በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የይሖዋ ምሥክሮች

የይሖዋ ምሥክሮች

ፍቺ:- ስለ ይሖዋ አምላክና እርሱ ለሰው ልጆች ስላለው ዓላማዎች በትጋት ምሥክርነት የሚሰጡ ሰዎች የሚገኙበት ዓለም አቀፍ ክርስቲያናዊ ማኅበረሰብ ናቸው። የእምነታቸው መሠረት የሚያደርጉት መጽሐፍ ቅዱስን ብቻ ነው።

የይሖዋ ምሥክሮችን ከሌሎች ሃይማኖቶች የተለዩ የሚያደርጓቸው እምነቶች ምንድን ናቸው?

(1) መጽሐፍ ቅዱስ:- የይሖዋ ምሥክሮች ጠቅላላው መጽሐፍ ቅዱስ በአምላክ መንፈስ አነሣሽነት የተጻፈ የአምላክ ቃል ነው ብለው ያምናሉ፤ በሰው ወግ ላይ የተመሠረተን እምነት ከመከተል ይልቅ ለእምነቶቻቸው ሁሉ መመዘኛ የሚያደርጉት መጽሐፍ ቅዱስን ነው።

(2) አምላክ:- ይሖዋ ብቻ እውነተኛ አምላክ መሆኑን በማመን ያመልኩታል። ስለ እርሱና እርሱ ለሰው ልጆች ስላወጣቸው ፍቅራዊ ዓላማዎች ለሌሎች ሰዎች በግልጽ ይናገራሉ። ስለ ይሖዋ አምላክ ለሕዝብ የሚመሰክር ማንኛውም ሰው የአንድ ቡድን ይኸውም “የይሖዋ ምሥክሮች” አባል መሆኑ ይታወቃል።

(3) ኢየሱስ ክርስቶስ:- የይሖዋ ምሥክሮች ኢየሱስ ክርስቶስ አንደኛው የሥላሴ አካል ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው የአምላክ ልጅ፣ የአምላክ ፍጥረታት በኩር፤ ሰው ከመሆኑ በፊት ሕልውና የነበረው፤ ሕይወቱ ከሰማይ ወደ ድንግል ማርያም ማኅፀን የተዛወረ፤ መሥዋዕት የሆነው ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወቱ ለሚያምኑበት ሁሉ የዘላለም ሕይወት መዳን የሚያስገኝ እንደሆነና ከ1914 ጀምሮ አምላክ በምድር ሁሉ ላይ በሰጠው ሥልጣን ንጉሥ ሆኖ እየገዛ እንዳለ ያምናሉ።

(4) የአምላክ መንግሥት:- የይሖዋ ምሥክሮች የሰው ልጆች ተስፋ የአምላክ መንግሥት ብቻ ናት ብለው ያምናሉ። ይህች መንግሥት እውን መስተዳድር ነች፤ ሁሉንም ሰብዓዊ መስተዳድሮች ጨምሮ የአሁኑን ክፉ የነገሮች ሥርዓት በቅርቡ በማጥፋት ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሥርዓት ታቋቁማለች።

(5) ሰማያዊ ሕይወት:- 144,000 በመንፈስ የተቀቡ ክርስቲያኖች ከክርስቶስ ጋር በሰማያዊ መንግሥቱ ተካፋዮች በመሆን አብረውት ነገሥታት ሆነው እንደሚገዙ ያምናሉ። “ጥሩ” የሆኑ ሰዎች በሙሉ የሚያገኙት ሽልማት ወደ ሰማይ መሄድ ነው ብለው አያምኑም።

(6) ምድር:- አምላክ ለምድር ያለው የመጀመሪያ ዓላማ እንደሚፈጸም፣ ምድር ይሖዋን በሚያመልኩ ሰዎች ከዳር እስከ ዳር እንደምትሞላ፣ እነዚህም ሰዎች ሰብዓዊ ፍጽምና አግኝተው ለዘላለም እየተደሰቱ መኖር እንደሚችሉ፣ ሙታንም እንኳ ሳይቀሩ ከእነዚህ በረከቶች ተካፋዮች ለመሆን ከሞት እንደሚነሡ ያምናሉ።

(7) ሞት:- ሙታን ፈጽሞ አንዳች ነገር እንደማያውቁ፤ በአንድ ዓይነት መንፈሳዊ ዓለም ውስጥ በሥቃይ ወይም በደስታ ላይ እንዳልሆኑ፣ በአምላክ አእምሮ ውስጥ ከመታሰባቸው በቀር በሌላ መንገድ በሕይወት እንደሌሉ፤ በዚህም ምክንያት ወደ ፊት የሚኖራቸው ተስፋ የተመካው በትንሣኤ ላይ እንደሆነ ያምናሉ።

(8) የመጨረሻ ቀኖች:- ከ1914 ጀምሮ የምንኖረው በዚህ ክፉ የነገሮች ሥርዓት የመጨረሻ ቀኖች ውስጥ እንደሆነ፣ በ1914 የተፈጸሙትን ነገሮች የተመለከቱ አንዳንድ ሰዎች የአሁኑ ክፉ ዓለም ሲጠፋ እንደሚያዩ፣ ጽድቅ ወዳድ የሆኑት ግን ከጥፋቱ ተርፈው በጸዳች ምድር ላይ እንደሚኖሩ ያምናሉ።

