በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፉ መናፍስታዊ ኃይሎችን ተቋቋማቸው

ክፉ መናፍስታዊ ኃይሎችን ተቋቋማቸው

ምዕራፍ 12

ክፉ መናፍስታዊ ኃይሎችን ተቋቋማቸው

1. ኢየሱስ ከክፉ መናፍስት ጋር በተገናኘ ጊዜ ምን አደረገ?

ኢየሱስ ክርስቶስ ወዲያው እንደተጠመቀ ሊጸልይና ሊያሰላስል ወደ ይሁዳ ምድረ በዳ ሄደ። በዚያም ሰይጣን ዲያብሎስ የአምላክን ሕግ ሊያስጥሰው ሞከረ። ኢየሱስ ግን የዲያብሎስን መደለያ አልቀበልም በማለቱ በወጥመዱ ውስጥ ሳይወድቅለት ቀርቷል። ኢየሱስ በምድራዊ አገልግሎቱ ወቅት ከሌሎች ክፉ መናፍስት ጋር የተገናኘባቸው ጊዜያትም ነበሩ። በሁሉም ጊዜያት ገሠጻቸው እንጂ እሺ ብሎ ፈቃዳቸውን አልፈጸመም።​— ሉቃስ 4:​1–13፤ 8:​26–34፤ 9:​37–43

2. የትኞቹን ጥያቄዎች እንመረምራለን?

2 ኢየሱስ ስላጋጠሙት ስለነዚህ ሁኔታዎች የሚገልጹት የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች በእርግጥ ክፉ መናፍስት መኖራቸውን ሊያሳምኑን ይገባል። እነዚህ ክፉ መናፍስት ሰዎችን ለማሳሳት ይሞክራሉ። ይሁን እንጂ ልንቋቋማቸው እንችላለን። ሆኖም ክፉ መናፍስት የመጡት ከየት ነው? የሰው ልጆችን ለማታለል የሚሞክሩትስ ለምንድን ነው? ዓላማቸውን ለመፈጸምስ በምን ዘዴዎች ይጠቀማሉ? እንደነዚህ ላሉት ጥያቄዎች መልስ ማግኘት የክፉ መናፍስታዊ ኃይሎችን ጥቃት ለመመከት ይረዳናል።

ክፉ መናፍስት አመጣጣቸውና ግባቸው

3. ሰይጣን ዲያብሎስ እንዴት ይህን ስያሜ ሊያገኝ ቻለ?

3 ይሖዋ አምላክ ሰዎችን ከመፍጠሩ ከረዥም ጊዜ በፊት በጣም ብዙ መንፈሳዊ ፍጡራንን ፈጥሯል። (ኢዮብ 38:​4, 7) በምዕራፍ 6 ላይ እንደተገለጸው ከእነዚህ መላእክት አንዱ የሰው ልጆች ይሖዋን ማምለካቸውን ትተው እርሱን እንዲያመልኩት ተመኘ። ይህ ክፉ መልአክ ይህን ዓላማውን ለማሳካት ሲል ፈጣሪን ተቃወመ፣ ስሙንም አክፋፋ። እንዲያውም ለመጀመሪያይቱ ሴት አምላክ ውሸታም ነው እስከማለት ደረሰ። በዚህም ምክንያት ይህ ዓመፀኛ መንፈሳዊ ፍጡር ሰይጣን (ተቃዋሚ) ዲያብሎስ (ስም አጥፊ) ተብሎ ተጠራ፤ ይህም ተስማሚ ስያሜ ነው።​— ዘፍጥረት 3:​1–5፤ ኢዮብ 1:​6

4. አንዳንድ መላእክት በኖኅ ዘመን ኃጢአት የሠሩት እንዴት ነው?

