በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አምላክን የሚያስከብር ቤተሰብ መመሥረት

አምላክን የሚያስከብር ቤተሰብ መመሥረት

ምዕራፍ 15

አምላክን የሚያስከብር ቤተሰብ መመሥረት

1–3. ከትዳርና ልጅ ከመውለድ ጋር ተያይዘው የሚመጡ ችግሮችን አንዳንዶች መፍታት የሚያቅታቸው ለምንድን ነው? ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ በዚህ በኩል ሊረዳን የሚችለው ለምንድን ነው?

ለመኖሪያህ የሚሆን ቤት ለመሥራት አስበሃል እንበል። ቤቱ የሚሠራበትን መሬት ትገዛለህ። አዲሱ ቤትህ ምን እንደሚመስል ጉጉት ያድርብህና በዓይነ ሕሊናህ መመልከት ትጀምራለህ። ነገር ግን ለግንባታው የሚያገለግል መሣሪያም ሆነ ችሎታ ባይኖርህስ? ጥረትህ ሁሉ ከንቱ ሆኖ ይቀራል።

2 ብዙ ወንዶችና ሴቶች ደስተኛ ቤተሰብ ይኖረናል የሚል ጉጉት ይዘው ወደ ትዳር ዓለም ይገባሉ። ይሁን እንጂ ለዚህ የሚያስፈልገው መሣሪያም ሆነ ችሎታ አይኖራቸውም። ከሠርጉ ቀን በኋላ ብዙም ሳይቆይ አፍራሽ የሆኑ ጠባዮችና አዝማሚያዎች መታየት ይጀምራሉ። ጥልና ጭቅጭቅ የዕለታዊ ኑሯቸው ክፍል ይሆናሉ። ልጆች በሚወለዱበት ጊዜም አዲሶቹ አባትና እናት ልጅ የማሳደግ ችሎታቸው ትዳር ሲይዙ ከነበረበት ሁኔታ ያልተሻለ ሆኖ ያገ ኙታል።

3 ይሁን እንጂ ደስ ሊለን ይገባል፤ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ በዚህ ረገድ ሊረዳን ይችላል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙት መሠረታዊ ሥርዓቶች ደስተኛ ቤተሰብ ለመመሥረት እንደ መሣሪያ ሆነው ያገለግላሉ። (ምሳሌ 24:​3) ይህ እንዴት ሊሆን እንደሚችል እስቲ እንመልከት።

ደስታ የሰፈነበት ትዳር ለመመሥረት የሚያስችሉ መሣሪያዎች

4. በጋብቻ ውስጥ ችግሮች ይነሳሉ ብሎ መጠበቅ ተገቢ የሚሆነው ለምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ምን የሥነ ምግባር መስፈርቶችን አስቀምጧል?

4 አንድ ባልና ሚስት የቱንም ያህል እኩዮችና የሚመጣጠኑ መስለው ቢታዩ በስሜታቸው፣ ልጆች ሳሉ ባጋጠሟቸው ተሞክሮዎችና ከቤተሰቦቻቸው በቀሰሟቸው ነገሮች መለያየታቸው ያለ ነገር ነው። በዚህም ምክንያት ከተጋቡ በኋላ አንዳንድ ችግሮች ብቅ ማለታቸው አይቀርም። እነዚህ ችግሮች እንዴት ይፈታሉ? ሰዎች ቤት ለመሥራት ሲነሱ በመጀመሪያ የቤቱን ፕላን ይመለከታሉ። ቤቱ እንዴት መሠራት እንዳለበት የሚመራቸው የተነደፈው ፕላን ነው። መጽሐፍ ቅዱስም ደስተኛ ቤተሰብ ለመመሥረት የሚያስፈልጉትን የአምላክ መስፈርቶች የያዘ መጽሐፍ ነው። እስቲ ከእነዚህ የሥነ ምግባር መስፈርቶች አንዳንዶቹን እንመርምር።

5. መጽሐፍ ቅዱስ በጋብቻ ውስጥ ታማኝ የመሆንን አስፈላጊነት አጥብቆ የሚገልጸው እንዴት ነው?