(9) ከዓለም የተለዩ መሆን:- ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ተከታዮቹ ሲናገር “ከዓለም አይደሉም” እንዳለው የይሖዋ ምሥክሮችም የዚህ ዓለም ክፍል ላለመሆን ከልብ ይጥራሉ። ለሰው እውነተኛ ክርስቲያናዊ ፍቅር ያሳያሉ። በፖለቲካዊ ጉዳዮች አይሳተፉም ወይም በማንኛውም ብሔር ውስጥ በሚደረጉ ጦርነቶች ጣልቃ አይገቡም። ለቤተሰቦቻቸው የሚያስፈልጉትን ቁሳዊ ነገሮች ማቅረብ ቢኖርባቸውም ዓለም በጉጉት የሚያሳድዳቸውን ቁሳዊ ሀብቶች ማሳደድ፣ የግል ዝና ማግኘትና ከመጠን በላይ በተድላ መጠመድ አይፈልጉም።

(10) የመጽሐፍ ቅዱስን ምክር ተግባራዊ ማድረግ:- በቤት ውስጥ፣ በትምህርት ቤት፣ በሥራ ቦታና በጉባኤያቸው በየዕለቱ የአምላክን ቃል በሥራ ላይ ማዋል አስፈላጊ እንደሆነ ያምናሉ። አንድ ሰው ባለፈው ጊዜ ይከተለው የነበረው አኗኗር ምንም ይሁን ምን የአምላክ ቃል የሚያወግዛቸውን ሥራዎች ከተወና አምላካዊ ምክርን በሥራ ላይ ካዋለ ከይሖዋ ምሥክሮች አንዱ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን የይሖዋ ምሥክር ከሆነ በኋላ ማንም ሰው ምንዝር፣ ዝሙት፣ ግብረ ሰዶም እየፈጸመ፣ አደንዛዥ ዕፅ እየወሰደ፣ እየሰከረ፣ እየዋሸ ወይም እየሰረቀ እኖራለሁ ቢል ከድርጅቱ ይወገዳል።

(ከላይ የቀረበው ዝርዝር የይሖዋ ምሥክሮች የሚያምኑባቸውን ዋና ዋና እምነቶች ይገልጻል እንጂ ከሌሎች ቡድኖች የሚለዩባቸውን ነጥቦች በሙሉ አያካትትም። ከላይ የተገለጹት እምነቶች የተመሠረቱበት ቅዱስ ጽሑፋዊ ማስረጃ የዚህን መጽሐፍ የአርዕስት ማውጫ በመመልከት ማግኘት ይቻላል።)

የይሖዋ ምሥክሮች እምነት የአሜሪካ ሃይማኖት ነውን?

እነሱ የአምላክ መንግሥት ጠበቆች እንጂ በዚህ አሮጌ ዓለም ውስጥ የሚገኝ የየትኛውም አገር የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ ወይም የማኅበራዊ ሥርዓት ተሟጋቾች አይደሉም።

በዘመናችን የይሖዋ ምሥክሮች ሥራቸውን የጀመሩት በዩናይትድ ስቴትስ መሆኑ እውነት ነው። ዋና መሥሪያ ቤታቸው የተቋቋመው በዚህ አገር ውስጥ መሆኑ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጽሑፎችን እያተሙ ወደ አብዛኞቹ የዓለም ክፍሎች ለመላክ እንዲችሉ ረድቷቸዋል። ሆኖም ምሥክሮቹ አንዱን አገር ከሌላ አገር አስበልጠው አያዩም፤ ምሥክሮቹ ከሞላ ጐደል በሁሉም አገሮች የሚገኙ ሲሆን በእነዚህ አገሮች የሚያከናውኗቸውን ሥራዎች የሚቆጣጠሩ ቢሮዎችም በብዙ የምድር ክፍሎች አሏቸው።

ለምሳሌ:- ኢየሱስ አይሁዳዊ እንደመሆኑ የተወለደው በጳለስጢና ውስጥ ነበር፤ ታዲያ ክርስትና የጳለስጢና ነዋሪዎች ሃይማኖት ነውን? ከሁሉ የበለጠ ትኩረት ሊሰጥ የሚገባው ኢየሱስ ሰው ሆኖ ለተወለደበት ቦታ አይደለም። ኢየሱስ ያስተማረው ትምህርት የተገኘው የሁሉንም አገር ሰዎች ያለአድልዎ ከሚመለከተው ከአባቱ ከይሖዋ አምላክ ነው።—ዮሐ. 14:10፤ ሥራ 10:34, 35

የይሖዋ ምሥክሮች ሥራቸውን የሚያካሂዱበትን ገንዘብ የሚያገኙት ከየት ነው?

