በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አደንዛዥ ዕፆች

አደንዛዥ ዕፆች

ፍቺ:- “አደንዛዥ ዕፆች” ተብሎ የተተረጎመው “ድራግስ” የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል የተለያዩ ትርጉሞች አሉት። እዚህ ላይ ባለው አገባቡ ግን ለሕክምና አስፈላጊ ስለሆኑ ሳይሆን በሕይወት ውስጥ ከሚያጋጥሙ ችግሮች ለመሸሽ በሚደረግ ሙከራ፣ እንደ ቅዠት ባለ ሁኔታ ውስጥ በመሆን የደስታ ስሜት ወይም የደህንነት ስሜት ወይም የብልጽግና ስሜት ወይም ራስን ከፍ አድርጎ የመመልከት ስሜት እንዲሰማ ሲባል የሚወሰዱና በሚወሰዱበትም ጊዜ ጠባይን የሚቀይሩ ምግብነት የሌላቸውን ነገሮች ያመለክታል።

መጽሐፍ ቅዱስ ለደስታ ሲባል በዕፅ መጠቀምን በእርግጥ ይከለክላልን?

በእርግጥ መጽሐፍ ቅዱስ እንደ ሄሮይን፣ ኮኬይን፣ ኤል ኤስ ዲ፣ ፒ ሲ ፒ (ኤንጅል ደስት)፣ ማሪዋናና ትምባሆ ያሉትን በስም አይጠራቸውም። ይሁን እንጂ አምላክን ደስ ለማሰኘት ምን ማድረግ እንዳለብንና ከምን ነገር መራቅ እንዳለብን የሚገልጽ አስፈላጊ መመሪያ ይሰጠናል። በተመሳሳይም መጽሐፍ ቅዱስ በጠመንጃ ሰውን መግደል ስሕተት ነው ብሎ አይናገርም፤ ይሁን እንጂ ሰው መግደልን ይከለክላል።

ሉቃስ 10:25–27:- “የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ? . . . ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም ኃይልህም በፍጹም አሳብህም ውደድ፣ ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ።” (አንድ ሰው አምላክን በፍጹም ነፍሱና በፍጹም ሐሳቡ በእርግጥ የሚወደው ከሆነ ሕይወቱን የሚያሳጥርና አእምሮውን የሚያቆሽሽ ተግባር ይሠራልን? አንድ ሰው ዕፅ መግዣ ገንዘብ ለማግኘት ሲል ከሌሎች ሰዎች ገንዘብ ቢሰርቅ ለሰው ፍቅር ማሳየቱ ይሆናልን?)

2 ቆሮ. 7:1:- “እንግዲህ፣ ወዳጆች ሆይ፣ የዚህ ተስፋ ቃል ካለን፣ [ይሖዋ አምላካችንና አባታችን የመሆኑ ተስፋ ስላለን] በእግዚአብሔር ፍርሃት ቅድስናን ፍጹም እያደረግን ሥጋንና መንፈስን ከሚያረክስ ነገር ሁሉ ራሳችንን እናንጻ።” (ነገር ግን ሆን ብለን ሥጋችንን የሚያረክሱ ነገሮችን ብንሠራ በአምላክ ዘንድ ሞገስ እናገኛለን ብለን ተስፋ ለማድረግ እንችላለንን?)

ቲቶ 2:11, 12:- “ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሔር ጸጋ ተገልጦአልና፤ ይህም ጸጋ፣ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊ ምኞትን ክደን፣ . . . ራሳችንን በመግዛትና [“ጤነኛ አእምሮ በመያዝ” አዓት፤ “ራስን በመከልከል” ጀባ፤ ‘ራስን እየተቆጣጠሩ በመኖር’ ቱኢቨ ] በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል።” (የአንድን ሰው የማመዛዘን ችሎታ የሚያቃውሱ ወይም ራሱን እንዳይቆጣጠር በሚያደርጉ ዕፆች መጠቀም ከዚህ ምክር ጋር ይስማማልን?)