4 ቆየት ብሎ ሌሎች መላእክትም ከሰይጣን ዲያብሎስ ጎን ተሰለፉ። በጻድቁ ኖኅ ዘመን አንዳንድ መላእክት በሰማይ ያከናውኑ የነበረውን አገልግሎታቸውን ትተው ከምድራዊ ሴቶች ጋር የጾታ ግንኙነት በማድረግ ስሜታቸውን ለማርካት ሲሉ ሥጋ ለበሱ። እነዚህ መላእክት ይህን ያለመታዘዝ አካሄድ እንዲከተሉ ሰይጣን እንዳግባባቸው አያጠራጥርም። በዚህ ድርጊታቸው ምክንያት ኔፍሊም የሚባሉ ዲቃላዎች ተወለዱ። እነዚህ ልጆቻቸው በጉልበታቸው የሚመኩ አስጨናቂዎች ሆኑ። ይሖዋ የጥፋት ውኃ እንዲመጣ ባደረገ ጊዜ ምግባረ ብልሹ የሆኑት ሰዎችና እነዚህ ከተፈጥሮ ውጭ የተወለዱ የእምቢተኛ መላእክት ልጆች ተደመሰሱ። ዓመፀኞቹ መላእክት ሥጋዊ አካላቸውን ትተው ወደ መንፈሳዊው ዓለም በመመለስ ከጥፋቱ አመለጡ። ይሁን እንጂ አምላክ እነዚህን አጋንንት ከቤተሰቡ በማባረር በመንፈሳዊ ጨለማ ውስጥ ታጉረው እንዲኖሩ አደረገ። (ዘፍጥረት 6:​1–7, 17፤ ይሁዳ 6) ቢሆንም “የአጋንንት አለቃ” ሰይጣንና ክፉ መላእክቱ ዓመፃቸውን ገፍተውበታል። (ሉቃስ 11:​15) ግባቸው ምንድን ነው?

5. ሰይጣንና አጋንንቱ ግባቸው ምንድን ነው? ሰዎችንስ ለማጥመድ በምን ይጠቀ⁠ማሉ?

5 የሰይጣንና የአጋንንት ርኩስ ግብ ሰዎችን በይሖዋ አምላክ ላይ ማሳመፅ ነው። በዚህም ምክንያት እነዚህ ክፉዎች በታሪክ ዘመናት ሁሉ የሰው ልጆችን ሲያሳስቱ፣ ሲያስፈራሩና ሲያጠቁ ኖረዋል። (ራእይ 12:​9) በአሁኑ ጊዜ የአጋንንት ጥቃት ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ የተጠናከረና የተፋፋመ እንደሆነ በጊዜያችን የሚታዩ ምሳሌዎች ያረጋግጣሉ። አጋንንት ሰዎችን ለማጥመድ በተለያዩ መናፍስታዊ ድርጊቶች ይጠቀማሉ። አጋንንት በዚህ መደለያ የሚጠቀሙት እንዴት ነው? ራስህን ከጥቃቱ ለመከላከል የምትችለውስ እንዴት ነው?

ክፉ መናፍስት አንተን ለማሳሳት የሚሞክሩት እንዴት ነው?

6. መናፍስታዊ ድርጊት ምንድን ነው? አንዳንዶቹ መናፍስታዊ ሥራዎች ምንድን ናቸው?

6 መናፍስታዊ ድርጊት ምንድን ነው? ከአጋንንት ወይም ከክፉ መናፍስት ጋር በቀጥታም ይሁን በሌላ አገናኝ አማካኝነት መነጋገር ወይም መተባበር ማለት ነው። በወጥመድ ላይ የተቀመጠ የእንስሳት መደለያ ለአዳኞች የሚሰጠው አገልግሎት እንዳለ ሁሉ መናፍስታዊ ሥራም ለአጋንንት የሚፈይደው ነገር አለ። ዓላማው ሰለባውን መሳብ ነው። አንድ አዳኝ የሚያጠምደውን እንስሳ አታልሎ ወደ ወጥመዱ ለመሳብ በተለያዩ መደለያዎች እንደሚጠቀም ሁሉ ክፉ መናፍስትም የሰው ልጆችን በቁጥጥራቸው ውስጥ ለማስገባት የተለያዩ ዓይነት መናፍስታዊ ሥራዎች እንዲስፋፉ ያደርጋሉ። (ከመዝሙር 119:​110 ጋር አወዳድር።) ከእነዚህ የመናፍስት ሥራዎች መካከል ምዋርት፣ አስማት፣ ዕድልን ለማወቅ መሞከር፣ መተት፣ ድግምትና ጠንቋይ ወይም ሙታን ሳቢ መጠየቅ ይገኙበታል።

7. መናፍስታዊ ድርጊት ምን ያህል የተስፋፋ ነው? ክርስቲያን ናቸው በሚባሉ አገሮች እንኳን ሊስፋፋ የቻለውስ ለምንድን ነው?

