በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 87

የጌታ ራት

የጌታ ራት

አይሁዳውያን በየዓመቱ በኒሳን ወር 14ኛ ቀን ላይ ፋሲካን ያከብሩ ነበር። ይህን የሚያደርጉት ይሖዋ እስራኤላውያንን ከግብፅ ባርነት ነፃ አውጥቶ ወደ ተስፋይቱ ምድር እንዳስገባቸው ለማስታወስ ነበር። በ33 ዓ.ም. ኢየሱስና ሐዋርያቱ በኢየሩሳሌም፣ ሰገነት ላይ በሚገኝ አንድ ክፍል ውስጥ የፋሲካን በዓል አከበሩ። ራት በልተው እንደጨረሱ ኢየሱስ ‘ከእናንተ መካከል አንዱ ለጠላቶቼ አሳልፎ ይሰጠኛል’ አለ። ሐዋርያቱ ይህን ሲሰሙ ደነገጡ፤ ከዚያም ኢየሱስን ‘አሳልፎ የሚሰጥህ ማን ነው?’ ብለው ጠየቁት። ኢየሱስም ‘ይህን ዳቦ የምሰጠው ሰው ነው’ አላቸው። ከዚያም ለአስቆሮቱ ይሁዳ ቁራሽ ዳቦ ሰጠው። ይሁዳም ወዲያውኑ ተነስቶ ወጣ።

ከዚያም ኢየሱስ ከጸለየ በኋላ ቂጣ ቆራርሶ ለሐዋርያቱ ሰጣቸው። እንዲህም አላቸው፦ ‘ይህን ቂጣ ብሉ። ቂጣው ለእናንተ ስል የምሰጠውን ሥጋዬን ያመለክታል።’ ቀጥሎም የወይን ጠጅ አንስቶ ከጸለየ በኋላ ለሐዋርያቱ ሰጣቸው። እንዲህ አላቸው፦ ‘ይህን የወይን ጠጅ ጠጡ። የወይን ጠጁ የሰዎች ኃጢአት ይቅር እንዲባል የምሰጠውን ደሜን ያመለክታል። በሰማይ አብራችሁኝ እንደምትነግሡ ቃል እገባላችኋለሁ። እኔን ለማስታወስ በየዓመቱ ይህን አድርጉ።’ የኢየሱስ ተከታዮች አሁንም በየዓመቱ ኒሳን 14 ምሽት አንድ ላይ ይሰበሰባሉ። ይህ ስብሰባ የጌታ ራት ተብሎ ይጠራል።

ሐዋርያቱ በልተው ከጨረሱ በኋላ “ከመካከላችን ታላቅ የሆነው ማን ነው?” በሚል ተከራከሩ። በዚህ ጊዜ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፦ ‘ከመካከላችሁ ታላቅ የሆነው ራሱን ከሁላችሁም እንደሚያንስ አድርጎ የሚቆጥረው ነው።

‘እናንተ ጓደኞቼ ናችሁ። አባቴ እንድነግራችሁ የሚፈልገውን ነገር በሙሉ እነግራችኋለሁ። ከእናንተ ተለይቼ በሰማይ ወዳለው አባቴ የምሄድበት ጊዜ ቀርቧል። ሰዎች እርስ በርሳችሁ እንደምትዋደዱ ሲያዩ ደቀ መዛሙርቴ እንደሆናችሁ ያውቃሉ። ልክ እኔ እንደወደድኳችሁ፣ እናንተም እርስ በርስ ተዋደዱ።’

በመጨረሻም ኢየሱስ፣ ይሖዋ ደቀ መዛሙርቱን በሙሉ እንዲጠብቃቸው ጸለየ። እንዲሁም ደቀ መዛሙርቱ በሰላም አብረው መሥራት እንዲችሉ ይሖዋ እንዲረዳቸው ልመና አቀረበ። በተጨማሪም የይሖዋ ስም እንዲቀደስ ጸለየ። ኢየሱስና ሐዋርያቱ ለይሖዋ የውዳሴ መዝሙር ከዘመሩ በኋላ ከቤት ወጥተው ወደ ደብረ ዘይት ተራራ መጓዝ ጀመሩ። ኢየሱስ ተይዞ የሚታሰርበት ጊዜ ተቃርቦ ነበር።

“አንተ ትንሽ መንጋ አትፍራ፤ አባታችሁ መንግሥት ሊሰጣችሁ ወስኗልና።”—ሉቃስ 12:32