በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የማንን ሥልጣን መቀበል አለብህ?

የማንን ሥልጣን መቀበል አለብህ?

ምዕራፍ 14

የማንን ሥልጣን መቀበል አለብህ?

1, 2. ሁሉም ዓይነት ሥልጣን ጎጂ ነውን? አስረዳ።

ብዙ ሰዎች “ሥልጣን” የሚለው ቃል ራሱ አይጥማቸውም። ችግሩ ሊገባን ይችላል፤ ምክንያቱም በሥራ ቦታ፣ በቤተሰብ ውስጥና በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ሥልጣን ከአግባብ ውጭ በሆነ መንገድ ይሠራበታል። መጽሐፍ ቅዱስ “ሰው ሰውን የገዛው ለጉዳቱ ነው” በማለት ሁኔታውን ቁልጭ አድርጎ አስቀምጦታል። (መክብብ 8:​9 አዓት) አዎን፣ ብዙ ሰዎች ሥልጣናቸውን መጨቆኛና የራሳቸውን ጥቅም ማራመጃ አድርገው ተጠቅመውበታል።

2 ይሁን እንጂ ሥልጣን የተባለ ነገር ሁሉ ጎጂ ነው ማለት አይደለም። ለምሳሌ ያህል የራሳችን አካል በራሳችን ላይ ሥልጣን አለው ለማለት ይቻላል። እንድንተነፍስ፣ እንድንበላ፣ እንድንጠጣና እንድንተኛ “ያዘናል።” ታዲያ ይህ ጭቆና ነው ለማለት ይቻላልን? በፍጹም አይቻልም። እነዚህን የሰውነት ትእዛዞች የምናሟላው ለእኛው ጥቅም ስንል ነው። ሰውነታችን የሚፈልጋቸውን ነገሮች ለማሟላት ፈቃደኛ መሆናችንንና አለመሆናችንን መጠየቅ አስፈላጊ አይሁን እንጂ እሺ ብለን ለመገዛት ፈቃደኛ መሆናችን አስፈላጊ የሚሆንባቸው የሥልጣን ዓይነቶች አሉ። አንዳንድ ምሳሌዎችን እንመልከት።

የመጨረሻው ከፍተኛ ሥልጣን

3. ይሖዋ “ሉዓላዊ ጌታ” ተብሎ መጠራቱ ተገቢ የሆነው ለምንድን ነው?

3 ይሖዋ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከ300 ለሚበልጡ ጊዜያት (እንደ አዲሲቱ ዓለም ትርጉም) “ሉዓላዊ ጌታ” ተብሎ ተጠርቷል። ሉዓላዊ ጌታ የመጨረሻውን ከፍተኛ ሥልጣን የጨበጠ አካል ነው። ይሖዋ ይህን የመሰለ ታላቅ ደረጃ ለመያዝ ባለ መብት የሆነው ለምንድን ነው? ራእይ 4:​11 “ጌታችንና አምላካችን [“ይሖዋ” አዓት] ሆይ፣ አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረውማልና ክብር ውዳሴ፣ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል” በማለት መልሱን ይሰጠናል።

4. ይሖዋ በሥልጣኑ እንዴት መጠቀምን መርጧል?

4 ይሖዋ ፈጣሪያችን በመሆኑ ሥልጣኑን በፈለገው መንገድ የመጠቀም መብት አለው። አምላክ ‘የኃይል ብዛት’ ያለው መሆኑን ስንመለከት ይህ አስፈሪ ሆኖ ሊታየን ይችላል። “ሁሉን የሚችል አምላክ” ተብሎ ተጠርቷል። ይህ ቃል በዕብራይስጥ ቋንቋ በማንም፣ በምንም የማይበገርን ኃይል ያመለክታል። (ኢሳይያስ 40:​26፤ ዘፍጥረት 17:​1) ይሁን እንጂ የይሖዋ ዋነኛ ባሕርይ ፍቅር በመሆኑ ይህን ኃይሉን የሚጠቀምበት ለበጎ ነገር ብቻ ነው።​— 1 ዮሐንስ 4:​16

5. ለይሖዋ ሥልጣን መገዛት አስቸጋሪ የማይሆነው ለምንድን ነው?