5 ታማኝነት። ኢየሱስ “እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው” ብሏል። * (ማቴዎስ 19:​6) ሐዋርያው ጳውሎስ ደግሞ “መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል” ሲል ጽፏል። (ዕብራውያን 13:​4) ስለዚህ ባለ ትዳሮች ሁሉ በይሖዋ ፊት ለትዳር ጓደኞቻቸው ታማኝ የመሆን ግዴታ እንዳለባቸው ሊሰማቸው ይገባል።​— ዘፍጥረት 39:​7–9

6. ታማኝነት ጋብቻ እንዳይፈርስ ሊከላከል የሚችለው እንዴት ነው?

6 ታማኝነት ለአንድ ጋብቻ ክብርና አስተማማኝ መሠረት ይሰጠዋል። አንዳቸው ለሌላው ታማኝ ሆነው የሚኖሩ ባለ ትዳሮች የመጣው ቢመጣ እርስ በርሳቸው ተደጋግፈው እንደሚኖሩ ያውቃሉ። (መክብብ 4:​9–12) ችግር ገና ብቅ ማለት ሲጀምር ትዳራቸውን ጥለው ከሚሸሹት ተጋቢዎች ሁኔታ እንዴት የተለየ ነው! እንደነዚህ ያሉት ግለሰቦች ‘የተሳሳተ ምርጫ አድርጌአለሁ፣’ ‘ፍቅሬ አልቋል፣’ ‘መፍትሔው ሌላ ማግባት ብቻ ነው’ ብለው ለመደምደም ይቸኩላሉ። ይሁን እንጂ እንዲህ ያለው ድምዳሜ ሁለቱም ተጋቢዎች ስሜታዊ ብስለትና እድገት እንዲያገኙ ዕድል አይሰጣቸውም። ከዚህ ይልቅ እነዚህ ታማኝነት የጎደላቸው ግለሰቦች ያንኑ ችግራቸውን ወደ ሌላ የትዳር ጓደኛ ተሸክመው ይሄዳሉ። አንድ ሰው ጥሩ ቤት ቢኖረው ነገር ግን የቤቱ ጣሪያ ቢያፈስስ መፍትሔ የሚሆነው የጣሪያውን ቀዳዳ መድፈን እንጂ ቤት መቀየር አይደለም። የትዳር ጓደኛ መለወጥም በትዳር ውስጥ ለሚከሰተው ጭቅጭቅ መንስዔ የሆኑትን ችግሮች አያስወግድም። ስለዚህ ችግሮች በሚነሱበት ጊዜ ጋብቻ ጸንቶ የሚቆይበትን መንገድ ለማግኘት ተጣጣር እንጂ ከጋብቻው የምትላቀቅበትን መንገድ አትፈልግ። እንዲህ ያለው የታማኝነት አቋም የጋብቻው ጥምረት ሊጠበቅ፣ ሊጠናከርና እንክብካቤ ሊደረግለት አንደሚገባ ነገር አድርጋችሁ እንደምትመለከቱት ያሳ⁠ያል።

7. ባልና ሚስቶች ብዙ ጊዜ የሐሳብ ግንኙነት ማድረግ የሚያስቸግራቸው ለምንድን ነው? ይሁን እንጂ “አዲሱን ሰው” መልበስ እንዴት ሊረዳቸው ይችላል?

