በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አምላክ የሚቀበለው የእነማንን አምልኮ ነው?

አምላክ የሚቀበለው የእነማንን አምልኮ ነው?

ምዕራፍ 5

አምላክ የሚቀበለው የእነማንን አምልኮ ነው?

1. አንዲት ሳምራዊት ሴት ስለ አምልኮ ምን ነገር ለማወቅ ፈለገች?

‘አምላክ የሚቀበለው የእነማንን አምልኮ ነው?’ ብለህ ራስህን ጠይቀህ ታውቃለህ? አንዲት ሴት በሰማርያ አገር በገሪዛን ተራራ አጠገብ ኢየሱስን ባነጋገረች ጊዜ ይህ ጥያቄ ወደ አእምሮዋ ሳይመጣ አልቀረም። በሳምራውያንና በአይሁዳውያን መካከል ያለውን የአምልኮ ልዩነት በማመልከት “አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ፤ እናንተም:- ሰው ሊሰግድበት የሚገባው ስፍራ በኢየሩሳሌም ነው ትላላችሁ አለችው።” (ዮሐንስ 4:​20) ታዲያ ኢየሱስ ለሳምራዊቷ ሴት አምላክ ሁሉንም አምልኮ ይቀበላል አላት? ወይስ አምላክን ለማስደሰት ምን ምን እንደሚያስፈልግ ለይቶ ነገ⁠ራት?

2. ኢየሱስ የሳምራዊቷን ጥያቄ ሲመልስ ምን አለ?

2 ኢየሱስ “በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል” የሚል ያልተጠበቀ መልስ ሰጣት። (ዮሐንስ 4:​21) ሳምራውያን ለብዙ ዘመን ይሖዋን ሲፈሩና በገሪዛን ተራራ ሌሎችን አማልክት ሲያመልኩ የኖሩ ሕዝብ ናቸው። (2 ነገሥት 17:​33) አሁን ግን ኢየሱስ ይህ ተራራም ሆነ ኢየሩሳሌም ለእውነተኛ አምልኮ አስፈላጊ የማይሆኑበት ጊዜ እንደሚመጣ ተና⁠ገረ።

በመንፈስና በእውነት ማምለክ

3. (ሀ) ሳምራውያን አምላክን ያላወቁት ለምን ነበር? (ለ) የታመኑ አይሁዶችና ሌሎች ሰዎች አምላክን ሊያውቁ የቻሉት እንዴት ነው?

3 ኢየሱስ በመቀጠል ለሳምራዊቷ ሴት “እናንተስ ለማታውቁት ትሰግዳላችሁ፤ እኛ መዳን ከአይሁድ ነውና ለምናውቀው እንሰግዳለን” አላት። (ዮሐንስ 4:​22) ሳምራውያን የተሳሳተ ሃይማኖታዊ አስተሳሰብ ነበራቸው። በመንፈስ አነሳሽነት የተጻፉ ናቸው ብለው የሚቀበሉት በራሳቸው መስፈርት ብቻ የሳምራውያን ፔንታተች ብለው ይጠሯቸው የነበሩትን የመጀመሪያዎቹን አምስት የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት ብቻ ነበር። በዚህ ምክንያት አምላክን በትክክል ሊያውቁ አልቻሉም። አይሁዳውያን ግን የተሟላ የቅዱሳን ጽሑፎች እውቀት አግኝተው ነበር። (ሮሜ 3:​1, 2) የታመኑ አይሁዳውያንና ለማዳመጥ ፈቃደኛ የሆኑ ሌሎች ሰዎች አምላክን ለማወቅ የሚያስፈልጋቸውን መረጃ በሙሉ ከቅዱሳን ጽሑፎች ለማግኘት ችለው ነበር።

4. ኢየሱስ በተናገረው መሠረት አይሁዳውያንም ሆኑ ሳምራውያን አምልኮታቸው በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት እንዲኖረው ከፈለጉ ምን ማድረግ ነበረባቸው?

