በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአምላክ መንግሥት መግዛት ጀምሯል

የአምላክ መንግሥት መግዛት ጀምሯል

ምዕራፍ 10

የአምላክ መንግሥት መግዛት ጀምሯል

1, 2. ሰብዓዊ መንግሥታት ብቃት የጎደላቸው ሆነው የተገኙት እንዴት ነው?

አንድ አዲስ መሣሪያ ከገዛህ በኋላ አውጥተህ ስትሞክረው አልሠራ ይልሃል። መሣሪያውን የሚጠግንልህ ሰው ትጠራለህ። ‘ሠራሁ’ ብሎ ከሄደ በኋላ ወዲያው ተበላሽቶ ታገኘዋለህ። ይህ ምንኛ ተስፋ አስቆራጭ ነው!

2 ሰብዓዊ መንግሥታትም ሁኔታቸው ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው። የሰው ልጅ አስተማማኝ ሰላምና ደስታ የሚያስገኝለትን መንግሥት አጥብቆ ያልፈለገበት ዘመን የለም። ይሁን እንጂ በኅብረተሰቡ ውስጥ የሚታየውን ብልሽት ለመጠገን የተደረገው ብርቱ ጥረት የሰመረ ውጤት ለማስገኘት አልቻለም። በጣም ብዙ የሰላም ውሎች ተደርገው ፈርሰዋል። ከዚህም በላይ ድህነትን፣ በዘርና በሃይማኖት መጠላላትን፣ ወንጀልን፣ በሽታንና የአካባቢ መበከልን ሊያስወግድ የቻለ መንግሥት የትኛው ነው? የሰው አገዛዝ ሊጠገን የማይችል ሆኗል። የእስራኤል ንጉሥ የነበረው ጠቢቡ ሰሎሞን እንኳን “እንግዲያስ ሰው መንገዱን እንዴት ያስተውላል?” ሲል ጠይቋል።​— ምሳሌ 20:​24

3. (ሀ) የኢየሱስ ስብከት ዋነኛ ጭብጥ ምን ነበር? (ለ) አንዳንድ ሰዎች የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው ይላሉ?

3 ይሁን እንጂ በዚህ ተስፋ አትቁረጥ! ዓለምን የሚገዛ የተረጋጋ መንግሥት የመምጣቱ ጉዳይ ሕልም አይደለም። የኢየሱስ ስብከት ዋነኛ ጭብጥ ይህ መንግሥት ነበር። ኢየሱስ ይህን መንግሥት “የእግዚአብሔር መንግሥት” ብሎ ጠርቶታል፤ ተከታዮቹም ስለዚህ መንግሥት እንዲጸልዩ አስተምሯል። (ሉቃስ 11:​2፤ 21:​31) እርግጥ ነው በአንዳንድ ሃይማኖቶች የአምላክ መንግሥት የሚጠቀስበት ጊዜ አለ። እንዲያውም በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በየቀኑ የጌታን ጸሎት ወይም “አቡነ ዘበሰማያት”ን በሚደግሙበት ጊዜ ስለዚህ መንግሥት መጸለያቸው ነው። ይሁን እንጂ “የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው?” የሚል ጥያቄ ሲቀርብላቸው የሚሰጡት መልስ የተለያየ ነው። አንዳንዶች “የአምላክ መንግሥት በልብህ ውስጥ ያለ ነገር ነው” ይላሉ። ሌሎች ደግሞ የአምላክ መንግሥት ሲባል ሰማይ ማለት ነው ይላሉ። ቀጥለን እንደምንመለከተው መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ጉዳዩ ግልጽ ማብራሪያ ይሰጣል።

ዓላማ ያለው መንግሥት

4, 5. ይሖዋ አዲስ ዓይነት የሉዓላዊነቱን መግለጫ ለማምጣት የመረጠው ለምንድን ነው? ይህስ አዲስ መግለጫ ምን ነገር ያከናውናል?

