በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፍል 8

ከሐሰት ሃይማኖት ራቅ፤ እውነተኛውን ሃይማኖት ያዝ

ከሐሰት ሃይማኖት ራቅ፤ እውነተኛውን ሃይማኖት ያዝ

1. አምልኮን በተመለከተ በዛሬው ጊዜ ሰዎች የትኛውን ምርጫ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል?

ኢየሱስ “ከእኔ ጎን ያልቆመ ሁሉ ይቃወመኛል” ብሏል። (ማቴዎስ 12:30) ከይሖዋ ጎን ካልቆምን ከሰይጣን ጎን መሰለፋችን አይቀርም። አብዛኞቹ ሰዎች አምላክን ተቀባይነት ባለው መንገድ እያገለገሉ እንዳለ ያስባሉ፤ መጽሐፍ ቅዱስ ግን ሰይጣን “መላውን ዓለም እያሳሳተ” እንዳለ ይናገራል። (ራእይ 12:9) በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች አምላክን እያመለኩ እንደሆነ ይሰማቸዋል፤ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን የሚያገለግሉት ሰይጣን ዲያብሎስን ነው! በዛሬው ጊዜ ያሉ ሰዎች አንድ ዓይነት ምርጫ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፦ “የእውነት አምላክ” የሆነውን ይሖዋን ወይም “የውሸት አባት” የሆነውን ሰይጣንን ከማገልገል አንዱን መምረጣቸው የግድ ነው።—መዝሙር 31:5፤ ዮሐንስ 8:44

ከሐሰት ሃይማኖት ውጣ

2. ሰይጣን፣ ሰዎች ይሖዋን እንዳያመልኩ ለማድረግ ከሚሞክርባቸው መንገዶች አንዱ ምንድን ነው?

2 ይሖዋን ለማገልገል መወሰን ጥበብ ያዘለ ምርጫ ነው፤ ምክንያቱም ይህ ውሳኔ የአምላክን ሞገስ ያስገኛል። ይሁን እንጂ ሰይጣን፣ አምላክን በሚያገለግሉ ሰዎች አይደሰትም፤ ስለሆነም በእንዲህ ዓይነት ሰዎች ላይ ችግር እንዲደርስባቸው ያደርጋል። ሰይጣን ይህን ከሚያደርግባቸው መንገዶች አንዱ ወዳጆቻቸውንና የቅርብ ቤተሰቦቻቸውን ጨምሮ ሰዎች እንዲያፌዙባቸው ወይም እንዲቃወሟቸው ማድረግ ነው። ኢየሱስ “በእርግጥም የሰው ጠላቶቹ የገዛ ቤተሰቦቹ ይሆናሉ” በማለት አስጠንቅቋል።—ማቴዎስ 10:36

3. የቤተሰብህ አባላት ወይም ወዳጆችህ አምላክን እንዳታመልክ ቢቃወሙህ ምን ታደርጋለህ?

3 እንዲህ ያለ ነገር ቢያጋጥምህ ምን ታደርጋለህ? ብዙ ሰዎች የሚከተሉት ሃይማኖት ስህተት እንደሆነ ያውቃሉ፤ ያም ቢሆን ሃይማኖታቸውን ለመተው ያመነታሉ። ሃይማኖታቸውን መተዋቸው ለቤተሰባቸው ያላቸውን ታማኝነት ማጉደል እንደሆነ ይሰማቸዋል። እንዲህ ብሎ ማሰብ ምክንያታዊ ነው? አንድ የቤተሰብህ አባል አደገኛ ዕፅ እንደሚወስድ ብታውቅ የሚወስደው ዕፅ ጉዳት እንደሚያስከትልበት በመግለጽ ታስጠነቅቀዋለህ እንጂ አብረኸው ዕፅ እንደማትወስድ የታወቀ ነው።

4. ኢያሱ በዘመኑ ይካሄድ ስለነበረው አምልኮ እስራኤላውያንን ምን ብሏቸው ነበር?