የጥንት ክርስቲያኖች ያደርጉ እንደነበረው በበጎ ፈቃድ ከሚደረግ መዋጮ ነው። (2 ቆሮ. 8:12፤ 9:7) በስብሰባዎቻቸው ላይ ምንም ዓይነት ገንዘብ አይሰበስቡም፣ ከሕዝብም የገንዘብ እርዳታ እንዲደረግላቸው አይለምኑም። ፍላጎት ያላቸው ሰዎች የሚለግሱት ገንዘብ የሚውለው የይሖዋ ምሥክሮች በምድር ዙሪያ የሚያከናውኑትን መጽሐፍ ቅዱስን የማስተማር ሥራ ለማስፋፋት ነው።

የይሖዋ ምሥክሮች እነዚህን ጽሑፎች ይዘው ከቤት ወደ ቤት በመሄድ ወይም በመንገዶች ላይ በማበርከት ለሚፈጽሙት አገልግሎት ገንዘብ አይከፈላቸውም። ለአምላክና ለጐረቤቶቻቸው ያላቸው ፍቅር አምላክ ለሰው ልጆች ስላለው ፍቅራዊ ዝግጅት እንዲናገሩ ይገፋፋቸዋል።

የይሖዋ ምሥክሮች ሕጋዊ የሃይማኖት ማኅበር አድርገው የሚጠቀሙበት የፔንስልቫንያ የመጠበቂያ ግንብና የትራክት ማኅበር በዩናይትድ ስቴትስ የፔንስልቫንያ ክፍለ ሃገር የጋራ ብልጽግና ሕግ መሠረት አትራፊ ያልሆነ ድርጅት ሆኖ በ1884 የተመዘገበ ድርጅት ነው። ስለዚህ ይህ ማኅበር በተቋቋመበት ሕግ መሠረት የትርፍ ማስገኛ ድርጅት መሆን አይችልም፣ አይደለምም። ግለሰቦችም በዚህ ድርጅት አማካኝነት ምንም ዓይነት ትርፍ አያገኙም። ማኅበሩ የተቋቋመበት ቻርተር እንዲህ ይላል:- “[ማኅበሩ] በአጋጣሚም ይሁን ሆን ብሎ ለአባሎቹ፣ ለዲሬክተሮቹ ወይም ለሥራ ኃላፊዎቹ ልዩ የገንዘብ ጥቅም ወይም ትርፍ ለማስገኘት ፈጽሞ አያስብም።”

የይሖዋ ምሥክሮች ኑፋቄ ወይም አዲስ የመጣ አክራሪ ሃይማኖት (ከልት) ናቸውን?

አንዳንድ ሰዎች ኑፋቄ የሚለውን ቃል ከአንድ በደንብ ከደረጀ ሃይማኖት ተገንጥሎ የወጣ ቡድን ነው በማለት ይተረጉሙታል። ሌሎች ደግሞ ቃሉን የሚጠቀሙበት አንድን ተለይቶ የሚታወቅ ሰብዓዊ መሪ ወይም አስተማሪ ለሚከተል ቡድን ነው። ቃሉ ብዙ ጊዜ የሚሠራበት በማጥላላት መልክ ነው። የይሖዋ ምሥክሮች ከሌላ ቤተ ክርስቲያን ተገንጥለው የወጡ ሳይሆን ከሁሉም ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ክፍሎችና ሃይማኖቶች የተውጣጡ ሰዎች ናቸው። እነርሱም ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ ሰብዓዊ መሪ አይከተሉም።

ከልት ” የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል ከነባሩ ሃይማኖታዊ ትምህርት ጋር የማይስማማ ተብሎ የሚቆጠር ወይም አንድን ሃይማኖታዊ ሥርዓት በአክራሪነት የሚከተል ሃይማኖት ማለት ነው። ብዙዎቹ የከልት ሃይማኖቶች አንድን ሰብዓዊ መሪ ይከተላሉ። አማኞቹም አብዛኛውን ጊዜ ከኅብረተሰቡ ተገንጥለው በቡድን መልክ የሚኖሩ ናቸው። ከነባሩ ሃይማኖታዊ ትምህርት ጋር የሚስማማ መሆንና አለመሆኑን በተመለከተ መመዘኛው የአምላክ ቃል መሆን አለበት። የይሖዋ ምሥክሮች መጽሐፍ ቅዱስን በጥብቅ ይከተላሉ። አምልኮታቸውም የሕይወት መንገድ እንጂ ለአንድ የአምልኮ ሥርዓት ማደር አይደለም። ሰብዓዊ መሪ የሚከተሉ ወይም ራሳቸውን ከኅብረተሰቡ ያገለሉ አይደሉም። የሚኖሩትና የሚሠሩት በሌላው ሕዝብ መካከል ነው።

የይሖዋ ምሥክሮች ሃይማኖት ከተቋቋመ ምን ያህል ጊዜ ሆኖታል?

መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚገልጸው የይሖዋ ምሥክሮች የሆኑ ሰዎች ዝርዝር ወደ ኋላ ሲቆጠር እስከ አቤል ይደርሳል። ዕብራውያን 11:4 እስከ 12:1 [አዓት ] እንዲህ ይላል:- “አቤል ከቃየል ይልቅ የሚበልጥን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር በእምነት አቀረበ፤ . . . ኖኅ ገና ስለማይታየው ነገር ማስጠንቀቂያ ከተሰጠው በኋላ በእምነት አምላካዊ ፍርሃት አሳየ። . . . አብርሃም ርስት አድርጐ ሊቀበለው ወዳለው ቦታ በተጠራ ጊዜ በእምነት ለመሄድ ታዘዘ። . . . ሙሴ ባደገ ጊዜ ጊዜያዊ የኃጢአት ደስታ ከማግኘት ይልቅ ከአምላክ ሕዝቦች ጋር መነቀፍን ስለመረጠ የፈርኦን የልጅ ልጅ ተብሎ እንዳይጠራ በእምነት እምቢ አለ። . . . እንግዲያውስ ይህንን የሚያክሉ ብዙ የምሥክሮች ደመና በዙሪያችን ስላሉ ማናቸውንም ሸክምና በቀላሉ የሚጠመጠምብንን ኃጢአት እናስወግድና ከፊታችን ያለውን ሩጫ በጽናት እንሩጥ።”

