በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሕይወት

ሕይወት

ፍቺ:- ሕይወት ዕፅዋትን፣ እንስሳትን፣ ሰዎችንና መንፈሳዊ ፍጡሮችን በድን ከሆኑ ነገሮች የሚለያቸው ሁኔታ ነው። ግዑዝ አካል ያላቸው ሕያዋን ነገሮች ሁሉ የማደግ፣ በሰውነታቸው ውስጥ የኬሚካል ለውጥ የማድረግ፣ በአካባቢያቸው ለሚከናወኑ ሁኔታዎች ምላሽ የመስጠትና የመራባት ችሎታ አላቸው። ዕፅዋት ሕይወት ቢኖራቸውም ስሜት እንዳላቸው ነፍሳት አይደሉም። ምድራዊ ነፍሳት በሙሉ (ሰዎችም ሆኑ እንስሳት) ሕያው አድርጎ የሚያንቀሳቅሳቸው የሕይወት ኃይልና ይህን የሕይወት ኃይል ደግፎ የሚያቆይ እስትንፋስ አላቸው።

ሕይወት የሚለውን ቃል የማሰብ ችሎታ ላላቸው ፍጥረታት በተሟላ ትርጉሙ ስንጠቀምበት ፍጹም የሆነ ሕልውናና የመኖር መብት ማግኘት ማለት ነው። የሰው ነፍስ ፈጽሞ የማትሞት ነገር አይደለችም። ከአምላክ ታማኝ አገልጋዮች አብዛኞቹ ፍጽምና አግኝተው በምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ ሲኖራቸው ‘ታናሹ መንጋ’ ደግሞ የአምላክ መንግሥት ወራሽ በመሆን በሰማይ ይኖራል። እነዚህ የመንግሥቱ አባሎች መንፈሳዊ ሕይወት አግኝተው በሚነሡበት ጊዜ የአለመሞትን ባሕርይ ስለሚለብሱ ሕይወታቸውን ደግፎ የሚያቆም ፍጥረታዊ ነገር አያስፈልጋቸውም።

 የሰብዓዊ ሕይወት ዓላማ ምንድን ነው?

ሕይወታችን ዓላማ ያለው እንዲሆን የሕይወት ምንጭ ማን መሆኑን በማወቃችንና በመቀበላችን ላይ የተመካ ነው። ሕይወት አእምሮ የሌለው ጭፍን ዕድል ውጤት ከሆነ ሕልውናችን ዓላማ አይኖረውም። ዕቅድ የምናወጣለትና አስተማማኝ የሆነ የወደፊት ኑሮ አይኖረንም። ሥራ 17:24, 25, 28 ግን እንዲህ ሲል ይገልጽልናል:- “ዓለሙንና በእርሱ ውስጥ ያሉትን ነገሮች የፈጠረ አምላክ . . . እርሱ ሕይወትንና እስትንፋስን ሁሉንም ነገሮች ለሁሉ ይሰጣልና። በእርሱ ሕያዋን ነንና እንንቀሳቀሳለን እንኖርማለን።” በ⁠ራእይ 4:11 ላይ ለአምላክ የቀረበው ምስጋና እንዲህ ይላል:- “ጌታችንና አምላካችን ሆይ፣ አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረውማልና ክብር ውዳሴ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል።” (በተጨማሪ በገጽ 146–152 ላይ “አምላክ” በሚለው ዋና ርዕስ ሥር ተመልከት።)

ፈጣሪ ካወጣቸው ብቃቶችና ደስታ ያስገኛሉ ብሎ ከሰጣቸው መመሪያዎች ጋር የሚጋጭ የሕይወት መንገድ መከተል የውጥን አለመሳካትና ብስጭት ያመጣል። ገላትያ 6:7, 8 እንዲህ በማለት ያስጠነቅቃል:- “አትሳቱ፤ እግዚአብሔር አይዘበትበትም። ሰው የሚዘራውን ሁሉ ያንኑ ደግሞ ያጭዳልና፤ በገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና።”—በተጨማሪ ገላትያ 5:19–21 (እንዲሁም “በራስ መመራት” የሚለውን ዋና ርዕስ ተመልከት።)

