በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ተግሣጽን የምትመለከተው እንዴት ነው?

ተግሣጽን የምትመለከተው እንዴት ነው?

ምዕራፍ 13

ተግሣጽን የምትመለከተው እንዴት ነው?

1–4. (ሀ) ሁላችንም ስሕተት ማድረግ የሚቀናን ለምንድን ነው? (ለ) ከእውቀት ጉድለት ሌላ ስሕተቶችን እንድንፈጽም የሚያደርገን ሌላው ነገር ምንድን ነው?

ተሳስቻለሁ ወይም አጥፍቻለሁ ብሎ መናገርን ፈጽሞ የማይወድ የክፍልህ ተማሪ ወይም አስተማሪ ታውቅ ይሆናል። እንደዚህ ስላለው ሰው ምን ይሰማሃል? አንድ ቀን መጥቶ “ይቅርታ አድርግልኝ፣ ተሳስቼ እንደነበር አሁን ተረድቻለሁ” ቢልህ ለእርሱ ያለህ ግምት ከፍ ይላል ወይስ ዝቅ ይላል?

2 ሁላችንም ስሕተት እንሠራለን፤ አይደለም እንዴ? ማናችንም ብንሆን ፍጹም ወይም እንከን የለሽ አይደለንም። መጽሐፍ ቅዱስም ይህንኑ ይነግረናል። በመጀመሪያው አባታችን በአዳም አለመታዘዝ ምክንያት ሁሉም ሰዎች አለፍጽምናን ይኸውም ኃጢአትን ወርሰው እንደሚወለዱ ይገልጽልናል። መጽሐፍ ቅዱስ “ስለዚህ ምክንያት ኃጢአት በአንድ ሰው [በአዳም] ወደ ዓለም ገባ፤ በኃጢአትም ሞት፤ እንዲሁም ሁሉ ኃጢአት ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ” በማለት ያስረዳል። — ሮሜ 5:12

3 አንዳንድ ስሕተቶች የሚደረጉት ‘ባለማወቅ’ ነው፤ ይሁን እንጂ ሁሉም ስሕተቶች የሚፈጸሙት በዚህ ምክንያት አይደለም። ብዙ ስሕተቶች የሚፈጸሙት በግዴለሽነት ነው። ለምሳሌ ያህል በአይሮፕላን የሚጓዝ መንገደኛ አስተናጋጅዋ ስለ መንሳፈፊያ ጃኬቶች አጠቃቀም ወይም ስለ አይሮፕላኑ የኦክስጂን አቅርቦት ስትገልጽ ትኩረት ሰጥቶ አላዳመጠ ይሆናል። በዚህ ምክንያት በአደጋ ጊዜ መንገደኛው በእነዚህ ዝግጅቶች ሳይጠቀም ቢቀርና ሕይወቱን ቢያጣ ስላላወቀ ነው ለማለት አይቻልም። ከዚህ ይልቅ ለማወቅ ግድ ስላልነበረው ነው።

4 ስለዚህ ሁሉም ጥፋቶች በተራ ስሕተት ሊመካኙ አይችሉም። ብዙውን ጊዜ ለዚህ ምክንያቱ ሆን ብሎ ለማወቅ አለመፈለግ ነው። ከሁሉ የሚከፋው ደግሞ አንድ ሰው በተለያየ ምክንያት አሳቦ ስህተት መሆኑን እያወቀ ያንን ነገር መፈጸሙ ነው።

5, 6. (ሀ) ለወጣትም ሆነ ለአዋቂ እርማት ጠቃሚ የሚሆነው ለምንድን ነው? (ለ) የተግሣጽ ዓላማ ምንድን ነው? (ምሳሌ 1:​1–4)

5 ይህ ሁሉ የተግሳጽን አስፈላጊነት ያሳያል። ተግሳጽ እርማት መስጠትን ይጨምራል። ወጣቶችም ሆንን አዋቂዎች ሁላችንም እርማት ያስፈልገናል። እንዲያውም ተግሳጽ ወይም እርማት ባይኖር ኖሮ በማንኛውም የሰው ኑሮ ዘርፍ መሻሻል አይገኝም ነበር። ሰዎች ያንኑን የተሳሳተ አስተሳሰብ አምነው ያንኑ ስሕተት በተደጋጋሚ እየፈጸሙ ይኖሩና በእውቀት ወይም በችሎታ በፍጹም መራመድ አይችሉም ነበር።

6 ይሁን እንጂ ተግሣጽ ወይም ዲሲፕሊን ማለት እርማት መስጠት ማለት ብቻ አለመሆኑን ታውቅ ነበርን? ቅርጽ የሚሰጥ፣ የሚያጠነክር ወይም የሚያሻሽል ማሰልጠኛም ሊሆን ይችላል። ተግሳፅ ለወደፊቱ እርማትና መሻሻልን ለማምጣት ታስቦ የሚሰጥ ተገቢ የሆነ ነገር ነው።

ተግሳፅን መቀበል ለምን ይከብዳል?

