በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ፍጥረት

ፍጥረት

ፍቺ:- በመጽሐፍ ቅዱስ አገባቡ ፍጥረት ማለት ሁሉን የሚችለው አምላክ መላውን ጽንፈ ዓለም፣ መንፈሳዊ ፍጡሮችንና በምድር ላይ የሚኖሩትን ሕያዋን ነገሮች ንድፍ አውጥቶ ወደ ሕልውና አምጥቷቸዋል ማለት ነው።

በዚህ ዘመናዊ የሳይንስ ዓለም በፍጥረት ማመን ምክንያታዊ ነውን?

“የጽንፈ ዓለም የተፈጥሮ ሕጐች ዝንፍ የማይሉ ስለሆኑ ሰዎች ያለ አንዳች ችግር የጠፈር መንኮራኩሮችን ሠርተው ወደ ጨረቃ ለመላክና ከበረራ ጊዜያቸውም አንዲት ሴኮንድ እንኳን ዝንፍ እንዳይሉ አድርገው ለመሥራት ችለዋል። እነዚህን ሕጐች ያዘጋጀ አንድ አካል መኖር አለበት።”—የአሜሪካን ጠፈርተኞች ወደ ጨረቃ በመላክ ረገድ ከፍተኛ ሚና የነበራቸው ቨርነር ፎን ብራውን ከተናገሩት የተጠቀሰ።

ግዑዛን አካላትን የያዘው ጽንፈ ዓለም:- ወደፊት ሳይቀድም ወደኋላም ሳይዘገይ በትክክል የሚቆጥር ሰዓት ብታገኝ በአጋጣሚ ደቃቅ የሆኑ የአቧራ ብናኞች ተሰባስበው ይህ ሰዓት ተገኘ ብለህ ታስባለህን? ሰዓቱን የማሰብ ችሎታ ያለው ሰው እንደሠራው ግልጽ ነው። ከዚህ ይበልጥ በጣም አስደናቂ የሆነ “ሰዓት” አለ። በእኛ ሥርዓተ ፀሐይ (ሶላር ሲስተም) ውስጥ የሚገኙት ፕላኔቶችና በመላው ጽንፈ ዓለም ውስጥ የተበተኑት ከዋክብት ሰው ከሠራው ከማንኛውም ዓይነት ሰዓት በበለጠ ሁኔታ በትክክል ፍጥነታቸውን ጠብቀው ይንቀሳቀሳሉ። የእኛ ሥርዓተ ፀሐይ የሚገኝበት የከዋክብት ረጨት (ጋላክሲ) ከአንድ መቶ ቢልዮን የሚበልጡ ከዋክብት አሉት። በጽንፈ ዓለም ውስጥ ከአንድ መቶ ቢልዮን በላይ የሚሆኑ የከዋክብት ረጨቶች እንዳሉ የከዋክብት ተመራማሪዎች ይገምታሉ። ሰዓት አንድ የማሰብ ችሎታ ያለው ሰው የሠራው ለመሆኑ ግልጽ ማስረጃ ንድፍ ከሆነ ከዚህ እጅግ በጣም የሚበልጥ ስፋትና ውስብስብነት ያለው ጽንፈ ዓለም የበለጠ የማሰብ ችሎታ አይጠይቅምን? የዚህን ጽንፈ ዓለም ንድፍ ያወጣው “ሰማያትን የፈጠረና የዘረጋ . . . ታላቁና እውነተኛው አምላክ ይሖዋ” እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይገልጻል።—ኢሳ. 42:5 አዓት40:26መዝ. 19:1