ከአዳም የተወረሰው ኃጢአት ሰዎች አምላክ በመጀመሪያ አውጥቶ በነበረው ዓላማ መሠረት ከሕይወታቸው የተሟላ ደስታ እንዳያገኙ ዕንቅፋት ሆኖባቸዋል። አዳም ኃጢአት ከሠራ በኋላ በተበየነበት መለኮታዊ ፍርድ ምክንያት ‘ፍጥረት (የሰው ልጅ) ለከንቱነት እንደተገዛ’ ሮሜ 8:20 ይገልጻል። ሐዋርያው ጳውሎስ እንደ አንድ ኃጢአተኛ ሰው ሆኖ ስለሚኖርበት ሁኔታ ሲገልጽ እንዲህ በማለት ጽፏል:- “እኔ . . . ከኃጢአት በታች ልሆን የተሸጥሁ የሥጋ ነኝ። የማልወደውን ክፉን ነገር አደርጋለሁና ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም። በውስጡ ሰውነቴ በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለኛልና፣ ነገር ግን በብልቶቼ ከአእምሮዬ ሕግ ጋር የሚዋጋውንና በብልቶቼ ባለ በኃጢአት ሕግ የሚማርከኝን ሌላ ሕግ አያለሁ። እኔ ምንኛ ጐስቋላ ሰው ነኝ!”—ሮሜ 7:14, 19, 22–24

በአሁኑ ጊዜ ማግኘት የሚቻለውን የመጨረሻውን ከፍተኛ ደስታ የምናገኘውና ሕይወታችን በጣም የሚያረካ ትርጉም ሊኖረው የሚችለው የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች በሥራ ላይ ስናውልና ከሁሉም ነገር ቅድሚያ የምንሰጠው የአምላክን ፈቃድ ለማድረግ ሲሆን ነው። አምላክን ስላገለገልነው እርሱን አናበለጽገውም፤ እርሱ እኛን ‘የሚጠቅመንን’ ነገር ያስተምረናል። (ኢሳ. 48:17) መጽሐፍ ቅዱስ:- “ለጌታ ሥራ የምትደክሙት በከንቱ አለመሆኑን ዐውቃችሁ፣ ሳታቋርጡ ዘወትር የጌታን ሥራ ለመሥራት ትጉ” ይላል።—1 ቆሮ. 15:58 የ1980 ትርጉም

ይሖዋ ሕይወት እንድናገኝ ባደረገልን ዝግጅት ላይ እምነት ብንጥልና በመንገዶቹ ብንሄድ ወደፊት በፍጽምና ለዘላለም የመኖር ተስፋ መጽሐፍ ቅዱስ ከፊታችን አስቀምጧል። ይህ ተስፋ በጠንካራ መሠረት ላይ የቆመ ነው፤ ሳይፈጸም ቀርቶ የሚያሳዝን ተስፋ አይደለም። በዚህ ተስፋ መሠረት የምናደርገው የሥራ እንቅስቃሴ ዛሬም እንኳን ቢሆን ሕይወታችን እውነተኛ ትርጉም ያለው እንዲሆን ሊያደርገው ይችላል።—ዮሐ. 3:16፤ ቲቶ 1:2፤ 1 ጴጥ. 2:6

ሰዎች የተፈጠሩት ጥቂት ዓመታት ከኖሩ በኋላ እንዲሞቱ ነበርን?

ዘፍ. 2:15–17:- “እግዚአብሔር አምላክ ሰውን [አዳምን] ወስዶ ያበጃትም ይጠብቃትም ዘንድ በዔድን ገነት አኖረው። እግዚአብሔር አምላክም ሰውን እንዲህ ብሎ አዘዘው:- ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካሙንና ክፉውን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና።” (አምላክ እዚህ ላይ የተናገረው ሞት ሊቀር የማይችል ነገር እንደሆነ አድርጎ ሳይሆን የኃጢአት ውጤት መሆኑን ነው። እንዲያውም ከሞት እንዲጠነቀቅ አዳምን አጥብቆ አሳስቦት ነበር። ከ⁠ሮሜ 6:23 ጋር አወዳድር።)

ዘፍ. 2:8, 9:- “እግዚአብሔር አምላክም በምሥራቅ በዔድን ገነትን ተከለ የፈጠረውንም ሰው ከዚያ አኖረው። እግዚአብሔር አምላክም ለማየት ደስ የሚያሰኘውን፣ ለመብላትም መልካም የሆነውን ዛፍ ሁሉ ከምድር አበቀለ፤ በገነትም መካከል የሕይወትን ዛፍ . . . አበቀለ።” (ዘፍጥረት 3:22, 23 እንደሚነግረን አዳም ኃጢአት ከሠራ በኋላ እነዚያ ሰብዓዊ ባልና ሚስት ከሕይወት ዛፍ እንዳይበሉ ከኤደን ተባረሩ። አዳም ለፈጣሪው ታዛዥ ቢሆን ኖሮ ለዘላለም ለመኖር የተገባው መሆኑን ለማረጋገጥ ከጊዜ በኋላ ከዚያ ዛፍ እንዲበላ አምላክ ሊፈቅድለት ይችል የነበረ ይመስላል። በኤደን ውስጥ የሕይወት ዛፍ መኖሩ ይህንን የወደፊት ተስፋ ያመለክት ነበር።)

መዝ. 37:29:- “ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ፣ በእርስዋም ለዘላለም ይኖራሉ።” (አምላክ ለምድርና ለሰው ያለው መሠረታዊ ዓላማ እስከ አሁን እንዳልተለወጠ ይህ የተስፋ ቃል ግልጽ ያደርገዋል።)

በተጨማሪ በገጽ 97, 98 ላይ “ሞት” በሚለው ዋና ርዕስ ሥር ተመልከት።

ዛሬ በእኛ ሁኔታ ላይ እንደሚታየው ሕይወት ብዙውን ጊዜ በሥቃይ የተሞላ የአጭር ጊዜ ሕልውና ብቻ እንዲሆን አምላክ ዓላማው ነበርን?

