በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የወደፊት ሕይወትህ አስደሳች ሊሆን ይችላል!

የወደፊት ሕይወትህ አስደሳች ሊሆን ይችላል!

ምዕራፍ 1

የወደፊት ሕይወትህ አስደሳች ሊሆን ይችላል!

1, 2. ፈጣሪ ምን እንድታገኝ ይፈልጋል?

የምትወደው ሰው በናፍቆት እቅፍ አድርጎ ሲስምህ፣ ከምትወዳቸው ሰዎች ጋር ሆነህ ጥሩ ምግብ ከበላህ በኋላ ከልብህ ስትስቅ፣ ልጆችህ ደስ ብሏቸው ሲቦርቁ በዓይነ ሕሊናህ ተመልከት። እነዚህን የመሰሉት አስደሳች ጊዜያት በጥሩ ትዝታ የሚታወሱ የሕይወት ክፍል ናቸው። ለብዙ ሰዎች ግን ሕይወት የተለያዩ ችግሮች መፈራረቂያ ሆኖባቸዋል። የአንተም ሕይወት ይህን የመሰለ ከነበረ ተስፋ አት ቁረጥ።

2 በጣም በተመቻቸና አስደናቂ በሆነ አካባቢ ዘላቂ ደስታ አግኝተህ እንድትኖር የአምላክ ፈቃድ ነው። ይህን አስደሳች የወደፊት ሕይወት የሚያስገኘውን ቁልፍ አምላክ ራሱ ስለሚሰጥህ የሕልም እንጀራ ሆኖ የሚቀር ምኞት አይደለም። ይህም ቁልፍ እውቀት ነው።

3. የደስታ ቁልፍ የሆነው እውቀት የትኛው ነው? አምላክስ ይህን እውቀት ይሰጠናል ብለን እርግጠኛ ለመሆን የምንችለው ለምንድን ነው?

3 እውቀት ስንል ከሰው ልጆች ጥበብ እጅግ ስለሚልቅ ልዩ ዓይነት እውቀት መናገራችን ነው። ይህ እውቀት “የአምላክ እውቀት” ነው። (ምሳሌ 2:​5) አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊ የዛሬ 2,000 ዓመት ገደማ “እያንዳንዱ ቤት በአንድ ሰው ተዘጋጅቶአልና፣ ሁሉን ያዘጋጀ ግን እግዚአብሔር ነው” ብሎ ነበር። (ዕብራውያን 3:​4) ሁሉን ነገር የፈጠረው አምላክ ምን ያህል ሰፊ እውቀት እንደሚኖረው ገምት! መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ ከዋክብትን በሙሉ እንደሚቆጥርና በየስማቸውም እንደሚጠራቸው ይናገራል። በእኛ ጋላክሲ ውስጥ ብቻ በመቶ ቢልዮን የሚቆጠሩ ከዋክብት ስላሉና የሥነ ፈለክ ተመራማሪዎች እንደሚሉት አንድ መቶ ቢልዮን የሚያክሉ ሌሎች ጋላክሲዎች ስለሚገኙ አምላክ እነዚህን ሁሉ በስም የሚያውቃቸው መሆኑን ማሰብ እንኳን በጣም ይከብዳል! (መዝሙር 147:​4) በተጨማሪም አምላክ ስለ እያንዳንዳችን ጠንቅቆ ያውቃል። ታዲያ ዐበይት ስለሆኑት የሕይወት ጥያቄዎች ከአምላክ የተሻለ መልስ ሊሰጠን የሚችል ማን ይኖራል?​— ማቴዎስ 10:​30

4. አምላክ የሚመራንን እውቀት ይሰጠናል ብለን መጠበቅ የምንችለው ለምንድን ነው? ይህንንስ እንድናገኝ የሚያስችለን የትኛው መጽሐፍ ነው?