7–9. (ሀ) ብዙውን ጊዜ ተግሳጽ ለመቀበል አስቸጋሪ የሚሆነው ለምንድን ነው? (ለ) ይህንንስ ሁኔታ እንዴት ማሸነፍ ይቻላል?

7 ሆኖም ተግሣጽ ይህን ያህል ጠቃሚ ከሆነ አብዛኞቹ ሰዎች ለመቀበል ከባድ የሚሆንባቸው ለምንድን ነው? መጀመሪያውኑ ተግሣጽ እንዲያስፈልገን ባደረገው ምክንያት ማለትም ባለፍጽምናችን ምክንያት ነው። ተግሣጽ በቀላሉ እንድናፍር ሊያደርገን ይችላል፤ አለዚያም ክብራችንን ይነካው ይሆናል። ይሁንና ሐዋርያው ጳውሎስ እንደገለጸው የተግሳፅን ሌላ ጎን ልብ ብላችሁ እስቲ ተመልከቱ:- “ቅጣት [ተግሣጽ] ሁሉ ለጊዜው የሚያሳዝን እንጂ ደስ የሚያሰኝ አይመስልም፣ ዳሩ ግን በኋላ ለለመዱት [ስልጠና ላገኙበት አዓት] የሰላምን ፍሬ እርሱም ጽድቅን ያፈራላቸዋል።” — ዕብራውያን 12:11

8 ትህትና የተግሣጽን የማመም ኃይል በብዛት ይቀንሰዋል። ይሁን እንጂ ብዙ ሰዎች ኩራትና እልከኝነት ተግሣጽን እንዲቃወሙ ያደርጋቸዋል። ነገር ግን እርማቱ ወይም ወቀሳው መሠረት ያለው ከሆነ በእልህ የሚቃወመው ሰው በሌሎች ፊት ራሱን ሞኝ ያደርጋል። የአምላክ ቃል “ሞኞች ግን ጥበብንና ተግሣጽን ይንቃሉ” በማለት ይናገራል። — ምሳሌ 1:7 የ1980 ትርጉም

9 ከዚህ በተቃራኒ “ጠቢብን ገስጽ ይወድህማል” የሚለውን ቃል እናነባለን። ጠቢቡ የሚገስጸውን ለምን ይወዳል? ምክንያቱም በእርማቱ አማካኝነት “በይበልጥ ጥበበኛ እንደሚሆን” ስለሚያውቅ ነው። — ምሳሌ 9:​8, 9

አንተስ ተግሳጽ ቢሰጥህ ምን ይሰማሃል?

10–12. (ሀ) በምሳሌ 19:​20 ላይ እንደተመለከተው ተግሣጽ ሕይወታችንን እንዴት ሊነካው ይችላል? (ለ) አምላክ የሚገሥጸን ለምንድን ነው? (ዕብራውያን 12:​5, 6) (ሐ) ተግሣጽ እንዲሰጡን ሥልጣን የተሰጣቸው እነማን ናቸው?

10 ዋናው ጥያቄ ‘በሕይወትህ ምን ልትሠራበት ትፈልጋለህ?’ የሚለው ነው። እንዲያው ያለ ዓላማ ለመነዳት ትፈልጋለህን? ወይስ ጊዜህንና ጉልበትህን ልታጠፋለት ለሚገባ ወደፊት ለሚገኝ ሕይወት ለመሥራት ፈቃደኛ ነህ? ይህንን ጉዳይ የምትመለከተው እንዴት ነው? “ምክርን ስማ፣ ተግሣጽንም ተቀበል በፍጻሜህ ጠቢብ ትሆን ዘንድ” በማለት ከሚመክርህ ከአምላክ ቃል ጋር ትስማማለህን? — ምሳሌ 19:20

11 አመለካከትህ ምንም ይሁን ምን በሕይወትህ ውስጥ አንዳንድ ጊዜ መገሰጽህ የማይቀር ነው። ይህም የአምላክ ዝግጅት መሆኑን ካስታወስህ ተግሳጽን መቀበል የበለጠ አስደሳችና ቀላል ሆኖ ታገኘዋለህ። አምላክ ተግሣጽን የሚሰጠን ስለሚወደንና እንድናሻሽል ሊረዳን ስለሚፈልግ ነው። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ተግሣጽን የሚጠላ ሰው ‘የአምላክን ቃል ወደ ኋላው እየጣለ’ መሆኑን ይናገራል። — መዝሙር 50:17

12 ተግሣጽ የሚመጣው ሥልጣን ካለው ምንጭ ነው። ይህም መሆኑ ተገቢ ነው። ለወጣቶች ተግሣጽን ለመስጠት ከማንም የተሻለ ቦታ ያለው ማን ነው ብለህ ታስባለህ? ለልጆቻቸው ሕይወት ኃላፊዎቹ ወላጆች ስለሆኑ አምላክ ተግሳጽ የመስጠቱን ሥልጣን ለወላጆች ሰጥቶአቸዋል። በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥም አምላክ ‘ጤናማ በሆነ ትምህርት ደግሞ ሊመክሩ ተቃዋሚዎችንም ሊወቅሱ የሚችሉ’ በመንፈሳዊ “ሽማግሌዎች” የሆኑ ሰዎች ሰጥቷል። — ቲቶ 1:​5–9