ፕላኔቷ ምድር:- ባዶና ጠፍ የሆነ በረሃ በምታቋርጥበት ጊዜ ሁሉም ነገር ተስተካክሎ ወደ ተዘጋጀበትና ምግብ ወደሞላበት ውብ ቤት ብትደርስ ቤቱ በአጋጣሚ በተከሰተ ፍንዳታ የተገኘ ነው ብለህ ታስባለህን? አታስብም። ከፍተኛ ጥበብ ያለው ሰው እንደሠራው ትገነዘባለህ። ሳይንቲስቶች እስካሁን ድረስ ከምድር በስተቀር በእኛ ሥርዓተ ፀሐይ ውስጥ በሚገኙት ሌሎች ፕላኔቶች ላይ ሕይወት ያላቸውን ነገሮች አላገኙም። እስከ አሁን በተገኘው መረጃ መሠረት ሌሎቹ ፕላኔቶች ባዶና ጠፍ ናቸው። ዚ ኧርዝ (ምድር) የተባለው መጽሐፍ ይህችን ፕላኔት “የጽንፈ ዓለሙ ድንቅ አካል፣ አምሳያ የሌላት ሉል” ብሏታል። (ኒው ዮርክ፣ 1963፣ አርተር ባይሰር፣ ገጽ 10) ምድር ለሰው ሕይወት ተስማሚ በሆነ ትክክለኛ ቦታ ላይ ከፀሐይ ርቃ የምትገኝ ሲሆን በፀሐይ ዙሪያ በምትዞርበት ጊዜም ከምህዋርዋ እንዳትወጣ የሚያደርጋት ትክክለኛ ፍጥነት አላት። በምድር ዙሪያ ብቻ የሚገኘው ከባቢ አየር ሕይወትን ለማቆየት አስፈላጊ የሆኑ ትክክለኛ መጠን ያላቸው ጋዞች ቅንብር ነው። ከዚህም በላይ የሚያስገርመው ከፀሐይ የሚመጣው ብርሃን፣ ከአየር የሚገኘው ካርቦንዳይኦክሳይድና ከለም አፈር የሚገኙት ውኃና ማዕድናት አንድ ላይ ተዋህደው ለምድር ነዋሪዎች የሚያስፈልገውን ምግብ ያስገኛሉ። ይህ ሁሉ ነገር በአንድ ወቅት በኅዋ ውስጥ ከቁጥጥር ውጭ በሆነ ሁኔታ በተፈጠረ ፍንዳታ ምክንያት የተገኘ ነውን? ሳይንስ ኒውስ እንዲህ ሲል ሐቁን አምኗል:- “እነዚህ ልዩና ትክክለኛ ሁኔታዎች በአጋጣሚ መምጣት የሚችሉ አይመስልም።” (ነሐሴ 24 እና 31፣ 1974፣ ገጽ 124) “እያንዳንዱ ቤት በአንድ ሰው ተዘጋጅቶአልና፣ ሁሉን ያዘጋጀ ግን እግዚአብሔር ነው” የሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ መደምደሚያ ምክንያታዊ ነው።—ዕብ. 3:4

የሰው አንጐል:- ዘመናዊ ኮምፒውተሮች የብዙ ጊዜ እልህ አስጨራሽ ምርምርና ጥንቃቄ የተሞላበት ምሕንድስና ሥራ ውጤት ናቸው። እንዲሁ “በአጋጣሚ የተገኙ” አይደሉም። ታዲያ የሰው ጭንቅላትስ እንዲሁ በአጋጣሚ የተገኘ ነውን? የአንድ ሕፃን ልጅ አንጎል ከማንኛውም እንስሳ አንጎል በተለየ ሁኔታ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ሲወለድ ከነበረበት መጠን በሦስት እጥፍ ያድጋል። የሰው አእምሮ እንዴት እንደሚሠራ እስካሁን ለሳይንስ ሊቃውንት በአብዛኛው እንቆቅልሽ ነው። በሰዎች ውስጥ ብዙ ቋንቋዎችን ለመማር፣ ውበትን ለማድነቅ፣ ሙዚቃ ለመድረስ፣ የሕይወትን አመጣጥና ትርጉም ለማሰብ የሚያስችል ችሎታ አለ። የአእምሮ ቀዶ ሕክምና ሐኪም የሆኑት ሮበርት ዋይት “ከሰው የመረዳት ችሎታ በላይ የሆነውን አስደናቂ የአእምሮና የአንጎል ግንኙነት ንድፍ ያወጣና የሠራ ተወዳዳሪ የሌለው ጥበበኛ አካል እንዳለ ከመቀበል በቀር ሌላ ምርጫ የለኝም” ብለዋል። (ዘ ሪደርስ ዳይጀስት፣ መስከረም 1978፣ ገጽ 99) የዚህ አስደናቂ አካል ዕድገት የሚጀምረው በማኅፀን ውስጥ ካለ ከትንሽ ፅንስ ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ ፀሐፊ የነበረው ዳዊት ይህን አስደናቂ ሁኔታ በማስተዋል “ግሩምና ድንቅ ሆኜ ተፈጥሬአለሁና አመሰግንሃለሁ፤ ሥራህ ድንቅ ነው፣ ነፍሴም እጅግ ታውቀዋለች” በማለት ለይሖዋ ተናግሯል።—መዝ. 139:14