5 ይሖዋ ንስሐ ባልገቡ ኃጢአተኞች ላይ ቅጣት እንደሚያመጣ ቢያስጠነቅቅም ሙሴ በዋነኛነት ያወቀው “ለሚወዱትም፣ ትእዛዙንም ለሚጠብቁ ቃል ኪዳኑንና ምሕረቱን [“ፍቅራዊ ደግነቱን” አዓት] እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ የሚጠብቅ የታመነ አምላክ” መሆኑን ነው። (ዘዳግም 7:​9) እስቲ ቆም ብለህ አስብ! የአጽናፈ ዓለሙ የመጨረሻ ታላቅ ባለ ሥልጣን እንድናገለግለው አያስገድደንም። ከዚህ ይልቅ ወደ እርሱ የምንሳበውና የምንጠጋው በፍቅሩ ምክንያት ነው። (ሮሜ 2:​4፤ 5:​8) እንዲያውም ለይሖዋ ሥልጣን መገዛት በጣም የሚያስደስት ነገር ነው፤ ምክንያቱም ሕጎቹ ሁሉ በመጨረሻው ጥቅም የሚያስገኙልን ናቸው።​— መዝሙር 19:​7, 8

6. በኤደን የአትክልት ሥፍራ የሥልጣን ጥያቄ የተነሣው እንዴት ነው? ምንስ ውጤት አስከተለ?

6 የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን የአምላክን ሉዓላዊነት አንፈልግም አሉ። ምን ነገር ጥሩ ወይም መጥፎ እንደሆነ ራሳቸው ለመወሰን ፈለጉ። (ዘፍጥረት 3:​4–6) በዚህም ምክንያት መኖሪያቸው ከሆነችው ገነት ተባረሩ። ከዚያ በኋላ ይሖዋ የሰው ልጆች ሥርዓት ባለው ኅብረተሰብ ተደራጅተው ለመኖር የሚያስችላቸውን የሥልጣን መዋቅር (ፍጽምና የጎደለው መዋቅር ቢሆንም) እንዲያቋቁሙ ፈቀደ። ታዲያ አንዳንዶቹ የሥልጣን ቦታዎች ምንድን ናቸው? አምላክስ እንድንገዛላቸው የሚጠብቅብን እስከምን ድረስ ነው?

‘የበላይ ባለ ሥልጣኖች’

7. ‘በበላይ ያሉ ባለ ሥልጣኖች’ የተባሉት እነማን ናቸው? የእነርሱስ ሥልጣን ከአምላክ ሥልጣን ጋር ሲወዳደር ደረጃው ምንድን ነው?

7 ሐዋርያው ጳውሎስ “ነፍስ ሁሉ በበላይ ላሉት ባለ ሥልጣኖች ይገዛ። ከእግዚአብሔር ካልተገኘ በቀር ሥልጣን የለምና” ሲል ጽፏል። እነዚህ ‘በበላይ ያሉ ባለ ሥልጣኖች’ እነማን ናቸው? በቀጣዮቹ ቁጥሮች የሠፈሩት የጳውሎስ ቃላት የሰብዓዊ መንግሥታት ባለ ሥልጣኖች መሆናቸውን ያመለክታሉ። (ሮሜ 13:​1–7፤ ቲቶ 3:​1) ይሖዋ የሰው ልጆች መንግሥታት እንዲኖሩ ፈቀደላቸው እንጂ እርሱ ያቋቋማቸው ወይም ከእርሱ የመነጩ አይደሉም። በዚህም ምክንያት ጳውሎስ “ያሉትን ባለ ሥልጣኖች ገደብ ባለው ቦታቸው ያስቀመጠው አምላክ ነው” (አዓት) ብሎ ሊጽፍ ችሏል። ታዲያ ይህ አነጋገር ስለ ምድራዊ ሥልጣን ምን ያመለክታል? ከአምላክ ሥልጣን ያነሰ ደረጃ እንዳለው ወይም ዝቅተኛ ሥልጣን መሆኑን ያመለክታል። (ዮሐንስ 19:​10, 11) ስለዚህ የሰው ልጆች ሕግ ከአምላክ ሕግ ጋር በሚጋጭበት ጊዜ ክርስቲያኖች በመጽሐፍ ቅዱስ በሰለጠነው ሕሊናቸው መመራት ይኖርባቸዋል። ‘ከሰው ይልቅ ለእግዚአብሔር ሊታዘዙ ይገባቸዋል።’​— ሥራ 5:​29

8. የበላይ ባለ ሥልጣኖች ጥቅም የሚሰጡህ እንዴት ነው? ለእነርሱ እንደምትገዛስ እንዴት ልታሳይ ትችላለህ?