7 የሐሳብ ግንኙነት። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኝ አንድ ምሳሌ “ምክር ከሌለች ዘንድ የታሰበው ሳይሳካ ይቀራል፤ መካሮች በበዙበት ዘንድ ግን ይጸናል” ይላል። (ምሳሌ 15:​22) ይሁን እንጂ አንዳንድ ባልና ሚስቶች የሐሳብ ግንኙነት ማድረግ ይቸግራቸዋል። ለምን? ምክንያቱም የአንድ ሰው የሐሳብና የስሜት አገላለጽ ስልት ከሌላው ስለሚለይ ነው። ይህም ብዙ ጊዜ ላለመግባባትና ለብስጭት መንስዔ ይሆናል። አስተዳደግ በዚህ ጉዳይ ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ ያሳድራል። ለምሳሌ ያህል አንዳንዶች ያደጉት ወላጆች በሚጨቃጨቁበት ቤት ውስጥ ሊሆን ይችላል። አሁን አድገው የራሳቸውን ትዳር ሲመሠርቱ የትዳር ጓደኛቸውን እንዴት በደግነት እንደሚያነጋግሩ ላያውቁ ይችላሉ። ቢሆንም ቤታችሁ ‘ጭቅጭቅ የማይጠፋበት ቤት’ እስከሚሆን ድረስ ማዝቀጥ አይኖርበትም። (ምሳሌ 17:​1) መጽሐፍ ቅዱስ “አዲሱን ሰው” መልበስ እንዳለብን አጥብቆ ይናገራል። ክፉና መራራ መሆንን፣ ጩኸትና ስድብ የተሞሉ አነጋገሮችን አይደግፍም።​— ኤፌሶን 4:​22–24, 31

8. ከትዳር ጓደኛህ ጋር በሐሳብ መስማማት ባትችሉ ምን ነገር ሊረዳችሁ ይችላል?

8 በሐሳብ በማትስማሙበት ጊዜ ምን ልታደርጉ ትችላላችሁ? የስሜት መጋጋል ተፈጥሮ ሁኔታው ወደ ጠብ ማምራት ከጀመረ “ጠብ ሳይበረታ አንተ ክርክርን ተው” የሚለውን የምሳሌ 17:​14ን ምክር ብትከተሉ ጥሩ ይሆናል። ውይይቱን ለጊዜው አቁማችሁ አንተም ሆንክ የትዳር ጓደኛህ ቀዝቀዝ በምትሉበት ጊዜ ልትነጋገሩ ትችላላችሁ። (መክብብ 3:​1, 7) በማንኛውም ሁኔታ ቢሆን ‘ለመስማት የፈጠንክ፣ ለመናገርም የዘገየህ፣ ለቁጣም የዘገየህ’ ለመሆን ጥረት አድርግ። (ያዕቆብ 1:​19) ግብህ ለችግሩ እልባት ለመስጠት እንጂ በክርክሩ ለማሸነፍ መሆን የለበትም። (ዘፍጥረት 13:​8, 9) የአንተንም ሆነ የትዳር ጓደኛህን ቁጣ የሚያበርድና የሚያረጋጋ የአነጋገር ስልትና ቃል ምረጥ። (ምሳሌ 12:​18፤ 15:​1, 4፤ 29:​11) ከሁሉ በላይ ደግሞ እንደተቆጣችሁ አትቀጥሉ፤ ከዚህ ይልቅ አብራችሁ ወደ አምላክ በትሕትና በመጸለይ እንዲረዳችሁ ጠይቁት።​— ኤፌሶን 4:​26, 27፤ 6:​18

9. የሐሳብ ግንኙነት የሚጀምረው ከልብ ነው ሊባል የሚችለው ለምንድን ነው?

9 አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሳሌ “የጠቢብ ልብ አፉን ያስተምራል፣ ለከንፈሩም ትምህርትን [“የማግባባትን ችሎታ” አዓት] ይጨምራል” ይላል። (ምሳሌ 16:​23) ስለዚህ ጥሩ የሐሳብ ግንኙነት ለማድረግ ቁልፉ ልብ አንጂ አፍ አይደለም። ለትዳር ጓደኛህ ያለህ ዝንባሌ እንዴት ያለ ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ክርስቲያኖች እርስ በእርሳቸው እንዲተዛዘኑ ያበረታታል። (1 ጴጥሮስ 3:​8) የትዳር ጓደኛህ የሚያስጨንቅ ሁኔታ ሲያጋጥማት ይህን ዓይነት አዘኔታ ልታሳያት ትችላለህን? እንዲህ ካደረግህ ምን ምላሽ ብትሰጣት የተሻለ እንደሚሆን ልታውቅ ትችላለህ።​— ኢሳይያስ 50:​4

10, 11. አንድ ባል የ1 ጴጥሮስ 3:​7ን ምክር ሥራ ላይ ሊያውል የሚችለው እንዴት ነው?

