በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የምናረጀውና የምንሞተው ለምንድን ነው?

የምናረጀውና የምንሞተው ለምንድን ነው?

ምዕራፍ 6

የምናረጀውና የምንሞተው ለምንድን ነው?

1. የሳይንስ ሊቃውንት ስለ ሰው ልጅ ሕይወት ሊያስረዱ ያልቻሉት ምን ነገር አለ?

የሳይንስ ሊቃውንት የሰው ልጆች ለምን እንደሚያረጁና እንደሚሞቱ አያውቁም። የሰውነታችን ሴሎች ዘወትር እየታደሱ መቀጠልና እኛም ለዘላለም መኖር መቻል የነበረብን ይመስላል። ሃዮጁን ሶሺኪጋኩ (የሴሎች መሠረታዊ ጥናት) የተባለው መጽሐፍ “የሴሎች እርጅና ከአንድ ግለሰብ እርጅናና ሞት ጋር የሚዛመድበት መንገድ ታላቅ ምሥጢር ነው” ይላል። ብዙ ሳይንቲስቶች ሕይወት “ተፈጥሯዊ” ድንበር እንዳለው ያምናሉ። እነዚህ ሳይንቲስቶች ትክክል ናቸው ብለህ ታምናለህ?

2. አንዳንዶች የሰው ዕድሜ በጣም አጭር በመሆኑ ምክንያት ምን አድርገዋል?

2 የሰው ልጆች ዕድሜያቸውን ለማራዘምና ከዚያም አልፈው ዘላለማዊነትን ለማግኘት ብርቱ ጥረት አድርገዋል። ከአራተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ ጀምሮ ያለመሞትን ባሕርይ ያላብሳሉ የተባሉ መድኃኒቶች የቻይናውያንን መኳንንት ትኩረት ስበው ነበር። በኋላ የተነሱ አንዳንድ ቻይናውያን ንጉሠ ነገሥታትም ዕድሜ ቀጥል ነው ተብሎ የተሰጣቸውን ከሜርኩሪ የተቀመመ መድኃኒት ጠጥተው ሞተዋል። በማንኛውም የምድር ክፍል የሚኖሩ ሰዎች ሞት የሕልውናቸው ማክተሚያ እንዳልሆነ ያምናሉ። ቡድሂስቶች፣ ሂንዱዎች፣ ሙስሊሞችና ሌሎች ሰዎች ከሞት በኋላ ሕይወት አለ የሚል ብሩሕ ተስፋ አላቸው። በሕዝበ ክርስትና ውስጥ ያሉ ሰዎችም ከምድራዊ ሕይወት በኋላ በሰማይ ተድላና ደስታ የሞላበት ሕይወት እንኖራለን ብለው ተስፋ ያደርጋሉ።

3. (ሀ) የሰው ልጆች የዘላለም ሕይወት ለማግኘት የሚናፍቁት ለምንድን ነው? (ለ) ስለ ሞት የሚነሱ የትኞቹ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት አለባቸው?

3 ከሞት በኋላ ደስታ ስለ ማግኘት ልዩ ልዩ ጽንሰ ሐሳብ መኖሩ ሰዎች የዘላለም ሕይወት ለማግኘት የሚናፍቁ መሆናቸውን ያሳያል። መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ በሰው ልጆች ውስጥ ስለተከለው ለዘላለም የመኖር ሐሳብ ሲናገር “ዘላለምነትን በልቡ ሰጠው” ይላል። (መክብብ 3:​11) የመጀመሪያዎቹን ሰዎች ሲፈጥር በምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ እንዲኖራቸው አድርጎ ነበር። (ዘፍጥረት 2:​16, 17) ታዲያ የሰው ልጆች የሚሞቱት ለምንድን ነው? ሞት ወደ ዓለም የገባው እንዴት ነው? ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ የሚሰጠን ከአምላክ የሚገኝ እውቀት ነው።​— መዝሙር 119:​105

መዘዘኛ ደባ

4. ኢየሱስ የሰው ልጆችን ለሞት የዳረጋቸው ወንጀለኛ ማን መሆኑን ያጋለጠው እንዴት ነው?