4 ኢያሱ፣ እስራኤላውያን የአባቶቻቸውን የተሳሳቱ ሃይማኖታዊ ልማዶችና ወጎች እንዲተዉ አሳስቦ ነበር። “ይሖዋን ፍሩ፤ በንጹሕ አቋምና በታማኝነትም አገልግሉት፤ አባቶቻችሁ ከወንዙ ማዶና በግብፅ ምድር ያገለገሏቸውን አማልክት አስወግዱ፤ ይሖዋን አገልግሉ” ብሏቸዋል። (ኢያሱ 24:14) ኢያሱ ለይሖዋ ታማኝ ነበር፤ ይሖዋም ባርኮታል። እኛም ለይሖዋ ታማኝ ብንሆን ይባርከናል።—2 ሳሙኤል 22:26

ለሐሰት አምልኮ ትጠቀምባቸው የነበሩ ቁሳቁሶችን አስወግድ

5. ምትሃታዊ ኃይል እንዳላቸው ተደርገው የሚቆጠሩ ቁሳቁሶችን ማስወገድ የሚኖርብን ለምንድን ነው?

5 ከሐሰት ሃይማኖት ነፃ መውጣት፣ እንደ ክታብ ወይም ድግምት እንደተደረገበት ቀለበትና አምባር ያሉ ምትሃታዊ ኃይል እንዳላቸው ተደርገው የሚቆጠሩ ቁሳቁሶችን በሙሉ ማስወገድን ይጨምራል። እንዲህ ማድረጋችን በጣም አስፈላጊ ነው፤ ምክንያቱም በይሖዋ ላይ ሙሉ በሙሉ እንደምንታመን ያሳያል።

6. አንዳንድ የጥንት ክርስቲያኖች የጥንቆላ መጽሐፎቻቸውን ምን አድርገው ነበር?

6 አንዳንድ የጥንት ክርስቲያኖች እውነተኛውን ሃይማኖት ለመከተል ሲወስኑ ምን እንዳደረጉ ተመልከት። መጽሐፍ ቅዱስ “አስማት ይሠሩ ከነበሩት መካከል ብዙዎች መጽሐፎቻቸውን አንድ ላይ ሰብስበው በማምጣት በሰው ሁሉ ፊት አቃጠሉ” በማለት ይናገራል።—የሐዋርያት ሥራ 19:19

7. አጋንንት ጥቃት የሚሰነዝሩብን ከሆነ ምን ማድረግ እንችላለን?

7 የጥንቆላና የአስማት ድርጊቶችን ይፈጽሙ የነበሩ አንዳንድ ሰዎች ይሖዋን ማገልገል ሲጀምሩ ከአጋንንት ጥቃት ሊሰነዘርባቸው ይችላል። እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ካጋጠመህ የይሖዋን ስም ጮክ ብለህ በመጥራት ጸልይ። እሱም ይረዳሃል።—ምሳሌ 18:10፤ ያዕቆብ 4:7

8. ክርስቲያኖች ከሐሰት አምልኮ ጋር የተያያዙ ሥዕሎችን፣ ምስሎችንና ጣዖታትን በተመለከተ ምን ዓይነት አመለካከት አላቸው?

8 ይሖዋን ለማገልገል የሚፈልጉ ሁሉ ከሐሰት አምልኮ ጋር የተያያዘ ማንኛውንም ዓይነት ሥዕል፣ ምስል ወይም ጣዖት ማስወገድ ይኖርባቸዋል። እውነተኛ ክርስቲያኖች የሚመላለሱት “በእምነት እንጂ በማየት አይደለም።” (2 ቆሮንቶስ 5:7) ማንኛውንም ዓይነት ምስል ለአምልኮ መጠቀምን የሚከለክለውን የአምላክን ሕግ ያከብራሉ።—ዘፀአት 20:4, 5

ከይሖዋ ሕዝቦች ጋር ተቀራረብ

9. መጽሐፍ ቅዱስ፣ ጥበበኛ ስለ መሆን ምን ምክር ይሰጣል?