10 ማክበርና ማስከበር። ክርስቲያን ባሎች “እናንተም ባሎች ሆይ፣ ደካማ ዕቃን በክብር እንደምትይዙ እነርሱን፣ ሴቶችን በክብር እየያዛችሁ በዚሁ መንገድ አብራችሁ በእውቀት መኖራችሁን ቀጥሉ” የሚል ምክር ተሰጥቷቸዋል። (1 ጴጥሮስ 3:​7 አዓት) ባል ለሚስቱ ክብር መስጠት አለበት ሲባል ለእርሷ ከፍተኛ ግምት ሊኖረው ይገባል ማለት ነው። ከሚስቱ ጋር “በእውቀት” የሚኖር ባል ስሜቶችዋን፣ ጠንካራ ጎኖችዋን፣ የማሰብ ችሎታዋንና ሰብዓዊ ክብርዋን ከፍ አድርጎ መመልከት ይኖርበታል። በተጨማሪም ይሖዋ ሴቶችን እንዴት እንደሚመለከትና እንዴት እንዲያዙ እንደሚፈልግ ይበልጥ ለማወቅ ፍላጎት ሊያድርበት ይገባል።

11 ቤትህ ውስጥ በጣም ጠቃሚ የሆነና በቀላሉ የሚሰበር ዕቃ አለ እንበል። ይህን ዕቃ በከፍተኛ ጥንቃቄ አትይዘውም? ጴጥሮስም “ደካማ ዕቃ” የሚለውን አነጋገር የተጠቀመው በዚህ መንፈስ ነው። ይህም አንድ ክርስቲያን ባል ለውድ ሚስቱ ጥንቃቄ የተሞላበት አያያዝ እንዲያደርግ ሊገፋፋው ይገባል።

12. አንዲት ሚስት ባልዋን በጥልቅ እንደምታከብር እንዴት ልታሳይ ትችላለች?

12 መጽሐፍ ቅዱስ ለሚስቶችስ ምን ምክር ይሰጣል? ጳውሎስ “ሚስትም ባልዋን በጥልቅ ታክብር” ሲል ጽፏል። (ኤፌሶን 5:​33 አዓት) ሚስት ባልዋ እንደሚያከብራትና እንደሚወዳት ሊሰማት እንደሚያስፈልግ ሁሉ ባልም ሚስቱ እንደምታከብረው እንዲሰማው ያስፈልጋል። ባልዋን የምታከብር ሚስት ባልዋ ክርስቲያን ይሁንም አይሁን አድራጎቷ የሚያስከትለውን ጉዳት ሳታጤን ጉድለቶቹን እየዞረች አታውጅም። ብቻቸውን ሲሆኑም ሆነ በሰዎች ፊት ባልዋን በመንቀፍና በመተቸት ክብሩን አትገፍም።​— 1 ጢሞቴዎስ 3:​11፤ 5:​13

13. የግል አስተያየትን ሰላማዊ በሆነ መንገድ መግለጽ የሚቻለው እንዴት ነው?