4 ማንኛውም ወንጀለኛ ዱካውን ለማጥፋት ይሞክራል። በቢልዮን ለሚቆጠሩ ሰዎች መሞት ምክንያት የሆነውን ወንጀል የጠነሰሰው ወንጀለኛም ይህንኑ ለማድረግ ሞክሯል። የሰው ልጆች ሞት በአደናጋሪ ምሥጢሮች እንዲሸፈን አድርጓል። ኢየሱስ ክርስቶስ ሊገድሉት ይፈልጉ ለነበሩት ሰዎች “እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ። እርሱ ከመጀመሪያ ነፍሰ ገዳይ ነበረ፤ እውነትም በእርሱ ስለ ሌለ በእውነት አልቆመም” በማለት የዚህን ወንጀለኛ ማንነት አጋልጧል።​— ዮሐንስ 8:​31, 40, 44

5. (ሀ) በኋላ ሰይጣን ዲያብሎስ የሆነው ፍጡር ከየት መጣ? (ለ) “ሰይጣን” እና “ዲያብሎስ” የሚሉት ቃላት ትርጉማቸው ምንድን ነው?

5 አዎን፣ ዲያብሎስ ጨካኝ “ነፍሰ ገዳይ” ነው። እርሱ በሰው ልብ ውስጥ የሚያድር ክፋት ሳይሆን የራሱ ሕልውናና አካል ያለው ፍጥረት እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይገልጻል። (ማቴዎስ 4:​1–11) ጻድቅ መልአክ ሆኖ ቢፈጠርም “በእውነት አልቆመም።” ሰይጣን ዲያብሎስ ተብሎ መጠራቱ ምንኛ የተገባ ነው! (ራእይ 12:​9) ይሖዋን ስለተጻረረና ስለተቃወመ “ሰይጣን” ወይም “ተቃዋሚ” ተብሏል። በተጨማሪም ይህ ወንጀለኛ ለአምላክ የማይገባ ስም በመስጠት ስሙን ስላጠፋ “ስም አጥፊ” የሚል ትርጉም ያለው “ዲያብሎስ” የተባለ ስም ተሰጥቶታል።

6. ሰይጣን በአምላክ ላይ ያመፀው ለምንድን ነው?

6 ሰይጣንን በአምላክ ላይ እንዲያምፅ ያነሳሳው ነገር ምን ነበር? ስግብግብነት ነበር። ይሖዋ ከሰው ልጆች ይቀርብለት የነበረውን አምልኮ ለማግኘት ሰይጣን በስግብግብነት ቋመጠ። ዲያብሎስ የፈጣሪ ብቸኛ መብት የሆነውን አምልኮ ለመውሰድ ያደረበትን ፍላጎት ከአእምሮው ለማውጣት አልሞከረም። (ከሕዝቅኤል 28:​12–19 ጋር አወዳድር።) ከዚህ ይልቅ ሰይጣን የሆነው ይህ መልአክ የስግብግብነት ምኞቱ ሥር ሰድዶ ኃጢአት እስኪወልድ ድረስ አሳደገው።​— ያዕቆብ 1:​14, 15

7. (ሀ) የሰውን ልጆች እንዲሞቱ የሚያደርጋቸው ነገር ምንድን ነው? (ለ) ኃጢአት ምንድን ነው?

7 በወንጀል ድርጊቱ ለሰው ልጆች መሞት ምክንያት የሆነው ሸረኛ ማን እንደሆነ አውቀናል። ይሁን እንጂ ለሰው ልጆች ሞት ምክንያት የሆነው ነገር ምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ “የሞት መውጊያ ኃጢአት ነው” ይላል። (1 ቆሮንቶስ 15:​56) ታዲያ ኃጢአት ምንድን ነው? የዚህን ቃል ትርጉም ለመረዳት የመጽሐፍ ቅዱስ በኩረ ጽሑፍ በተጻፈባቸው ቋንቋዎች ቃሉ የነበረውን ትርጉም እንመልከት። “ኃጢአት መሥራት” ተብለው የተተረጎሙት የዕብራይስጥና የግሪክኛ ግሦች “ዒላማ መሳትን” ወይም አንድን ደረጃ አለማሟላትን ወይም አንድ ግብ ላይ አለመድረስን የሚያመለክት ትርጉም አላቸው። ሁላችንም ያላሟላነው ደረጃ ምንድን ነው? ለአምላክ ፍጹም ታዛዥ የመሆንን ደረጃ አናሟላም። ይሁን እንጂ ኃጢአት ወደ ዓለም የገባው እንዴት ነው?