4 መኪናቸውን ለመጠገን የሚሞክሩ ሁለት ሰዎችን በዓይነ ሕሊናህ ተመልከት። አንደኛው ሰውዬ ጥገናው ስላልተሳካለት ተበሳጭቶ መሣሪያዎቹን ይወረውራል። ሌላኛው ግን ረጋ ብሎ የመኪናውን ጉድለት ካስተካከለ በኋላ ቁልፉን ከፍቶ ሞተሩን ያስነሳና ሞተሩ አላንዳች ችግር ሲሠራ በፈገግታ ይመለከታል። ከእነዚህ ሁለት ሰዎች መካከል የፋብሪካው የጥገና መመሪያ መጽሐፍ የነበረው የትኛው እንደሆነ ለመገመት ብዙ ማሰብ አያስፈልግህም። ታዲያ አምላክስ ለሕይወታችን የሚያስፈልገንን መመሪያ ይሰጠናል ብለን ብናስብ ምክንያታዊ አይሆንምን? መጽሐፍ ቅዱስ ከፈጣሪያችን ትምህርትና መመሪያ እንድናገኝበት እንዲሁም አምላክ የሚሰጠውን እውቀት እንድንቀስምበት ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን ራሱ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገር ታውቅ ይሆናል።​— 2 ጢሞቴዎስ 3:​16

5. መጽሐፍ ቅዱስ የያዘው እውቀት ምን ያህል ዋጋ ያለው ነው?

5 መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ራሱ የሚናገረው ይህ አባባል እውነት ከሆነ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ምን ያህል የእውቀት ክምችት ሊኖር እንደሚችል ገምት! በምሳሌ 2:​1–5 ላይ እውቀትን እንድንፈልግ፣ እንደተቀበረ ውድ ሀብትም ቆፍረን እንድናወጣ ተመክረናል። ይህን እውቀት ቆፍረን የምናወጣው ግን ከሰው ልጆች አእምሮ ሳይሆን ከአምላክ ቃል ውስጥ ነው። አጥብቀን ብንፈላልግ “የአምላክን እውቀት” እናገኛለን። አምላክ የአቅማችንን ውስንነትና ምን ነገሮች እንደሚያስፈልጉን ስለሚያውቅ ሰላማዊና ደስተኛ ኑሮ እንድንኖር የሚያስችለንን መመሪያ ይሰጠናል። (መዝሙር 103:​14፤ ኢሳይያስ 48:​17) ከዚህም በላይ አምላክ ከሚሰጠው እውቀት በደስታ የሚያስፈነድቅ ምሥራች እናገኛለን።

የዘላለም ሕይወት!

6. ኢየሱስ ክርስቶስ ከአምላክ ስለሚገኘው እውቀት ምን ዋስትና ሰጥቷል?

6 በታሪክ በጣም ታዋቂ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ስለዚህኛው ከአምላክ የሚገኝ የእውቀት ዘርፍ በግልጽ ተናግሯል። “የዘላለም ሕይወትም፣ ብቻህን እውነተኛ አምላክ የሆንከውን አንተንና የላክኸውን ኢየሱስ ክርስቶስን ማወቅ ነው” ብሏል። (ዮሐንስ 17:​31980 ትርጉም፤ ፊደላቱን ጋደል አድርገን የጻፍናቸው እኛ ነን።) እስቲ ቆም ብለህ አስብ። ወደ ዘላለም ሕይወት የሚመራ እውቀት ማግኘት ይቻላል!

7. አምላክ እንድንሞት ዓላማው እንዳልነበረ የሚያረጋግጥልን ምን ማስረጃ አለ?

7 ሊሆን የማይችል ከንቱ ሕልም ነው ብለህ ይህን የዘላለም ሕይወት ተስፋ ከአእምሮህ ለማውጣት አትቸኩል። ከዚህ ይልቅ የሰው አካል የተሠራበትን ሁኔታ ተመልከት። አካላችን ለመቅመስ፣ ለመስማት፣ ለማሽተት፣ ለማየትና ለመዳሰስ እንዲችል ተደርጎ በአስደናቂ ንድፍ የተሠራ ነው። በዚህች ምድር ላይ የስሜት ሕዋሳቶቻችንን የሚያረኩልን ብዙ ነገሮች አሉ። ጣፋጭ ምግብ፣ የሚጥም ዜማ ያለው የአእዋፍ ዝማሬ፣ የአበቦች መዓዛ፣ በጣም ውብ የሆኑ አካባቢዎች፣ ደስ የሚያሰኙ ጓደኞች ከእነዚህ አንዳንዶቹ ናቸው። እንደነዚህ ያሉትን ነገሮች እንድናጣጥምና በእነርሱም እንድንደሰት የሚያስችለን አንጎላችን ደግሞ በጣም የሚያስደንቅ ሲሆን እጅግ ኃይለኛ የሆነው ኮምፒዩተር እንኳን አይተካከለውም። ፈጣሪያችን እነዚህን ነገሮች ሁሉ ጥለን እንድንሞት የሚፈልግ ይመስልሃል? በደስታ እንድንኖርና የዘላለም ሕይወት እንድናገኝ ይፈልጋል ብለን ብንደመድም ይበልጥ ምክንያታዊ አይሆንም? አምላክ የሚሰጠው እውቀት ይህን የዘላለም ሕይወት ሊያስጨብጥህ ይችላል።

ሕይወት በገነት ውስጥ

8. መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሰው ልጅ የወደፊት ኑሮ ምን ይላል?