ገላ. 5:19–21 አዓት:- “የሥጋ ሥራዎች የተገለጡ ናቸው፤ እነርሱም:- . . . መናፍስትነት፣ . . . ፈንጠዝያና የመሳሰሉት ናቸው። . . . እንደዚህ የመሳሰሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም።” (እዚህ ላይ “መናፍስትነት” ተብሎ የተተረጐመው የግሪክኛ ቃል ፋርማኪያ ሲሆን ቃል በቃል ትርጉሙ “በዕፅ መስከር” ማለት ነው። በደብልዩ ኢ ቫይን የተዘጋጀው አን ኤክዝፖዚተሪ ዲክሽነሪ ኦቭ ኒው ቴስታመንት ወርድስ ስለዚህ ግሪክኛ ቃል አስተያየት ሲሰጥ:- “ከመተት ሥራ ጋር በተያያዘ ሁኔታ ይሰጡ የነበሩት ቀላልም ይሁኑ ኃይለኛ ዕፆች አብዛኛውን ጊዜ ለመናፍስት ከሚቀርቡ ልመናዎችና ድግምቶች እንዲሁም የጌጣ ጌጥ ስጦታዎች ወዘተ ጋር አብረው ይቀርቡ ነበርይህም የሚለማመነውን ወይም የታመመውን ሰው ከአጋንንት ትኩረትና ኃይል ለመጠበቅ ነው ቢባልም እውነቱ ግን የመተት አድራጊው ምሥጢራዊ ችሎታና ኃይል በሚለማመነው ሰው አእምሮ እንዲቀረጽ ለማድረግ ነበር” ብሏል። [ለንደን፣ 1940፣ ጥራዝ 4፣ ገጽ 51, 52] ዛሬም በተመሳሳይ ዕፅ የሚወስዱ ብዙ ሰዎች በመናፍስት ሥራ ይካፈላሉ ወይም ከመናፍስት ጋር ግንኙነት ይፈጥራሉ። ባዶ የሆነ አእምሮ ወይም በቅዠት ዓለም ውስጥ የሚዋዥቅ አእምሮ በቀላሉ የአጋንንት መጠቀሚያ ይሆናል። ከ⁠ሉቃስ 11:24–26 ጋር አወዳድር።)

ቲቶ 3:1:- “ለገዦችና ለባለ ሥልጣኖች የሚገዙና የሚታዘዙ [ይሁኑ።]” (በብዙ አገሮች አንዳንድ ዕፆችን ይዞ መገኘትና መጠቀም ሕግ ተላላፊነት ነው።)

አንዳንድ ዕፆች አንድ ሰው ጥሩ ስሜት እንዲሰማው ሊረዱት ስለሚችሉ በእርግጥ ጐጂ ናቸው ማለት ይቻላልን?

2 ጢሞ. 3:1–5:- “ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ። ሰዎች . . . ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ . . . ከእነዚህ ደግሞ ራቅ።” (መጽሐፍ ቅዱስ እንደዚህ ያለው የተድላ ፍላጎታችን በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኙትን የጽድቅ መሠረታዊ ሥርዓቶች በሥራ ላይ ከማዋልና የእርሱን ሞገስ ከማግኘት እንዳይበልጥብን በግልጽ ያስጠነቅቃል።)