ደባው የተፈጸመው እንዴት ነው?

8. ሰይጣን የሰው ልጆችን አምልኮ ለማግኘት የሞከረው እንዴት ነው?

8 ሰይጣን የሰው ልጆችን በሙሉ ለመግዛትና እርሱን እንዲያመልኩት ለማድረግ የሚያስችለውን ሴራ በጥንቃቄ ሸረበ። የመጀመሪያዎቹን ባልና ሚስት፣ አዳምንና ሔዋንን በአምላክ ላይ ኃጢአት እንዲሠሩ ለማድረግ ወሰነ። ይሖዋ ለመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን ወደ ዘላለም ሕይወት ሊመራቸው የሚችል እውቀት ሰጥቷቸው ነበር። ፈጣሪያቸው በጣም ውብ በሆነው የኤደን አትክልት ሥፍራ አስቀምጧቸው ስለነበረ ጥሩ አምላክ መሆኑን ያውቁ ነበር። በተለይ አዳም ቆንጆ እና ጥሩ ረዳት የምትሆን ሚስት አምላክ ሰጥቶት ስለነበረ የሰማያዊ አባቱ ጥሩነት ተሰምቶት ነበር። (ዘፍጥረት 1:​26, 29፤ 2:​7–9, 18–23) የመጀመሪያዎቹ ባልና ሚስት ሕይወት ቀጣይነት ለአምላክ በመታዘዛቸው ላይ የተመካ ነበር።

9. አምላክ ለመጀመሪያዎቹ ሰዎች ምን ትእዛዝ ሰጥቶ ነበር? ይህስ ትእዛዝ ምክንያታዊ የነበረው ለምንድን ነው?

9 አምላክ አዳምን “ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህ” ሲል አዘዘው። (ዘፍጥረት 2:​16, 17) ይሖዋ አምላክ የሁሉም ነገር ፈጣሪ እንደመሆኑ መጠን ለፍጥረቶቹ የሥነ ምግባር መስፈርቶችን የማውጣትና ምን ነገሮች ጥሩ ወይም ምን ነገሮች ክፉ እንደሆኑ የመደንገግ መብት አለው። የሰጣቸውም ትእዛዝ ቢሆን ምክንያታዊ ነበር፤ ለምን ቢባል አዳምና ሔዋን በአትክልቱ ውስጥ ከነበሩት ሌሎች ፍሬዎች በሙሉ የመብላት ነጻነት ነበራቸው። በትዕቢት ተነሳስተው የራሳቸውን የሥነ ምግባር መስፈርት ከማውጣት ይልቅ ይህን ሕግ ቢታዘዙ ኖሮ ይሖዋ ላለው ትክክለኛ የመግዛት መብት አክብሮትና አድናቆት ያሳዩ ነበር።

10. (ሀ) ሰይጣን የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ተባባሪዎቹ እንዲሆኑ ለማድረግ የቀረባቸው እንዴት ነበር? (ለ) ሰይጣን የይሖዋ ውስጣዊ ዓላማ ምንድን ነው አለ? (ሐ) አንተስ ሰይጣን በአምላክ ላይ ስለ ሰነዘረው ጥቃት ምን ይሰማሃል?