8 መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ የምድርና የሰው ልጆች ሁኔታ የሚሰጠውን መግለጫ “ገነት!” በሚል አንድ ቃል ማጠቃለል ይቻላል። ኢየሱስ ክርስቶስ በሞት ጣር ላይ ለሚገኝ አንድ ሰው “ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ” በማለት ስለዚህ ገነት ተናግሯል። (ሉቃስ 23:​43) ይህ ሰው ገነት የሚለውን ቃል ሲሰማ የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን አዳምና ሔዋን የነበሩበትን አስደሳች ሁኔታ ሳያስታውስ አልቀረም። አዳምና ሔዋን አምላክ ሲፈጥራቸው ፍጹማን የነበሩ ከመሆናቸውም በላይ አምላክ በተከለውና ባዘጋጀው የአትክልት ሥፍራ ውስጥ ይኖሩ ነበር። ኤደን የሚለው ቃል ደስታን የሚያመለክት ስለሆነ ይህ ሥፍራ የኤደን አትክልት ቦታ ተብሎ መጠራቱ ተገቢ ነበር።

9. በመጀመሪያዋ ገነት ውስጥ ኑሮ ምን ይመስል ነበር?

9 ይህ የአትክልት ሥፍራ እንዴት የሚያስደስት ነበር! እውነተኛ ገነት ነበር። ከሚያምሩት ዛፎቹ መካከል ጣፋጭ ፍሬ የሚያፈሩ ዛፎች ነበሩ። አዳምና ሔዋን ግዛታቸውን ተዘዋውረው ሲመለከቱ፣ ከጣፋጭ ውኃዎቹ ሲጠጡና ከዛፎቹ ፍራፍሬ ሲለቅሙ ስለ ወደፊቱ ጊዜ የሚጨነቁበት ወይም የሚሰጉበት አንዳች ምክንያት አላጋጠማቸውም። አምላክ እንስሳት እንኳን ለአዳምና ለሚስቱ በፍቅር እንዲገዙ አድርጎ ስለነበረ አራዊትን የሚፈሩበት ምክንያት አልነበራቸውም። በተጨማሪም የመጀመሪያዎቹ ባልና ሚስት ሙሉ ጤንነት ነበራቸው። አምላክን እስከታዘዙ ድረስ ደስታ የሞላበት ዘላለማዊ ሕይወት ከፊታቸው ተዘርግቶላቸው ነበር። አስደናቂ የሆነውን ገነታዊ መኖሪያቸውን የመንከባከብና የማበጀት አርኪ ሥራ ተሰጥቷቸው ነበር። ከዚህም በላይ አምላክ ለአዳምና ሔዋን ‘ምድርን የመሙላትና የመግዛት’ ሥልጣን ሰጥቷል። እነርሱና ልጆቻቸው መላዋ ምድር ውበትና ደስታ የሰፈነባት እስክትሆን ድረስ የገነትን ወሰን በሁሉም አቅጣጫ ማስፋት ነበረባቸው።​— ዘፍጥረት 1:​28

10. ኢየሱስ ስለ ገነት በተናገረ ጊዜ በአእምሮው ውስጥ ይዞት የነበረው ነገር ምንድን ነው?

10 ይሁን እንጂ ኢየሱስ ገነትን በጠቀሰ ጊዜ ይህ ሊሞት የተቃረበ ሰው በጥንት ዘመን ስለነበረችው ገነት እንዲያስብ መጠየቁ አልነበረም። ኢየሱስ ስለመጪው ጊዜ መናገሩ ነበር። መኖሪያችን የሆነችው መላዋ ምድር ገነት እንደምትሆን ያውቅ ነበር። አምላክም ይህን በማድረግ ለሰው ልጆችና ለምድራችን የነበረውን የመጀመሪያ ዓላማ ፍጻሜ ላይ ያደርሳል። (ኢሳይያስ 55:​10, 11) አዎን፣ ገነት ዳግመኛ ትቋቋማለች! ታዲያ ይህች ገነት ምን ዓይነት ቦታ ትሆናለች? የአምላክ ቃል መጽሐፍ ቅዱስ መልሱን ይስጠን።

ወደፊት በምትቋቋመው ገነት ውስጥ የሚኖረው ሕይወት

11. ዳግመኛ በምትቋቋመው ገነት ውስጥ በሽታ፣ እርጅናና ሞት ምን ይሆናሉ?