7 በመላው ዓለም የሚኖሩ ሰዎች በመናፍስትነት ድርጊቶች ስለተጠመዱ ሽንገላው ሠርቷል ማለት ይቻላል። በገጠር የሚኖሩ ሰዎች ወደ ባለ መድኃኒቶች ሲሄዱ በከተማ የሚኖሩ የቢሮ ሠራተኞች ደግሞ ኮከብ ቆጣሪዎችን ይጠይቃሉ። መናፍስትነት ክርስቲያን በሚባሉት አገሮች እንኳን የተስፋፋ ነው። በዩናይትድ ስቴትስ ብቻ ልዩ ልዩ የመናፍስትነት ጽሑፎች የሚወጡባቸው በድምሩ 10,000,000 የሚያክል ስርጭት ያላቸው 30 የተለያዩ መጽሔቶች እንዳሉ ጥናቶች ያመለክታሉ። ብራዚላውያን በየዓመቱ ለመናፍስትነት ጽሑፎችና ዕቃዎች ከ500 ሚልዮን ዶላር በላይ ያወጣሉ። ይሁን እንጂ በዚያች አገር የመናፍስትነት ድርጊቶች የሚፈጸምባቸውን ቦታዎች ከሚያዘወትሩት ሰዎች መካከል 80 በመቶ የሚያክሉት የተጠመቁና ወደ አብያተ ክርስቲያናት እየሄዱ የሚያስቀድሱ ካቶሊኮች ናቸው። አንዳንድ ቀሳውስት መናፍስታዊ ድርጊቶችን የሚፈጽሙ በመሆናቸው ብዙ ሃይማኖተኛ ሰዎች አምላክ መናፍስታዊ ድርጊቶችን የሚቀበል ይመስላቸዋል። ይሁን እንጂ ነገሩ እንደዚያ ነውን?

መጽሐፍ ቅዱስ መናፍስታዊ ድርጊቶችን የሚያወግዘው ለምንድን ነው?

8. ቅዱሳን ጽሑፎች ስለ መናፍስታዊ ድርጊቶች ያላቸው አመለካከት ምንድን ነው?

8 በአንዳንድ መናፍስታዊ ድርጊቶች አማካኝነት ከጥሩ መናፍስት ጋር መገናኘት ይቻላል የሚል ትምህርት ሰምተህ ከነበረ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ መናፍስታዊ ሥራዎች የሚናገረውን ስታውቅ ልትገረም ትችላለህ። የይሖዋ ሕዝቦች “ወደ መናፍስት ጠሪዎችና ወደ ጠንቋዮች አትሂዱ፤ እንዳትረክሱባቸውም አትፈልጉአቸው” የሚል ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው ነበር። (ዘሌዋውያን 19:​31፤ ፊደላቱን ጋደል አድርገን የጻፍናቸው እኛ ነን፤ 20:​6, 27) የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የራእይ መጽሐፍ መናፍስታዊ ድርጊት የሚፈጽሙ ሁሉ “ዕድላቸው በዲንና በእሳት በሚቃጠል ባሕር ነው፤ ይኸውም ሁለተኛ ሞት ነው” በማለት ያስጠነቅቃል። (ራእይ 21:​8፤ 22:​15) ይሖዋ አምላክ ማንኛውንም ዓይነት መናፍስታዊ ድርጊት አይቀበልም። (ዘዳግም 18:​10–12) ይህ የሆነው ለምንድን ነው?

9. በአሁኑ ጊዜ ከመንፈሳዊው ዓለም የሚመጡ ድምፆች ከይሖዋ የመጡ አይደሉም ብለን ልንደመድም የምንችለው ለምንድን ነው?