10 ዲያብሎስ የመጀመሪያዎቹን ወንድና ሴት ከአምላክ ለማራቅ የሚያስችለውን ተንኮል ሸረበ። ሰይጣን ከእርሱ ጎን እንዲሰለፉ ለመሸንገል የሐሰት ቃል ተናገረ። ራሳቸው እየተናገሩ አሻንጉሊት እንደሚናገር የሚያስመስሉ ሰዎች እንደሚያደርጉት ዲያብሎስም እባብ የተናገረ በማስመሰል ሔዋንን “በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን?” ሲል ጠየቃት። ሔዋን አምላክ የሰጠውን ትእዛዝ ከነገረችው በኋላ “ሞትን አትሞቱም” አላት። ከዚያም “ከእርስዋ በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንዲከፈቱ እንደ እግዚአብሔርም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንድትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው እንጂ” በማለት ይሖዋ በመጥፎ ዓላማ ተነሳስቶ የሰጠው ትእዛዝ እንደሆነ ገለጸላት። (ዘፍጥረት 3:​1–5) ዲያብሎስ በዚህ አነጋገሩ አምላክ የከለከላቸው ጥሩ ነገር እንዳለ ጠቆማቸው። እውነተኛና አፍቃሪ በሆነው ሰማያዊ አባት ላይ የተሰነዘረ እንዴት ያለ አስከፊ ስም የማጥፋት ጥቃት ነበር!

11. አዳምና ሔዋን የሰይጣን ግብረ አበሮች የሆኑት እንዴት ነው?

11 ሔዋን መለስ ብላ ዛፉን ተመለከተች። በዚህ ጊዜ በተለይ የዛፉ ፍሬ የሚያስጎመጅ ሆኖ ታያት። ከፍሬውም ወሰደችና በላች። ቆየት ብሎም ባልዋ ሆነ ብሎ በዚህ አምላክን ያለመታዘዝ አድራጎት ተባበራት። (ዘፍጥረት 3:​6) ምንም እንኳ ሔዋን የተታለለች ብትሆንም እርስዋም ሆነች አዳም ሰይጣን ለሸረበው የሰውን ዘር የመግዛት ሴራ ድጋፍ ሰጥተዋል። ይህን በማድረጋቸውም የሰይጣን ግብረ አበሮች ሆነዋል።​— ሮሜ 6:​16፤ 1 ጢሞቴዎስ 2:​14

12. የሰው ልጅ በአምላክ ላይ ያደረገው ዓመፅ ምን አስከተለ?

12 አዳምና ሔዋን ድርጊታቸው ያስከተለባቸውን መዘዝ መቀበል ነበረባቸው። ልዩ እውቀት አግኝተው እንደ አምላክ ለመሆን አልቻሉም። ከዚህ ይልቅ እፍረት ተሰምቷቸው ራሳቸውን ሸሸጉ። ይሖዋ አዳምን ጠርቶ ለፈጸመው ድርጊት መልስ እንዲሰጥ ከጠየቀው በኋላ የሚከተለውን ፍርድ በየነበት:- “ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ፤ አፈር ነህና፣ ወደ አፈርም ትመለሳለህና።” (ዘፍጥረት 3:​19) የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን መልካሙንና ክፉውን ከሚያስታውቀው ዛፍ በበሉበት “ቀን” አምላክ ሞት ፈረደባቸውና በእርሱ አመለካከት የሞቱ ሆኑ። ከዚያም ከገነት ተባረሩና ወደ አካላዊ ሞት ማሽቆልቆል ጀመሩ።

ኃጢአትና ሞት ወደ ሌሎች የተዛመቱት እንዴት ነው?

13. ኃጢአት ወደ መላው የሰው ዘሮች የተዛመተው እንዴት ነው?

13 ሰይጣን የሰው ልጆች እንዲያመልኩት የጠነሰሰው ተንኮል የሰመረለት መሰለ። ይሁን እንጂ አምላኪዎቹን በሕይወት ለማኖር አልቻለም። ኃጢአት በመጀመሪያዎቹ ባልና ሚስት ውስጥ ከሰረጸ በኋላ የፍጽምናን ባሕርይ ለልጆቻቸው ለማስተላለፍ አልቻሉም። ኃጢአት በድንጋይ ጽላት ላይ እንደተቀረጸ ጽሕፈት የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን በነበሯቸው ጅን በተባሉ ባሕርይ አስተላላፊዎች ላይ ተቀርጾ ነበር። በዚህም ምክንያት ሊወልዱ የቻሉት ፍጽምና የጎደላቸውን ልጆች ብቻ ነበር። ዘሮቻቸው በሙሉ የተጸነሱት አዳምና ሔዋን ኃጢአት ከሠሩ በኋላ በመሆኑ ሁሉም ኃጢአትና ሞት ወረሱ።​— መዝሙር 51:​5፤ ሮሜ 5:​12