አንዳንድ ከዕፅ የተቀመሙ መድኃኒቶች (ናርኮቲክስ) ሥቃይን በማስታገስ እፎይታ ይሰጣሉ፤ የደስታ ስሜትም ለመፍጠር ይችላሉ። ሆኖም ሱስ የሚያስይዙና ከመጠን በላይ ከተወሰዱም ሞት የሚያስከትሉ ሊሆኑ ይችላሉ። አንዳንድ ለመበጥበጫነት የሚያገለግሉ ቅመሞችን (ሶልቨንትስ) ማሽተት የደስታ ስሜት ሊሰጥ ይችላል። ነገር ግን መንተባተብንና የዓይን መፍዘዝን፣ ጡንቻን መቆጣጠር አለመቻልን፣ በተጨማሪም በአእምሮ፣ በጉበትና በኩላሊት ላይ ሊጠገን የማይችል ጉዳት ሊያስከትል ይችላል። ሀሉሲኖጂንስ የሚባሉት መድኃኒቶች “የስካር” ስሜት እንዲሰማ ያደርጋሉ፤ ድካምን የሚያስወግዱ ይመስላሉ። በተጨማሪም የርቀት መጠን የመገመት ችሎታን ያጠፋሉ፣ አስተካክሎ የማሰብ ችሎታን ያበላሻሉ፣ ሊስተካከል የማይችል የባሕርይ ለውጥ ሊፈጥሩ ይችላሉ። ራስን ወይም ሌላውን ሰው የመግደል ዝንባሌ ያሳድራሉ።

ማሪዋናስ ጉዳት አለው? አንዳንድ ዶክተሮች ጉዳት የለውም ይላሉ

ቀድሞ በበርክሌይ ካሊፎርኒያ ዩኒቨርስቲ፣ በካወል ሆስፒታል ውስጥ የሥነ አእምሮ ሕክምና ክፍል ኃላፊ የነበሩት ዶክተር ዴቪድ ፖልስን በአንድ ወቅት ማሪዋና መውሰድ በሕግ የተፈቀደ እንዲሆን ሲከራከሩ ነበር። ተጨማሪ መረጃዎች ከተገኙ በኋላ ግን እንዲህ በማለት ጽፈዋል:- “ማሪዋና ልንዋጋው የሚያስፈልግ በጣም አደገኛ የሆነ ዕፅ መሆኑን አሁን አምኛለሁ:- 1. ዕፁን መውሰድ ሲጀመር የሚሰማው ስሜት አታላይ ነው። ማሪዋና የሚወስድ ሰው ጥሩ ስሜት ይሰማዋል፣ የአእምሮና የአካል አሠራር ጉዳት እየደረሰበት እንዳለ ሊታወቀው አይችልም። 2. አንድ ሰው ማሪዋና መውሰዱን ከቀጠለ የከንቱነት ስሜት እንዲያድርበት ያደርገዋል። ከአንድ ዓመት እስከ ሦስት ዓመት ለሚደርስ ጊዜ ያለ ማቋረጥ ከተወሰደ በትክክለኛው የአእምሮ አስተሳሰብ አሠራር ቦታ የስሜት ለውጥ የሚያስከትሉ አስተሳሰቦች መተካት ይጀምራሉ።”—ኤክዘኪዩቲቭ ሔልዝ ሪፖርት፣ ጥቅምት 1977፣ ገጽ 8

ባለፉት ጊዜያት ማሪዋና የሚያስከትለው ጉዳት በጣም አነስተኛ ነው እንዳሉ የሚነገርላቸው የዩናይትድ ስቴትስ ብሔራዊ የአደንዛዥ ዕፆች መከላከያ ኢንስቲትዩት ዲሬክተር ዶ/ር ሮበርት ኤል ዱፖ በቅርቡ እንዲህ ብለዋል:- “አሳሳቢው ጉዳይ ይህ ወረርሽኝ [የወጣቱ ትውልድ ማሪዋና መውሰድ] የሚያስከትለው የጤና ችግር ነው። ይህም ችግር ቢያንስ ሁለት ዓይነት ነው። አንደኛው ዕፁ በሚያስከትለው ስካር ምክንያት የሚመጣው ውጤት ሲሆን ይህም መኪና በሚያሽከረክሩበት ጊዜ ከሚፈጠረው አደገኛ ውጤት ጀምሮ ለማንኛውም ነገር ደንታ ቢስ እስከ መሆን ይደርሳል። ሁለተኛው ደግሞ በአካል ላይ የሚያስከትለው ጉዳት ነው። እዚህ ላይ አሳሳቢ የሆነው ነገር ማሪዋና በሚጠቀሙ ሰዎች ላይ አዘውትሮ ከሚታየው ብሮንካይተስ ጀምሮ በሆርሞንና ሰውነት በሽታን ለመከላከል ባለው ችሎታ ላይ ሊደርስ እስከሚችለው አደገኛ ውጤት ድረስ ሊያስከትል የሚችለው አደጋ ነው። ይህ አደገኛ ውጤት ካንሰር ሊያመጣ ይችላል።”—ሞንትሪያል ጋዜት፣ መጋቢት 22, 1979፣ ገጽ 9