ሕያው ሴል:- ሕያው የሆነ ነጠላ ሴል አንዳንድ ጊዜ “አነስተኛና ቀላል” የሆነ የሕይወት ዓይነት እንደሆነ ተደርጎ ይቆጠራል። ይሁን እንጂ ባለ አንድ ሴል እንስሳ ምግቡን ለመሰብሰብ ይችላል፣ ቆሻሻ ከሰውነቱ ያስወግዳል፣ ለራሱ ቤት ይሠራል፣ የፆታ ግንኙነት ያደርጋል። በሰው ውስጥ ያለው እያንዳንዱ ሴል በግንብ የታጠረ ከተማ ጋር ይመሳሰላል። ሥነ ሥርዓት የሚያስከብር ማዕከላዊ አስተዳደር፣ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ፣ ፕሮቲን የሚሠሩ ፋብሪካዎች፣ ውስብስብ የሆነ የማጓጓዣ ሥርዓት፣ ወደ ውስጥ የሚገቡት የተፈቀደላቸው ብቻ መሆናቸውን የሚቆጣጠሩ ዘበኞች አሉት። የአንድ ሰው አካል 100 ትሪሊዮን በሚያክሉ ሴሎች የተገነባ ነው። “አቤቱ፣ [“ይሖዋ” አዓት ] ሥራህ እጅግ ብዙ ነው፤ ሁሉን በጥበብ አደረግህ” የሚሉት የመዝሙር 104:24 ቃላት ለዚህ ምንኛ ተስማሚ ናቸው!

አምላክ የተለያዩ ሕያዋን ነገሮችን ለመፍጠር በዝግመተ ለውጥ ተጠቅሟል የሚለውን ሐሳብ መጽሐፍ ቅዱስ ይቀበለዋልን?

ዘፍጥረት 1:11, 12 ሣርና ዛፎች እያንዳንዳቸው “እንደ ወገኑ” እንዲያፈሩ ተደርገው እንደተፈጠሩ ይናገራል። ቁጥር 21, 24, 25 ላይም አምላክ የባሕር ፍጥረታትን፣ በራሪ ነፍሳትንና በመሬት ላይ የሚኖሩትን እንስሳት እያንዳንዱን “እንደ ወገኑ” እንደፈጠረ ጨምሮ ይናገራል። እዚህ ላይ አንዱ ወገን በዝግመተ ለውጥ ወደሌላው እንደተለወጠ የሚያሳይ ነገር የለም።

