በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ፍቺ:- የይሖዋ አምላክና እውነተኛውን አምላክ የሚያመልኩ ሰዎች ዋነኛ ጠላት የሆነ መንፈሳዊ ፍጡር ነው። ሰይጣን የሚለው ስም የተሰጠው የይሖዋ ተቃዋሚ ስለሆነ ነው። በተጨማሪም ሰይጣን የአምላክን ስም ለማጥፋት ስለሞከረ ዲያብሎስ ተብሎ ይጠራል። በኤደን ውስጥ በእባብ ተጠቅሞ ሔዋንን ስላሳተ የቀደመው እባብ ተብሎ ተጠርቷል። በዚህም ምክንያት “እባብ” “አታላይነትን” የሚያመለክት ምሳሌ ሆኗል። በተጨማሪም ሰይጣን በራእይ መጽሐፍ ውስጥ በሚውጥ ዘንዶ ተመስሏል።

እንዲህ ያለ መንፈሳዊ አካል ስለመኖሩ እንዴት እርግጠኞች ለመሆን እንችላለን?

ዋነኛው ማስረጃችን መጽሐፍ ቅዱስ ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰይጣን በተደጋጋሚ (ሰይጣን 52 ጊዜ፣ ዲያብሎስ 33 ጊዜ) በስም ተጠርቷል። በተጨማሪም በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ሰይጣን መኖሩን የሚያረጋግጥ የዓይን ምሥክር ቃል ይገኛል። ይህ የዓይን ምሥክር ማን ነው? ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት በሰማይ ይኖር የነበረውና ይህን ክፉ በስም ደጋግሞ የጠራው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።—ሉቃስ 22:31፤ 10:18፤ ማቴ. 25:41

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሰይጣን ዲያብሎስ የሚናገረው የማይመስል ነገር አይደለም። በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸመው ክፉ ድርጊት በሰዎች ብቻ የተፈጸመ ነው ለማለት ያስቸግራል። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሰይጣን አመጣጥና ስለ ሥራዎቹ የሚሰጠው መግለጫ አብዛኞቹ ሰዎች በሰላም ለመኖር የሚፈልጉ ቢሆኑም የሰው ልጅ በጥላቻ፣ በዓመፅ፣ በጦርነት በሺህ ለሚቆጠሩ ዓመታት የተዋጠበትንና ይህ ሁኔታ መላውን የሰው ዘር ለማጥፋት በተቃረበበት ደረጃ ላይ የተገኘበትን ምክንያት ግልጽ ያደርግልናል።

ዲያብሎስ ባይኖር ኖሮ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ዲያብሎስ የሚናገረውን መቀበል ለማንም ሰው ጥቅም አያስገኝም ነበር። ይሁን እንጂ ከዚህ በፊት ጥንቆላ ወይም የመናፍስትነት ሥራ ይፈጽሙ የነበሩ ሰዎች ይህን ድርጊት ይፈጽሙ በነበረበት ጊዜ ከማያዩት ቦታ “ድምፅ” ስለሚሰሙ ወይም ከሰው በላይ በሆነ ኃይል “ስለተያዙ” በጣም ይጨነቁ እንደነበር ተናግረዋል። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሰይጣንና ስለ አጋንንቱ የሚናገረውን ሲያወቁና የመናፍስትነት ሥራዎችን ትተው የይሖዋን እርዳታ በጸሎት እንዲጠይቁ የሚገልጸውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር ሥራ ላይ ሲያውሉ ከዚህ ጭንቀታቸው ተገላግለዋል።—በገጽ 383–387 ላይ “መናፍስትነት” በሚለው ርዕስ ሥር ተመልከት።