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ይላል:- “አሜን የሆነው፣ የታመነውና እውነተኛው ምስክር፣ በእግዚአብሔር ፍጥረት መጀመሪያ የነበረው እንዲህ ይላል።” (ፊደላቱን ጋደል አድርገን የጻፍናቸው እኛ ነን።) ኢየሱስ የማን ምሥክር ነበር? እርሱ ራሱ የአባቱን ስም እንዳስታወቀ ተናግሯል። ግንባር ቀደሙ የይሖዋ ምሥክር ኢየሱስ ነበር።—ራእይ 3:14፤ ዮሐ. 17:6

አንዳንድ አይሁዳውያን እንኳ ኢየሱስ ያደርግ የነበረው ነገር “አዲስ ትምህርት” እንደሆነ ተናግረው ነበር። (ማር. 1:27) በሌላ ጊዜም አንዳንድ ግሪኮች ሐዋርያው ጳውሎስ “አዲስ ትምህርት” እያስተዋወቀ ነው ብለው አስበው ነበር። (ሥራ 17:19, 20) አዲስ የነበረው ያዳምጡ ለነበሩት ሰዎች ጆሮ ነበር፤ አስፈላጊው ነገር ግን ከአምላክ ቃል ጋር ሙሉ በሙሉ የሚስማማ እውነት መሆኑ ነበር።

የዛሬዎቹ የይሖዋ ምሥክሮች ታሪክ በ1870ዎቹ መጀመሪያ ላይ በአሊጌኒ፣ ፔንስልቫንያ፣ ዩናይትድ ስቴትስ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ቡድን በማቋቋም ተጀመረ። በመጀመሪያ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ብቻ በመባል ይታወቁ ነበር፤ ከ1931 ወዲህ ግን የይሖዋ ምሥክሮች የሚለውን ቅዱስ ጽሑፋዊ ስም ይዘዋል። (ኢሳ. 43:10–12) እምነቶቻቸውና ተግባሮቻቸው አዲስ ሳይሆኑ የመጀመሪያውን መቶ ዘመን ክርስትና መልሰው ያቋቋሙ ናቸው።

የይሖዋ ምሥክሮች የእነርሱ ሃይማኖት ብቻ ትክክለኛ ነው ብለው ያምናሉን?

አምላክን ለማምለክ ተቀባይነት ያላቸው ብዙ መንገዶች አሉ ከሚለው ዘመናዊ አስተሳሰብ ጋር መጽሐፍ ቅዱስ አይስማማም። ኤፌሶን 4:5 “አንድ ጌታ፣ አንድ ሃይማኖት” አለ በማለት ይናገራል። ኢየሱስ እንዲህ በማለት ተናግሯል:- “ወደ ሕይወት የሚወስደው ደጅ የጠበበ፣ መንገዱም የቀጠነ ነውና፣ የሚያገኙትም ጥቂቶች ናቸው። . . . በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፣ ጌታ ሆይ፣ ጌታ ሆይ፣ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም።”—ማቴ. 7:13, 14, 21፤ በተጨማሪም 1 ቆሮንቶስ 1:10⁠ን ተመልከት።

መጽሐፍ ቅዱስ እውነተኛ ክርስቲያናዊ ትምህርቶችን በጥቅል “እውነት” እያለ በተደጋጋሚ ይጠራቸዋል፤ ክርስትናም “የእውነት መንገድ” ተብሎ ተጠርቷል። (1 ጢሞ. 3:15፤ 2 ዮሐ. 1፤ 2 ጴጥ. 2:2) የይሖዋ ምሥክሮች እምነት በሙሉ፣ አኗኗራቸውና ድርጅታዊ አሠራራቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ያላቸው እምነት ራሱ የያዙት ነገር በእርግጥ እውነት ስለመሆኑ ያላቸውን እርግጠኝነት ያጠነክረዋል። አቋማቸው ስለ ራሳቸው ጉራ ለመንዛት ሳይሆን የግል ሃይማኖትን ለመመዘን ትክክለኛው መለኪያ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሆነ ያላቸውን እምነት የሚያንጸባርቅ ነው። የይሖዋ ምሥክሮች ራስ ወዳዶች ስላልሆኑ እምነታቸውን ለሌሎች ለማካፈል ብርቱ ፍላጎት አላቸው።

ሌሎች ሃይማኖቶችስ መጽሐፍ ቅዱስን ይከተሉ የለምን?