4 እንዲያውም ኢየሱስ አይሁዳውያንም ሆኑ ሳምራውያን አምላክን ለማስደሰት ከፈለጉ አምልኮ የሚያቀርቡበትን መንገድ ማስተካከል እንደሚያስፈልጋቸው አመልክቷል። እንዲህ አለ:- “በእውነት የሚሰግዱ ለአብ በመንፈስና በእውነት የሚሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኗል። አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና፤ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፣ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል።” (ዮሐንስ 4:​23, 24) አምላክን በእምነትና በፍቅር በተሞላ ልብ ተገፋፍተን “በመንፈስ” ማምለክ ያስፈልገናል። ቃሉን፣ መጽሐፍ ቅዱስን በማጥናትና በዚያ ውስጥ በተገለጠልን እውነት መሠረት ብናመልከው እርሱን “በእውነት” አምልከነዋል ለማለት እንችላለን። ይህን ለማድረግ ትመኛለህን?

5. (ሀ) “አምልኮ” ሲባል ምን ማለት ነው? (ለ) አምላክ አምልኮታችንን እንዲቀበልልን ከፈለግን ምን ማድረግ ይኖርብናል?

5 አምላክ እውነተኛ አምልኮ እንደሚፈልግ ኢየሱስ አበክሮ ተናግሯል። ይህም ይሖዋ የማይቀበላቸው የአምልኮ ዓይነቶች እንዳሉ ያመለክታል። አምላክን ማምለክ ማለት ለእርሱ ጥልቅ አክብሮት ማሳየትና ቅዱስ አገልግሎት ማቅረብ ማለት ነው። ለአንድ ኃያል ገዥ አክብሮት ማሳየት ብትፈልግ እርሱን ለማገልገልና የሚያስደስተውን ነገር ለማድረግ መፈለግህ አይቀርም። እኛም በተመሳሳይ አምላክን ለማስደሰት እንፈልጋለን። ስለዚህም ‘የራሴ ሃይማኖት ተስማምቶኛል’ ከማለት ይልቅ አምልኮታችን የአምላክን ብቃቶች የሚያሟላ መሆኑንና አለመሆኑን ማረጋገጥ ያስፈልገናል።

የአብን ፈቃድ ማድረግ

6, 7. ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ ነን የሚሉትን አንዳንድ ሰዎች የማይቀበለው ለምንድን ነው?

6 እስቲ ማቴዎስ 7:​21–23ን እናንብብና ሁሉም የአምልኮ ዓይነት አምላክን የሚያስደስት መሆንና አለመሆኑን የሚያረጋግጠውን አንዱን ወሳኝ ነገር ለይተን ለማወቅ እንሞክር። ኢየሱስ እንዲህ አለ:- “በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፣ ጌታ ሆይ፣ ጌታ ሆይ፣ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም። በዚያ ቀን ብዙዎች:- ጌታ ሆይ፣ ጌታ ሆይ፣ በስምህ ትንቢት አልተናገርንምን፣ በስምህስ አጋንንትን [ክፉ መንፈሳዊ ፍጡራንን] አላወጣንምን፣ በስምህስ ብዙ ተአምራት አላደረግንምን? ይሉኛል። የዚያን ጊዜም:- ከቶ አላወቅኋችሁም፤ እናንተ ዓመፀኞች፣ ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ።”

7 ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታ መሆኑን መቀበል በእውነተኛ አምልኮ ውስጥ አስፈላጊ ከሆኑት ነገሮች አንዱ ነው። ይሁን እንጂ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ነን የሚሉ የብዙ ሰዎች አምልኮ አንድ የሚጎድለው ነገር እንደሚኖር ጥቅሱ ያመለክታል። አንዳንዶች በተአምር እንደመፈወስ የመሰሉትን “ተአምራት” እንደሚያደርጉ ተናግሯል። ይሁን እንጂ ኢየሱስ እጅግ አስፈላጊ ነው ያለውን ነገር ሳያደርጉ ቀርተዋል። ‘የአባቱን ፈቃድ’ አላደረጉም። አምላክን ለማስደሰት ከፈለግን የአብን ፈቃድ ማወቅና ማድረግ ይኖርብናል።

ትክክለኛ እውቀት ከብክለት ይከላከላል

8. የአምላክን ፈቃድ ለማድረግ ከፈለግን ምን ነገር ይጠበቅብናል? ምን ዓይነት የተሳሳተ አመለካከትስ ማስወገድ ይኖርብናል?