ሰይጣን አለ ብሎ ማመን ቀንዶች፣ ሹል ጭራ እንዳለውና መንሽ ይዞ የሚለበልብ እሳት ባለበት ሲኦል ውስጥ ሰዎችን የሚጠብስ ነው የሚለውን አስተሳሰብ መቀበል ማለት አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሰይጣን እንዲህ የመሰለ መግለጫ አይሰጥም። ይህ ዓይነቱ አስተሳሰብ ፓን በተባለው የግሪካውያን አምላክ ምስልና ኢጣሊያዊው ባለ ቅኔ ዳንቴ አሊጌሪ በጻፈው ኢንፌርኖ በተባለ መጽሐፍ ከተመሩ የመካከለኛው ዘመን ሰዓሊዎች አእምሮ የመነጨ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ የሚያቃጥል እሳት አለ ብሎ አያስተምርም። ከዚህ ይልቅ “ሙታን አንዳች . . . አያውቁም” በማለት ይናገራል።—መክ. 9:5

ሰይጣን የሚባለው ምናልባት በሰው ውስጥ ያለ የክፋት ባሕርይ ይሆን?

ኢዮብ 1:6–12 እና 2:1–7 በይሖዋ አምላክና በሰይጣን መካከል ስለተደረገ የንግግር ልውውጥ ይነግረናል። ሰይጣን በአንድ ሰው ወይም አካል ውስጥ የሚያድር የክፋት ባሕርይ ቢሆን ኖሮ ይሖዋ የተነጋገረው ከራሱ የክፋት ባሕርይ ጋር ነው ማለት ነው። ነገር ግን ይህ ዓይነቱ አስተሳሰብ መጽሐፍ ቅዱስ “በእርሱም ዘንድ ዓመፃ የለም” ብሎ ስለ ይሖዋ ከሚናገረው ሐሳብ ጋር ሙሉ በሙሉ ይጋጫል። (መዝ. 92:15፤ ራእይ 4:8) የዕብራይስጡ ጽሑፍ በኢዮብ ታሪክ ላይ ሐስሳታን (ሰይጣን) በሚል ሐረግ የሚጠቀም መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው። ይህ አነጋገር የይሖዋን ተቃዋሚ በቀጥታ የሚመለከት መሆኑን ያመለክታል።—በተጨማሪም ዘካርያስ 3:1, 2አዓት ባለማጣቀሻ እትም የግርጌ ማስታወሻ ተመልከት።

ሉቃስ 4:1–13 ዲያብሎስ ኢየሱስን በፈተና አሳስቶ እንዲሰግድለት ለማድረግ እንደሞከረ ይገልጻል። ታሪኩ ዲያብሎስ ስለተናገራቸው ቃላትና ኢየሱስ ስለሰጣቸው መልሶች ይናገራል። ታዲያ ኢየሱስ በዚህ ጊዜ የተፈተነው በውስጡ ባለው ክፋት ነውን? እንዲህ ያለው አስተሳሰብ ኢየሱስ ኃጢአት የሌለበት እንደሆነ ከሚገልጸው የመጽሐፍ ቅዱስ መግለጫ ጋር አይስማማም። (ዕብ. 7:26፤ 1 ጴጥ. 2:22) ዲያቦሎስ የሚለው የግሪክኛ ቃል በ⁠ዮሐንስ 6:70 ላይ በይሁዳ አስቆሮቱ ውስጥ መብቀል ስለጀመረ መጥፎ ባሕርይ ለማመልከት ቢያገለግልም በ⁠ሉቃስ 4:3 ላይ የተጠቀሰው አንድን የተለየ አካል ለማመልከት የሚያገለግለው ሆ ዲያቦሎስ (ዲያብሎስ) ነው።

በዲያብሎስ ላይ ማሳበብ ለመጥፎ ሁኔታዎች ተጠያቂ ላለመሆን የተደረገ ሙከራ ነውን?

አንዳንድ ሰዎች ራሳቸው ያደረጉትን ጥፋት በዲያብሎስ ላይ ያሳብባሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ግን ሰዎች በራሳቸው ጥፋትም ሆነ ሌሎች ሰዎች ባደረሱባቸው ነገሮች ምክንያት ክፉ ነገር ሲያጋጥማቸው በኃላፊነት የሚጠየቁት ራሳቸው እንደሆኑ ይገልጻል። (መክ. 8:9፤ ገላ. 6:7) ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ በሰው ልጅ ላይ ይህን የሚያክል መከራ ያደረሰ ታላቅ ጠላት መኖሩንና ይህ ጠላት ስለሚጠቀምባቸው ዘዴዎች ይናገራል። ከእርሱም መዳፍ እንዴት ልንወጣ እንደምንችል ያመለክታል።

ሰይጣን የመጣው ከየት ነው?