13 ይህ ማለት ግን ሚስት ፈጽሞ አስተያየቷን መግለጽ አትችልም ማለት አይደለም። ስሜቷን የሚረብሽ ነገር ካለ አክብሮት በተሞላበት ሁኔታ ሐሳቧን ልትገልጽ ትችላለች። (ዘፍጥረት 21:​9–12) ሐሳቧን የምትሰነዝርበት ሁኔታ ለባልዋ ኳስ ከመወርወር ጋር ሊመሳሰል ይችላል። ኳሱን በቀላል ሊይዘው በሚችልበት ሁኔታ ቀስ አድርጋ ልትወረውር ወይም መትቶ ሊጎዳው በሚችል ሁኔታ በኃይል ልትወረውረው ትችላለች። ባልና ሚስቱ እርስ በርሳቸው ከመካሰስና ከመወነጃጀል ይልቅ ደግነትና ጨዋነት በተሞላ ሁኔታ ቢነጋገሩ ምንኛ የተሻለ ይሆናል!​— ማቴዎስ 7:​12፤ ቆላስይስ 4:​6፤ 1 ጴጥሮስ 3:​3, 4

14. የትዳር ጓደኛህ/ጓደኛሽ በትዳራችሁ ውስጥ የአምላክን ቃል መሠረታዊ ሥርዓቶች ሥራ ላይ ለማዋል ደንታ ቢስ ከሆነ/ከሆነች ምን ማድረግ ይገባል?

14 ቀደም ሲል እንደተመለከትነው የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ደስተኛ ትዳር እንድትመሠርት ሊረዱህ ይችላሉ። የትዳር ጓደኛህ ወይም ጓደኛሽ መጽሐፍ ቅዱስ ስለሚናገራቸው ነገሮች ምንም ደንታ የሌለው ወይም የሌላት ቢሆኑስ? አምላክ በሚሰጠው እውቀት በመጠቀም የራስህን ወይም የራስሽን ድርሻ ብትፈጽሙ ብዙ ውጤት ሊገኝ ይችላል። ጴጥሮስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “እናንተ ሚስቶች ሆይ፣ ከባሎቻችሁ አንዳንዱ ለትምህርት የማይታዘዙ ቢኖሩ፣ በፍርሃት [“በጠለቀ አክብሮት” አዓት] ያለውን ንጹሑን ኑሮአችሁን እየተመለከቱ ያለ ትምህርት በሚስቶቻቸው ኑሮ እንዲገኙ [“እንዲሸነፉ” አዓት] ተገዙላቸው።” (1 ጴጥሮስ 3:​1, 2) ይህ ምክር ለመጽሐፍ ቅዱስ ግድ የሌላት ሚስት ላለችው ባልም ይሠራል። የትዳር ጓደኛችሁ የትኛውንም አካሄድ ብትመርጥ ወይም ቢመርጥ የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች አንተን ወይም አንቺን የተሻላችሁ የትዳር ጓደኛ እንድትሆኑ ሊያደርጓችሁ ይገባል። ከአምላክ የሚገኘው እውቀት የተሻላችሁ ወላጅ እንድትሆኑ ሊያደርጋችሁም ይችላል።

ልጆችን ከአምላክ በሚገኘው እውቀት መሠረት ማሳደግ

15. የተሳሳቱ የልጅ አስተዳደግ ዘዴዎች አንዳንድ ጊዜ ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፉት እንዴት ነው? ይሁን እንጂ ይህን ሰንሰለት እንዴት መበጠስ ይቻላል?

15 አንድ ሰው መጋዝ ወይም መዶሻ ስለኖረው ብቻ የተዋጣለት አናጺ አይሆንም። በተመሳሳይም አንድ ሰው ልጆች ስለወለደ ብቻ ጥሩ ወላጅ አይሆንም። ብዙውን ጊዜ ወላጆች አውቀውም ሆነ ሳያውቁት ልጆቻቸውን የሚያሳድጉት እነርሱ ራሳቸው ባደጉበት መንገድ ነው። በዚህ ሁኔታ የተሳሳቱ የአስተዳደግ ዘዴዎች ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፉ ይሄዳሉ። አንድ የዕብራውያን የጥንት ምሳሌ “አባቶች ጨርቋ የወይን ፍሬ በሉ፣ የልጆችም ጥርሶች ጠረሱ” ይላል። ይሁን እንጂ አንድ ሰው ወላጆቹ ያቆዩለትን መንገድ የግድ መከተል እንደማይኖርበት ቅዱሳን ጽሑፎች ያመለክታሉ። የይሖዋን ሕጎች የሚያስከብር የተለየ መንገድ ለመከተል ሊመርጥ ይችላል።​— ሕዝቅኤል 18:​2, 14, 17

16. ቤተሰብህ የሚያስፈልጉትን ነገሮች ማቅረብ በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? ይህስ ምን ምን ማድረግን ያካትታል?