9 መጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎ ከማለቁ በፊት ይሖዋ ለአንዳንድ ሰዎች መልእክት ለማስተላለፍ በጻድቃን መላእክት ተጠቅሞ ነበር። የአምላክ ቃል ተጽፎ ካለቀ ወዲህ ግን ሰዎች ይሖዋን ተቀባይነት ባለው መንገድ ለማገልገል የሚያስፈልጋቸውን መመሪያ በሙሉ ከመጽሐፍ ቅዱስ ማግኘት ይችላሉ። (2 ጢሞቴዎስ 3:​16, 17፤ ዕብራውያን 1:​1, 2) ይሖዋ የገዛ ራሱን ቃል በመቃረን በመናፍስት አገናኞች በኩል መልእክት አያስተላልፍም። በዛሬው ጊዜ ከመንፈሳዊው ዓለም የሚገኙ መልእክቶች በሙሉ ከክፉ መናፍስት የመጡ ናቸው። በመናፍስትነት ድርጊቶች መካፈል ለአጋንንት ጥቃት ይዳርጋል ወይም በአጋንንት ወደመያዝ ሊያደርስ ይችላል። ስለዚህም አምላክ በማንኛውም ዓይነት መናፍስታዊ ድርጊቶች እንዳንካፈል በፍቅር ያስጠነቅቀናል። (ዘዳግም 18:​14፤ ገላትያ 5:​19–21) ከዚህም በላይ ይሖዋ ስለ መናፍስታዊ ድርጊቶች ያለውን አመለካከት ካወቅን በኋላ በእነዚህ ድርጊቶች ብንቀጥል ዓመፀኛ ከሆኑት ክፉ መናፍስት ጎን እንሰለፋለን፤ እንዲሁም የአምላክ ጠላቶች እንሆናለን።​— 1 ሳሙኤል 15:​23፤ 1 ዜና መዋዕል 10:​13, 14፤ መዝሙር 5:​4

10. ጥንቆላ ምንድን ነው? ከጥንቆላ መራቅ ያለብንስ ለምንድን ነው?

10 በጣም ከተለመዱት መናፍስታዊ ድርጊቶች አንዱ ጥንቆላ ነው። ጥንቆላ በመናፍስት እርዳታ ገና ወደፊት ስለሚሆነው ወይም ስላልታወቀ ነገር ለማወቅ መሞከር ነው። አንዳንዶቹ የጥንቆላ ዓይነቶች ኮከብ ቆጠራ፣ ሕልም መፍታት፣ የእጅ አሻራ ማንበብ፣ አውደ ነገሥት መግለጥ፣ በካርታ አማካኝነት የሰው ዕድል መናገር ናቸው። ብዙ ሰዎች ጥንቆላ ምንም ጉዳት የማያስከትል ጥሩ ጨዋታ ነው ብለው ያስባሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ግን ጠንቋዮችና ክፉ መናፍስት የማይነጣጠሉ እንደሆኑ ያመለክታል። ለምሳሌ ያህል ሥራ 16:​16–19 አንዲት ልጃገረድ የመጠንቆል ችሎታ እንዲኖራት ስላስቻለ “የምዋርተኝነት መንፈስ” ይናገራል። ጋኔኑ ከወጣ በኋላ ግን ወደፊት ስለሚሆነው ነገር የመናገር ችሎታዋን አጣች። ጥንቆላ አጋንንት ሰዎችን ወደ ወጥመዳቸው የሚያስገቡበት መደለያ እንደሆነ ግልጽ ነው።

11. ከሞቱ ሰዎች ጋር ለመነጋገር መሞከር ወጥመድ ውስጥ ሊያስገባ የሚችለው እንዴት ነው?