የይሖዋ ሥራዎች በሙሉ ፍጹም ናቸው። እርሱ የዓመፅ አመንጪ ስላልሆነ ክፉ የሆነ ነገር አይፈጥርም። (ዘዳ. 32:4፤ መዝ. 5:4) ሰይጣን የሆነው ፍጡር በመጀመሪያ ፍጹም የአምላክ መንፈሳዊ ልጅ ነበር። ኢየሱስ ዲያብሎስ “በእውነት አልቆመም” ሲል በተናገረ ጊዜ በአንድ ወቅት ‘በእውነት ውስጥ’ እንደነበረ አመልክቷል። (ዮሐ. 8:44) ይሁን እንጂ የማሰብ ችሎታ እንዳለው እንደ ማንኛውም የአምላክ ፍጥረት ይህም መንፈሳዊ ልጅ የፈቀደውን ለማድረግ ነፃነት ተሰጥቶት ነበር። እርሱ ግን በምርጫ ነፃነቱ አለአግባብ ተጠቀመ። በልቡ ውስጥ ራሱን ከፍ ከፍ የማድረግ ስሜት እንዲያድግ ፈቀደ። ለአምላክ ብቻ የሚገባውን አምልኮ መመኘት ስለ ጀመረ አዳምና ሔዋን አምላክን ከመታዘዝ ይልቅ እሱን እንዲሰሙና እንዲታዘዙ አግባባቸው። ስለዚህ በራሱ አካሄድና ምግባር ራሱን ሰይጣን አደረገ። ሰይጣን ማለት “ተቃዋሚ” ወይም “ባላጋራ” ማለት ነው።—ያዕ. 1:14, 15፤ በተጨማሪም በገጽ 371 ላይ “ኃጢአት” በሚለው ርዕስ ሥር ተመልከት።

ሰይጣን እንዳመፀ አምላክ ወዲያው ያላጠፋው ለምንድን ነው?

ሰይጣን ከበድ ያሉ ጥያቄዎችን አስነሥቶ ነበር። (1) የይሖዋ ሉዓላዊ አገዛዝ በጽድቅ ላይ የተመሠረተና ትክክል የመሆኑ ጉዳይ። ይሖዋ ለሰው ልጆች ደስታ አስተዋጽዖ ሊያበረክት የሚችለውን ነፃነት ነፍጓቸዋልን? የሰው ልጆች የራሳቸውን ጉዳይ በተሳካ ሁኔታ ማካሄዳቸውና ዘላቂነት ያለው ሕይወት ማግኘታቸው በእርግጥ አምላክን በመታዘዝ ላይ የተመካ ነውን? ይሖዋ አለመታዘዝ ሞት ያመጣል የሚል ሕግ ሲሰጣቸው ዋሽቷቸዋልን? (ዘፍ. 2:16, 17፤ 3:3–5) ይህ ከሆነስ ይሖዋ በእርግጥ የመግዛት መብት አለውን? (2) የማሰብ ችሎታ ያላቸው ፍጥረታት በይሖዋ ፊት አቋማቸውን ሳያጐድፉ በንጽሕና የመመላለሳቸው ጉዳይ። አዳምና ሔዋን በማፈንገጣቸው ምክንያት ‘የይሖዋ አገልጋዮች አምላክን በፍቅር ተነሣስተው ይታዘዙታል ወይስ ሁሉም አምላክን ክደው የሰይጣንን መሪነት ይከተላሉ?’ የሚል ጥያቄ ተነሣ። ይህንን ሁለተኛ ጥያቄ ሰይጣን በኢዮብ ዘመን ይበልጥ ግልጽ አድርጎታል። (ዘፍ. 3:6፤ ኢዮብ 1:8–11፤ 2:3–5፤ በተጨማሪም ሉቃስ 22:31⁠ን ተመልከት።) እነዚህ ጥያቄዎች ዓመፀኞቹን በመግደል ብቻ መልስ ሊያገኙ የሚችሉ አልነበሩም።