8 የአምላክን ፈቃድ ለማድረግ ይሖዋ አምላክንና ኢየሱስ ክርስቶስን በትክክል ማወቅ ያስፈልጋል። ይህን የመሰለው እውቀት ወደ ዘላለም ሕይወት ይመራል። ስለዚህ ሁላችንም ከአምላክ ቃል ከመጽሐፍ ቅዱስ የሚገኘውን ትክክለኛ እውቀት ስለ መቅሰም አጥብቀን ለማሰብ እንደምንፈልግ የተረጋገጠ ነው። አንዳንዶች በቅንነትና በቅንዓት እስካመለክን ድረስ ትክክለኛ እውቀት ስለማግኘት የምንጨነቅበት ምክንያት የለም ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ‘ብዙ ካወቅህ ብዙ ይጠበቅብሃል’ ይላሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ግን ስለ አምላክና ስለ ዓላማዎቹ ያለንን እውቀት እንድንጨምር ያበረታታናል።​— ኤፌሶን 4:​13፤ ፊልጵስዩስ 1:​9፤ ቆላስይስ 1:​9

9. ትክክለኛ እውቀት አምልኮታችንን ከብከላ የሚጠብቅልን እንዴት ነው? ይህን የመሰለው መከላከያ አስፈላጊ የሆነውስ ለምንድን ነው?

9 እንዲህ ያለው እውቀት አምልኮታችን እንዳያድፍና እንዳይበከል ይከላከልልናል። ሐዋርያው ጳውሎስ “የብርሃን መልአክ” ለመምሰል ስለሚሞክር አንድ መንፈሳዊ ፍጡር ተናግሯል። (2 ቆሮንቶስ 11:​14) ሰይጣን የተባለው ይህ መንፈሳዊ ፍጡር ራሱን በመሰወር የአምላክን ፈቃድ የሚቃረን ነገር እንድናደርግ ለማሳት ይሞክራል። የሰይጣን ተባባሪዎች የሆኑ ሌሎች መንፈሳውያን ፍጥረታትም የሰዎችን አምልኮ ሲበክሉ ቆይተዋል። ጳውሎስ “አሕዛብ የሚሠዉት ለአጋንንት እንዲሆን እንጂ ለእግዚአብሔር እንዳይሠዉ እላለሁ” ብሏል። (1 ቆሮንቶስ 10:​20) ብዙዎች አምላክ የሚፈልግባቸውን ነገር የማያደርጉ ቢሆኑም አምልኮታችን ትክክለኛ ነው ብለው ያስቡ ይሆናል። ንጹሕ ወዳልሆነና ሐሰተኛ ወደሆነ አምልኮ ተሳስተው ገብተዋል። ወደፊት ስለ ሰይጣንና ስለ አጋንንት የምንማራቸው ተጨማሪ ነገሮች ቢኖሩም እነኚህ የአምላክ ጠላቶች የሰው ልጆችን አምልኮ በመበከል ላይ መሆናቸው የተረጋገጠ ነው።

10. አንድ ሰው ሆን ብሎ ውኃ የምትቀዳበትን ምንጭ ቢመርዝብህ ምን ታደርጋለህ? የአምላክ ቃል ትክክለኛ እውቀትስ ምን እንድናደርግ ያስችለናል?

10 አንድ ሰው ውኃ በምትቀዳበት ምንጭ ውስጥ ሆን ብሎ መርዝ እንደጨመረበት ብታውቅ ከዚሁ ውኃ መጠጣትህን ትቀጥላለህን? ሌላ ንጹሕና ያልተመረዘ ውኃ የምታገኝበትን እርምጃ ወዲያው እንደምትወስድ የታወቀ ነው። ከአምላክ ቃል የተገኘ ትክክለኛ እውቀትም እውነተኛውን ሃይማኖት ለይተን ለማወቅና አንድን አምልኮ በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት እንዲያጣ የሚያደርጉ እድፈቶችን ለማስወገድ ያስችለናል።

የሰው ሥርዓት የሆነ ትምህርት

11. የብዙ አይሁዳውያን አምልኮ ምን ጉድለት ነበረው?