ሳይንስ ዳይጀስት የሚከተለውን ዝርዝር ሐተታ አቅርቧል:- “ማሪዋና አዘውትሮ ማጨስ ውሎ ሲያድር እንደ ማስታወስ፣ ውስጣዊ ስሜትና ባሕርይ ለመሳሰሉት በጣም ጠቃሚ ተግባሮች አስፈላጊ በሆኑት የአእምሮ የነርቭ መጋጠሚያዎች መካከል ያለውን ክፍተት እንዲሰፋ ያደርጋል። ነርቮች ተግባራቸውን ለማከናወን እንዲችሉ መልእክት መለዋወጥ መቻል አለባቸው።” ከዚያም በመቀጠል ጽሑፉ በእንስሳት ላይ ስለተደረገው ሙከራ ውጤት አስተያየት ሲሰጥ “ጐላ ብለው የሚታዩ ጉዳቶች የደረሱት ስሜትን በሚቆጣጠረው የሴፕታል አካባቢ፣ የማስታወስ ችሎታ በሚቀረጽበት በሂፖካምፐስና ጠባይን የተመለከቱትን ድርጊቶች በሚቆጣጠረው በአሚግዳላ ላይ ነው” ብሏል።—መጋቢት 1981፣ ገጽ 104

ማሪዋና መውሰድ የአልኮል መጠጦችን ከመጠጣት የከፋ ነውን?

አልኮል ምግብ ነው። ሰውነት አልኮልን ወደ ኃይል ለውጦ ከተጠቀመበት በኋላ ቀሪውን ያስወግደዋል። ማሪዋና ግን አንድ ሳይኮፋርማኮሎጂስት (መድኃኒቶች በአእምሮና በጠባይ ላይ የሚያስከትሉትን ውጤት የሚያጠኑ ባለሙያ) እንዳሉት “በጣም ኃይለኛ ዕፅ ነው። ትልቁ ስህተታችን ማሪዋናን ከአልኮል ጋር ማወዳደራችን ነው።” “የአልኮልና የማሪዋና ሞለኪዩሎች ሲወዳደሩ [በማሪዋና ውስጥ ያለው] ቲ ኤች ሲ (THC) ለማስከር ያለው ኃይል ከአልኮል 10,000 ጊዜ የሚበልጥ ነው። . . . ቲ ኤች ሲ ከሰውነት የሚወገደው ቀስ በቀስ ሲሆን ከሚያደርሰውም ጉዳት ለማገገም ብዙ ወራት ይወስዳል።” (ኤክሰኪዩቲቭ ሄልዝ ሪፖርት፣ ጥቅምት 1977፣ ገጽ 3) ፈጣሪያችን እንዴት እንደተፈጠርን ያውቃል፤ ቃሉም በመጠኑ አልኮል እንድንጠጣ ይፈቅድልናል። (መዝ. 104:15፤ 1 ጢሞ. 5:23) ነገር ግን ሆዳምነትን እንደሚያወግዝ ሁሉ ከልክ በላይ አብዝቶ መጠጣትንም በጥብቅ ያወግዛል።—ምሳሌ 23:20, 21፤ 1 ቆሮ. 6:9, 10

የይሖዋ ምሥክሮች ሲጋራ ማጨስን እንደ ትልቅ ኃጢአት የሚቆጥሩት ለምንድን ነው?