4 ይሖዋ አምላክ የአጽናፈ ዓለሙ ንጉሥ ወይም ሉዓላዊ ገዥ ያልነበረበት ዘመን የለም። የሁሉ ነገር ፈጣሪ በመሆኑ ይህ ከፍተኛ ሥልጣን ሊኖረው ችሏል። (1 ዜና መዋዕል 29:​11፤ መዝሙር 103:​19፤ ሥራ 4:​24) ኢየሱስ የሰበከው መንግሥት ግን ከአምላክ አጽናፈ ዓለማዊ ሉዓላዊነት የበታች ወይም ሁለተኛ ደረጃ ሆኖ የሚሠራ መንግሥት ነው። ይህ መሲሐዊ መንግሥት የተወሰነ ዓላማ ያለው መንግሥት ነው። ይህ ዓላማ ምንድን ነው?

5 በምዕራፍ 6 ላይ እንደተብራራው የመጀመሪያዎቹ ሰብዓውያን ባልና ሚስት በአምላክ ሥልጣን ላይ ዓመፁ። በዚህ ጊዜ በተነሱት ዐበይት ጥያቄዎች ምክንያት ይሖዋ አዲስ የሆነ የሉዓላዊነቱ መግለጫ ለማቋቋም መረጠ። አምላክ እባቡን ማለትም ሰይጣንን የሚቀጠቅጥና የሰው ልጅ በውርሻ ያገኘው ኃጢአት ያስከተለውን መጥፎ ውጤት የሚያስተካክል “ዘር” ለማስገኘት ዓላማ እንዳለው አስታወቀ። ዋነኛው “ዘር” ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን ሰይጣንን ድል ለማድረግ መሣሪያ ሆኖ የሚያገለግለው “የእግዚአብሔር መንግሥት” ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ መንግሥት አማካኝነት በመላው ምድር ላይ በይሖዋ ስም የሚካሄድ አገዛዝ ተመልሶ እንዲቋቋም ያደርጋል። ትክክለኛ የሆነውንም የአምላክ ሉዓላዊነት ለዘላለም ያረጋግጣል።​— ዘፍጥረት 3:​15፤ መዝሙር 2:​2–9

6, 7. (ሀ) መንግሥቱ የት ሆኖ ይገዛል? ንጉሡና ተባባሪ ገዥዎቹስ እነማን ናቸው? (ለ) የአምላክ መንግሥት ዜጎች እነማን ናቸው?

6 በአንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም መሠረት ኢየሱስ ለክፉዎቹ ፈሪሳውያን “መንግሥተ ሰማያት በውስጣችሁ ነው” ብሏቸዋል። (ሉቃስ 17:​21 ኪንግ ጀምስ ትርጉም) ታዲያ ኢየሱስ የአምላክ መንግሥት በእነዚያ ምግባረ ብልሹ ፈሪሳውያን ክፉ ልብ ውስጥ አድሯል ማለቱ ነበርን? በፍጹም አይደለም። ግሪክኛው ቃል በትክክል ሲተረጎም “የአምላክ መንግሥት በመካከላችሁ ነው” ይላል። ­በመካከላቸው የነበረው ኢየሱስ በዚህ አነጋገሩ የመንግሥቱ የወደፊት ንጉሥ እርሱ ራሱ መሆኑን አመልክቷል። የአምላክ መንግሥት በሰው ልብ ውስጥ የሚያድር ነገር ሳይሆን ገዥና ተገዥዎች ያሉት የራሱ የሆነ ሥራና እንቅስቃሴ ያለው እውን መስተዳድር ነው። “መንግሥተ ሰማያት” እና “የእግዚአብሔር መንግሥት” ተብሎ ስለሚጠራም ሰማያዊ መስተዳድር ነው። (ማቴዎስ 13:​11፤ ሉቃስ 8:​10) ነቢዩ ዳንኤል በተመለከተው ራእይ ላይ የዚህ መንግሥት ገዥ “የሰው ልጅ የሚመስል” እንደሆነና እርሱም ሁሉን ወደሚችለው አምላክ ቀርቦ “ወገኖችና አሕዛብ በልዩ ልዩ ቋንቋም የሚናገሩ ሁሉ ይገዙለት ዘንድ ግዛትና ክብር መንግሥትም” እንደተሰጠው አይቷል። (ዳንኤል 7:​13, 14) ይህ ንጉሥ ማን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስን “የሰው ልጅ” እያለ ይጠራዋል። (ማቴዎስ 12:​40፤ ሉቃስ 17:​26) አዎን፣ ይሖዋ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ ንጉሥ እንዲሆን ሾሞታል።