አምላክ ራሱን በመጠራጠር ማረጋገጥ የሚያስፈልገው ነገር ነበር ማለት አይደለም። ይሁን እንጂ እነዚህ ጥያቄዎች ዳግመኛ የጽንፈ ዓለሙን ሰላምና ደህንነት እንዳያናጉ በማያጠራጥር ሁኔታ መልስ እንዲያገኙ በቂ ጊዜ ፈቀደ። አዳምና ሔዋን የአምላክን ትእዛዝ ከሻሩ በኋላ መሞታቸው ከጊዜ በኋላ በግልጽ ታየ። (ዘፍ. 5:5) ይሁን እንጂ ጥያቄ ምልክት የተደረገበት ሌላም ጉዳይ ነበር። በዚህም ምክንያት አምላክ፣ ሰይጣንም ሆነ የሰው ልጆች ራሳቸው የፈጠሯቸውን የተለያዩ የመስተዳድር ሥርዓቶች እንዲሞክሩ ፈቀደ። ከእነዚህ የመስተዳድር ዓይነቶች አንዳቸውም ቢሆኑ ዘላቂ ደስታ ሊያመጡ አልቻሉም። የሰው ልጆች የአምላክን የአቋም ደረጃዎች ቸል በማለት የፈለጉትን ሁሉ እንዲያደርጉ እስከ መጨረሻው ድረስ ፈቅዶላቸዋል። የዚህ ውጤት ምን እንደሆነ ፍሬው ራሱ ይናገር። መጽሐፍ ቅዱስ በትክክል እንደሚናገረው “አቤቱ፣ የሰው መንገድ ከራሱ እንዳይደለ አውቃለሁ፣ አካሄዱን ለማቅናት ከሚራመድ ሰው አይደለም” ለማለት እንገደዳለን። (ኤር. 10:23) በዚሁ ጊዜ አምላክ አገልጋዮቹ በሰይጣን አነሣሽነት የሚደርስባቸውን ስደትና ሽንገላ ሁሉ ተቋቁመው እርሱን በፍቅር በመታዘዝ ለእርሱ ያላቸውን ታማኝነት የሚያረጋግጡበትን አጋጣሚ ፈቅዷል። ይሖዋ አገልጋዮቹን “ልጄ ሆይ፣ ጠቢብ ሁን፣ ልቤንም ደስ አሰኘው፣ ለሚሰድበኝ መልስ መስጠት ይቻለኝ ዘንድ” በማለት አጥብቆ ይመክራቸዋል። (ምሳሌ 27:11) የታመኑ ሆነው የሚገኙ ሁሉ በአሁኑ ጊዜ ብዙ ጥቅሞችን ከማግኘታቸውም ሌላ ወደ ፊትም ፍጹም የሆነ የዘላለም ሕይወት የማግኘት ተስፋ ይጠብቃቸዋል። ይህንንም ሕይወታቸውን መንገዱንና ባሕርያቱን ከልብ የሚወዱትን አምላክ፣ የይሖዋን ፈቃድ ለማድረግ ይጠቀሙበታል።

ሰይጣን በአሁኑ ዓለም ውስጥ ምን ያህል ኃያል ነው?

ሰይጣን “የዓለም ገዢ” እንደሆነ በመናገር አብዛኞቹ የሰው ልጆች የአምላክን ትእዛዛት ችላ በማለት የሚታዘዙት እርሱን እንደሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ገልጿል። (ዮሐ. 14:30፤ ኤፌ. 2:2) በተጨማሪም መጽሐፍ ቅዱስ “የዚህ የነገሮች ሥርዓት አምላክ” ይለዋል። ይህንን ሥርዓት የሚደግፉ ሰዎች በሚፈጽሟቸው ሃይማኖታዊ ተግባራት የሚያከብሩት ሰይጣንን ነው ማለት ነው።—2 ቆሮ. 4:4 አዓት፤ 1 ቆሮ. 10:20