አጫሹ ለሕይወት ስጦታ አክብሮት እንደሌለው ያሳያል

ሥራ 17:24, 25:- “ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ . . . ሕይወትንና እስትንፋስን ሁሉንም ለሁሉ ይሰጣል።”

“ሲጋራ ማጨስ ሕይወትን የሚያሳጥር ስለመሆኑ ብዙ ማስረጃ ተገኝቷል። በሲጋራና በሞት መካከል ያለው ዝምድና ከማንኛውም የሕክምና ጭብጥ ባላነሰ ሁኔታ ተረጋግጧል።”—ሳይንስ 80፣ መስከረም/ጥቅምት፣ ገጽ 42

በየዓመቱ በሲጋራ ሳቢያ የሚሞቱት ሰዎች ቁጥር በዩናይትድ ስቴትስ 300,000፣ በብሪታንያ 50,000፣ በካናዳ 50,000 እንደሚደርስ ሪፖርቶች ያሳያሉ። “በየዓመቱ ሲጋራ ከማጨስ ጋር በተያያዘ በሽታ የሚሞቱት ሰዎች ቁጥር ከአንድ ሚልዮን በላይ ነው። ይህም ከዓለም 52% የሚሆነው ሲጋራ በሚጨስባቸው የሦስተኛው ዓለም አገሮች በሲጋራ ጠንቅ የሚሞቱትን ሰዎች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረው ነው።”—ዘ ጆርናል (ቶሮንቶ)፣ መስከረም 1, 1983፣ ገጽ 16

የቀድሞው የዩናይትድ ስቴትስ የጤና፣ የትምህርትና የደህንነት ሚኒስትር፣ ጆሴፍ ካሊፋኖ እንዲህ ብለዋል:- “ሲጋራ ማጨስ ራስን ቀስ በቀስ መግደል መሆኑን በዛሬው ጊዜ ሊጠራጠር የሚችል ማንም የለም።”—ስኮላስቲክ ሳይንስ ወርልድ፣ መጋቢት 20, 1980፣ ገጽ 13

ሲጋራ ማጨስ አምላክ ክርስቲያኖች እንዲያቀርቡለት ከሚፈልገው አገልግሎት ጋር አይጣጣምም

ሮሜ 12:1:- “ወንድሞች ሆይ፣ ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ሕያው ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እለምናችኋለሁ።”

የዩናይትድ ስቴትስ የጤና ጥበቃ ሚንስትር የሆኑት ሲ ኤቨርት ኩፕ እንዲህ ብለዋል:- “ሲጋራ ኅብረተሰባችን ሊከላከለው የሚችል ሞት ከሚያስከትሉ መንስዔዎች አንደኛውን ደረጃ የሚይዝ መሆኑ በግልጽ ታውቋል።” (ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ፣ የካቲት 23, 1982፣ ገጽ ኤ1) “ሲጋራ የሚያጨስ ሰው አማካይ ዕድሜ ሲጋራ ከማያጨሰው ሰው በሦስትና በአራት ዓመት እንደሚያንስ . . . የሕክምና ጥናቶች ይጠቁማሉ። ሁለት ፓኬትና ከዚያ በላይ ሲጋራ የሚያጨስ የአንድ ከባድ አጫሽ የሕይወት ዘመን ሲጋራ ከማያጨሰው ሰው ጋር ሲነፃፀር በስምንት ዓመት ያህል ሊያንስ ይችላል።” (ዘ ወርልድ ቡክ ኢንሳይክሎፔድያ፣ 1984ጥራዝ 17፣ ገጽ 430) ሕይወቱን ለአምላክ አገልግሎት ያቀረበ ሰው ይህን ሕይወቱን ቀስ በቀስ ቢያጠፋ ትክክል ይሆናልን?