8 ይሁን እንጂ እነዚህ መንግሥታዊ የበላይ ባለ ሥልጣኖች ‘ለጥቅማችን የሚሠሩ የእግዚአብሔር አገልጋዮች’ የሚሆኑበት ጊዜ ብዙ ነው። (ሮሜ 13:​4) በምን በምን መንገድ? የበላይ ባለ ሥልጣኖቹ የሚሰጡትን እንደ ፖስታ፣ ፖሊስ፣ እሳት አደጋ መከላከያ፣ ጤና ጥበቃና ትምህርት የመሰሉትን አገልግሎቶች ማስታወስ አለብን። ሐዋርያው ጳውሎስ “ስለዚህ ደግሞ ትገብራላችሁና፤ በዚህ ነገር የሚተጉ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ናቸውና” ሲል ጽፏል። (ሮሜ 13:​6) ግብርና ቀረጥ መክፈልን ወይም ሌሎች ሕጋዊ ግዴታዎችን መፈጸምን በሚመለከት “በሁሉም ነገር ሐቀኞች ሆነን” መገኘት ይገባናል።​— ዕብራውያን 13:​18 አዓት

9, 10. (ሀ) የበላይ ባለ ሥልጣኖች በአምላክ ዝግጅት ውስጥ ምን ሚና አላቸው? (ለ) የበላይ ባለ ሥልጣኖችን መቃወም ስህተት የሚሆነው ለምንድን ነው?

9 አንዳንድ ጊዜ የበላይ ባለ ሥልጣኖች ሥልጣናቸውን አለ አግባብ ይጠቀሙበታል። ታዲያ ይህ አድራጎታቸው ለእነርሱ እንድንገዛ ካለብን ግዴታ ነፃ ያደርገናልን? አያደርገንም። እነዚህ ባለ ሥልጣኖች የሚሠሯቸውን መጥፎ ድርጊቶች ይሖዋ ይመለከታል። (ምሳሌ 15:​3) ይሖዋ የሰው ልጆች አገዛዝ በምድር ላይ እንዲኖር መፍቀዱ ስለ ምግባረ ብልሹነታቸው ግድ የለውም ማለት አይደለም። እኛም ብንሆን ይሖዋ ስለዚህ ሁኔታ ምንም የማይሰማን እንድንሆን አይጠብቅብንም። የአምላክ መንግሥት በቅርቡ “እነዚያንም መንግሥታት ሁሉ ትፈጫቸዋለች ታጠፋቸውማለች።” (ዳንኤል 2:​44) ይህ እስከሚሆንበት ጊዜ ድረስ ግን የበላይ ባለ ሥልጣኖች ጠቃሚ የሆነ ዓላማ ያከናው⁠ናሉ።

10 ጳውሎስ “ባለ ሥልጣንን የሚቃወም የእግዚአብሔርን ሥርዓት ይቃወማል” በማለት ነገሩን ግልጽ አድርጎታል። (ሮሜ 13:​2) የበላይ ባለ ሥልጣኖች ትርምስና ሥርዓተ አልበኝነትን በመከላከል መጠነኛ የሆነ ሥርዓት እንዲኖር ስለሚያደርጉ የአምላክ “ሥርዓት” ወይም ዝግጅት ናቸው። እነርሱን መቃወም ቅዱስ ጽሑፋዊ ትእዛዝን መቃወም ከመሆኑም በላይ ሞኝነት ነው። ነገሩን በምሳሌ ለማስረዳት ኦፕራሲዮን ወይም ቀዶ ሕክምና ተደርጎልሃል እንበል። የተቀደደው የሰውነት ክፍል የተያያዘው በስፌት ነው። የስፌቱ ክር ለሰውነትህ ባዕድ ቢሆንም ለተወሰነ ጊዜ የሚሰጠው አገልግሎት አለ። አለጊዜው ፈትተህ ብታወጣው ጉዳት ያስከትልብሃል። በተመሳሳይም አምላክ በመጀመሪያ የሰብዓዊ መንግሥታት ባለ ሥልጣኖች እንዲኖሩ ዓላማው አልነበረም። የእርሱ መንግሥት ምድርን ሙሉ በሙሉ መግዛት እስክትጀምር ግን ሰብዓዊ መንግሥታት ኀብረተሰቡ ተስማምቶ እንዲኖር በማስቻል አምላክ ለአሁኑ ጊዜ ካለው ፈቃድ ጋር የሚስማማ ተግባር ይፈጽማሉ። ስለዚህ ለአምላክ ሕግና ሥልጣን ቅድሚያ እየሰጠን ለበላይ ባለ ሥልጣኖች መገዛታችንን እንቀጥላለን።

በቤተሰብ ውስጥ ያለ ሥልጣን

11. የራስነትን መሠረታዊ ሥርዓት እንዴት ብለህ ትገልጸዋለህ?