14. (ሀ) ኃጢአተኛ መሆናቸውን የማይቀበሉ ሰዎችን በማን ልንመስላቸው እንችላለን? (ለ) እስራኤላውያን ኃጢአተኛ መሆናቸውን እንዲያውቁት የተደረገው እንዴት ነበር?

14 ይሁን እንጂ በአሁኑ ጊዜ የሚኖሩ ብዙ ሰዎች ኃጢአተኞች እንደሆኑ አድርገው አያስቡም። በአንዳንድ የዓለም ክፍሎች ኃጢአት ወርሰናል የሚለው ጽንሰ ሐሳብ በአብዛኛው ሕዝብ ዘንድ አይታወቅም። ይሁን እንጂ ይህ ኃጢአት ላለመኖሩ ማስረጃ ሊሆን አይችልም። አንድ ፊቱ የቆሸሸ ልጅ ንጹሕ ነኝ ሊል ይችላል። መስተዋት ካላየ በስተቀር መቆሸሹን አይቀበልም። የጥንቶቹ እስራኤላውያን የአምላክን ሕግ በነቢዩ ሙሴ በኩል በተቀበሉ ጊዜ ልክ እንደዚህ ልጅ ነበሩ። ይህ ሕግ ኃጢአት መኖሩን ግልጽ አደረገላቸው። ሐዋርያው ጳውሎስ ይህን ሲያስረዳ “በሕግ ባይሆን ኃጢአትን ባላወቅሁም ነበር” ብሏል። (ሮሜ 7:​7–12) ልጁ መስተዋቱን ሲያይ የፊቱን መቆሸሽ እንደሚገነዘብ ሁሉ እስራኤላውያንም በሕጉ አማካኝነት በይሖዋ ዓይን ንጹሐን አለመሆናቸውን ሊመለከቱ ችለዋል።

15. እንደ መስተዋት የሆነውን የአምላክ ቃል በመመርመር ምን መገንዘብ ይቻ⁠ላል?

15 እኛም እንደ መስተዋት የሆነውን የአምላክ ቃል በመመርመርና የሥነ ምግባር መስፈርቶችን በማስተዋል ፍጹማን አለመሆናችንን ለማየት እንችላለን። (ያዕቆብ 1:​23–25) ለምሳሌ ያህል ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክንና ሰዎችን ስለመውደድ በማቴዎስ 22:​37–40 ላይ ለደቀ መዛሙርቱ የተናገረውን እንመልከት። ሰዎች በዚህ መስክ ስንት ጊዜ አምላክ ያወጣውን ደረጃ ሳያሟሉ ይቀራሉ! እንዲያውም ብዙ ሰዎች ለአምላክና ለባልንጀሮቻቸው ፍቅር ባለማሳየታቸው ሕሊናቸውን እንኳን አይቆረቁራቸውም።​— ሉቃስ 10:​29–37

በሰይጣን ዘዴዎች እንዳትወድቅ ተጠንቀቅ!

16. በሰይጣን የተንኮል ወጥመድ እንዳንያዝ ምን ማድረግ እንችላለን? ይህስ ቀላል ያልሆነው ለምንድን ነው?