“ሲጋራ ማጨስ በተለይ በልብና በሳንባ ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያስከትል በመሆኑ ለሚያጨስ ሰው የሚሰጥ ማንኛውም የበሽታ መከላከያ መድኃኒት ምንም ያህል ጥቅም አያመጣለትም።” (የደቡባዊ ካሊፎርኒያ ዩኒቨርስቲ የዜና አገልግሎት፣ የካቲት 18, 1982) “ሊወገዱ ከሚችሉት የጤና ጠንቆች መካከል ዋነኛው ሲጋራ ማጨስ ሳይሆን አይቀርም።” (ዶ/ር ኤች ማህለር፣ የዓለም የጤና ድርጅት ዋና ዲሬክተር፣ በወርልድ ሄልዝ ላይ የገለጹት፣ የካቲት/መጋቢት 1980፣ ገጽ 3) አንድ ሰው ራሱን ለአምላክ ቅዱስ አገልግሎት ማቅረቡና ሕይወቱን ሆን ብሎ መጉዳቱ ሁለቱ እርስ በርሳቸው የሚጣጣሙ ድርጊቶች ናቸውን?

ሲጋራ ማጨስ ሰውን እንድንወድ የተሰጠንን መለኮታዊ መመሪያ መጣስ ነው

ያዕ. 2:8:- “ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ።”—ከ⁠ማቴዎስ 7:12 ጋር አወዳድር።

“አንድ በቅርቡ የተደረገ ጥናት . . . የሚያጨሱ ባሎች ያሏቸው የማያጨሱ ሚስቶች ባሎቻቸውም እነሱም ከማያጨሱ ሚስቶች በአማካይ አራት ዓመት ቀድመው እንደሚሞቱ ያሳያል።” (ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ፣ ኅዳር 22, 1978፣ ገጽ ሲ5) “በእርግዝና ወራት ማጨስ በፅንሱ ላይ ከባድ የአካል ቅርጽ ብልሽት ወይም አካለ ጎዶሎነት ሊያስከትል ስለሚችል አንድም ፅንሱ ይሞታል አለዚያም ከተወለደ በኋላ ወዲያው ይሞታል።” (ፋምሊ ሄልዝ፣ ግንቦት 1979፣ ገጽ 8) እንዲህ ያለው ለቤተሰብ አባሎች የሚደረግ ፍቅር የጐደለው አያያዝ አንድ ሰው በክርስቲያናዊ አካሄድ እንደማይመላለስ የሚያሳይ ግልጽ ማስረጃ ነው።—ከ⁠1 ጢሞቴዎስ 5:8 ጋር አወዳድር።

“አንድ መካከለኛ አጫሽ የሆነ ሰው ሲጋራው ተቀጣጥሎ በሚቆይበት ጊዜ ውስጥ ጭሱን የሚስበው ለአጭር ጊዜ ብቻ ስለሆነ በአጠገቡ የሚኖረው ሲጋራ የማያጨስ ሰው ሳይወድ በግድ የአጫሹን ያህል ካርቦን ሞኖክሳይድ፣ ታርና ኒኮቲን እንደሚስብ ጥናቶች ያሳያሉ።” (ቱዴይስ ሄልዝ፣ ሚያዝያ 1972፣ ገጽ 39) በዚህ አድራጎቱ አብሮት ያለውን ባልንጀራውን አለመውደዱን የሚያሳይ ሰው አምላክን እወዳለሁ ለማለት አይችልም።—1 ዮሐንስ 4:20⁠ን ተመልከት።

ከዕፅዋት የሚገኙ አደንዛዥ መድኃኒቶችን መጠቀም ስህተት ከሆነ አምላክ እነዚህን ዕፅዋት ለምን ፈጠረ?