11 ቤተሰብ የሰብዓዊ ኅብረተሰብ መሠረታዊ አካል ነው። በቤተሰብ ክልል ውስጥ ባልና ሚስት በጥሩ ጓደኝነት አብረው ለመኖር ከመቻላቸውም በላይ ልጆች ጥበቃ አግኝተውና ወደፊት ትልቅ ሰው ሲሆኑ የሚያስፈልጋቸውን ሥልጠና አግኝተው ያድጋሉ። (ምሳሌ 5:​15–21፤ ኤፌሶን 6:​1–4) እንዲህ ያለው ክቡር የሆነ ዝግጅት የቤተሰብ አባሎች ሰላምና ስምምነት አግኝተው እንዲኖሩ በሚያስችላቸው መንገድ መደራጀት ይኖርበታል። ይሖዋም ይህን ዓላማ ለማሳካት የራስነትን ሥርዓት አቋቁሟል። ይህ የራስነት ሥርዓት በ1 ቆሮንቶስ 11:​3 ላይ በሚገኙት በሚከተሉት ቃላት ተጠቃልሏል:- “የወንድ ሁሉ ራስ ክርስቶስ፣ የሴትም ራስ ወንድ፣ የክርስቶስም ራስ እግዚአብሔር እንደሆነ ልታውቁ እወዳለሁ።”

12, 13. የቤተሰብ ራስ ማን ነው? ኢየሱስ የራስነት ሥልጣኑን ከተጠቀመበት መንገድ ምን ትምህርት ሊገኝ ይችላል?

12 ባል የቤተሰብ ራስ ነው። ቢሆንም እርሱ ራሱ ከበላዩ ሌላ ራስ አለው። እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ጳውሎስ “ባሎች ሆይ፣ ክርስቶስ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ወደዳት ሚስቶቻችሁን ውደዱ” ሲል ጽፏል። (ኤፌሶን 5:​25) አንድ ባል ኢየሱስ ጉባኤውን በያዘበት መንገድ ሚስቱን በመያዝ ለክርስቶስ የሚገዛ መሆኑን ያሳያል። (1 ዮሐንስ 2:​6) ኢየሱስ በጣም ታላቅ የሆነ ሥልጣን ተሰጥቶታል። ይሁን እንጂ ይህን ሥልጣን ከፍተኛ ደግነት፣ ፍቅርና ምክንያታዊነት እያሳየ ይሠራበታል። (ማቴዎስ 20:​25–28) ኢየሱስ ሰው በነበረበት ጊዜ ሥልጣኑን አለ አግባብ አልተጠቀመበትም። ‘የዋህ በልቡም ትሑት ነበር።’ ተከታዮቹንም “ባሮች” ሳይሆን “ወዳጆች” ብሎ ይጠራቸው ነበር። ከጭንቀት “አሳርፋችኋለሁ” አላቸው፤ ይህንንም ቃል ፈጽሞላቸዋል።​— ማቴዎስ 11:​28, 29፤ ዮሐንስ 15:​15

13 ባሎች ክርስቲያናዊ የራስነት ቦታ ጨቁኖ ለመግዛት ሥልጣን የማያሰጥ መሆኑን ከኢየሱስ አርዓያ ይማራሉ። ከዚህ ይልቅ አክብሮትንና የራስን ጥቅም የሚሠዋ ፍቅር ማሳየትን የሚጠይቅ ቦታ ነው። ይህም የትዳር ጓደኛቸውን በአካልም ሆነ በቃል እንዲያሠቃዩ አይፈቅድላቸውም። (ኤፌሶን 4:​29, 31, 32፤ 5:​28, 29፤ ቆላስይስ 3:​19) እንግዲያው አንድ ክርስቲያን ወንድ ሚስቱን በዚህ መንገድ የሚበድል ከሆነ የቀሩት መልካም ሥራዎቹ በሙሉ ዋጋ ቢስ ይሆናሉ። ጸሎቱም ይታገድበታል።​— 1 ቆሮንቶስ 13:​1–3፤ 1 ጴጥሮስ 3:​7

14, 15. አምላክ የገለጸው እውቀት ሚስት ለባልዋ ተገዥ እንድትሆን የሚረዳት እንዴት ነው?