ሰውን በተመለከተ ዘፍጥረት 1:26 አምላክ “ሰውን በምሳሌያችንና በመልካችን እንፍጠር” አለ ይላል። ስለዚህ ሰው የወረሰው አምላካዊ ባሕርዮችን ነው እንጂ ተሻሽለው የተገኙ እንስሳትን ባሕርዮች አይደለም። በተጨማሪም ዘፍጥረት 2:7 “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን [ይኖር ከነበረ ሕይወት ያለው ነገር ሳይሆን] ከምድር አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት” ይላል። እዚህም ላይ ቢሆን ለዝግመተ ለውጥ ቦታ የሚሰጥ ምንም ነገር የለም። ከዚህ ይልቅ የሚገልጸው ስለ አዲስ ፍጥረት ነው።

አምላክ ዛሬ በምድር ላይ የሚኖሩትን በሚልዮን የሚቆጠሩ የተለያዩ ሕያዋን ፍጥረታት በሙሉ ፈጥሯልን?

ዘፍጥረት ምዕራፍ 1 አምላክ እያንዳንዱን “እንደ ወገኑ” ፈጠረ ይላል። (ዘፍ. 1:12, 21, 24, 25) በኖኅ ዘመን ለደረሰው የጥፋት ውኃ ዝግጅት ለማድረግ አምላክ በምድር ላይ የሚኖሩትን እንስሳትና የሚበሩትን ፍጥረታት የሚወክሉ እንስሳትን ‘ከየወገናቸው’ ወደ መርከቡ እንዲገቡ መመሪያ ሰጥቷል። (ዘፍ. 7:2, 3, 14) እያንዳንዱ “ወገን” በጣም ብዙ ዓይነት ዘሮችን ለማስገኘት የሚያስችሉ የዘር ባሕርያት አሉት። በዚህም ምክንያት ከ400 የሚበልጡ የተለያዩ የውሻ ዝርያዎች፣ ከ250 የበለጡ የፈረስ ዝርያዎችና ዓይነቶች እንዳሉ ይነገራል። እርስ በርሱ ሊዋለድ የሚችል የእንስሳ ዝርያ ሁሉ በፍጥረቱ አንድ “ወገን” ነው። በተመሳሳይ ሁሉም የሰው ዝርያዎች ማለትም እስያዊ፣ አፍሪካዊ፣ ካውካስያን በሱዳን ውስጥ የሚገኙት ሁለት ሜትር ያህል ቁመት ያላቸው ረጃጅሞቹ ዲንካዎች እንዲሁም አንድ ሜትር ያህል ቁመት ያላቸው አጭሮቹ ፒግሚዎች፣ ሁሉም የተገኙት ከአንድ አባትና እናት ይኸውም ከአዳምና ሔዋን ነው።—ዘፍ. 1:27, 28፤ 3:20

በሕያዋን ነገሮች ላይ መሠረታዊ የሆነ የአሠራር ተመሳሳይነት የሚታየው ለምንድን ነው?

‘ሁሉንም ነገር የፈጠረው አምላክ ነው።’ (ኤፌ. 3:9) ስለዚህ ፍጥረታት ሁሉ የተሠሩት በአንድ ታላቅ ንድፍ አውጪ ነው።

“ሁሉ በእርሱ [በምድር ሳለ ኢየሱስ ክርስቶስ ተብሎ በተጠራው በአምላክ አንድያ ልጅ አማካኝነት] ሆነ፣ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም።” (ዮሐ. 1:3) ስለዚህ ይሖዋ የፍጥረት ሥራዎቹን ሲያከናውን ዋና ሠራተኛ አድርጎ የተጠቀመበት አንድ ልጅ ነበረው።—ምሳሌ 8:22, 30, 31

ጽንፈ ዓለምን ለመፍጠር የሚያስፈልገው ማቴሪያል ከየት ተገኘ?