11 ኢየሱስ በምድር ላይ ይኖር በነበረበት ዘመን ብዙ አይሁዳውያን ይመላለሱ የነበሩት ትክክለኛ በሆነና አምላክ በሚሰጠው እውቀት እየተመሩ አልነበረም። በዚህም ምክንያት በይሖዋ ፊት ንጹሕ አቋም ይዘው ለመገኘት ሳይችሉ ቀርተዋል። ጳውሎስ ስለነዚህ አይሁዳውያን ሲጽፍ “በእውቀት አይቅኑ እንጂ ለእግዚአብሔር እንዲቀኑ እመሰክርላቸዋለሁ” ብሏል። (ሮሜ 10:​2) አምላክ የተናገራቸውን ከማዳመጥ ይልቅ እርሱን ስለሚያመልኩበት መንገድ የራሳቸውን ውሳኔ አደረጉ።

12. የእስራኤላውያንን አምልኮ ያሳደፈባቸው ነገር ምን ነበር? ይህስ ምን ውጤት አስከተለባቸው?

12 እስራኤላውያን ከአምላክ የተሰጠ ንጹሕ ሃይማኖት ነበራቸው፤ በኋላ ግን በሰዎች ትምህርትና ፍልስፍና ተበከለ። (ኤርምያስ 8:​8, 9፤ ሚልክያስ 2:​8, 9፤ ሉቃስ 11:​52) ፈሪሳውያን ተብለው ይጠሩ የነበሩት ሃይማኖታዊ መሪዎቻቸው አምልኮታችን በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት አለው ብለው የሚያስቡ ቢሆኑም ኢየሱስ እንደሚከተለው ብሏቸዋል:- “ኢሳይያስ ስለ እናንተ ስለ ግብዞች:- ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል ልቡ ግን ከእኔ በጣም የራቀ ነው የሰውም ሥርዓት የሆነ ትምህርት እያስተማሩ በከንቱ ያመልኩኛል ተብሎ እንደ ተጻፈ በእውነት ትንቢት ተናገረ።”​— ማርቆስ 7:​6, 7

13. ፈሪሳውያን ያደረጉትን እኛም እያደረግን ሊሆን የሚችለው እንዴት ነው?

13 እኛስ እንደ ፈሪሳውያን ልንሆን የምንችልበት መንገድ ይኖር ይሆን? አምላክ ራሱ ስለ አምልኮ የተናገረውን ከመመርመር ይልቅ ከአባቶቻችን ሲወርድ ሲዋረድ የመጣውን ወግና ልማድ ብንከተል እንደነርሱ ልንሆን እንችላለን። ጳውሎስ ስለዚህ አደገኛ ሁኔታ ሲያስጠነቅቅ እንዲህ ብሏል:- “መንፈስ ግን በግልጥ:- በኋለኞች ዘመናት አንዳንዶች የሚያስቱ መናፍስትንና በውሸተኞች ግብዝነት የተሰጠውን የአጋንንትን ትምህርት እያደመጡ፣ ሃይማኖትን ይክዳሉ ይላል።” (1 ጢሞቴዎስ 4:​1) ስለዚህ አምልኮታችን አምላክን ያስደስተዋል ብሎ ማሰብ ብቻውን አይበቃም። አምልኮታችን ከኢየሱስ ጋር ተገናኝታ እንደተነጋገረችው ሳምራዊት ከወላጆቻችን የወረስነው ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ የምናደርገው ነገር በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት ያለው መሆኑን ማረጋገጥ ያስፈልገናል።

አምላክን ላለማሳዘን መጠንቀቅ

14, 15. ስለ አምላክ ፈቃድ መጠነኛ እውቀት ቢኖረንም እንኳን መጠንቀቅ የሚያስፈልገን ለምንድን ነው?