14 ባል የክርስቶስን አርዓያ ሲከተል ሚስትም በኤፌሶን 5:​22, 23 ላይ ያለውን ትእዛዝ ለመፈጸም ቀላል ይሆንላታል:- “ሚስቶች ሆይ፣ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁ ተገዙ፤ ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደ ሆነ እርሱም አካሉን የሚያድን እንደ ሆነ ባል የሚስት ራስ ነውና።” ባል ለክርስቶስ መገዛት እንደሚኖርበት ሁሉ ሚስትም ለባልዋ መገዛት ይኖርባታል። በተጨማሪም መጽሐፍ ቅዱስ ባለሞያ የሆኑ ሚስቶች ለአምላካዊ ጥበባቸውና ለታታሪነታቸው ክብርና ምስጋና ሊሰጣቸው እንደሚገባ በግልጽ ያመለክታል።​— ምሳሌ 31:​10–31

15 አንዲት ክርስቲያን ሚስት ለባልዋ የምትገዛው ገደብ ባለው ሁኔታ ነው። ይህም ለባልዋ የምትገዛባቸው አንዳንድ ሁኔታዎች መለኮታዊውን ሕግ እንድትጥስ የሚያደርጓት ከሆነ ከሰው ይልቅ ለአምላክ መታዘዝ ይገባታል ማለት ነው። በዚህም ጊዜ ቢሆን የሚስቲቱ ጽኑ አቋም ‘ዝግተኛና የዋህ በሆነ መንፈስዋ’ መለዘብ ይኖርበታል። ከአምላክ ያገኘችው እውቀት የተሻለች ሚስት እንዳደረጋት በግልጽ መታየት መቻል አለበት። (1 ጴጥሮስ 3:​1–4) የማታምን ሚስት ያለችው ክርስቲያን ወንድ ሁኔታም ከዚህ የተለየ አይደለም። ከመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ጋር ተስማምቶ መኖሩ የተሻለ ባል ሊያደርገው ይገባል።

16. ልጆች ኢየሱስ ወጣት ሳለ ያሳየውን አርዓያ ሊከተሉ የሚችሉት እንዴት ነው?

16 ኤፌሶን 6:​1 “ልጆች ሆይ፣ ለወላጆቻችሁ በጌታ ታዘዙ፣ ይህ የሚገባ ነውና” በማለት ልጆች በቤተሰብ ውስጥ ስላላቸው ሚና ይገልጻል። ክርስቲያን ልጆች የኢየሱስን ምሳሌ ይከተላሉ። ኢየሱስ እያደገ በሄደባቸው ዓመታት ሁሉ ለወላጆቹ ይገዛ ነበር። ኢየሱስ ታዛዥ ልጅ በመሆን “በጥበብና በቁመት በሞገስም በእግዚአብሔርና በሰው ፊት ያድግ ነበር።”​— ሉቃስ 2:​51, 52

17. የወላጆች የሥልጣን አጠቃቀም በልጆች ላይ ምን ተጽእኖ ሊያሳድር ይች⁠ላል?

17 ወላጆች ኃላፊነታቸውን የሚያከናውኑበት መንገድ ልጆቻቸው ሥልጣንን የሚያከብሩ ወይም አሻፈረኝ ብለው የሚያምፁ በመሆናቸው ላይ ተጽእኖ ሊያሳድር ይችላል። (ምሳሌ 22:​6) ስለዚህ ወላጆች ‘ሥልጣኔን የምጠቀምበት በፍቅር ነው ወይስ በኃይል? ስድ የምለቅ ነኝን?’ ብለው ራሳቸውን መጠየቅ ይኖርባቸዋል። ለአምላክ አክብሮት ያለው ወላጅ በአንድ በኩል አፍቃሪና አሳቢ፣ በሌላው በኩል ደግሞ አምላካዊ መሠረታዊ ሥርዓቶችን በጥብቅ የሚከተል እንዲሆን ይጠበቅበታል። እንግዲያው ጳውሎስ “እናንተም አባቶች ሆይ፣ ልጆቻችሁን በጌታ ምክርና በተግሣጽ አሳድጉአቸው እንጂ አታስቆጡአቸው [አታስመርሯቸው]” ማለቱ ተገቢ ነው።​— ኤፌሶን 6:​4፤ ቆላስይስ 3:​21

18. ወላጆች ተግሣጽ መስጠት የሚገባቸው እንዴት ነው?