ዲያብሎስ ኢየሱስ ክርስቶስን በፈተና ለማሳት በሞከረበት ጊዜ “ረጅም ወደ ሆነ ተራራ አውጥቶ የዓለምን መንግሥታት ሁሉ በቅጽበት አሳየው። ዲያብሎስም:- ይህ ሥልጣን ሁሉ ክብራቸውም ለእኔ ተሰጥቶአል ለምወደውም ለማንም እሰጠዋለሁና ለአንተ እሰጥሃለሁ። ስለዚህ አንተ በእኔ ፊት [“አንድ ጊዜ” አዓት] ብትሰግድ፣ ሁሉ ለአንተ ይሆናል አለው።” (ሉቃስ 4:5–7) ራእይ 13:1, 2 ሰይጣን ለምድር አቀፉ የአገዛዝ ፖለቲካዊ ሥርዓት ‘ኃይል፣ ዙፋንና ታላቅ ሥልጣን’ እንደሰጠው ይገልጻል። ዳንኤል 10:13, 20 ሰይጣን በዋነኞቹ የምድር መንግሥታት ላይ አጋንንታዊ መሣፍንት ሾሞ እንደሚገዛ ያሳያል። ኤፌሶን 6:12 ስለነዚህ አጋንንት ሲናገር ‘አለቆች፣ ሥልጣናት፣ የዚህ ጨለማ ዓለም ገዥዎች፣ በሰማያዊ ሥፍራ ያሉ የክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት’ እንደሆኑ ይናገራል።

1 ዮሐንስ 5:19 “ዓለም በሞላው በክፉው እንደ ተያዘ” መናገሩ አያስደንቅም። ይሁን እንጂ ሥልጣኑ የሚቆየው ለተወሰነ ጊዜና ሁሉን የሚችለው አምላክ ይሖዋ እስከፈቀደለት ጊዜ ድረስ ብቻ ነው።

ሰይጣን የሰው ልጆችን እንዲያስት የሚፈቀድለት እስከ መቼ ድረስ ነው?

በሰይጣን ክፉ የነገሮች ሥርዓት መጨረሻ ቀኖች ውስጥ የምንኖር ስለመሆናችን መረጃ ለማግኘት በገጽ 94–97 ላይ “የዘመናት ስሌት” እና “የመጨረሻ ቀኖች” በሚሉት ርዕሶች ሥር ተመልከት።

ከሰይጣን ክፉ ተጽዕኖ የምንገላገልበት ዝግጅት በሚከተለው መንገድ በምሳሌ ተገልጿል:- “የጥልቁንም መክፈቻና ታላቁን ሰንሰለት በእጁ የያዘ መልአክ ከሰማይ ሲወርድ አየሁ። የቀደመውንም እባብ ዘንዶውን እርሱም ዲያብሎስና ሰይጣን የተባለውን ያዘው፣ ሺህ ዓመትም አሰረው፣ ወደ ጥልቅም ጣለው አሕዛብንም ወደ ፊት እንዳያስት ሺህ ዓመት እስከኪጸም ድረስ በእርሱ ላይ ዘግቶ ማኅተም አደረገበት፤ ከዚያም በኋላ ለጥቂት ጊዜ ይፈታ ዘንድ ይገባዋል።” (ራእይ 20:1–3) ከዚያ በኋላ ምን ይከተላል? “ያሳታቸውም ዲያብሎስ . . . ወደ እሳቱና ወደ ዲኑ ባሕር ተጣለ።” (ራእይ 20:10) ታዲያ ይህ ምን ማለት ነው? ራእይ 21:8 “ይኸውም ሁለተኛው ሞት ነው” በማለት መልሱን ይሰጠናል። ለዘላለም ይጠፋል!

ሰይጣን ‘በጥልቁ ውስጥ መጣሉ’ ለ1,000 ዓመታት ማንንም በማያስትባት ባድማ የሆነች ምድር ላይ ተወስኖ ይኖራል ማለት ነውን?