11 በጣም የምትወደው የቤተሰብህ አባል ወይም የቅርብ ወዳጅህ ሞቶብህ በሐዘን ላይ የምትገኝ ከሆነ በቀላሉ በሌላ ዓይነት የመደለያ ወጥመድ ውስጥ ልትገባ ትችላለህ። አንድ ጠንቋይ አንድ ያልታወቀ ነገር ሊገልጽልህ ወይም የሞተውን ሰው ድምፅ አስመስሎ ሊያነጋግርህ ይችላል። ተጠንቀቅ! ከሞቱ ሰዎች ጋር ለመነጋገር መሞከር ወጥመድ ውስጥ ያስገባል። ለምን? ምክንያቱም ሙታን ሊናገሩ አይችሉም። እንደምታስታውሰው አንድ ሰው ሲሞት ‘ወደ አፈር እንደሚመለስና በዚያም ቀን ሐሳቡ ሁሉ እንደሚጠፋ’ የአምላክ ቃል በግልጽ ይናገራል። ሙታን “አንዳች አያውቁም።” (መዝሙር 146:​4 አዓት፤ መክብብ 9:​5, 10) በተጨማሪም የሟቹን ድምፅ አስመስለው የሚናገሩትና ለመናፍስት ጠሪው ስለ ሟቹ የሚገልጽ ነገር የሚናገሩት አጋንንት እንደሆኑ የታወቀ ነው። (1 ሳሙኤል 28:​3–19) ስለዚህ ‘ሙታንን የሚያነጋግር’ ማንኛውም ሰው በክፉ መናፍስት ወጥመድ ውስጥ ከመውደቁም በላይ የይሖዋን ፈቃድ የሚቃወም ድርጊት ይፈጽማል።​— ዘዳግም 18:​11, 12፤ ኢሳይያስ 8:​19

ከሸንጋይነት ወደ አጥቂነት

12, 13. አጋንንት ሰዎችን ማሳሳታቸውንና ማጥቃታቸውን እንዳላቆሙ የሚያሳይ ምን ማስረጃ አለ?

12 የአምላክ ቃል ስለ መናፍስታዊ ሥራ የሚሰጠውን ምክር ስትከተል አጋንንት የሚያቀርቡልህን መሸንገያ ማጣጣልህ ነው። (ከመዝሙር 141:​9, 10 ጋር አወዳድር፤ ሮሜ 12:​9) ይሁን እንጂ ከዚያ በኋላ ክፉ መናፍስት አንተን እጃቸው ውስጥ ለማስገባት የሚያደርጉትን ሙከራ ያቆማሉ ማለት ነውን? በፍጹም አይደለም! ሰይጣን ኢየሱስን ሦስት ጊዜ ከፈተነው በኋላ “ሌላ አመቺ ጊዜ እስኪያገኝ ድረስ ተወው።” (ሉቃስ 4:​13 አዓት) በተመሳሳይም እልከኛ የሆኑት መናፍስት ሰዎችን እየሸነገሉ ለመሳብ በመሞከር ብቻ ሳይወሰኑ ጥቃት ይሰነዝሩባቸዋል።

13 ሰይጣን የአምላክ አገልጋይ በነበረው በኢዮብ ላይ ስለ ሰነዘረው ጥቃት ቀደም ስንል ተመልክተናል። ዲያብሎስ ከብቶቹና ከአገልጋዮቹ ብዙዎቹ እንዲሞቱ አድርጎ ነበር። ሰይጣን የኢዮብን ልጆች በሙሉ እስከ መግደልም ደርሷል። ከዚያ ቀጥሎ ራሱን ኢዮብን በጣም በሚያሠቃይ ደዌ መታው። ኢዮብ ግን አቋሙን ሳያጎድፍ ከአምላክ ጋር በመጣበቁ በእጅጉ ተባርኳል። (ኢዮብ 1:​7–19፤ 2:​7, 8፤ 42:​12) ከዚያ ጊዜ ጀምሮ አጋንንት አንዳንድ ሰዎችን ሲያሳውሩና ድዳ ሲያደርጉ ቆይተዋል። የሰውን ልጆች መከራ በማየትም ይፈነድቃሉ። (ማቴዎስ 9:​32, 33፤ 12:​22፤ ማርቆስ 5:​2–5) በዛሬው ጊዜ አጋንንት በአንዳንዶች ላይ የወሲብ ጥቃት እንደሚያደርሱና ሌሎችን ደግሞ እንደሚያሳብዱ ይነገራል። አንዳንዶችን ደግሞ ራሳቸውን ወይም ሌሎች ሰዎችን በመግደል በአምላክ ላይ ኃጢአት እንዲሠሩ ያነሳሳሉ። (ዘዳግም 5:​17፤ 1 ዮሐንስ 3:​15) ይሁን እንጂ በአንድ ወቅት በእነዚህ ክፉ መናፍስት ወጥመድ ተይዘው የነበሩ በሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች ከአጋንንት ጥቃት ነፃ ለመውጣት ችለዋል። ይህን ለማድረግ የቻሉት እንዴት ነው? በጣም አስፈላጊ የሆኑ እርምጃዎችን በመውሰድ ነው።

ክፉ መናፍስትን እንዴት መከላከል ይቻላል?

14. በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩትን የኤፌሶን ክርስቲያኖች አርዓያ በመከተል ክፉ መናፍስትን እንዴት መቋቋም ትችላለህ?

14 ክፉ መናፍስትን ለመከላከልና ራስህንም ሆነ ቤተሰብህን ከክፉ መናፍስት ወጥመዶች ለመጠበቅ ከሚያስችሉት መንገዶች አንዱ ምንድን ነው? በኤፌሶን የነበሩና አማኞች ከመሆናቸው በፊት በመናፍስታዊ ድርጊቶች ተጠምደው የነበሩ የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖች ቆራጥ እርምጃ ወስደው ነበር። “ከአስማተኞችም ብዙዎቹ መጽሐፋቸውን ሰብስበው በሰው ሁሉ ፊት አቃጠሉት” የሚል እናነባለን። (ሥራ 19:​19) በመናፍስታዊ ድርጊቶች ተሳትፈህ የማታውቅ ብትሆንም እንኳን መናፍስታዊ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ወይም ከመናፍስታዊ ድርጊቶች ጋር ሊዛመድ የሚችል ማንኛውንም ነገር አስወግድ። ይህም መጻሕፍት፣ መጽሔቶች፣ ቪዲዮዎች፣ ፖስተሮች፣ የሙዚቃ ክሮችና ለመናፍስታዊ ዓላማ ያገለግሉ የነበሩ ዕቃዎች ሊሆኑ ይችላሉ። ከጉዳት ይጠብቃሉ ተብለው የሚደረጉ ክታቦች፣ ምስሎች፣ መናፍስታዊ ድርጊት ከሚፈጽሙ ሰዎች የተሰጡ ስጦታዎችም ከነዚህ የሚቆጠሩ ናቸው። (ዘዳግም 7:​25, 26፤ 1 ቆሮንቶስ 10:​21) ለምሳሌ ያህል በታይላንድ የሚኖሩ ባልና ሚስት ብዙ ጊዜ በአጋንንት ይረበሹ ነበር። ከመናፍስታዊ ድርጊቶች ጋር ዝምድና ያላቸውን ነገሮች በሙሉ ባስወገዱ ጊዜ ግን ምን ሆነ? ከአጋንንት ጥቃት ተገላገሉ። ከዚያም በኋላ ጥሩ መንፈሳዊ እድገት ለማድረግ ቻሉ።

15. ክፉ መናፍስታዊ ኃይሎችን በመቋቋም ረገድ ሌላው አስፈላጊ እርምጃ ምንድን ነው?

15 የክፉ መናፍስትን ጥቃት ለመከላከል መወሰድ የሚኖርበት ሌላው አስፈላጊ እርምጃ ሐዋርያው ጳውሎስ አምላክ የሰጠንን መንፈሳዊ የጦር ትጥቆች በሙሉ እንድንለብስ የሰጠንን ምክር መፈጸም ነው። (ኤፌሶን 6:​11–17) ክርስቲያኖች ከክፉ መናፍስት ራሳቸውን የሚጠብቁበትን መከላከያ ማጠናከር ይኖርባቸዋል። ይህ እርምጃ ምን ነገሮችን ይጨምራል? ጳውሎስ “በሁሉም ላይ ጨምራችሁ የሚንበለበሉትን የክፉውን ፍላጻዎች ሁሉ ልታጠፉ የምትችሉበትን የእምነትን ጋሻ አንሡ” ብሏል። በእርግጥ እምነትህ እየጎለበተ በሄደ መጠን ክፉ መናፍስታዊ ኃይሎችን የመከላከል ችሎታህ ይበልጥ ይጠናከራል።​— ማቴዎስ 17:​14–20

16. እምነትህን እንዴት ለማጎልበት ትችላለህ?