18 ወላጆች፣ በተለይ ልጆቻቸው ታዛዥ ሆነው እንዲያስደስቱአቸው ከፈለጉ፣ የማሠልጠን ዘዴያቸውን መመርመር ይኖርባቸዋል። (ምሳሌ 23:​24, 25) በመጽሐፍ ቅዱስ መሠረት ተግሣጽ አንዱ የትምህርት መስጫ ዘዴ ነው። (ምሳሌ 4:​1፤ 8:​33 አዓት) የሚዛመደውም ከቁጣና ከጭካኔ ጋር ሳይሆን ከፍቅርና ከየዋህነት ጋር ነው። ስለዚህ ክርስቲያን ወላጆች ልጆቻቸውን ለማስተካከል ተግሣጽ በሚሰጡበት ጊዜ ጥበበኞችና ራሳቸውን የሚገዙ መሆን ይገባቸዋል።​— ምሳሌ 1:​7

በጉባኤ ውስጥ ያለ ሥልጣን

19. አምላክ በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ጥሩ ሥርዓት እንዲኖር ያስቻለው እንዴት ነው?

19 ይሖዋ ሥርዓታማ አምላክ በመሆኑ ለሕዝቦቹ የመወሰን ሥልጣን ያለውና በሚገባ የተደራጀ አመራር ያዘጋጅላቸዋል ብሎ ማሰቡ ምክንያታዊ ነው። በዚህ መሠረት ኢየሱስን የክርስቲያን ጉባኤ ራስ አድርጎ ሾሞታል። (1 ቆሮንቶስ 14:​33, 40፤ ኤፌሶን 1:​20–23) አምላክ በማይታየው የክርስቶስ አመራር ሥር የሚያገለግሉ ሽማግሌዎች በየጉባኤው ተሹመው መንጋውን በትጋት፣ በፈቃደኝነትና በፍቅር የሚጠብቁበት ዝግጅት እንዲኖር አድርጓል። (1 ጴጥሮስ 5:​2, 3) ዲያቆናትም እነዚህን ሽማግሌዎች በተለያዩ መንገዶች በማገዝ በጉባኤው ውስጥ በጣም ጠቃሚ የሆነ አገልግሎት ያከናውናሉ።​— ፊልጵስዩስ 1:​1

20. ለተሾሙ ክርስቲያን ሽማግሌዎች መገዛት የሚኖርብን ለምንድን ነው? ይህስ ጠቃሚ የሚሆነው ለምንድን ነው?

20 ጳውሎስ ስለ ክርስቲያን ሽማግሌዎች እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ለዋኖቻችሁ ታዘዙና ተገዙእነርሱ ስሌትን እንደሚሰጡ አድርገው፣ ይህንኑ በደስታ እንጂ በኃዘን እንዳያደርጉት፣ ይህ የማይጠቅማችሁ ነበርና፣ ስለ ነፍሳችሁ ይተጋሉ።” (ዕብራውያን 13:​17) አምላክ በጥበቡ በጉባኤው ውስጥ ላሉ ሁሉ መንፈሳዊ እንክብካቤ የማድረግን ኃላፊነት ለበላይ ተመልካቾች በአደራ ሰጥቷል። እነዚህ ሽማግሌዎች ቀሳውስት አይደሉም። ሽማግሌዎች ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳደረገው የእምነት ባልደረቦቻቸውን የሚያገለግሉ የአምላክ ባሮችና አገልጋዮች ናቸው። (ዮሐንስ 10:​14, 15) ቅዱስ ጽሑፋዊ ብቃቶችን ያሟሉ ወንዶች ስለ መንፈሳዊ እድገታችንና መሻሻላችን እንደሚያስቡ ማወቃችን ለእነርሱ እንድንገዛና እንድንተባበራቸው ያበረታታናል።​— 1 ቆሮንቶስ 16:​16

21. የተሾሙ ሽማግሌዎች ክርስቲያን ባልደረቦቻቸውን በመንፈሳዊ ለመርዳት የሚጥሩት እንዴት ነው?