9 መጽሐፍ ቅዱስ “ከጥበበኞች ጋር የሚሄድ ጥበበኛ ይሆናል” ይላል። (ምሳሌ 13:20) ጥበበኛ መሆን ከፈለግን ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መሄድ ወይም መቀራረብ ያስፈልገናል። ወደ ዘላለም ሕይወት በሚወስደው መንገድ ላይ እየተጓዙ ያሉት እነሱ ናቸው።—ማቴዎስ 7:14

10. የይሖዋ ምሥክሮች አምላክን እንድታገለግል ሊረዱህ የሚችሉት እንዴት ነው?

10 የይሖዋ ምሥክሮች ለሰዎች ከልብ ያስባሉ። የዘላለም ሕይወት ለማግኘት የሚያስችለውን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ቅን ልብ ላላቸው ሰዎች ያስተምራሉ። ለአንተም መጽሐፍ ቅዱስን ያለምንም ክፍያ ሊያስተምሩህ ይችላሉ። ለጥያቄዎችህ መልስ ይሰጡሃል፤ እንዲሁም የመጽሐፍ ቅዱስን እውቀት በሕይወትህ ተግባራዊ ማድረግ የምትችለው እንዴት እንደሆነ እንድታውቅ ይረዱሃል።—ዮሐንስ 17:3

11. ክርስቲያናዊ ስብሰባዎች የሚረዱህ እንዴት ነው?

11 አብዛኛውን ጊዜ በመንግሥት አዳራሾች ውስጥ በሚደረጉት የይሖዋ ምሥክሮች ስብሰባዎች ላይ ስለ ይሖዋ መንገዶች ተጨማሪ እውቀት ታገኛለህ። የምታገኘው እውቀት እውነተኛውን ሃይማኖት ለመከተል ያደረግከውን ውሳኔ ይበልጥ ያጠናክርልሃል። በተጨማሪም ለሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ለማስተማር የሚያስችል ሥልጠና ታገኛለህ።—ዕብራውያን 10:24, 25

12. ጸሎት አምላክን እንድታገለግል የሚረዳህ እንዴት ነው?

12 ስለ ይሖዋ ዓላማና ፈቃድ ይበልጥ ባወቅክ መጠን ፍቅር ስለሚንጸባረቅባቸው መንገዶቹ ያለህ ግንዛቤና አድናቆት እየጨመረ መሄዱ አይቀርም። በተጨማሪም ይሖዋን የሚያስደስተውን ነገር ለማድረግና እሱን ከሚያሳዝነው ነገር ለመራቅ ያለህ ፍላጎት ይጨምራል። ትክክል የሆነውን ነገር ማድረግና ስህተት ከሆነው ነገር መራቅ ትችል ዘንድ እንዲረዳህ ይሖዋን በጸሎት መጠየቅ እንደምትችል አስታውስ።—1 ቆሮንቶስ 6:9, 10፤ ፊልጵስዩስ 4:6

እውነተኛውን ሃይማኖት መከተል የምትችለው እንዴት ነው?

13. የይሖዋን ልብ ማስደሰት የምትችለው እንዴት ነው?

13 በመንፈሳዊ እያደግክ ስትሄድ፣ ራስህን ለአምላክ ወስነህ በመጠመቅ የይሖዋ ምሥክር መሆን እንደሚያስፈልግህ መገንዘብህ አይቀርም። የይሖዋ ምሥክር ስትሆን ደግሞ የይሖዋን ልብ ታስደስታለህ። (ምሳሌ 27:11) አምላክ “በመካከላቸው እኖራለሁ፤ ከእነሱም ጋር እሄዳለሁ፤ እኔ አምላካቸው እሆናለሁ፣ እነሱ ደግሞ ሕዝቤ ይሆናሉ” በማለት ከተናገረላቸው ደስተኛ ሕዝቦች አንዱ ትሆናለህ።—2 ቆሮንቶስ 6:16