16 ክርስቲያን ወላጆች ለልጆቻቸው ትክክለኛ አመራርና እንክብካቤ እንዲሰጡ ይሖዋ ይጠብቅባቸዋል። ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ለእርሱ ስለ ሆኑት ይልቁንም ስለ ቤተ ሰዎቹ የማያስብ ማንም ቢሆን፣ ሃይማኖትን የካደ ከማያምንም ሰው ይልቅ የሚከፋ ነው።” (1 ጢሞቴዎስ 5:​8) እንዴት ኃይለኛ አነጋገር ነው! ለልጆች የሚያስፈልጉትን አካላዊ፣ መንፈሳዊና ስሜታዊ ነገሮች የማቅረብን ኃላፊነት በሚገባ መወጣት አምላካዊ አቋም ያለው ሰው መብትና ግዴታ ነው። ወላጆች ለልጆቻቸው የሚያስደስት ሁኔታና አካባቢ ሊፈጥሩ የሚችሉባቸው መሠረታዊ ሥርዓቶች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተገልጸዋል። ከእነዚህ ውስጥ አንዳንዶቹን እንመልከት።

17. የአምላክ ቃል በልጆችህ ልብ ውስጥ እንዲቀረጽ ምን ማድረግ ያስፈልጋል?

17 ጥሩ ምሳሌ መሆን። እስራኤላውያን ወላጆች “ለልጆችህም [የአምላክን ቃል] አስተምረው፣ በቤትህም ስትቀመጥ፣ በመንገድም ስትሄድ፣ ስትተኛም፣ ስትነሣም ተጫወተው” የሚል ትእዛዝ ተሰጥቷቸው ነበር። ወላጆች ለልጆቻቸው አምላክ ያወጣቸውን የሥነ ምግባር መስፈርቶች እንዲያስተምሩ ይጠበቅባቸው ነበር። ከዚህ ትእዛዝ በፊት ግን “እኔም ዛሬ አንተን የማዝዘውን ይህን ቃል በልብህ ያዝ” የሚል ምክር ሰፍሯል። (ዘዳግም 6:​6, 7፤ ፊደላቱን ጋደል አድርገን የጻፍናቸው እኛ ነን።) አዎን፣ ወላጆች ራሳቸው የሌላቸውን ነገር ለልጆቻቸው ሊሰጡ አይችሉም። የአምላክ ቃል በልጆቻችሁ ልብ ውስጥ እንዲቀረጽና እንዲጻፍ ከፈለጋችሁ አስቀድሞ በእናንተ ልብ ውስጥ መጻፍ ይኖርበታል።​— ምሳሌ 20:​7፤ ከሉቃስ 6:​40 ጋር አወዳድር።

18. ፍቅር በማሳየት ረገድ ይሖዋ ለወላጆች ወደር የማይገኝለት አርዓያ የሆነው እንዴት ነው?

18 የምትወዷቸው መሆኑን አረጋግጡላቸው። ይሖዋ ኢየሱስ በተጠመቀበት ጊዜ “የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፣ በአንተ ደስ ይለኛል” ብሎት ነበር። (ሉቃስ 3:​22) በዚህ መንገድ ይሖዋ ኢየሱስን እንደሚወደውና በእርሱም ደስ እንደሚለው አረጋግጦለታል። ኢየሱስም ቆየት ብሎ ለአባቱ ‘ዓለም ሳይፈጠር ወደድኸኝ’ ብሎ ተናግሯል። (ዮሐንስ 17:​24) እንግዲያው አምላካዊ አቋም ያላቸው ወላጆች እንደ መሆናችሁ መጠን ልጆቻችሁን የምትወድዱ መሆናችሁን በቃልም ሆነ በአካል አዘውትራችሁ ግለጹላቸው። “ፍቅር ያንጻል” የሚለውን ቃል ምን ጊዜም አስታውሱ።​— 1 ቆሮንቶስ 8:​1