ሮሜ 5:12:- “ኃጢአት በአንድ ሰው [በአዳም] ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት፣ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ።” (ይህ የአምላክ ዓላማ በመሆኑ ሳይሆን፣ በአዳም ኃጢአት ሳቢያ ሁላችንም የወረስነው ነው።) (በተጨማሪ “ዕድል” የሚለውን ዋና ርዕስ ተመልከት።)

ኢዮብ 14:1:- “ከሴት የተወለደ ሰው የሕይወቱ ዘመን ጥቂት ቀን ነው፣ መከራም ይሞላዋል።” (ፍጽምና በጐደለው የነገሮች ሥርዓት ውስጥ ሕይወት በአብዛኛው ይህንን የመሰለ ነው።)

ይሁን እንጂ በእነዚህ ሁኔታዎችም ሥር ቢሆን ሕይወታችን ትርጉም ያለውና የድካማችንን ዋጋ የምናይበት ሊሆን ይችላል።  በገጽ 243, 244 ላይ ስለ ሰብዓዊ ሕይወት ዓላማ የሚናገረውን ተመልከት።

በምድር ላይ ያለው ሕይወት እነማን ወደ ሰማይ እንደሚሄዱ የሚረጋግጥ መፈተኛ ነውን?

ገጽ 162–168 “ሰማይ” በሚለው ዋና ርዕስ ሥር ተመልከት።

ሥጋዊ አካል ከሞተ በኋላ በሕይወት መኖሯን የምትቀጥል የማትሞት ነፍስ አለች?

በገጽ 374–378 “ነፍስ” በሚለው ዋና ርዕስ ሥር ተመልከት።

አንድ ሰው ከአሁኑ አጭር ሰብዓዊ ሕይወት የበለጠ ሕይወት አገኛለሁ ብሎ ተስፋ ማድረግ የሚችለው በምን መሠረት ነው?

ማቴ. 20:28:- “የሰው ልጅ [ኢየሱስ ክርስቶስ] ሊያገለግል ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉት አልመጣም።”

ዮሐ. 3:16:- “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለምን እንዲሁ ወዶአልና።”— ፊደላቱን ጋደል አድርገን የጻፍናቸው እኛ ነን።

ዕብ. 5:9 አዓት:- “ፍጹም ከተደረገ በኋላ [ኢየሱስ ክርስቶስ] ለሚታዘዙት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆነላቸው።” (በተጨማሪ ዮሐንስ 3:36)

ወደፊት ሕይወት የማግኘቱ ተስፋ የሚፈጸመው እንዴት ነው?

ሥራ 24:15 የ1980 ትርጉም:- “እነርሱም ተስፋ እንደሚያደርጉት እኔም ጻድቃንና ኃጥአን ከሞት እንደሚነሡ በእግዚአብሔር ተስፋ አደርጋለሁ።” (ይህ ትንሣኤ ባለፉት ዘመናት አምላክን በታማኝነት ያገለገሉትንና እውነተኛውን አምላክ አውቀው መንገዶቹን የመቀበልም ሆነ ያለመቀበል ምርጫ ለማድረግ ሳይችሉ የቀሩትን ብዙ ሰዎች ይጨምራል።)

ዮሐ. 11:25, 26:- “ኢየሱስም [በኋላ ከሞት ያስነሣው ሰው እኅት የነበረችውን]:- ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፤ ሕያው የሆነም የሚያምንብኝም ሁሉ ለዘላለም አይሞትም፤ ይህንን ታምኚያለሽን? አላት።” (ስለዚህ ከትንሣኤ ተስፋ በተጨማሪ የአሁኑ ክፉ ዓለም በሚጠፋበት ጊዜ በሕይወት ለሚኖሩት ሰዎች ኢየሱስ አንድ ሌላ ተስፋ ሰጥቷል። የአምላክ መንግሥት ምድራዊ ተገዥዎች የመሆን ተስፋ ያላቸው ሁሉ ከመጪው ጥፋት በሕይወት የመትረፍና ሞትን ፈጽሞ ሳያዩ የመኖር አጋጣሚ አላቸው።)

የሰብዓዊ አካል አሠራር የሰው ልጅ ለዘላለም እንዲኖር ተደርጎ እንደተፈጠረ የሚያሳይ ማስረጃ አለውን?