11 በሽታ፣ እርጅናና ሞት አይኖሩም። “በዚያን ጊዜም የዕውሮች ዓይን ይገለጣል የደንቆሮችም ጆሮ ይከፈታል። በዚያን ጊዜ አንካሳ እንደ ሚዳቋ ይዘልላል፣ የድዳም መላስ ይዘምራል።” (ኢሳይያስ 35:​5, 6) “እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ [ከሰው ልጆች] ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤ እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፣ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፣ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፣ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና።”​— ራእይ 21:​3, 4

12. ወደፊት በምትቋቋመው ገነት ውስጥ ወንጀል፣ ዓመፅና ክፋት እንደማይኖር እርግጠኛ ልንሆን የምንችለው ለምንድን ነው?

12 ወንጀል፣ ዓመፅና ክፋት ለዘላለም ይወገዳሉ። “ክፉ አድራጊዎች ይጠፋሉና፤ . . . ገና ጥቂት፣ ኃጢአተኛም አይኖርም፤ . . . ገሮች ግን ምድርን ይወርሳሉ፣ በብዙም ሰላም ደስ ይላቸዋል።” (መዝሙር 37:​9–11) “ኀጥአን ግን ከምድር ይጠፋሉ፣ ዓመፀኞችም ከእርስዋ ይነጠቃሉ።”​— ምሳሌ 2:​22

13. አምላክ ሰላም እንዲሰፍን የሚያደርገው እንዴት ነው?

13 ሰላም በምድር ላይ ከዳር እስከ ዳር ይሰፍናል። አምላክ “እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ጦርነትን ይሽራል፤ ቀስትን ይሰብራል፣ ጦርንም ይቆርጣል።” (መዝሙር 46:​9) “ጽድቅ ያብባል፣ ጨረቃም እስኪያልፍ ድረስ ሰላም ብዙ ነው።”​— መዝሙር 72:​7

14, 15. መጽሐፍ ቅዱስ እንደገና በምትቋቋመው ገነት ውስጥ ስለሚኖረው የመኖሪያ ቤት፣ የሥራና የምግብ ሁኔታ ምን ይናገራል?

14 መኖሪያ ቤት የማጣት ሥጋት አይኖርም፤ የሚያረካ ሥራም ይኖራል። “ቤቶችንም ይሠራሉ ይቀመጡባቸውማል፤ . . . ሌላ እንዲቀመጥበት አይሠሩም፣ ሌላም እንዲበላው አይተክሉም፤ የሕዝቤ ዕድሜ እንደ ዛፍ ዕድሜ ይሆናልና፣ እኔም የመረጥኋቸው በእጃቸው ሥራ ረጅም ዘመን ደስ ይላቸዋልና። . . . በከንቱ አይደክሙም ለጥፋትም አይወልዱም።”​— ኢሳይያስ 65:​21–23

15 ጤንነት የሚገነባ ምግብ ይትረፈረፋል። “በምድሩ ላይ በቂ እህል ይኑር፤ ተራራዎች በሰብል ይሸፈኑ።” (መዝሙር 72:​161980 ትርጉም) “በዚያን ጊዜ ምድር ብዙ ፍሬ ትሰጣለች፤ እግዚአብሔር አምላካችን ይባርከናል።”​— መዝሙር 67:​61980 ትርጉም

16. በገነት ውስጥ መኖር በጣም አስደሳች የሚሆነው ለምንድን ነው?