19, 20. ለልጆች በተገቢው መንገድ ተግሣጽ መስጠት ምን ነገሮችን ያካትታል? ወላጆች የይሖዋን ምሳሌ ከመከተል ሊጠቀሙ የሚችሉት እንዴት ነው?

19 ተግሣጽ። መጽሐፍ ቅዱስ በፍቅር የሚሰጥን ተግሣጽ አስፈላጊነት አበክሮ ይገልጻል። (ምሳሌ 1:​8) ልጆቻቸውን የመምራት ኃላፊነታቸውን ዛሬ ገሸሽ ያደረጉ ወላጆች ነገ ልብ የሚያሳዝን ውጤት እንደሚመጣባቸው የተረጋገጠ ነው። ቢሆንም ወላጆች በዚህ ረገድ ሚዛናቸውን ስተው ወደ ተቃራኒው ጽንፍ እንዳይሄዱ ተመክረዋል። ጳውሎስ “አባቶች ሆይ፣ ልባቸው እንዳይዝል ልጆቻችሁን አታበሳጩአቸው” ሲል ጽፏል። (ቆላስይስ 3:​21) ወላጆች ለልጆቻቸው እርማት ከማብዛት ወይም ሁልጊዜ በስህተቶቻቸውና በጉድለቶቻቸው ላይ ከማተኮር እንዲሁም የሚያደርጉትን ሙከራ ሁሉ ከመንቀፍ መቆጠብ አለባቸው።

20 የሰማዩ አባታችን ይሖዋ አምላክ በተግሣጽ አሰጣጥ ረገድ ጥሩ ምሳሌ ይሆነናል። አምላክ የሚሰጠው እርማት ከመጠኑ አልፎ አያውቅም። ለሕዝቡ “በመጠን እቀጣሃለሁ” ብሏቸዋል። (ኤርምያስ 46:​28) በዚህ ረገድ ወላጆች ይሖዋን መምሰል ይኖርባቸዋል። ከተገቢው መጠን ያለፈ ወይም ከታሰበለት የማረምና የማስተማር ዓላማ አልፎ የሚሄድ ተግሣጽ በእርግጥም ያበ ሳጫል።

21. ወላጆች የሚሰጡት ተግሣጽ ግቡን መምታት አለመምታቱን እንዴት ሊያረጋግጡ ይችላሉ?

21 ወላጆች የሚሰጡት ተግሣጽ ግቡን የሚመታ መሆኑንና አለመሆኑን እንዴት ሊገመግሙ ይችላሉ? ‘የምሰጠው ተግሣጽ ምን ውጤት ያስገኛል?’ ብለው ራሳቸውን ሊጠይቁ ይችላሉ። ተግሣጹ ትምህርት ሰጪ መሆን ይኖርበታል። ልጅህ ለምን ተግሣጽ እንደተሰጠው መረዳት ይኖርበታል። በተጨማሪም ወላጆች የሰጡት እርማት የኋላ የኋላ የሚያመጣውን ውጤት ማሰብ ይኖርባቸዋል። ሁሉም ልጆች በመጀመሪያ ላይ ተግሣጽ እንደማያስደስታቸው የታወቀ ነው። (ዕብራውያን 12:​11) ቢሆንም ተግሣጽ ልጁ ፍርሃት እንዲሰማው ወይም የተጣለና በተፈጥሮው ክፉ ስለሆነ ፈጽሞ ሊሻሻል እንደማይችል እንዲሰማው የሚያደርግ መሆን አይኖርበትም። ይሖዋ ሕዝቡን ከማረሙ በፊት “እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ” ብሏል። (ኤርምያስ 46:​28) አዎን፣ ልጁ እናንተ ወላጆቹ ምን ጊዜም ከጎኑ እንደቆማችሁና ድጋፋችሁ እንደማይለየው እንዲሰማው በሚያደርግ መንገድ እርማት ሊሰጠው ይገባዋል።

ጥሩ የአመራር ችሎታ ማዳበር

22, 23. ደስተኛ ቤተሰብ ለመመሥረት የሚያስችለውን የአመራር ብቃት እንዴት ልታዳብር ትችላለህ?