ለ70 ዓመትም ኖርን ለ100 ዓመት አንጐላችን በሕይወታችን ውስጥ የቱንም ያህል ብንጠቀምበት ያለውን ችሎታ ሁሉ እንደማይጠቀምበት ባሁኑ ጊዜ በሰፊው የታወቀ ሆኗል። ኢንሳይክሎፔድያ ብሪታኒካ የሰው አንጐል “በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሰው ከሚጠቀምበት የበለጠ ችሎታ አለው” ብሏል። (1976፣ ጥራዝ 12፣ ገጽ 998) ካርል ሳጋን የተባሉት ሳይንቲስት የሰው አእምሮ ሊይዝ የሚችለው እውቀት “ሃያ ሚልዮን መጻሕፍት ሊወጣው ይችላል። ይህም የዓለም ታላላቅ ቤተ መጻሕፍት የያዟቸውን ያህል ነው” ብለዋል። (ኮስሞስ፣ 1980፣ ገጽ 278) አይዛክ አሲሞቭ የተባሉ ባዮኬሚስት የሰው አንጐል ብዙ “እውቀት ለማከማቸት” ያለውን ችሎታ አስመልክተው “የሰው አንጐል ሰዎች ሊያኖሩበት የሚችሉትን የመማርና የማስታወስ ጭነት ብቻ ሳይሆን ሊያኖሩበት ከሚችሉት አንድ ቢልዮን ጊዜ የሚበልጥ ጭነት ለመሸከም ይችላል” ሲሉ ጽፈዋል።—ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ ማጋዚን፣ ጥቅምት 9, 1966፣ ገጽ 146 (የሰው አእምሮ እንዲጠቀምበት ታስቦ ካልሆነ በስተቀር ይህን የመሰለ ችሎታ ለምን ተሰጠው? ለሁልጊዜው የሚቀጥል የመማር ችሎታ ያላቸው የሰው ልጆች ለዘላለም እንዲኖሩ ታስበው የተሠሩ ናቸው ቢባል ምክንያታዊ አይደለምን?)

በሌሎች ፕላኔቶች ላይ ሕይወት አለን?

ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ የተባለው መጽሔት እንዲህ በማለት ዘግቧል:- “ከእኛ ውጭ ባለው የጽንፈ ዓለም ክፍል ውስጥ የማሰብ ችሎታ ያላቸው ፍጥረታት ይኖሩ እንደሆነ ፍለጋ የተጀመረው . . . ከ25 ዓመታት በፊት ነው። . . . በመቶ ቢልዮን የሚቆጠሩትን ከዋክብት መመርመርን የሚያጠቃልለው ይህ ከባድ ሥራ ከምድር ውጭ ሕይወት ስለመኖሩ ያስገኘው ግልጽ ማስረጃ የለም።”—ሐምሌ 2, 1984፣ ገጽ ኤ1

ዘ ኢንሳይክሎፔድያ አሜሪካና እንዲህ ይላል:- “[እኛ ከምንገኝበት ሶላር ሲስተም ውጭ] ሌላ ፕላኔት ሊገኝ አልቻለም። ይሁን እንጂ ከሶላር ሲስተም ውጭ ፕላኔት ከተገኘ በዚህ ፕላኔት ላይ ተጀምሮ ወደ ከፍተኛ ሥልጣኔ ያደገ ሕይወት የሚኖርበት አጋጣሚ ይኖራል።” (1977፣ ጥራዝ 22፣ ገጽ 176) (ከዚህ መግለጫ መረዳት እንደሚቻለው ይህ በውጭ ዓለማት ውስጥ ሕይወት ይኖር እንደሆነ ለማወቅ የሚደረገው ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቅ ምርምር የሚካሄድበት ዋነኛ ዓላማ ዝግመተ ለውጥን ማለትም ሰው በአምላክ እንዳልተፈጠረና በዚህም ምክንያት በአምላክ ዘንድ ተጠያቂነት እንደሌለበት የሚያረጋግጥ ማስረጃ ለማግኘት ይሆን?)

መጽሐፍ ቅዱስ ሕይወት የሚገኘው በዚህ ምድር ላይ ብቻ እንዳልሆነ ይገልጻል። በእውቀታቸውም ሆነ በማሰብ ችሎታቸው ከሰው እጅግ በጣም የሚበልጡ መንፈሳዊ አካላት ማለትም አምላክና መላእክት አሉ። እነርሱም ሕይወት የተገኘው ከየት እንደሆነና በዓለም ላይ ለተጋረጡት ከባድ ችግሮች መፍትሔው ምን እንደሆነ ለሰው ልጆች አሳውቀዋል። (“መጽሐፍ ቅዱስ” እና “አምላክ” የሚሉትን ዋና ዋና ርዕሶች ተመልከት።)