ሳይንቲስቶች ቁስ አካል ታምቆ የተያዘ ኃይል ወይም ኢነርጂ እንደሆነ ደርሰውበታል። ይህም በኑክሌር መሣሪያዎች ፍንዳታ ተረጋግጧል። ስለ ከዋክብት ኬሚካላዊና ፊዚካላዊ ሁኔታዎች የሚያጠኑት ሳይንቲስት ጆሲፕ ክሊቼክ እንዲህ በማለት ገልጸዋል:- “አብዛኞቹ ወይም ሁሉም መሠረታዊ ቅንጣቶች ኃይልን ወደ ቁስ አካል (ማተር) በመለወጥ ሊፈጠሩ ይችላሉ።”—ዘ ዩኒቨርስ (ጽንፈ ዓለም) (ቦስተን፣ 1976)፣ ጥራዝ 11፣ ገጽ 17

ይህ ኃይል ከየት ሊገኝ ይችላል? መጽሐፍ ቅዱስ “እነዚህን [ከዋክብትንና ዓለማትን] የፈጠረ ማን ነው?” በማለት ከጠየቀ በኋላ ስለ ይሖዋ አምላክ እንዲህ ብሎ ይገልጻል:- “በኃይሉ ብዛትና በችሎቱ ብርታት አንድስ እንኳ አይታጣውም።” (ኢሳ. 40:26) ስለዚህ ጽንፈ ዓለምን ለመፍጠር ለሚያስፈልገው ‘ከፍተኛ ኃይል’ ምንጩ አምላክ ራሱ ነው።

የሚታዩት ፍጥረታት በሙሉ ተፈጥረው ያበቁት ባለፉት 6,000 እና 10,000 ዓመታት መካከል በሚገኙ ስድስት ቀናት ውስጥ ነውን?

ሐቁ ከዚህ መደምደሚያ ጋር አይስማማም:- (1) አንድሮሜዳ ኔቡላ ከሚባለው የከዋክብት ረጨት የሚመጣው ብርሃን የሌሊቱ ሰማይ ብሩህ በሚሆንበት ጊዜ በሰሜን ንፍቀ ክበብ ሊታይ ይችላል። ይህ ብርሃን መሬት ላይ ለመድረስ 2,000,000 ዓመት ይወስድበታል። ስለዚህ ጽንፈ ዓለሙ ቢያንስ በሚልዮን የሚቆጠሩ ዓመታት ዕድሜ አለው ማለት ነው። (2) በመሬት አለቶች ውስጥ የሬዲዮ ጨረር የሚረጩ ማዕድናት ቅሪት የሆኑ ነገሮች በቢልዮን ለሚቆጠሩ ዓመታት ሳይነካኩ የቆዩ አንዳንድ አለቶች መኖራቸውን ያመለክታል።

ዘፍጥረት 1:3–31 እየተናገረ ያለው የቁስ አካልን ወይም በሰማይ ላይ ስለሚገኙት አካሎች የመጀመሪያ አፈጣጠር አይደለም። ጥቅሱ የሚገልጸው ቀደም ብላ የተፈጠረችው መሬት ለሰው መኖሪያ እንድትሆን ስለተደረገው ዝግጅት ነው። ይህም ዕፅዋት፣ በባሕር ውስጥ የሚገኙ ሕይወት ያላቸው ነገሮች፣ በራሪ ነፍሳት፣ የየብስ እንስሳትና የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት በየወገናቸው መፈጠራቸውን የሚያጠቃልል ነው። ይህ ሁሉ በስድስት “ቀን” ተከናውኗል። ይሁን እንጂ “ቀን” ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል ‘ረጅም ጊዜ፣ አንድ ልዩ ሁኔታ የተከናወነበት ዘመን’ የሚሉና ሌሎች የተለያዩ ትርጉሞች አሉት። (ኦልድ ቴስታመንት ወርድ ስተዲስ (የብሉይ ኪዳን ቃላት ጥናት)ግራንድ ራፒድስ፣ ሚችጋን፣ 1978፣ ደብልዩ ዊልሰን፣ ገጽ 109) ቃሉ ባሉት ትርጉሞች መሠረት በዘፍጥረት ላይ የተጠቀሰው እያንዳንዱ “ቀን” በሺህ የሚቆጠሩ ዓመታት ርዝመት ሊኖረው ይችላል።