22 ይሖዋ ደስተኛ ቤተሰብ ለመመሥረት የሚያስችሉንን መሣሪያዎች በሙሉ ስለሰጠን ልናመሰግነው ይገባል። ይሁን እንጂ መሣሪያዎቹን ማግኘት ብቻውን በቂ አይሆንም። በመሣሪያዎቹ አዘውትረን በትክክል መጠቀም ይኖርብናል። ለምሳሌ ያህል አንድ ግንበኛ በመሣሪያዎቹ አጠቃቀም ረገድ ልክ ያልሆኑ ልማዶች ይኖሩት ይሆናል። አንዳንዶቹን መሣሪያዎች ፈጽሞ ስሕተት ለሆነ ዓላማ ሊያውላቸው ይችላል። እንዲህ ካደረገ የሚሠራው ነገር የጥራት ደረጃው ዝቅተኛ ይሆናል። አንተም በተመሳሳይ በቤተሰብህ ውስጥ ጤናማ ያልሆነ ልማድ ቀደም ሲል ሠርጎ የገባ መሆኑን አሁን ትገነዘብ ይሆናል። አንዳንዶቹ ልማዶች ሥር የሰደዱ ይሆኑና ፈጥኖ ለመለወጥ የሚያስቸግሩ ሊሆኑ ይችላሉ። ቢሆንም “ጠቢብ እነዚህን ከመስማት ጥበብን ይጨምራል፣ አስተዋይም መልካም ምክርን ገንዘቡ ያደርጋል” የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር ተከተል።​— ምሳሌ 1:​5

23 አምላክ የሚሰጠውን እውቀት መቅሰምህን ከቀጠልክ ብቃት ያለው አመራር የመስጠት ችሎታ ልታዳብር ትችላለህ። በቤተሰብ ሕይወት ላይ ተፈጻሚነት ያላቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች በንቃት ተከታተል። አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝም ተገቢውን ማስተካከያ አድርግ። በትዳራቸውና በወላጅነታቸው ጥሩ ምሳሌ የሚሆኑ የጎለመሱ ክርስቲያኖችን ተመልከት። አነጋግራቸው። ከሁሉ በላይ ደግሞ የሚያሳስብህን ነገር ሁሉ ለይሖዋ በጸሎት አስታውቅ። (መዝሙር 55:​22፤ ፊልጵስዩስ 4:​6, 7) እርሱን የሚያስከብርና ደስታ የሰፈነበት የቤተሰብ ሕይወት እንዲኖርህ ሊረዳህ ይችላል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.5 የትዳር ጓደኛ ፈትቶ ሌላ ለማግባት የሚያስችለው ቅዱስ ጽሑፋዊ ምክንያት “ምንዝር” ወይም ከጋብቻ ውጭ ሩካቤ ሥጋ መፈጸም ብቻ ነው።​— ማቴዎስ 19:​9

እውቀትህን ፈትሽ

ታማኝነት፣ የሐሳብ ግንኙነትና የትዳር ጓደኛን ማክበርና ማስከበር በትዳር ለመደሰት አስተዋጽኦ የሚያደርጉት እንዴት ነው?

ወላጆች ልጆቻቸውን እንደሚወዱ በምን መንገዶች ሊያረጋግጡላቸው ይችላሉ?

ተገቢ የሆነ ተግሣጽ ምን ነገሮችን ያካትታል?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 147 ላይ የሚገኝ ባለ ሙሉ ገጽ ሥዕል]