13–17. ተግሣጽ ሲሰጠን ቅር የሚለን ከሆነ አስተሳሰባችንን ለማስተካከል ሊረዱን የሚችሉ ምን ሃሳቦችን ማስታወስ እንችላለን? (ምሳሌ 4:​1, 2፤ 13:​24፤ 15:​32)

13 ወላጆችህ ተግሣጽ ሲሰጡህ እንዴት ይሰማሃል? ብዙ ወጣቶች ለጊዜውም ቢሆን ቅር ይሰኙበታል። ከቤት እስከ መኰብለልም እንኳ ይደርሳሉ። አንድ ሰው ተግሳጽ ወይም ምክር ስለሰጠህ ተበሳጭተህ ከሆነ ቆም በልና እርሱ ይህን ለማድረግ ጊዜና ጥረት ያጠፋው ለምንድን ነው? ብለህ ራስህን ጠይቅ። ሁልጊዜ ባይሆንም አብዛኛውን ጊዜ ተግሳጽ መስጠት ለሰጪዎቹ ለራሳቸውም አስደሳች እንዳልሆነ ትገነዘባለህ። ይህን ጥረት የሚያደርጉት ለአንተ ግድ ስላላቸውና ስለሚያስቡልህ ነው። ይህ ራሱ ብቻ እንኳ እነርሱ የሚናገሩትን በጥሞና እንድታስብበት ሊያደርግህ ይገባል።

14 እውነት ነው፤ ስህተትን አምኖ መቀበል ጥንካሬን ይጠይቃል። በተለይ ተግሳጹ አስፈላጊ አልነበረም ብለህ የምታስብ ከሆነ ተግሳጹን መቀበል ትህትናን ይጠይቃል። ምንም ሳታንገራግር ጸጥ ብለህ ከተቀበልከው ትጠቀምበታለህ። ይህም ሁኔታውን ቀላል ያደርገዋል።

15 ከዚህም በተጨማሪ ተግሣጽ የሚሰጡህ ሰዎች የሕይወትን ጉዞ አስቸጋሪ ሊያደርጉብህና አንተን “ለማስጨነቅ” እየሞከሩ እንዳልሆነ ማስታወስ አለብህ። ከዚህ ይልቅ መሻሻል እንድታደርግ ሊረዱህ እየሞከሩ ነው። ጥበብ ያለበት ተግሣጽ ከጎጂ አደጋዎች ይጠብቅሃል፤ በችግር ተብትበው እርምጃህን አስቸጋሪ ከሚያደርጉ ነገሮች ነፃ ያደርግሃል። እርማትን የምትቀበል ከሆነ መጽሐፍ ቅዱስ “በሄድህ ጊዜ እርምጃህ አይጠብም፣ በሮጥህም ጊዜ አትሰናከልም፣ ተግሳጽን ያዝ፣ አትተወውም፤ ጠብቀው እርሱ ሕይወትህ ነውና” የሚል ተስፋ ይሰጥሃል። — ምሳሌ 4:​10–13

16 እርግጥ ሌሎች እስኪያርሙህ ድረስ መጠበቅ አያስፈልግህም። ራስህን በራስህ መገሠጽን ለመለማመድ ትችላለህ። ንቁ ከሆንክ ብዙዎቹን ስሕተቶችህን ለመገንዘብና እነርሱን የሚያርም እርምጃ ለመውሰድ ትችላለህ።

17 ተግሣጽን ተቀባይ በመሆን ብዙ ጥቅሞች ይገኛሉ። ስሕተትን ያለማወላወል አምኖ መቀበል በውስጥህ ጥሩ ስሜት እንዲሰማህ ያደርጋል። ትክክል ለሆነው ነገር ልብህንና አእምሮህን ያጠነክርልሃል። ከሌሎች ጋር ጥሩ ግንኙነት እንዲኖርህ ያደርጋል። ሰዎቹ ሐቀኛ፣ ትሑት፣ ሚዛናዊና በዛሬው ጊዜ ካሉት ብዙ ሰዎች የተለየ መንፈስን የሚያነቃቃ ሁኔታ ያለህ አድርገው በደስታ ይቀበሉሃል። ከሁሉም በላይ ደግሞ ተግሳጽ ከይሖዋ አምላክ ጋር ጥሩ ዝምድና ለማግኘትና በዚያው እንድትቀጥል ለማድረግ አስፈላጊ ነው። ወደፊት ዘላቂ የሆነና ደስታ ያለበት ሕይወት እንድታገኝም ዋስትና ሊሰጥህ ይችላል። አዎ፤ “የተግሣጽ ዘለፋ የሕይወት መንገድ ነው።” — ምሳሌ 6:23

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 95 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

እርማት ሲሰጥህ እንዴት ይሰማሃል?