7 ኢየሱስ የሚገዛው ብቻውን አይደለም። ከእርሱ ጋር የሚገዙ ‘ከምድር የተዋጁ’ 144,000 ተባባሪ ነገሥታትና ካህናት ይኖራሉ። (ራእይ 5:​9, 10፤ 14:​1, 3፤ ሉቃስ 22:​28–30) የአምላክ መንግሥት ዜጎች ለክርስቶስ አመራር የሚገዙ በመላዋ ምድር እንደ አንድ ቤተሰብ ሆነው የሚኖሩ የሰው ልጆች ይሆናሉ። (መዝሙር 72:​7, 8) ታዲያ ይህ መንግሥት የአምላክን ሉዓላዊነት እንደሚያረጋግጥና በምድራችን ላይ ገነታዊ ሁኔታ እንዲሰፍን እንደሚያደርግ እንዴት እርግጠኞች ለመሆን እንችላለን?

የአምላክ መንግሥት እውንነት

8, 9. (ሀ) የአምላክ መንግሥት ተስፋ አስተማማኝ መሆኑን እንዴት በምሳሌ ለማስረዳት እንችላለን? (ለ) ስለ አምላክ መንግሥት እውንነት እርግጠኛ መሆን የምንችለው ለምንድን ነው?

8 ቤትህ በእሳት ተቃጥሎ ወደመብህ እንበል። ወዲያው በቂ አቅምና ችሎታ ያለው አንድ ወዳጅህ ቤቱን መልሶ እንደሚያሠራልህና ለቤተሰብህ የሚያስፈልገውን ምግብ በሙሉ እንደሚያቀርብልህ ቃል ይገባልሃል። ይህ ወዳጅህ ከዚያ በፊት ሁልጊዜ እውነት የሚናገር ከነበረ ይህን የተናገረውን ቃል አታምነውምን? በማግስቱ ከሥራ ስትመለስ የጥገና ሠራተኞች የቃጠሎውን ፍርስራሽ ማነሳሳትና ማጽዳት ጀምረው ቢጠብቁህና ለቤተሰብህ የሚያስፈልገው ምግብ ሁሉ ቀርቦ ብትመለከትስ? ከጊዜ በኋላ እንዲያውም ከቀድሞ ቤትህ የተሻለ መኖሪያ እንደምታገኝ እርግጠኛ እንደምትሆን አያጠራጥርም።

9 ይሖዋም በተመሳሳይ ስለ መንግሥቱ እውንነት ማረጋገጫ ሰጥቶናል። የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በሆነው በዕብራውያን መጽሐፍ እንደተመለከተው የሕጉ የተለያዩ ክፍሎች ለመንግሥቱ ዝግጅት ጥላ ነበሩ። (ዕብራውያን 10:​1) በተጨማሪም ምድራዊው የእስራኤል መንግሥት በአምላክ መንግሥት የሚኖረው ሁኔታ ምን እንደሚመስል ጭላንጭል ሰጥቷል። የእስራኤል መንግሥት ተራ መስተዳድር አልነበረም፤ ምክንያቱም ገዥዎቹ የተቀመጡት ‘በይሖዋ ዙፋን ላይ’ ነበር። (1 ዜና መዋዕል 29:​23) ከዚህም በላይ “ሴሎ እስኪመጣ ድረስ በትረ መንግሥት ከይሁዳ እጅ አይወጣም፣ የአዛዥም ዘንግ ከእግሮቹ መካከል፤ የሕዝቦችም መታዘዝ ለእርሱ ይሆናል።” (ዘፍጥረት 49:​10 አዓት) * አዎን፣ የአምላክ መንግሥት ዘላለማዊ ንጉሥ የሚሆነው ኢየሱስ የሚወለደው ከይሁዳ የትውልድ ሐረግ ነበር።​— ሉቃስ 1:​32, 33

10. (ሀ) የአምላክ መንግሥት መሠረት የተጣለው መቼ ነበር? (ለ) የኢየሱስ የወደፊት ተባባሪ ገዥዎች በምድር ላይ የትኛውን ሥራ በግንባር ቀደምትነት ያስፋ⁠ፋሉ?