16 ገነት በምትሆነው ምድር ላይ የሚገኘው ሕይወት በጣም አስደሳች ይሆናል። “ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ፣ በእርስዋም ለዘላለም ይኖራሉ።” (መዝሙር 37:​29) “ምድረ በዳውና ደረቁ ምድር ደስ ይላቸዋል፣ በረሀውም ሐሴት ያደርጋል እንደ ጽጌ ረዳም ያብባል።”​— ኢሳይያስ 35:​1

እውቀትና የወደፊት ሕይወትህ

17. (ሀ) በገነት ውስጥ መኖሩ የሚማርክህ ከሆነ ምን ማድረግ ይኖርብሃል? (ለ) አምላክ በምድር ላይ ታላቅ ለውጥ እንደሚያመጣ እንዴት ልናውቅ እንችላ⁠ለን?

17 በገነት ለመኖር የምትመኝ ከሆነ አምላክ የሰጠንን እውቀት እንዳትቀስም ምንም ነገር እንዲያግድህ አትፍቀድ። አምላክ የሰው ልጆችን ስለሚወድ ምድርን ገነት ለማድረግ የሚያስፈልጉትን ለውጦች ያመጣል። ሌላው ይቅርና አንተ እንኳን በአሁኑ ጊዜ በዓለም ላይ ተስፋፍቶ የሚገኘውን ችግርና የፍትሕ መዛባት ለማጥፋት ኃይል ቢኖርህ ዝም ብለህ ትመለከት ነበር? ታዲያ አምላክ ከዚህ ያነሰ ነገር ያደርጋል ብለን ልንጠብቅ እንችላለን? እንዲያውም መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ ይህን በችግር ተወጥሮ የተያዘ ሥርዓት አስወግዶ ፍጹም የሆነ የጽድቅ አገዛዝ የሚተካበት ጊዜ እንደሚመጣ በግልጽ ይናገራል። (ዳንኤል 2:​44) ይሁን እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ ስለዚህ ጊዜ በመናገር ብቻ አያበቃም። እንዴት ከጥፋቱ በሕይወት ተርፈን አምላክ ወደሚያመጣው አዲስ ዓለም መግባት እንደምንችል ጭምር ይነግረናል።​— 2 ጴጥሮስ 3:​13፤ 1 ዮሐንስ 2:​17

18. አምላክ የሚሰጠው እውቀት በአሁኑ ጊዜም ቢሆን ምን ሊያስገኝልህ ይች⁠ላል?

18 አምላክ የሚሰጠው እውቀት በአሁኑ ጊዜም ቢሆን ብዙ ጥቅም ሊያስገኝልህ ይችላል። ስለ ሕይወት የሚጠየቁ በጣም ጥልቅና እረፍት የሚነሱ ጥያቄዎች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ መልስ አግኝተዋል። መጽሐፍ ቅዱስ የሚጠቁምልህን አቅጣጫ መከተልህ ከአምላክ ጋር ወዳጅነት እንድትመሠርት ያስችልሃል። ይህ ደግሞ በጣም ታላቅ መብት ነው! አምላክ ብቻ የሚሰጠው ሰላም እንድታገኝ ያስችልሃል። (ሮሜ 15:​13, 33) ይህን ለሕይወት የግድ አስፈላጊ የሆነ እውቀት መቅሰም መጀመርህ በሕይወትህ በሙሉ ካደረግሃቸው ነገሮች በጠቅላላ የሚበልጥ ታላቅ እርምጃ ነው። ወደ ዘላለም ሕይወት የሚመራውን የአምላክ እውቀት ለማግኘት በመነሳሳትህ ፈጽሞ አትጸጸትም።

19. በሚቀጥለው ምዕራፍ የምንወያየው ስለ የትኛው ጥያቄ ነው?

19 መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ የገለጸው እውቀት የሚገኝበት መጽሐፍ እንደሆነ ጠቅሰናል። ይሁን እንጂ ይህ መጽሐፍ በሰዎች ጥበብ ላይ የተመሠረተ እንዳልሆነና የሰው አእምሮ ሊያመነጭ የማይችለው ታላቅ መጽሐፍ መሆኑን እንዴት እናውቃለን? ይህን ጥያቄ በሚቀጥለው ምዕራፍ እንመረምራለን።

እውቀትህን ፈትሽ

ከአምላክ የሚገኝ እውቀት ዘላለማዊ ወደሆነ ደስታ ሊያስገባህ የሚችለው ለምንድን ነው?

በመጪው ምድራዊ ገነት ውስጥ የሚኖረው ሕይወት ምን ዓይነት ይሆናል?

በአሁኑ ጊዜ እንኳን አምላክ የሚሰጠውን እውቀት በመቅሰም ምን ጥቅም ልታገኝ ትችላለህ?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]