አንዳንድ ሰዎች ይህንን ሐሳብ ለመደገፍ ራእይ 20:3​ን ይጠቅሳሉ። (ከላይ ተጠቅሷል) “ጥልቁ” ወይም “መጨረሻ የሌለው ጉድጓድ” (ኪጄ ) ባድማ የሆነውን የምድር ገጽታ ያመለክታል ይላሉ። ግን ትክክል ነውን? ራእይ 12:7–9, 12 ሰይጣን በጥልቁ ውስጥ ከመጣሉ በፊት ከሰማይ ወደ ምድር ‘ተጥሎ’ በሰው ልጆች ላይ ብዙ መከራ እንደሚያመጣ ያመለክታል። ስለዚህ በ⁠ራእይ 20:3⁠ም መሠረት ሰይጣን ‘ወደ ጥልቁ ሲጣል’ ቀድሞም በነበረበት ምድር ተወስኖ ለሰዎች በማይታይ ሁኔታ ይኖራል ማለቱ አይደለም። “አሕዛብንም ወደ ፊት እንዳያስት ሺህ ዓመት እስኪፈጸም ድረስ” ከምድር ይርቃል። ራእይ 20:3 በሺው ዓመት መጨረሻ ላይ አሕዛብ ሳይሆኑ ሰይጣን ከጥልቁ ይፈታል ብሎ እንደሚናገር ልብ በል። ሰይጣን በሚፈታበት ጊዜ እነዚህ አሕዛብ ቀደም ብለው ዝግጁ ሆነው ይጠብቁታል።

ኢሳይያስ 24:1–6 እና ኤርምያስ 4:23–29 ይህንን እምነት ይደግፋሉ ተብለው የሚጠቀሱበት ጊዜ አለ። እነዚህ ጥቅሶች እንዲህ ይላሉ:- “እነሆ፣ እግዚአብሔር ምድርን ባዶ ያደርጋታል፣ ባድማም ያደርጋታል፣ . . . ምድር መፈታትን ትፈታለች፣ ፈጽማም ትበላሻለች፤ እግዚአብሔር ይህን ቃል ተናግሮአልና።” “ምድሪቱን አየሁ፣ እነሆም ባዶ ነበረች አንዳችም አልነበረባትም፤ . . . አየሁ፣ እነሆም፣ ሰው አልነበረም፣ . . . እግዚአብሔርም እንዲህ ይላል:- ምድር ሁሉ ባድማ ትሆናለች፤ . . . ከተማ ሁሉ ተለቅቃለች የሚቀመጥባትም ሰው የለም።” የእነዚህ ትንቢቶች ትርጉም ምንድን ነው? እነዚህ ትንቢቶች በመጀመሪያ በኢየሩሳሌምና በይሁዳ ምድር ላይ ተፈጽመዋል። ይሖዋ የቅጣት ፍርዱን ለመፈጸም ባቢሎናውያን ምድሪቱን እንዲወሩ አደረገ። በኋላም ባድማና ምድረ በዳ ሆነች። (በተጨማሪም ኤርምያስ 36:29⁠ን ተመልከት።) ይሁን እንጂ በዚያን ጊዜ አምላክ መላዋን ምድር ባድማ ወይም ሰው አልባ አላደረጋትም። ወደ ፊትም ቢሆን እንዲህ አያደርግም። (በተጨማሪም “ምድር” በሚለው ሥር እንዲሁም በገጽ 113–115 ላይ “ሰማይ” የሚለውን ዋና ርዕስ ተመልከት።) ይሁን እንጂ የአምላክን ስም የምታሰድበውን የከዳተኛይቱ ኢየሩሳሌም አምሳያ የሆነችውን ሕዝበ ክርስትናን እና መላውን የሰይጣን የሚታይ ድርጅት ባድማ ያደርጋል።

ሰይጣን በጥልቁ ውስጥ በሚሆንበት ጊዜ መላዋ ምድር በክርስቶስ የሺህ ዓመት ግዛት ዘመን ባድማ ከመሆን ይልቅ ገነት ትሆናለች። (“ገነት” የሚለውን ተመልከት።)