10 የኢየሱስ ሐዋርያት በተመረጡ ጊዜ የአምላክ መሲሐዊ መንግሥት መሠረት ተጥሏል። (ኤፌሶን 2:​19, 20፤ ራእይ 21:​14) እነዚህ ሐዋርያት ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ተባባሪ ነገሥታት ሆነው ከሚገዙት 144,000 ሰዎች የመጀመሪያዎቹ ተመራጮች ናቸው። እነዚህ የወደፊት ተባባሪ ገዥዎች በምድር ላይ በሚኖሩበት ጊዜ ኢየሱስ “ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው . . . ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” በማለት የሰጠውን ትእዛዝ ለመፈጸም የምሥክርነቱን ዘመቻ በግንባር ቀደምትነት ያካሂዳሉ።​— ማቴዎስ 28:​19

11. የመንግሥቱ ስብከት ሥራ በአሁኑ ጊዜ በመከናወን ላይ የሚገኘው እንዴት ነው? ምንስ ውጤት በማስገኘት ላይ ነው?

11 ደቀ መዛሙርት አድርጉ የሚለው ትእዛዝ በአሁኑ ጊዜ ታይቶ በማያውቅ መጠን በመፈጸም ላይ ነው። የይሖዋ ምሥክሮች “ለአሕዛብ ሁሉ ምስክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፣ በዚያን ጊዜም መጨረሻው ይመጣል” ከሚለው የኢየሱስ ትንቢት ጋር በሚስማማ መንገድ በመላው ምድር ላይ ­የመንግሥቱን ምሥራች በመስበክ ላይ ናቸው። (ማቴዎስ 24:​14) ታላቅ የሆነ የትምህርት መስጫ ፕሮግራም ተዘርግቷል። ይህም የመንግሥቱ ስብከት ሥራ አንዱ ገጽታ ነው። ራሳቸውን ለአምላክ መንግሥት ሕግጋትና መሠረታዊ ሥርዓቶች ያስገዙ ሰዎች ሁሉ ሰብዓዊ መንግሥታት ሊያመጡ ያልቻሉትን ሰላምና አንድነት በማግኘት ላይ ናቸው። ይህ ሁሉ የአምላክ መንግሥት እውን ወይም ተጨባጭ መሆኑን በግልጽ የሚያረጋግጥ ማስረጃ ነው!

12. (ሀ) የመንግሥቱን ሰባኪዎች የይሖዋ ምሥክሮች ብሎ መጥራት ተገቢ የሚሆነው ለምንድን ነው? (ለ) የአምላክ መንግሥት ከሰብዓውያን መንግሥታት የሚለየው እንዴት ነው?

12 ይሖዋ ለእስራኤላውያን “እናንተ የመረጥሁትም ባሪያዬ ምስክሮቼ ናችሁ” ብሏቸዋል። (ኢሳይያስ 43:​10–12) “የታመነው ምስክር” ኢየሱስ የአምላክን መንግሥት ምሥራች በቅንዓት ሰብኳል። (ራእይ 1:​5፤ ማቴዎስ 4:​17) ስለዚህ የዘመናችን የመንግሥት ሰባኪዎች አምላክ ራሱ ባወጣው የይሖዋ ምሥክሮች በሚል ስም መጠራታቸው ተገቢ ነው። ይሁን እንጂ እነዚህ ምሥክሮች ስለ አምላክ መንግሥት ለሰዎች በመናገር ይህን ያህል ጉልበትና ጊዜ የሚያጠፉት ለምንድን ነው? የሰው ልጆች ብቸኛ ተስፋ ይህ መንግሥት ስለሆነ ነው። ሰብዓውያን መንግሥታት ፈጥነውም ይሁን ዘግይተው ሲወድቁ ታይቷል። የአምላክ መንግሥት ግን ዘላለማዊ ነው። ኢሳይያስ 9:​6, 7 የዚህ መንግሥት ገዥ የሆነውን ኢየሱስ ‘የሰላም መስፍን’ ብሎ ከጠራ በኋላ የ1980 ትርጉም “ለንጉሣዊ ሥልጣኑ ወሰን የለውም” ይላል። የአምላክ መንግሥት ዛሬ ብቅ ብለው ነገ እንደሚገለበጡት ሰብዓዊ መንግሥታት አይደለም። ዳንኤል 2:​44 “የሰማይ አምላክ ለዘላለም የማይፈርስ መንግሥት ያስነሣል፤ ለሌላ ሕዝብም የማይሰጥ መንግሥት ይሆናል . . . ለዘላለምም ትቆማለች” በማለት ሁኔታውን በትክክል ገልጾታል።

13. (ሀ) የአምላክ መንግሥት በተሳካ ሁኔታ መፍትሔ ከሚያስገኝላቸው ችግሮች አንዳንዶቹ ምንድን ናቸው? (ለ) የአምላክ ተስፋ እንደሚፈጸም እርግጠኛ ልንሆን የምንችለው ለምንድን ነው?