ብዙ ሃይማኖቶች በመጠኑም ቢሆን በመጽሐፍ ቅዱስ ይጠቀማሉ። ነገር ግን በእርግጥ መጽሐፍ ቅዱስ የያዛቸውን ትምህርቶች ያስተምራሉን? በሥራስ ላይ ያውላሉልን? ለምሳሌ:- (1) ከብዙዎቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞቻቸው ውስጥ በሺህ ለሚቆጠሩ ጊዜያት የተጠቀሰውን የእውነተኛውን አምላክ ስም አስወጥተውታል። (2) የሥላሴ ትምህርትም ሆነ ስለ አምላክ ያላቸው ፅንሰ ሐሳብ ከአረማውያን ምንጮች የተቀዳና መጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎ ካለቀ ከአያሌ መቶ ዘመናት በኋላ የአሁኑን ቅርጽ እንዲይዝ የተደረገ ነው። (3) ሕይወት ከሞት በኋላ ይቀጥላል ለሚለው አባባላቸው መሠረት ያደረጉት የማትሞት የሰው ነፍስ አለች የሚለው እምነታቸው ከመጽሐፍ ቅዱስ የተገኘ አይደለም፤ የዚህ እምነት መሠረት የጥንቷ ባቢሎን ናት። (4) የኢየሱስ ስብከት አርዕስት የአምላክ መንግሥት ነበረች፤ ደቀ መዛሙርቱንም ስለዚህች መንግሥት ለሌሎች ሰዎች በግል እንዲነግሩ ልኳቸዋል። የዛሬዎቹ አብያተ ክርስቲያናት ግን ስለዚህች መንግሥት የሚናገሩት አልፎ አልፎ ነው፤ አባሎቻቸውም “ይህን የመንግሥት ምሥራች” እየሰበኩ አይደሉም። (ማቴ. 24:14 አዓት ) (5) ኢየሱስ የእርሱ እውነተኛ ተከታዮች እርስ በርሳቸው በሚያሳዩት ራስን መሥዋዕት እስከማድረግ የሚያደርስ ፍቅር ተለይተው ሊታወቁ እንደሚችሉ ተናግሯል። መንግሥታት ጦርነት በሚያደርጉበት ጊዜ የሕዝበ ክርስትና ሃይማኖቶች ይህን የመሰለውን ፍቅር አያሳዩም። (6) መጽሐፍ ቅዱስ የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት የዚህ ዓለም ክፍል እንደማይሆኑ ይናገራል። እንዲሁም የዓለም ወዳጅ መሆን የሚፈልግ ራሱን የአምላክ ጠላት ያደርጋል በማለት ያስጠነቅቃል። የሕዝበ ክርስትና አብያተ ክርስቲያናትና አባሎቻቸው ግን በየመንግሥታቱ የፖለቲካ ጉዳዮች በሰፊው ይካፈላሉ። (ያዕ. 4:4) ከዚህ ተመዝግቦ ከሚገኝ ታሪካቸው አንጻር ሲታይ መጽሐፍ ቅዱስን በትክክል ይከተላሉ ብሎ በሐቅ መናገር ይቻላልን?

የይሖዋ ምሥክሮች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጧቸውን ማብራሪያዎች የሚያገኙት እንዴት ነው?

ዋነኛው ቁልፍ ጉዳይ ምሥክሮቹ መጽሐፍ ቅዱስ የአምላክ ቃል እንደሆነና በውስጡ የሚገኙት ትምህርቶችም ለእኛ መመሪያ ሆነው እንደሚያገለግሉ ማመናቸው ነው። (2 ጢሞ. 3:16, 17፤ ሮሜ 15:4፤ 1 ቆሮ. 10:11) ስለዚህ ግልጽ የሆነውን የእውነት ሐሳብ ለማጥፋት ወይም የመጽሐፍ ቅዱስን የሥነ ምግባር አቋሞች የተዉትን ሰዎች የአኗኗር መንገድ ትክክለኛነት ለማረጋገጥ የፍልስፍና ክርክር አያመጡም።

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኝን ምሳሌያዊ አነጋገር ትርጉም በሚገልጹበት ጊዜ ትርጉሙ ይህ ነው በማለት የራሳቸውን መላ ምት በመስጠት ፈንታ ማብራሪያውን ራሱ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲሰጥ ያደርጋሉ። (1 ቆሮ. 2:13) የምሳሌያዊ አነጋገሮች ትርጉም ብዙ ጊዜ በሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ውስጥ ይገኛል። (ለምሳሌ ያህል ራእይ 21:1⁠ን ተመልከትና እዚያ ላይ የተጠቀሰውን “ባሕር” ትርጉም ለማግኘት ኢሳይያስ 57:20⁠ን አንብብ። በ⁠ራእይ 14:1 ላይ “በጉ” ተብሎ የተጠቀሰው ማን መሆኑን ለማወቅ ዮሐንስ 1:29⁠ንና 1 ጴጥሮስ 1:19⁠ን ተመልከት።)

የትንቢቶችን ፍጻሜ በተመለከተ አስቀድመው ከተተነበዩት ትንቢቶች ጋር የሚዛመዱትን በየጊዜው የሚፈጸሙትን ሁኔታዎች ነቅቶ ስለ መከታተል ኢየሱስ የተናገረውን ቃል ተግባራዊ ያደርጋሉ። (ሉቃስ 21:29–31፤ ከ⁠2 ጴጥሮስ 1:16–19 ጋር አወዳድር።) ስለ እነዚህ ሁኔታዎች በጥንቃቄ ያስታውቃሉ፣ ስለ ትርጉማቸውም መጽሐፍ ቅዱስ ምን እንደሚገልጽ ያመለክታሉ።