16 ሰይጣን ሆን ብለን ኃጢአት እየሠራን እንድንኖር ይፈልጋል። (1 ዮሐንስ 3:​8) በሰይጣን ወጥመድ እንዳንወድቅ ራሳችንን ልንጠብቅ የምንችልበት መንገድ ይኖራልን? አዎን፣ አለ። ይሁን እንጂ ይህ መንገድ ወደ ኃጢአት የሚመራንን ዝንባሌ እንድንዋጋ ይፈልግብናል። ነገር ግን በውስጣችን ያለው የኃጢአት ዝንባሌ በጣም ጠንካራ በመሆኑ ይህን ዝንባሌ መዋጋት ቀላል አይደለም። (ኤፌሶን 2:​3) ጳውሎስ ብርቱ ትግል ማድረግ አስፈልጎት ነበር። ለምን? የኃጢአት ማደሪያ ሆኖ ስለነበረ ነው። እኛም የአምላክን ሞገስ ለማግኘት ከፈለግን በውስጣችን የሚኖረውን የኃጢአት ዝንባሌ መዋጋት ይገባናል።​— ሮሜ 7:​14–24፤ 2 ቆሮንቶስ 5:​10

17. ከኃጢአተኛ ዝንባሌአችን ጋር የምናደርገውን ውጊያ ይበልጥ አስቸጋሪ የሚያደርግብን ነገር ምንድን ነው?

17 ሰይጣን የአምላክን ሕግ እንድንጥስ የሚያጠምድበትን አጋጣሚ ሁልጊዜ ስለሚፈልግ ከኃጢአት ጋር የምናደርገው ውጊያ ቀላል አይደለም። (1 ጴጥሮስ 5:​8) ጳውሎስ “እባብ በተንኮሉ ሔዋንን እንዳሳታት፣ አሳባችሁ ተበላሽቶ ለክርስቶስ ከሚሆን ቅንነትና ንጽሕና ምናልባት እንዳይለወጥ ብዬ እፈራለሁ” በማለት ለክርስቲያን ባልደረቦቹ የነበረውን ስጋት ገልጿል። (2 ቆሮንቶስ 11:​3) ዛሬም ቢሆን ሰይጣን በተመሳሳይ ዘዴዎች ይጠቀማል። የይሖዋን ጥሩነትና የአምላክን ትእዛዛት ማክበር የሚያስገኘውን ጥቅም እንድንጠራጠር ሲል የጥርጣሬ ዘር ይዘራብናል። ዲያብሎስ በወረስነው የኃጢአት ዝንባሌ በመጠቀም የኩራት፣ የስግብግብነት፣ የዘር ጥላቻና የአድልዎ አካሄድ እንድንከተል ለማድረግ ይጥራል።

18. ሰይጣን ኃጢአትን ለማስፋፋት ዓለምን መሣሪያ አድርጎ የሚጠቀመው እንዴት ነው?

18 ዲያብሎስ በእኛ ላይ ከሚጠቀምባቸው መሣሪያዎች አንዱ በእሱ ቁጥጥር ሥር የሚገኘው ዓለም ነው። (1 ዮሐንስ 5:​19) ጠንቃቆች ካልሆን በዙሪያችን በሚገኘው ዓለም ውስጥ ያሉ ምግባረ ብልሹ የሆኑና በሐቅ የማይሠሩ ሰዎች የአምላክን የሥነ ምግባር መስፈርቶች እንድናጓድል ተጽእኖ ሊያደርጉብን ይችላሉ። (1 ጴጥሮስ 4:​3–5) ብዙዎች የአምላክን ሕግጋት ችላ ከማለታቸውም በላይ የሕሊናቸውን ወቀሳ ለመስማት እምቢተኞች በመሆን በመጨረሻው ያደነዝዙታል። (ሮሜ 2:​14, 15፤ 1 ጢሞቴዎስ 4:​1, 2) አንዳንዶች ቀስ በቀስ ፍጹም ያልሆነው ሕሊናቸው እንኳን ይከለክላቸው የነበረውን አካሄድ ይዘው ይገኛሉ።​— ሮሜ 1:​24–32፤ ኤፌሶን 4:​17–19

19. ንጹሕ ኑሮ መኖር ብቻውን በቂ የማይሆነው ለምንድን ነው?

