በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 29

ይሖዋ ኢያሱን መረጠው

ይሖዋ ኢያሱን መረጠው

ሙሴ የእስራኤልን ብሔር ለብዙ ዓመታት ሲመራ ከቆየ በኋላ የሚሞትበት ጊዜ ተቃረበ። ይሖዋ ሙሴን እንዲህ አለው፦ ‘እስራኤላውያንን ወደ ተስፋይቱ ምድር የምታስገባቸው አንተ አይደለህም። ምድሪቱን ግን አሳይሃለሁ።’ ከዚያም ሙሴ ሕዝቡን የሚመራ አዲስ መሪ እንዲመርጥ ይሖዋን ጠየቀው። ይሖዋም ‘ወደ ኢያሱ ሂድና ሕዝቡን የሚመራው እሱ እንደሆነ ንገረው’ አለው።

ሙሴ፣ የሚሞትበት ጊዜ እንደተቃረበና ይሖዋ ወደ ተስፋይቱ ምድር እየመራ እንዲያስገባቸው ኢያሱን እንደመረጠ ለእስራኤላውያን ነገራቸው። ከዚያም ሙሴ ኢያሱን ‘አትፍራ። ይሖዋ ይረዳሃል’ አለው። ብዙም ሳይቆይ ሙሴ ወደ ነቦ ተራራ ወጣ። በዚያም ይሖዋ ተስፋይቱን ምድር አሳየው፤ ይህች ምድር ይሖዋ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ እንደሚሰጣቸው ቃል የገባላቸው ምድር ናት። ከዚያም ሙሴ በ120 ዓመቱ ሞተ።

ይሖዋ ኢያሱን እንዲህ አለው፦ ‘የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻገርና ወደ ከነአን ምድር ግባ። ሙሴን እንደረዳሁት ሁሉ አንተንም እረዳሃለሁ። ሕጌን በየቀኑ አንብብ። አትፍራ። ደፋር ሁን። ያዘዝኩህን ነገር ሁሉ አድርግ።’

ከዚያም ኢያሱ ወደ ኢያሪኮ ከተማ ሁለት ሰላዮችን ላከ። ሰላዮቹ በዚያ ምን እንዳጋጠማቸው በሚቀጥለው ታሪክ ላይ እንመለከታለን። ሰላዮቹ ሲመለሱ፣ በዚህ ወቅት ወደ ከነአን ለመግባት ቢሞክሩ እንደሚሳካላቸው ተናገሩ። በቀጣዩ ቀን ኢያሱ ሕዝቡን ለጉዞ እንዲዘጋጁ ነገራቸው። ከዚያም የቃል ኪዳኑን ታቦት የተሸከሙትን ካህናት ከሕዝቡ ቀድመው ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ እንዲሄዱ ነገራቸው። በዚህ ጊዜ ወንዙ በጣም ሞልቶ ነበር። ሆኖም ካህናቱ እግራቸውን ገና ውኃው ውስጥ ሲያስገቡ ወንዙ መፍሰሱን አቆመና ውኃው ደረቀ! መላው የእስራኤል ብሔር ወንዙን እስኪሻገር ድረስ ካህናቱ በወንዙ መካከል ደረቅ መሬት ላይ ቆሙ። ይህ ተአምር ይሖዋ በቀይ ባሕር ያደረገውን ነገር ሳያስታውሳቸው አይቀርም።

እስራኤላውያን ከእነዚያ ሁሉ ዓመታት በኋላ ወደ ተስፋይቱ ምድር ገቡ። በዚያ ቤቶችንና ከተሞችን መገንባት ይችላሉ። በተጨማሪም መሬታቸውን ማረስ እንዲሁም ወይንና የፍራፍሬ ዛፎች መትከል ይችላሉ። በተስፋይቱ ምድር ጣፋጭ የሆኑ ብዙ ምግቦችና የሚጠጡ ነገሮች ስለነበሩ ይህች ምድር ‘ወተትና ማር የምታፈስ ምድር’ ተብላ ትጠራ ነበር።

“ይሖዋ ምንጊዜም ይመራሃል፤ ደረቅ በሆነ ምድርም እንኳ ፍላጎትህን ያረካል።”—ኢሳይያስ 58:11