14 ካልተጠነቀቅን አምላክ የማይቀበለውን ነገር ልናደርግ እንችላለን። ለምሳሌ ያህል ሐዋርያው ዮሐንስ በመልአኩ እግር ላይ ወድቆ ሰግዶለታል። መልአኩ ግን “እንዳታደርገው ተጠንቀቅ፤ ከአንተ ጋር የኢየሱስም ምስክር ካላቸው ከወንድሞችህ ጋር አብሬ ባሪያ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ” ብሎታል። (ራእይ 19:​10) ታዲያ አምልኮትህ በማንኛውም ዓይነት የጣዖት አምልኮ ያልተበከለ መሆኑን ማረጋገጥ አስፈላጊ መሆኑን ተገንዝበሃል?​— 1 ቆሮንቶስ 10:​14

15 አንዳንድ ክርስቲያኖች አምላክን የማያስደስት ሃይማኖታዊ ልማድ መፈጸም በጀመሩ ጊዜ ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጠይቋቸዋል:- “እንደ ገና ወደ ደካማ ወደሚናቅም ወደ መጀመሪያ ትምህርት እንዴት ትመለሳላችሁ? እንደ ገና ባሪያዎች ሆናችሁ ዳግመኛ ለዚያ ልትገዙ ትወዳላችሁን? ቀንንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችሁ። ምናልባት በከንቱ ለእናንተ ደክሜአለሁ ብዬ እፈራችኋለሁ።” (ገላትያ 4:​8–11) እነዚህ ሰዎች አምላክን አውቀው ነበር። በኋላ ግን በይሖዋ ዘንድ ተቀባይነት የሌላቸውን ሃይማኖታዊ ልማዶችና በዓሎች በማክበር ተሳስተዋል። እኛም ጳውሎስ እንዳለው “ለጌታ ደስ የሚያሰኘውን” መርምረን ማረጋገጥ ያስፈልገናል።​— ኤፌሶን 5:​10

16. ዮሐንስ 17:​16 እና 1 ጴጥሮስ 4:​3 በዓሎችና ልማዶች አምላክን ያስደስቱና አያስደስቱ እንደሆነ እንድንወስን የሚረዱን እንዴት ነው?

16 የአምላክን መሠረታዊ ሥርዓቶች የሚያስጥሱ ሃይማኖታዊ በዓሎችንና ልማዶችን ማስወገድ ያስፈልገናል። (1 ተሰሎንቄ 5:​21) ለምሳሌ ያህል ኢየሱስ ስለ ተከታዮቹ ሲናገር “እኔ ከዓለም እንዳይደለሁ ከዓለም አይደሉም” ብሏል። (ዮሐንስ 17:​16) ታዲያ ሃይማኖትህ ከዚህ ዓለም ጉዳዮች ገለልተኛ እንድንሆን የሚያዘውን መሠረታዊ ሥርዓት በሚቃረኑ በዓሎ⁠ችና የአከባበር ሥነ ሥርዓቶች ይካፈላልን? ወይም የሃይማኖትህ ተከታዮች ሐዋርያው ጴጥሮስ የገለጻቸውን የመሰሉ ድርጊቶች የሚፈጽሙባቸው ልማዶችና በዓሎች አሉን? ሐዋርያው ጴጥሮስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና።”​— 1 ጴጥሮስ 4:​3

17. የዓለምን መንፈስ ከሚያንጸባርቅ ከማንኛውም ነገር መራቅ የሚኖርብን ለምንድን ነው?

17 ሐዋርያው ዮሐንስ በዙሪያችን ያለውን ለአምላክ ደንታ የሌለው ዓለም መንፈስ ከሚያንጸባርቁ ድርጊቶች መራቅ አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝቧል። እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ዓለምን ወይም በዓለም ያሉትን አትውደዱ፤ በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለ ገንዘብም መመካት ከዓለም ስለ ሆነ እንጂ ከአባት ስላልሆነ፣ ማንም ዓለምን ቢወድ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም። ዓለሙም ምኞቱም ያልፋሉ፤ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል።” (1 ዮሐንስ 2:​15–17) ‘የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርጉ ለዘላለም ይኖራሉ’ የሚለውን አስተውለሃል? አዎን፣ የአምላክን ፈቃድ ብናደርግና የዚህን ዓለም መንፈስ ከሚያንጸባርቁ ድርጊቶች ብንርቅ የዘላለም ሕይወት የማግኘት ተስፋ ሊኖረን ይችላል!