ኢየሱስ በምድር ላይ “ታማኝና ልባም ባሪያ” (እንደ አንድ ቡድን ተደርገው የሚታዩ የእርሱ ቅቡዓን ተከታዮች) እንደሚኖረውና በእርሱ በኩል ለእምነት ቤተሰቦች መንፈሳዊ ምግብ እንደሚሰጥ ተናግሯል። (ማቴ. 24:45–47) የይሖዋ ምሥክሮች ይህንን ዝግጅት ይቀበላሉ። የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖች ያደርጉ እንደነበረው ሁሉ የዛሬዎቹም የይሖዋ ምሥክሮች አስቸጋሪ ጥያቄዎች ሲያጋጥሟቸው መልስ ለማግኘት የዚህን “ባሪያ” የአስተዳደር አካል ይጠይቃሉ። የአስተዳደር አካል አባሎች ለጥያቄዎቹ መልስ የሚሰጡት የሰውን ጥበብ ተንተርሰው ሳይሆን የአምላክ ቃል የሚሰጠውን እውቀትና አምላክ ከባሪያዎቹ ጋር በነበረው ግንኙነት ያደረጋቸውን ነገሮች መሠረት በማድረግ እንዲሁም በአምላክ መንፈስ እርዳታ ነው። ይህን መንፈስ ለማግኘት አጥብቀው ይጸልያሉ።—ሥራ 15:1–29፤ 16:4, 5

ባለፉት ዓመታት በይሖዋ ምሥክሮች ትምህርት ላይ ለውጦች የተደረጉት ለምንድን ነው?

ይሖዋ ባሪያዎቹ ዓላማዎቹን እንዲረዱ የሚያደርገው ደረጃ በደረጃ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ያሳያል። (ምሳሌ 4:18፤ ዮሐ. 16:12) የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን እንዲጽፉ በአምላክ መንፈስ የተነሣሱት ነቢያት የጻፉትን ነገር ትርጉም ሙሉ በሙሉ አይረዱም ነበር። (ዳን. 12:8, 9፤ 1 ጴጥ. 1:10–12) የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያት በጊዜአቸው ያልተረዷቸው ብዙ ነገሮች እንደነበሩ አውቀዋል። (ሥራ 1:6, 7፤ 1 ቆሮ. 13:9–12) ‘በፍጻሜው ዘመን’ የእውነት እውቀት በጣም እንደሚጨምር መጽሐፍ ቅዱስ ያሳያል። (ዳን. 12:4) ብዙውን ጊዜ የእውቀት መጨመር የአስተሳሰብ ማስተካከያ ማድረግን ይጠይቃል። የይሖዋ ምሥክሮች እንደዚህ ያለውን ማስተካከያ ለማድረግ ፈቃደኞች ናቸው።

የይሖዋ ምሥክሮች ከቤት ወደ ቤት እየሄዱ የሚሰብኩት ለምንድን ነው?

ኢየሱስ በዘመናችን የሚሠራውን ሥራ ሲያመለክት “ለአሕዛብም ሁሉ ምስክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፣ በዚያን ጊዜም መጨረሻው ይመጣል” በማለት ተንብዮአል። ለተከታዮቹም እንዲህ በማለት መመሪያ ሰጥቷቸው ነበር:- “ሂዱና . . . ከሁሉም አገር ሕዝቦች ደቀ መዛሙርት አድርጉ።”—ማቴ. 24:14፤ 28:19 አዓት

ኢየሱስ የመጀመሪያዎቹን ደቀ መዛሙርቱን በላካቸው ጊዜ ወደ ሰዎች ቤት እንዲሄዱ መመሪያ ሰጥቷቸዋል። (ማቴ. 10:7, 11–13) ሐዋርያው ጳውሎስም አገልግሎቱን በተመለከተ እንዲህ ብሎ ነበር:- “ለእናንተ ጠቃሚ ከሆኑት ነገሮች ውስጥ አንዳችም እንኳ በሕዝብ ፊትና ከቤት ወደ ቤት በመሄድ ከማስተማር ምንም አላስቀረሁባችሁም።”—ሥራ 20:20, 21 አዓት፤ በተጨማሪም ሥራ 5:42⁠ን ተመልከት።

ምሥክሮቹ የሚያውጁት መልእክት የሰዎችን ሕይወት የሚመለከት ነው፤ ስለዚህ ማንንም እንዳያልፉ ይጠነቀቃሉ። (ሶፎ. 2:2, 3) ወደ ሰዎች ቤት በመሄድ ሰዎቹን ለማነጋገር የሚገፋፋቸው በመጀመሪያ ለአምላክ በሁለተኛ ደረጃም ለሰው ያላቸው ፍቅር ነው።