21 አንዳንድ ጊዜ በጎች ሊባዝኑ ወይም ጎጂ የሆኑ ዓለማዊ ግፊቶች አደጋ ሊያመጡባቸው ይችላሉ። ሽማግሌዎች የበታች እረኞች እንደመሆናቸው መጠን በእረኞቹ አለቃ እየተመሩ ለሚጠብቋቸው በጎች አስፈላጊውን እንክብካቤ ያደርጋሉ፤ ተግተውም በግል ይረዷቸዋል። (1 ጴጥሮስ 5:​4) የጉባኤውን አባሎች በየቤታቸው እየሄዱም ማበረታቻ ይለግሷቸዋል። ዲያብሎስ የአምላክን ሕዝቦች ሰላም ለማደፍረስ እንደሚፈልግ ስለሚያውቁ ማንኛውንም ችግር በላይኛይቱ ጥበብ በመመራት ይፈታሉ። (ያዕቆብ 3:​17, 18) ኅብረትና የእምነት አንድነት እንዲኖር በትጋት ይጥራሉ። ኢየሱስም ይህ ሁኔታ እንዲሰፍን ጸልዮአል።​— ዮሐንስ 17:​20–22፤ 1 ቆሮንቶስ 1:​10

22. አንድ ክርስቲያን ኃጢአት በሚሠራበት ጊዜ ሽማግሌዎች ምን እርዳታ ይሰ⁠ጣሉ?

22 አንድ ክርስቲያን ክፉ ነገር ቢደርስበት ወይም ኃጢአት በመሥራቱ ምክንያት ቅስሙ ቢሰበር ምን ያደርጋል? ሽማግሌዎቹ ለዚህ ክርስቲያን የሚሰጡት ፈዋሽ የመጽሐፍ ቅዱስ ምክርና የሚያቀርቡለት ልባዊ ጸሎት መንፈሳዊ ጤንነቱ እንዲመለስለት ሊረዳው ይችላል። (ያዕቆብ 5:​13–15) በተጨማሪም እነዚህ በመንፈስ ቅዱስ የተሾሙ ወንዶች በክፉ መንገድ የሚመላለሱትን ወይም የጉባኤውን መንፈሳዊነትና የሥነ ምግባር ንጽሕና አደጋ ላይ የሚጥሉትን ሰዎች የመገሠጽና የመውቀስ ሥልጣን አላቸው። (ሥራ 20:​28፤ ቲቶ 1:​9፤ 2:​15) ግለሰቦችም ከባድ በደል መሠራቱን ሲመለከቱ የጉባኤውን ንጽሕና ለመጠበቅ ሲባል ለሽማግሌዎች ማስታወቃቸው አስፈላጊ ሊሆን ይችላል። (ዘሌዋውያን 5:​1) ከባድ ኃጢአት የሠራ ክርስቲያን የተሰጠውን ቅዱስ ጽሑፋዊ ተግሣጽና ወቀሳ ተቀብሎ ከልቡ ንስሐ መግባቱን ቢያሳይ እርዳታ ይደረግለታል። እርግጥ፣ የአምላክን ሕግ ከመተላለፍ የማይመለሱና ንስሐ የማይገቡ ሁሉ ይወገዳሉ።​— 1 ቆሮንቶስ 5:​9–13

23. ክርስቲያን የበላይ ተመልካቾች ለጉባኤው ደኅንነት ምን አስተዋጽኦ ያደር⁠ጋሉ?

23 መጽሐፍ ቅዱስ በኢየሱስ ክርስቶስ ንግሥና ሥር የአምላክን ሕዝቦች የሚያጽናኑ፣ የሚጠብቁና የሚያነቃቁ መንፈሳዊ ጉልምስና ያላቸው ወንዶች እንደሚሾሙ አስቀድሞ ተናግሮ ነበር። (ኢሳይያስ 32:​1, 2) መንፈሳዊ እድገት ለማራመድ በወንጌላዊነት፣ በእረኝነትና በማስተማር ሥራ በግንባር ቀደምትነት እንደሚሰለፉም ተገልጾ ነበር። (ኤፌሶን 4:​11, 12, 16) ክርስቲያን የበላይ ተመልካቾች የእምነት ባልደረቦቻቸውን የሚወቅሱበት፣ የሚገሥጹበትና የሚመክሩበት ጊዜ ቢኖርም ሽማግሌዎቹ የሚሰጡትን በአምላክ ቃል የተመሠረተ ጤናማ ትምህርት ተቀብለን ሥራ ላይ ማዋላችን ሁላችንም ከሕይወት መንገድ እንዳንወጣ ይረዳናል።​— ምሳሌ 3:​11, 12፤ 6:​23፤ ቲቶ 2:​1

ይሖዋ ስለ ሥልጣን ያለው አመለካከት አንተም ይኑርህ

24. በየቀኑ በምን ጉዳይ ላይ እንፈተናለን?