የአምላክን የሥነ ምግባር መስፈርቶች ማሟላት

18. አንዳንድ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ስለ ምግባር የተሳሳተ አመለካከት የነበራቸው እንዴት ነው? እኛስ ከዚህ ምን እንማራለን?

18 ይሖዋ አምላኪዎቹ እንዲሆኑ የሚፈልገው ከፍተኛ የሆኑትን የሥነ ምግባር መስፈርቶቹን የሚያሟሉ ሰዎችን ነው። በጥንትዋ ቆሮንቶስ ይኖሩ ከነበሩ ክርስቲያኖች አንዳንዶቹ አምላክ የብልግና ድርጊቶችን ዝም ብሎ ይመለከታል የሚል የተሳሳተ አስተሳሰብ አድሮባቸው ነበር። 1 ቆሮንቶስ 6:​9, 10ን ብናነብ ምን ያህል ተሳስተው እንደነበረ እንገነዘባለን። አምላክን ተቀባይነት ባለው መንገድ ለማምለክ ከፈለግን በአነጋገራችንም ሆነ በድርጊቶቻችን እሱን ማስደሰት ይገባናል። የአንተስ አምልኮ አምላክን እንድታስደስት እያስቻለህ ነውን?​— ማቴዎስ 15:​8፤ 23:​1–3

19. እውነተኛ አምልኮ ከሌሎች ሰዎች ጋር የሚኖረንን ግንኙነት የሚነካው እንዴት ነው?

19 በተጨማሪም የአምላክ የሥነ ምግባር መስፈርቶች ከሌሎች ሰዎች ጋር በምናደርጋቸው ግንኙነቶች መንጸባረቅ ይኖርባቸዋል። ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች ለእኛ ሊያደርጉልን የምንፈልገውን ሁሉ ለሌሎች እንድናደርግ አሳስቦናል። ይህን ማድረግ አንደኛው የእውነተኛ አምልኮ ክፍል ነው። (ማቴዎስ 7:​12) ስለ ወንድማማች መዋደድ የተናገረውንም አስተውል። “እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ፣ ደቀ መዛሙርቴ እንደሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ” ብሏል። (ዮሐንስ 13:​35) የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት እርስ በርሳቸው መዋደድና ለአምልኮ ባልደረቦቻቸውም ሆነ ለሌሎች ሰዎች ጥሩ ማድረግ ይኖርባቸዋል።​— ገላትያ 6:​10

በሙሉ ነፍስ የሚቀርብ አምልኮ

20, 21. (ሀ) አምላክ የሚፈልገው ምን ዓይነት አምልኮ ነው? (ለ) ይሖዋ በሚልክያስ ዘመን የእስራኤላውያንን አምልኮ ያልተቀበለው ለምንድን ነው?

20 በልብህ አምላክን ተቀባይነት ባለው መንገድ ለማምለክ ትፈልግ ይሆናል። እንግዲያው ይሖዋ ስለ አምልኮ ያለው አመለካከት ሊኖርህ ይገባል። አስፈላጊው ነገር የእኛ አመለካከት ሳይሆን የአምላክ አመለካከት እንደሆነ ደቀ መዝሙሩ ያዕቆብ አበክሮ ተናግሯል። እንዲህ አለ:- “ንጹሕ የሆነ ነውርም የሌለበት አምልኮ በእግዚአብሔር አብ ዘንድ ይህ ነው፤ ወላጆች የሌላቸውን ልጆች ባልቴቶችንም በመከራቸው መጠየቅ፣ በዓለምም ከሚገኝ እድፍ ሰውነቱን መጠበቅ ነው።” (ያዕቆብ 1:​27) እያንዳንዳችን አምላክን የማስደሰት ፍላጎት ካለን አምልኮታችን አምላካዊ ባልሆኑ ድርጊቶች ያልተበከለ መሆኑንና አምላክ አስፈላጊ ናቸው ከሚላቸው ነገሮች መካከል የማናደርጋቸው ነገሮች አለመኖራቸውን ማረጋገጥ ያስፈልገናል።​— ያዕቆብ 1:​26