በስፔይን የተደረገ አንድ የሃይማኖት መሪዎች ስብሰባ ይህንን አስተያየት ሰጥቷል:- “ምሥክሮቹ ከሁሉ የበለጠ ትኩረት ሰጥተው የሚሠሩትን፣ ይኸውም በጥንቱ ቤተ ክርስቲያን የሐዋርያት ዘዴ የነበረውን በየቤቱ እየሄዱ ሰዎችን ማነጋገርን [አብያተ ክርስቲያናት] ጨርሶ ቸል ብለውታል። አብያተ ክርስቲያናት ብዙ ጊዜ ቤተ መቅደሳቸውን በመሥራት፣ ሰዎችን ለመሳብ ደወላቸውን በመደወልና አምልኮ በሚደረግባቸው ቦታዎች ላይ ሆነው በመስበክ ሲወሰኑ [ምሥክሮቹ] ግን በእያንዳንዱ አጋጣሚ ምሥክርነት ለመስጠት እንዲችሉ ሐዋርያት ያደርጉት የነበረውን ከቤት ወደ ቤት የመሄድ ዘዴ ይከተላሉ።”—ኤል ካቶሊሲዝሞ፣ ቦጐታ፣ ኮሎምቢያ፣ መስከረም 14, 1975፣ ገጽ 14

ይሁንና ምሥክሮቹ የእነርሱ እምነት ተከታዮች ወዳልሆኑ ሰዎች ቤት በተደጋጋሚ የሚሄዱት ለምንድነው?

ሌሎች ሰዎች መልእክታቸውን እንዲቀበሉ አያስገድዱም። ነገር ግን ሰዎች መኖሪያ እንደሚቀይሩና የሰዎች ሁኔታ እንደሚለዋወጥ ያውቃሉ። አንድ ሰው ዛሬ ሥራ ስለበዛበት ለመስማት አልቻለ ይሆናል፤ በሌላ ጊዜ ግን ረጋ ብሎ ለመስማት ደስተኛ ሊሆን ይችላል። አንድ የቤተሰብ አባል ለመስማት ፍላጎት ባይኖረውም ሌሎች ሊኖራቸው ይችላል። ሰዎች ራሳቸው ይለወጣሉ፤ በኑሯቸው የሚያጋጥማቸው ከባድ ችግር መንፈሳዊ ጉድለታቸው እንዲታወቃቸው ሊያደርግ ይችላል።—በተጨማሪ ኢሳይያስ 6:8, 11, 12⁠ን ተመልከት።

የይሖዋ ምሥክሮች የሚሰደዱትና ሰዎች በክፉ የሚያነሷቸው ለምንድን ነው?

ኢየሱስ እንዲህ ብሏል:- “ዓለም ቢጠላችሁ ከእናንተ በፊት እኔን እንደ ጠላኝ እወቁ። ከዓለምስ ብትሆኑ ዓለም የራሱ የሆነውን ይወድ ነበር፤ ነገር ግን እኔ ከዓለም መረጥኋችሁ እንጂ ከዓለም ስለ አይደላችሁ ስለዚህ ዓለም ይጠላችኋል።” (ዮሐ. 15:18, 19፤ በተጨማሪ 1 ጴጥሮስ 4:3, 4⁠ን ተመልከት።) ዓለም በሞላው በሰይጣን ቁጥጥር ሥር እንዳለ መጽሐፍ ቅዱስ ይገልጻል፤ የስደቱ ዋና ቆስቋሽም እርሱ ነው።—1 ዮሐ. 5:19፤ ራእይ 12:17

ደግሞም ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ:- “በሁሉም ዘንድ ስለ ስሜ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ” ብሎ ነግሯቸው ነበር። (ማር. 13:13) “ስሜ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው የኢየሱስን ሥልጣን ወይም መሲሐዊ ንጉሥ መሆኑን ነው። ስደት የሚነሣባቸው የይሖዋ ምሥክሮች የኢየሱስን ትእዛዛት ከምድራዊ ገዥዎች ትእዛዝ ስለሚያስቀድሙ ነው።

አንድ ሰው እንዲህ ቢልስ:-

‘እናንተ የዓለምን (የኅብረተሰቡን) ኑሮ ለማሻሻል በሚደረገው ጥረት ለምን አትካፈሉም?’

እንዲህ በማለት ልትመልስ ትችላለህ:- ‘በአካባቢው ያሉት ሁኔታዎች እርስዎን እንደሚያሳስቡዎት ሁሉ እኔንም ያሳስቡኛል። አንድ ጥያቄ ብጠይቅዎትስ፣ ቅድሚያ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው የትኛው ችግር ነው ብለው ያስባሉ?’ ከዚያም ምናልባት እንዲህ በማለት ልትቀጥል ትችላለህ:- ‘ይህ ዋና ችግር ነው ብለው ያሰቡት ለምንድን ነው? . . . በእርግጥ በጉዳዩ ላይ አፋጣኝ እርምጃ መውሰድ ጠቃሚ ሊሆን ይችላል፤ ሆኖም ዘላቂ የሆነ መፍትሔ ብናገኝ እንደሚስማሙ እርግጠኛ ነኝ። እኛ የይሖዋ ምሥክሮች ችግሩን ለመፍታት የምንከተለው ዘዴ ይህ ነው። (ሰዎች የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች በሥራ ላይ አውለው ያጋጠሟቸውን ችግሮች ከሥሩ ለማስወገድ እንዲችሉ ለመርዳት በግል በማነጋገር ምን እንደምናደርግ፣ እንዲሁም የአምላክ መንግሥት ወደ ፊት ምን እንደምታደርግና ይህም የሰውን ልጆች ችግር ለዘለቄታው ያስወግዳል የምንልበትን ምክንያት ግለጽ።)’