13 ጦርነትን፣ ወንጀልን፣ በሽታን፣ ረሀብንና ቤት የለሽነትን ማስቀረት የሚችል የትኛው ሰብዓዊ ንጉሥ ነው? የትኛውስ ምድራዊ ገዥ ነው ሙታንን ለማስነሳት የሚችለው? የአምላክ መንግሥትና የመንግሥቱ ንጉሥ ግን እነዚህን ነገሮች ያስተካክላሉ። ይህ መንግሥት ነጋ ጠባ ጥገና እንደሚፈልግ ሰንካላ መሣሪያ አይሆንም። ከዚህ ይልቅ የአምላክ መንግሥት ውጥኑ ሁሉ ይሰምርለታል። ምክንያቱም ይሖዋ “ከአፌ የሚወጣ ቃሌ እንዲሁ ይሆናል፤ የምሻውን ያደርጋል የላክሁትንም ይፈጽማል እንጂ ወደ እኔ በከንቱ አይመለስም” በማለት ቃል ገብቷል። (ኢሳይያስ 55:​11) የአምላክ ዓላማ አይከሽፍም። ይሁን እንጂ ይህ መንግሥት መግዛት መጀመር የሚኖርበት መቼ ነው?

መንግሥቱ መጀመር ያለበት መቼ ነው?

14. የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ስለ አምላክ መንግሥት ምን ያልተረዱት ነገር ነበር? ኢየሱስ ግን ስለ ራሱ አገዛዝ ምን ያውቅ ነበር?

14 “ጌታ ሆይ፣ በዚህ ወራት ለእስራኤል መንግሥትን ትመልሳለህን?” የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ያቀረቡት ይህ ጥያቄ የአምላክ ­መንግሥት ዓላማ ምን እንደሆነና መንግሥቱ መግዛት እንዲጀምር የተወሰነው ጊዜ መቼ እንደሆነ ገና ያላወቁ መሆናቸውን በግልጽ ያሳያል። ኢየሱስ ስለዚህ ጉዳይ ግምታዊ አስተሳሰብ እንዳይኖራቸው ሲያስጠነቅቃቸው “አብ በገዛ ሥልጣኑ ያደረገውን ወራትንና ዘመናትን ታውቁ ዘንድ ለእናንተ አልተሰጣችሁም” ብሏቸዋል። ኢየሱስ በምድር ላይ መግዛት የሚጀምረው ከሞት ከተነሣና ወደ ሰማይ ካረገ ከብዙ ጊዜ በኋላ እንደሆነ ያውቅ ነበር። (ሥራ 1:​6–11፤ ሉቃስ 19:​11, 12, 15) እንዲህ እንደሚሆን ቅዱሳን ጽሑፎች ቀደም ሲል አመልክተው ነበር። እንዴት?

15. መዝሙር 110:​1 የኢየሱስ አገዛዝ ስለሚጀምርበት ጊዜ ፍንጭ የሚሰጠን እንዴት ነው?

15 ንጉሥ ዳዊት ኢየሱስን በትንቢት “ጌታ” ብሎ ከጠራ በኋላ “እግዚአብሔር ጌታዬን:- ጠላቶችህን ለእግርህ መቀመጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ አለው” ብሏል። (መዝሙር 110:​1፤ ከሥራ 2:​34–36 ጋር አወዳድር።) ይህ ትንቢት ኢየሱስ ወዲያው ወደ ሰማይ እንዳረገ መግዛት እንደማይጀምር ያመለክታል። ከዚህ ይልቅ በአምላክ ቀኝ ተቀምጦ መጠበቅ ነበረበት። (ዕብራውያን 10:​12, 13) መጠበቅ የሚኖርበት እስከ መቼ ድረስ ነው? ግዛቱስ መቼ መጀመር ነበረበት? መጽሐፍ ቅዱስ የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ እንድናገኝ ይረዳናል።

16. በ607 ከዘአበ ምን ነገር ተፈጸመ? ይህስ ከአምላክ መንግሥት ጋር ምን ዝምድና አለው?