21 ይሖዋን የሚያስደስተው ንጹሕና በሙሉ ነፍስ የቀረበ አምልኮ ብቻ ነው። (ማቴዎስ 22:​37፤ ቆላስይስ 3:​23) የእስራኤል ብሔር ይህን ሳያደርግ በቀረ ጊዜ አምላክ “ልጅ አባቱን፣ ባሪያም ጌታውን ያከብራል፤ እኔስ አባት ከሆንሁ ክብሬ ወዴት አለ? ጌታስ ከሆንሁ መፈራቴ ወዴት አለ?” ብሏቸዋል። የታወሩ፣ አንካሳ የሆኑና የታመሙ እንስሳትን መሥዋዕት አድርገው በማቅረብ አምላክን አሳዝነውት ነበር። እርሱም ይህን ዓይነቱን የአምልኮ ድርጊት አልተቀበለውም። (ሚልክያስ 1:​6–8) ይሖዋ በጣም ንጹሕ የሆነ አምልኮ ሊቀርብለት የሚገባው አምላክ ነው። ይህንንም አምልኮ ከማንም ወይም ከምንም ጋር ሊጋራ አይፈልግም።​— ዘጸአት 20:​5፤ ምሳሌ 3:​9፤ ራእይ 4:​11

22. አምልኮታችን በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት እንዲያገኝ ከፈለግን ከምን ነገር መራቅ ይኖርብናል? ምንስ ማድረግ ይገባናል?

22 ኢየሱስ ያነጋገራት ሳምራዊት መለኮታዊ ተቀባይነት ባለው መንገድ አምላክን የማምለክ ፍላጎት የነበራት ይመስላል። እኛም ይህን የመሰለ ፍላጎት ካለን ከማንኛውም ዓይነት በካይ ትምህርትና ልማድ እንርቃለን። (2 ቆሮንቶስ 6:​14–18) ከዚህ ይልቅ ስለ አምላክ ትክክለኛ እውቀት ለማግኘትና ፈቃዱን ለማድረግ ብርቱ ጥረት እናደርጋለን። አምላክ ተቀባይነት ላለው አምልኮ ያወጣቸውን ደንቦች አጥብቀን እንከተላለን። (1 ጢሞቴዎስ 2:​3, 4) የይሖዋ ምሥክሮች ለማድረግ የሚጥሩት ይህንን ነው። አንተም ከእነርሱ ጋር ተባብረህ አምላክን “በመንፈስና በእውነት” እንድታመልክ ሞቅ ባለ መንፈስ ያሳስቡሃል። (ዮሐንስ 4:​24) ኢየሱስ “አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና” ብሏል። (ዮሐንስ 4:​23) እንደዚህ ዓይነት ሰው እንደምትሆን ተስፋ እናደርጋለን። አንተም እንደዚያች ሳምራዊት ሴት የዘላለም ሕይወት ለማግኘት እንደምትፈልግ አያጠራጥርም። (ዮሐንስ 4:​13–15) ይሁን እንጂ ሰዎች ሲያረጁና ሲሞቱ ትመለከታለህ። ይህ የሚሆንበትን ምክንያት የሚቀጥለው ምዕራፍ ያብራራል።

እውቀትህን ፈትሽ

በዮሐንስ 4:​23, 24 ላይ እንደተመለከተው አምላክ የሚቀበለው ምን ዓይነት አምልኮ ነው?

አምላክ በአንዳንድ ልማዶችና በዓሎች ይደሰትና አይደሰት እንደሆነ እንዴት ልናውቅ እንችላለን?

በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት ያለው አምልኮ ሊያሟላቸው ከሚገቡት ብቃቶች አንዳንዶቹ ምንድን ናቸው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 44 ላይ የሚገኝ ባለ ሙሉ ገጽ ሥዕል]