19 በዚህ ዓለም ውስጥ ንጽሕናን ጠብቆ መኖር ጥረትን ይጠይቃል። ይሁን እንጂ ፈጣሪያችንን ለማስደሰት ከዚህ የበለጠ ነገር ያስፈልገናል። በአምላክ ልናምንና ለምናደርጋቸው ነገሮች በሙሉ በኃላፊነት የምንጠየቅ መሆናችን ሊሰማን ይገባል። (ዕብራውያን 11:​6) ደቀ መዝሙሩ ያዕቆብ “እንግዲህ በጎ ለማድረግ አውቆ ለማይሠራው ኃጢአት ነው” ሲል ጽፏል። (ያዕቆብ 4:​17) አዎን፣ አምላክንና ትእዛዛቱን ሆን ብሎ ችላ ማለት አንዱ የኃጢአት ዓይነት ነው።

20. ሰይጣን ትክክለኛውን ነገር እንዳታደርግ ሊያሰናክልህ የሚሞክረው እንዴት ነው? ይሁን እንጂ እንዲህ ያለውን ተጽእኖ እንድትቋቋም የሚረዳህ ምንድን ነው?

20 በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትህ አማካኝነት አምላክ የሚሰጠውን እውቀት ለማግኘት በምታደርገው ጥረት ላይ ሰይጣን ተቃውሞ ማስነሳቱ አይቀርም። እንዲህ ያለው ተጽእኖ ትክክል የሆነውን ነገር ከማድረግ እንደማያግድህ ተስፋ እናደርጋለን። (ዮሐንስ 16:​2) ኢየሱስ በምድር ላይ ያገለግል በነበረበት ዘመን በእርሱ ያመኑ ብዙ ገዥዎች ቢኖሩም ይኖሩበት የነበረው ማኅበረሰብ ይሸሸናል ብለው በመፍራታቸው ብቻ በግልጽ ሳይቀበሉት ቀርተዋል። (ዮሐንስ 12:​42, 43) ሰይጣን ከአምላክ የሚገኘውን እውቀት ለመቅሰም የሚፈልጉ ሰዎችን በጭካኔ ለማስፈራራት ይሞክራል። ይሁን እንጂ ሁልጊዜ ይሖዋ ያደረጋቸውን አስደናቂ ነገሮች ማስታወስና ማድነቅ ይኖርብሃል። እንዲያውም ተቃዋሚዎች የአንተን የመሰለ አድናቆት እንዲያድርባቸው ለመርዳት ትችል ይሆናል።

21. ዓለምንና ኃጢአተኛ ዝንባሌአችንን እንዴት ልናሸንፍ እንችላለን?

21 ፍጹማን እስካልሆን ድረስ ኃጢአት መሥራታችን አይቀርም። (1 ዮሐንስ 1:​8) ይሁን እንጂ ይህን ውጊያ በድል አድራጊነት እንድንወጣ የሚያስችል እርዳታ አለን። አዎን፣ ከክፉው ከሰይጣን ዲያብሎስ ጋር የምናደርገውን ውጊያ በድል አድራጊነት ልንወጣ እንችላለን። (ሮሜ 5:​21) ኢየሱስ በምድራዊ አገልግሎቱ መጨረሻ ላይ ተከታዮቹን “በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ” በማለት አጽናንቷቸዋል። (ዮሐንስ 16:​33) ፍጹማን ያልሆኑ ሰዎች እንኳን በአምላክ እርዳታ ዓለምን ለማሸነፍ ይችላሉ። ሰይጣን እርሱን በሚቃወሙና ‘ራሳቸውን ለአምላክ በሚያስገዙ’ ሰዎች ላይ ምንም ዓይነት ሥልጣን የለውም። (ያዕቆብ 4:​7፤ 1 ዮሐንስ 5:​18) ቀጥለን እንደምንመለከተው አምላክ ከኃጢአትና ከሞት እስራት ነፃ የምንወጣበትን መንገድ አዘጋጅቷል።

እውቀትህን ፈትሽ

ሰይጣን ዲያብሎስ ማን ነው?

ሰዎች የሚያረጁትና የሚሞቱት ለምንድን ነው?

ኃጢአት ምንድን ነው?

ሰይጣን ሰዎች ሆን ብለው ኃጢአት እንዲሠሩ የሚያደርገው እንዴት ነው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 54 ላይ የሚገኝ ባለ ሙሉ ገጽ ሥዕል]