16 በመላው ምድር ላይ ከሚገኙት ከተሞች መካከል ይሖዋ ስሙን ያኖረው በኢየሩሳሌም ላይ ብቻ ነበር። (1 ነገሥት 11:​36) በተጨማሪም ይህች ከተማ የአምላክ ቀጥተኛ ድጋፍ የነበረውና ለአምላክ ሰማያዊ መንግሥት ጥላ የሆነው ምድራዊ መንግሥት ዋና ከተማ ነበረች። ስለዚህ ኢየሩሳሌም በ607 ከዘአበ በባቢሎናውያን መጥፋትዋ ትልቅ ትርጉም ነበረው። ይህ እርምጃ አምላክ ሕዝቦቹን በቀጥታ መግዛቱን የሚያቋርጥበት ረዥም ዘመን የሚጀምርበት ጊዜ ሆነ። ኢየሱስ ስድስት መቶ ዘመናት ከሚያክል ጊዜ በኋላ ይህ የአምላክ አገዛዝ የሚቋረጥበት ዘመን ገና ያላበቃ መሆኑን በማመልከት “የአሕዛብ ዘመን እስኪፈጸም ድረስ ኢየሩሳሌም በአሕዛብ የተረገጠች ትሆናለች” ብሏል።​— ሉቃስ 21:​24

17. (ሀ) “የአሕዛብ ዘመን” ምንድን ነው? ምን ያህል ጊዜስ መቆየት ነበረበት? (ለ) “የአሕዛብ ዘመን” የጀመረውና ያለቀው መቼ ነበር?

17 በ“አሕዛብ ዘመን” ውስጥ ዓለማዊ መንግሥታት የአምላክ ድጋፍ ያለው መንግሥት ጣልቃ ሳይገባባቸው እንዲገዙ ተፈቅዶላቸዋል። ይህ ዘመን የጀመረው ኢየሩሳሌም በ607 ከዘአበ ስትጠፋ ሲሆን ለ“ሰባት ዘመናት” እንደሚቀጥል ዳንኤል አመልክቷል። (ዳንኤል 4:​23–25) ይህ “ሰባት ዘመን” ምን ያህል ርዝመት ይኖረዋል? መጽሐፍ ቅዱስ ሦስት ተኩል “ዘመናት” 1,260 ቀናት እንደሆኑ ያመለክታል። (ራእይ 12:​6, 14) የዚህ እጥፍ ወይም ሰባት ዘመናት 2,520 ቀናት ይሆናሉ ማለት ነው። ይሁን እንጂ ይህ አጭር ጊዜ ሲያበቃ የተፈጸመ ልዩ ነገር አልነበረም። “አንድ ቀን ለአንድ ዓመት” የሚለውን ደንብ በዳንኤል ትንቢት ላይ ብንጠቀምበትና ከ607 ከዘአበ በመነሳት 2,520 ዓመታት ብንቆጥር ግን ወደ 1914 እዘአ እንደርሳለን።​— ዘኁልቁ 14:​34፤ ሕዝቅኤል 4:​6

18. ኢየሱስ መንግሥታዊ ሥልጣኑን እንደተቀበለ ወዲያው ምን አደረገ? ይህስ በምድር ላይ ምን ዓይነት ሁኔታ አስከተለ?

18 ታዲያ ኢየሱስ በዚህ ጊዜ በሰማይ መግዛት ጀምሯልን? መግዛት እንደ ጀመረ የሚያረጋግጡትን ቅዱስ ጽሑፋዊ ምክንያቶች በሚቀጥለው ምዕራፍ እንመለከታለን። እርግጥ ኢየሱስ መግዛት እንደጀመረ በምድር ላይ ሰላም አይሰፍንም። ኢየሱስ መንግሥቱን ከተቀበለ በኋላ ሰይጣንንና አጋንንታዊ መላእክቱን ከሰማይ እንደሚያባርር ራእይ 12:​7–12 ያመለክታል። ይህም በምድር ላይ ወዮታ ያስከትላል። ይሁን እንጂ ዲያብሎስ “ጥቂት ጊዜ” ብቻ እንደቀረው ማወቃችን ያጽናናናል። በቅርቡ የአምላክ መንግሥት መግዛት በመጀመሩ ብቻ ሳይሆን ለምድርና ታዛዥ ለሆኑ የሰው ልጆች በረከቶች የሚያመጣ በመሆኑ ጭምር ደስ ለመሰኘት እንችላለን። (መዝሙር 72:​7, 8) ይህ ነገር በቅርቡ እንደሚሆን እንዴት እናውቃለን?