16 እምነትህን እንዴት ማጎልበት ትችላለህ? የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትህን በመቀጠልና መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጣቸውን ምክሮች በሕይወትህ ውስጥ ሥራ ላይ በማዋል ነው። የአንድ ሰው የእምነት ጥንካሬ በአብዛኛው የሚመካው የእምነቱ መሠረት ጠንካራ በመሆኑ ላይ ነው። ይህ የእምነት መሠረት ደግሞ ከአምላክ የሚገኝ እውቀት ነው። መጽሐፍ ቅዱስን ስታጠና ያገኘኸውና በልብህ ውስጥ ያኖርኸው ትክክለኛ እውቀት እምነትህን አልገነባልህም? (ሮሜ 10:​10, 17) ወደፊትም ይህን ጥናትህን ስትቀጥልና በይሖዋ ምሥክሮች ስብሰባዎች ላይ መገኘትን ልማድህ ስታደርግ እምነትህ ከዚህ ይበልጥ እንደሚጎለብት አያጠራጥርም። (ሮሜ 1:​11, 12፤ ቆላስይስ 2:​6, 7) ይህ እምነትህ የአጋንንትን ጥቃት የሚመክት ትልቅ ከለላ ይሆንልሃል።​— 1 ዮሐንስ 5:​5

17. ክፉ መናፍስታዊ ኃይሎችን ለመቃወም ምን ተጨማሪ እርምጃ አስፈላጊ ሊሆን ይችላል?

17 ክፉ መንፈሳዊ ኃይሎችን ለመቋቋም ቆርጦ የተነሣ ሰው ምን ተጨማሪ እርምጃዎች ሊወስድ ይችላል? የኤፌሶን ክርስቲያኖች በአጋንንታዊ ሥራዎች በተጥለቀለቀ ከተማ ይኖሩ ስለነበረ ከጥቃት ራሳቸውን መጠበቅ አስፈልጓቸው ነበር። በዚህም ምክንያት ጳውሎስ “ዘወትር በመንፈስ ጸልዩ” ብሏቸዋል። (ኤፌሶን 6:​18) እኛም አጋንንት በሚፈነጩበት ዓለም ውስጥ ስለምንኖር ክፉ መናፍስትን ለመቋቋም ከፈለግን አምላክ እንዲጠብቀን አጥብቀን መጸለይ አለብን። (ማቴዎስ 6:​13) በዚህ ረገድ በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ የሚገኙት የተሾሙ ሽማግሌዎች የሚሰጡት መንፈሳዊ እርዳታና ጸሎት ከፍተኛ ጥቅም ያስገኛል።​— ያዕቆብ 5:​13–15

ከክፉ መናፍስት ጋር የምታደርገውን ውጊያ አታቋርጥ

18, 19. አጋንንት አንድን ሰው መረበሻቸውን ካላቆሙ ምን ማድረግ ይቻላል?

18 ይሁን እንጂ አንዳንዶች እነዚህን መሠረታዊ እርምጃዎች ከወሰዱ በኋላም ቢሆን ከክፉ መናፍስት ጥቃት ደርሶባቸዋል። ለምሳሌ ያህል በኮት ዲቩዋር የሚኖር አንድ ሰው ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር ሲያጠና ከቆየ በኋላ ክታቦቹንና የአምልኮ ዕቃዎቹን በሙሉ አስወገደ። ከዚያም በኋላ ጥሩ እድገት አሳይቶ ራሱን ለይሖዋ በመወሰን ተጠመቀ። ከተጠመቀ ከአንድ ሳምንት በኋላ ግን እንደገና አጋንንት ይረብሹት ጀመር። አዲሱን ሃይማኖቱን እንዲተው የሚነግሩት ድምፆች መስማት ጀመረ። እንዲህ ያለ ነገር በአንተ ላይ ቢደርስ ይሖዋ አይጠብቅህም ማለት ነውን? ላይሆን ይችላል።