ወይም እንዲህ ለማለት ትችላለህ:- ‘(አንዳንድ ነጥቦችን ቀደም ብሎ ከተሰጠው መልስ ላይ በመውሰድ . . . ) አንዳንድ ሰዎች ለማኅበረሰቡ ኑሮ መሻሻል ገንዘብ በመስጠት አስተዋጽኦ ያደርጋሉ፣ ሌሎች ደግሞ የፈቃደኝነት አገልግሎት በመስጠት ይሳተፋሉ። የይሖዋ ምሥክሮች ሁለቱንም ያደርጋሉ። ይህንን ላብራራልዎት።’ ከዚያም ምናልባት እንዲህ በማለት ልትቀጥል ትችላለህ:- (1) ‘አንድ ሰው ከይሖዋ ምሥክሮች አንዱ ለመሆን ከፈለገ የመንግሥት ግብር በጥንቃቄ መክፈል ይኖርበታል። ይህ ደግሞ መንግሥት አስፈላጊ አገልግሎቶችን ለመስጠት የሚያስችለው ገንዘብ እንዲያገኝ ያስችለዋል።’ (2) ‘ከዚህም በላይ ወደ ሰዎች ቤት በመሄድ ነፃ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት እንሰጣለን። እነርሱም መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረውን ካወቁ በኋላ መመሪያዎቹን ተግባራዊ ማድረግን ይማሩና ችግሮቻቸውን መወጣት ይጀምራሉ።’

ሌላ አማራጭ:- ‘ጉዳዩን በማንሣትዎ ደስ ብሎኛል። ብዙ ሰዎች ምሥክሮቹ ኅብረተሰቡን የሚጠቅም ምን ነገር እንደሠሩ ለማወቅ ጠይቀው አያውቁም። እርዳታ መስጠት የሚቻልባቸው ብዙ መንገዶች አሉ።’ ከዚያም ምናልባት እንዲህ በማለት ልትቀጥል ትችላለህ:- (1) ‘አንዳንዶች ሆስፒታሎችን፣ የአረጋውያን መጠለያ ቤቶችን፣ የአደንዛዥ ዕፅ ሱሰኞችን መልሶ ማቋቋሚያ ማዕከሎችንና ሌሎች ተቋሞችን በማቋቋም እርዳታ ያደርጋሉ። ሌሎች ደግሞ ወደ ሰዎች ቤት ፈቃደኞች ሆነው በመሄድ የቻሉትን ያህል ተገቢ እርዳታ ይሰጣሉ። የይሖዋ ምሥክሮችም የሚያደርጉት ይህንኑ ነው።’ (2) ‘የአንድን ሰው አጠቃላይ የሕይወት አመለካከት ሊለውጥ የሚችል አንድ ነገር እንዳለ ተመልክተናል። እርሱም የሕይወት ትክክለኛ ዓላማ ምን እንደሆነና ወደ ፊት ምን እንደሚመጣ መጽሐፍ ቅዱስ የሚገልጸው እውቀት ነው።’

ተጨማሪ ሐሳብ:- ‘ይህንን ጥያቄ በማንሣትዎ ደስ ብሎኛል። ሁኔታዎች ተሻሽለው ለማየት እንፈልጋለን፤ አይደለም እንዴ? እስቲ አንድ ጥያቄ ልጠይቅዎት፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ ስላደረጋቸው ነገሮች ምን ይሰማዎታል? ኢየሱስ ሰዎችን ለመርዳት የተጠቀመበት ዘዴ ጠቃሚ ነበር ይላሉ? . . . እኛም የእርሱን ምሳሌ ለመከተል ነው የምንጥረው።’

‘ክርስቲያኖች ምሥክሮች መሆን የሚኖርባቸው ለይሖዋ ሳይሆን ለኢየሱስ ነው’

እንዲህ በማለት ልትመልስ ትችላለህ:- ‘ጥሩ ነጥብ አምጥተዋል። ስለ ኢየሱስ የመመሥከር ኃላፊነት እንዳለብን መናገርዎ ትክክል ነው። ታትመው በሚወጡ ጽሑፎቻችን ላይ በአምላክ ዓላማ ውስጥ ኢየሱስ ያለው ቦታ ጐላ ብሎ የሚገለጸው ለዚህ ነው። (ይህን ለማስረዳት በቅርቡ በወጣ መጽሐፍ ወይም መጽሔት ልትጠቀም ትችላለህ።) ለእርስዎ አዲስ ሊሆን የሚችል አንድ ሐሳብ እዚህ ላይ ይመልከቱ። (ራእይ 1:5) . . . ኢየሱስ “የታመነ ምሥክር” የሆነው ለማን ነበር? (ዮሐ. 5:43፤ 17:6) . . . ኢየሱስ ልንከተለው የሚገባንን ምሳሌ ትቶልናል፤ አይደለም እንዴ? . . . ኢየሱስንና አባቱን ማወቅ ይህን ያህል በጣም አስፈላጊ ነገር የሆነው ለምንድን ነው? (ዮሐ. 17:3)’