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.9 ሴሎ ማለት “ባለ ቤት ወይም ባለ መብት የሆነው” ማለት ነው። ከጊዜ በኋላ “ሴሎ” “ከይሁዳ ነገድ የሆነው አንበሳ” ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑ ግልጽ ሆነ። (ራእይ 5:​5) አንዳንድ የአይሁዳውያን የአረማይክ ቋንቋ ትርጉሞች “ሴሎ” የሚለውን ቃል “መሲሑ” ወይም “መሲሑ ንጉሥ” በሚሉ ቃላት ተክተዋል።

እውቀትህን ፈትሽ

የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው? የሚገዛውስ ከየት ነው?

የመንግሥቱ ገዥ ማን ነው? ዜጎቹስ?

ይሖዋ መንግሥቱ እውን መሆኑን ያረጋገጠልን እንዴት ነው?

“የአሕዛብ ዘመን” የጀመረውና ያለቀው መቼ ነው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 94 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

ከአምላክ መንግሥት ጋር ዝምድና ያላቸው አንዳንድ ዐበይት ክንውኖች

• ይሖዋ የእባቡን የሰይጣንን ራስ የሚቀጠቅጥ “ዘር” ለማስነሳት ያለውን ዓላማ አስታወቀ።​— ዘፍጥረት 3:​15

• በ1943 ከዘአበ ይሖዋ ይህ “ዘር” ከአብርሃም የትውልድ ሐረግ የሚወለድ ሰው እንደሚሆን አመለከተ።​— ዘፍጥረት 12:​1–3, 7፤ 22:⁠18

• በ1513 ከዘአበ ለእስራኤላውያን የተሰጠው የሕግ ቃል ኪዳን “ሊመጣ ላለው በጎ ነገር” ጥላ ሆነ።​— ዘጸአት 24:​6–8፤ ዕብራውያን 10:​1

• ምድራዊው የእስራኤል መንግሥት በ1117 ከዘአበ ተቋቁሞ በዳዊት የዘር ሐረግ እየተላለፈ ቆየ።​— 1 ሳሙኤል 11:​15፤ 2 ሳሙኤል 7:​8, 16

• ኢየሩሳሌም በ607 ከዘአበ ጠፋች፣ “የአሕዛብ ዘመን” ጀመረ።​— 2 ነገሥት 25:​8–10, 25, 26፤ ሉቃስ 21:​24

• በ29 እዘአ ኢየሱስ እጩ ንጉሥ ሆኖ ከተቀባ በኋላ ምድራዊ አገልግሎቱን ጀመረ።​— ማቴዎስ 3:​16, 17፤ 4:​17፤ 21:​9–11

• በ33 እዘአ ኢየሱስ ወደ ሰማይ አረገ። በዚያም በአምላክ ቀኝ ተቀምጦ ግዛቱ የሚጀምርበትን ጊዜ መጠባበቅ ጀመረ።​— ሥራ 5:​30, 31፤ ዕብራውያን 10:​12, 13

• በ1914 እዘአ “የአሕዛብ ዘመን” ሲፈጸም ኢየሱስ የሰማያዊው መንግሥት ንጉሥ ሆኖ መግዛት ጀመረ።​— ራእይ 11:​15

• ሰይጣንና አጋንንቱ ወደ ምድር አካባቢ ተጥለው በሰው ልጆች ላይ ተጨማሪ ወዮታ ማምጣት ጀመሩ።​— ራእይ 12:​9–12

• ኢየሱስ በዓለም ዙሪያ የሚካሄደውን የአምላክ መንግሥት ­ምሥራች ስብከት በበላይነት ይቆጣጠራል።​— ማቴዎስ 24:​14፤ 28:​19, 20