19 ፍጹም የነበረው ኢየሱስ ክርስቶስ መለኮታዊ ጥበቃ ያልተለየው ቢሆንም ክፉ መንፈሳዊ ፍጡር የሆነውን የሰይጣን ዲያብሎስን ድምፅ ሰምቷል። እንዲህ ባለው ጊዜ ማድረግ የሚኖርብንን ነገር ኢየሱስ አመልክቶናል። ዲያብሎስን “ሂድ፣ አንተ ሰይጣን” አለው። (ማቴዎስ 4:​3–10) አንተም በተመሳሳይ ከመናፍስት ዓለም የሚመጣውን ድምፅ ለመስማት እምቢ ማለት ይኖርብሃል። ይሖዋ እንዲረዳህ በመጸለይ የክፉ መናፍስትን ጥቃት ተቋቋም። አዎን፣ የአምላክን ስም በመጥራት ጮክ ብለህ ጸልይ። ምሳሌ 18:​10 እንዲህ ይላል:- “የእግዚአብሔር [“የይሖዋ” አዓት] ስም የጸና ግምብ ነው፤ ጻድቅ ወደ እርሱ ሮጦ ከፍ ከፍ ይላል።” በኮት ዲቩዋር የሚኖረው ክርስቲያን እንዲሁ አደረገና ክፉዎቹ መናፍስት ጥቃታቸውን አቆሙ።​— መዝሙር 124:​8፤ 145:​18

20. ባጠቃላይ ክፉ መናፍስትን ለመቋቋም ምን ልታደርግ ትችላለህ?

20 ይሖዋ ክፉ መናፍስት በሕይወት እንዲኖሩ ፈቅዶላቸዋል፤ ቢሆንም ሕዝቡን ለማዳን በሚወስዳቸው እርምጃዎች ኃይሉን አሳይቷል፤ ስሙም በመላዋ ምድር እንዲታወቅ በማድረግ ላይ ነው። (ዘጸአት 9:​16) ወደ አምላክ ተጠግተህ እስከኖርህ ድረስ ክፉ መናፍስትን መፍራት አያስፈልግህም። (ዘኁልቁ 23:​21, 23፤ ያዕቆብ 4:​7, 8፤ 2 ጴጥሮስ 2:​9) ያላቸው ኃይል የተወሰነ ነው። በኖኅ ዘመን ተቀጥተዋል። በቅርቡም ከሰማይ ተጥለዋል። በአሁኑ ጊዜም የመጨረሻ ፍርዳቸውን በመጠባበቅ ላይ ናቸው። (ይሁዳ 6፤ ራእይ 12:​9፤ 20:​1–3, 7–10, 14) እንዲያውም የሚመጣባቸውን ጥፋት ሲያስቡ ይንቀጠቀጣሉ። (ያዕቆብ 2:​19) ስለዚህ ክፉ መናፍስት በአንድ ዓይነት መደለያ ሊማርኩህ ቢሞክሩ ወይም በቀጥታ ጥቃት ቢሰነዝሩብህ ልትቋቋማቸው ትችላለህ። (2 ቆሮንቶስ 2:​11) ከማንኛውም ዓይነት መናፍስታዊ ድርጊት ራቅ፤ የአምላክ ቃል የሚሰጠውን ምክር ሥራ ላይ አውል። የይሖዋን ሞገስ ለማግኘት ጣር። የወደፊት ሕይወትህ ክፉ መናፍስታዊ ኃይሎችን በመቋቋም ላይ የተመካ ስለሆነ ይህን ከማድረግ አትዘ⁠ግይ!

እውቀትህን ፈትሽ

ክፉ መናፍስት ሰዎችን ለማሳሳት የሚሞክሩት እንዴት ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ መናፍስታዊ ድርጊቶችን የሚያወግዘው ለምንድን ነው?

አንድ ሰው ከክፉ መናፍስታዊ ኃይሎች ሊላቀቅ የሚችለው እንዴት ነው?

ክፉ መናፍስትን መቋቋምህን መቀጠል የሚኖርብህ ለምንድን ነው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 110 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የተለያየ መልክ ላላቸው መናፍስታዊ ድርጊቶች ምን አመለካከት አለህ?