ዓመታት ካለፉ በኋላ በይሁዳ አዲስ ንጉሥ ነገሠ። ካህናቱና ሐሰተኞቹ ነቢያት ኤርምያስ የሚናገረው መልእክት ያበሳጫቸው ነበር። በመሆኑም መኳንንቱን ‘ይህ ሰው መሞት ይገባዋል’ አሏቸው። ኤርምያስም እንዲህ አለ፦ ‘እኔን ከገደላችሁኝ ንጹሕ ሰው መግደላችሁ እንደሆነ እወቁ። ምክንያቱም እኔ የምናገረው የይሖዋን ቃል እንጂ የራሴን ቃል አይደለም።’ መኳንንቱም ይህን ሲሰሙ ‘ይህ ሰው መሞት አይገባውም’ አሉ።

ኤርምያስ መስበኩን ቀጠለ፤ መኳንንቱም በዚህ በጣም ተናደዱ። ወደ ንጉሡ ሄደው ኤርምያስ እንዲገደል ጠየቁት። ንጉሡም በኤርምያስ ላይ የፈለጉትን እንዲያደርጉበት ፈቀደላቸው። እነሱም ኤርምያስ እንዲሞት ጭቃ ያለበት ጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ጣሉት። ኤርምያስም ጭቃው ውስጥ መስመጥ ጀመረ።

ከዚያም ኤቤድሜሌክ የተባለ አንድ የቤተ መንግሥት ባለሥልጣን ወደ ንጉሡ ሄዶ እንዲህ አለው፦ ‘መኳንንቱ ኤርምያስን ጉድጓድ ውስጥ ጥለውታል! እዚያው ከተውነው መሞቱ አይቀርም።’ ንጉሡም ኤቤድሜሌክን 30 ሰዎች ይዞ እንዲሄድና ኤርምያስን ከጉድጓዱ እንዲያወጣው አዘዘው። እኛም ምንም ነገር ቢያጋጥመን እንደ ኤርምያስ መስበካችንን መቀጠል አይኖርብንም?

“በስሜ የተነሳም ሰዎች ሁሉ ይጠሏችኋል፤ እስከ መጨረሻው የጸና ግን ይድናል።”—ማቴዎስ 10:22