አግባብ ባልሆነ መንገድ ጥቅም ላይ የሚውሉ ነገሮች አብዛኛውን ጊዜ ተገቢ የሆነ አገልግሎትም አላቸው። ለሰው ልጅ የተሰጠው የመራባት ችሎታና የወይን ጠጅ ከነዚህ ነገሮች የሚመደቡ ናቸው። ማሪዋና የሚዘጋጀው ሄምፕ ከተባለው ተክል ላይ ከተወሰዱ የደረቁ ቅጠሎችና አበባዎች ሲሆን ከዚህ ተክል ለገመድና ለልብስ የሚሆን ጠቃሚ ቃጫ ይገኛል። ሲጋራ አጫሾች የትንባሆ ቅጠሎችን ተገቢ ባልሆነ መንገድ ቢጠቀሙባቸውም ከትንባሆ ፀረ ተባይና ፀረ ተውሳክ የሆኑ መድኃኒቶች ማዘጋጀት ይቻላል። በምድር ላይ የሚገኙትን የተፈጥሮ ሀብቶች እንዴት በተገቢ መንገድ መጠቀም እንደሚቻል ገና ብዙ ጥናት መደረግ ይኖርበታል። አረሞች እንኳን አፈር ተሸርሽሮ እንዳይወሰድ በመከላከልና ምርት በማይመረትበት ጊዜ ለአፈሩ ሽፋን በመሆን ያገለግላሉ።

አንድ ሰው ከሲጋራ ወይም ከሌሎች አደንዛዥ ዕፆች ለመላቀቅ ሞክሮ ሳይሳካለት ቢቀር ምን ማድረግ ይችላል?

በመጀመሪያ መጽሐፍ ቅዱስ በማጥናትና በማሰላሰል አምላክን ለማስደሰትና እርሱ በሚያዘጋጀው ጽድቅ የሠፈነበት የነገሮች ሥርዓት ለመኖር ጠንካራ ፍላጎት እንዲያድርብህ ማድረግ ያስፈልግሃል። ወደ አምላክ ብትቀርብ እርሱም የሚያስፈልገውን እርዳታ በመስጠት ወደ አንተ ይቀርባል።—ያዕ. 4:8

እነዚህ ልማዶች መጥፎ መሆናቸውን ማመንና በልብ ውስጥ ለነዚህ ልማዶች እውነተኛ ጥላቻ ማሳደር በጣም አስፈላጊ ነው። (መዝ. 97:10) ይህንንም ማድረግ የሚቻለው በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ስለዚህ ጉዳይ የቀረቡትን ቁምነገሮች እንደገና በመከለስና በማሰላሰል ነው። እንዲሁም ከእነዚህ ልማዶች የሚገኘውን ኃላፊና ጊዜያዊ ደስታ በማሰብ ሳይሆን አምላክን ደስ የሚያሰኙት ምን እንደሆኑና መጥፎ ልማዶች የሚያስከትሏቸው ውጤቶች ምን ያህል አስፀያፊ እንደሆኑ በማሰብ ነው።

እንድታጨስ ወይም አደንዛዥ ዕፅ እንድትወስድ የሚገፋፋ ከፍተኛ ስሜት ሲሰማህ አምላክ እንዲረዳህ አጥብቀህ ጸልይ። (ሉቃስ 11:9, 13፤ ከ⁠ፊልጵስዩስ 4:13 ጋር አወዳድር።) መጸለይ የሚገባህ ግፊቱ እንደተሰማህ ወዲያውኑ ነው። በተጨማሪ መጽሐፍ ቅዱስህን አውጣና ድምፅህን ከፍ አድርገህ አንብብ፤ ወይም ከአንድ የጐለመሰ ክርስቲያን ጋር ተገናኝ። ያጋጠመህን ሁኔታ ንገረውና እርዳታ እንዲያደርግልህ ጠይቀው።