በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 53

ዮዳሄ ያሳየው ድፍረት

ዮዳሄ ያሳየው ድፍረት

ኤልዛቤል ጎቶልያ የምትባል ልጅ ነበረቻት፤ ጎቶልያ ልክ እንደ እናቷ ክፉ ነበረች። ጎቶልያ የይሁዳን ንጉሥ አግብታ ነበር። ባሏ ሲሞት ወንድ ልጇ በአባቱ ምትክ መግዛት ጀመረ። ልጇ ሲሞት ግን ጎቶልያ ራሷ ይሁዳን መግዛት ጀመረች። ከዚያም ሌላ ሰው ሥልጣኑን እንዳይወስድባት ስትል የራሷን የልጅ ልጆች ጨምሮ የንጉሣውያኑን ቤተሰብ በሙሉ ለማስገደል ሞከረች። በዚህም የተነሳ ሰው ሁሉ ይፈራት ነበር።

ሊቀ ካህናቱ ዮዳሄና ሚስቱ የሆሼባ፣ ጎቶልያ የምታደርገው ነገር ትክክል እንዳልሆነ ተገንዝበው ነበር። ስለዚህ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ ጥለው ከጎቶልያ የልጅ ልጆች አንዱ የሆነውን ኢዮዓስ የተባለውን ሕፃን ደብቀው ወሰዱት። ከዚያም በቤተ መቅደሱ ውስጥ አሳደጉት።

ኢዮዓስ ሰባት ዓመት ሲሆነው ዮዳሄ መቶ አለቆቹንና ሌዋውያኑን በሙሉ በመሰብሰብ ‘የቤተ መቅደሱን በሮች ጠብቁ፤ ማንንም እንዳታስገቡ’ አላቸው። ከዚያም ዮዳሄ ኢዮዓስን የይሁዳ ንጉሥ አድርጎ ሾመው፤ በራሱም ላይ ዘውድ አደረገለት። የይሁዳ ሰዎችም ‘ንጉሡ ለዘላለም ይኑር!’ ብለው ጮኹ።

ንግሥት ጎቶልያ የሕዝቡን ጩኸት ስትሰማ በፍጥነት ወደ ቤተ መቅደሱ መጣች። አዲሱን ንጉሥ ስታይ ‘ይህ ተንኮል ነው! ተንኮል ነው!’ ብላ ጮኸች። ከዚያም መቶ አለቆቹ ይህችን ክፉ ንግሥት ይዘው አወጧትና ገደሏት። በሕዝቡ ላይ ያሳደረችው መጥፎ ተጽዕኖስ ይወገድ ይሆን?

ዮዳሄ ሕዝቡ ‘ይሖዋን ብቻ እናመልካለን’ ብለው ለይሖዋ ቃል እንዲገቡ አደረገ። እንዲሁም የባአልን ቤተ መቅደስ እንዲያፈርሱና ጣዖታቱን እንዲሰባብሩ አደረገ። በተጨማሪም ሕዝቡ በይሖዋ ቤተ መቅደስ ውስጥ በድጋሚ ይሖዋን ማምለክ እንዲችሉ በዚያ የሚያገለግሉ ካህናትንና ሌዋውያንን ሾመ። የረከሰ ሰው ወደ ቤተ መቅደሱ እንዳይገባ የሚከላከሉ በር ጠባቂዎችንም መደበ። ከዚያም ዮዳሄና መቶ አለቆቹ ኢዮዓስን ወደ ቤተ መንግሥቱ ወስደው ዙፋን ላይ አስቀመጡት። የይሁዳ ሰዎች በጣም ተደሰቱ። በመጨረሻ ክፉዋ ንግሥት ጎቶልያ በመገደሏና የባአል አምልኮ በመወገዱ ይሖዋን በነፃነት ማገልገል ቻሉ። በእርግጥም ዮዳሄ በድፍረት የወሰደው እርምጃ ብዙ ሰዎችን ጠቅሟል።

“ሥጋን የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይችሉትን አትፍሩ፤ ከዚህ ይልቅ ነፍስንም ሆነ ሥጋን በገሃነም ሊያጠፋ የሚችለውን ፍሩ።”—ማቴዎስ 10:28