24 የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት ለሥልጣን ይገዙ ወይም አይገዙ እንደሆነ ተፈትነዋል። እኛም በየቀኑ ተመሳሳይ ፈተና የሚያጋጥመን መሆኑ የሚያስደንቅ አይደለም። ሰይጣን ዲያብሎስ በሰው ልጆች መካከል የዓመፀኝነት መንፈስ እንዲስፋፋ አድርጓል። (ኤፌሶን 2:​2) በራስ ሐሳብ መመራት ለሌላው ከመገዛት የተሻለና የሚያስጎመጅ ሆኖ እንዲታይ ተደርጓል።

25. የዓለምን የዓመፀኝነት መንፈስ አስወግዶ ለአምላክና እርሱ ለፈቀደላቸው ባለ ሥልጣኖች መገዛት ምን ጥቅሞች ያስገኛል?

25 እኛ ግን የዓለም የዓመፀኝነት መንፈስ እንዳይጋባብን መከላከል ይኖርብናል። ይህንም ስናደርግ አምላካዊ ተገዥነታችን በአጸፋው በረከት የሚያስገኝ ሆኖ እናገኘዋለን። ለምሳሌ ያህል ከዓለማዊ ባለ ሥልጣኖች ጋር የሚጋጩ ሰዎች የሚደርስባቸው ጭንቀትና ብስጭት አያጋጥመንም። በብዙ ቤተሰቦች ውስጥ የሚታየው የሻከረ ግንኙነት በእኛ ቤተሰብ ውስጥ አይኖርም። ከክርስቲያን የእምነት ባልደረቦቻችን ጋር ሞቅ ያለና ፍቅር የሰፈነበት ዝምድና ይኖረናል። ከሁሉ በላይ ደግሞ አምላካዊ የመገዛት ጠባያችን የመጨረሻ የበላይ ባለ ሥልጣን ከሆነው ከይሖዋ ጋር ጥሩ ዝምድና እንዲኖረን ያስችለ⁠ናል።

እውቀትህን ፈትሽ

ይሖዋ ሥልጣኑን የሚሠራበት እንዴት ነው?

‘በበላይ ያሉ ባለ ሥልጣኖች’ እነማን ናቸው? ለእነርሱ የምንገዛውስ እንዴት ነው?

የራስነት መሠረታዊ ሥርዓት በእያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ላይ ምን ኃላፊነት ይጥላል?

በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ለሥልጣን የምንገዛ መሆናችንን እንዴት ልናሳይ እንችላለን?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 134 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ለመንግሥት የሚገዙ እንጂ ዓመፅ የሚያነሳሱ አይደሉም

የይሖዋ ምሥክሮች በሕዝባዊ ስብከታቸው የአምላክ መንግሥት ለሰው ልጆች የእውነተኛ ሰላምና ደኅንነት ብቸኛ ተስፋ መሆኑን አሳውቀዋል። ይሁን እንጂ እነዚህ ቀናተኛ የሆኑ የአምላክ መንግሥት ሰባኪዎች በሚያስተዳድሯቸው መንግሥታት ላይ በምንም ዓይነት ዓመፅ አያነሳሱም። እንዲያውም የይሖዋ ምሥክሮች እጅግ በጣም ሕግ አክባሪ ከሆኑት ዜጎች የሚቆጠሩ ናቸው። በአንድ የአፍሪካ አገር የሚኖሩ አንድ ባለ ሥልጣን “ሁሉም ሃይማኖቶች እንደ ይሖዋ ምሥክሮች ቢሆኑ ኖሮ ነፍስ ግድያ፣ ዘረፋ፣ ዓመፀኝነት፣ እስረኞችና አቶሚክ ቦምብ አይኖሩም ነበር። በሮች ቀንና ሌሊት አይቆለፉም ነበር” ብለዋል።

በብዙ አገሮች የሚኖሩ ባለ ሥልጣኖች ይህን ስለ ተገነዘቡ የምሥክሮቹ የስብከት ሥራ አለ አንዳች ገደብ እንዲካሄድ ፈቅደዋል። በሌሎች አገሮች ደግሞ የይሖዋ ምሥክሮች በኅብረተሰቡ ላይ በጎ ተጽእኖ የሚያሳድሩ መሆናቸውን ባለ ሥልጣኖች ሲገነዘቡ ተጥሎባቸው የነበረውን እገዳ አንስተዋል። ይህም ሐዋርያው ጳውሎስ “መልካሙን አድርግ ከእርሱም ምስጋና ይሆንልሃል” ብሎ የበላይ ባለ ሥልጣኖችን ስለመታዘዝ ከጻፈው ጋር የሚስማማ ነው።​— ሮሜ 13:​1, 3