በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ቤተሰቦቼ ድሆች ቢሆኑስ?

ቤተሰቦቼ ድሆች ቢሆኑስ?

ምዕራፍ 20

ቤተሰቦቼ ድሆች ቢሆኑስ?

በምሥራቅ አውሮፓ የሚኖረው ግሪጎሪ በምዕራብ አውሮፓ ያሉ ወጣቶች የሚገዟቸውን ዓይነት ልብሶች ወይም የኤሌክትሮኒክ ዕቃዎች ለመግዛት አቅሙ አይፈቅድለትም። ግሪጎሪ የኑሮው ሁኔታ በጣም ስለሚያበሳጨው ወደ ኦስትሪያ ለመሄድ ያስባል። ግሪጎሪ ድሃ ሊባል የሚችል ይመስልሃል?

□ አዎ □ አይ

በሌላው የዓለማችን ክፍል ደግሞ ሎይሶ የተባለ አንድ ወጣት በደቡባዊ አፍሪካ በምትገኝ አንዲት የገጠር መንደር ውስጥ ይኖራል። ከቤተሰቡ ጋር በአንዲት ደሳሳ ጎጆ ውስጥ የሚኖረው ሎይሶ በአቅራቢያው ባለ ከተማ በሚገኙት ወጣቶች ይቀናል፤ እነዚህ ወጣቶች የቧንቧ ውኃና የኤሌክትሪክ አገልግሎት ስለሚያገኙ የቅንጦት ሕይወት እንደሚመሩ ይሰማዋል። ሎይሶ ድሃ ሊባል የሚችል ይመስልሃል?

□ አዎ □ አይ

“ድሃ” ለሚለው ቃል የሚሰጠው ፍቺ አንጻራዊ እንደሆነና ከአገር አገር ሊለያይ እንደሚችል ግልጽ ነው። ለምሳሌ ያህል፣ ግሪጎሪ በድህነት እንደተጠቃ ይሰማው ይሆናል፤ ከሎይሶ ጋር ሲነጻጸር ግን እሱ የሚኖረው በምቾት ነው። አንተም የቱንም ያህል ድሃ ብትሆን ከአንተ በባሰ ሁኔታ ውስጥ ያሉ ሰዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ መገንዘብ ይገባሃል። ያም ቢሆን ግን ጥሩ የትምህርት ቤት ልብስ ከሌለህ ወይም እንደ ቧንቧ ውኃ ያሉ መሠረታዊ ነገሮችን የማታገኝ ከሆነ ከአንተ በባሰ ሁኔታ የሚኖሩ ሰዎች እንዳሉ ማወቅህ እምብዛም አያጽናናህ ይሆናል።

በድህነት ያደጉ አንዳንድ ወጣቶች የማይረቡ እንደሆኑ ስለሚሰማቸውና ራሳቸውን ዝቅ አድርገው ስለሚመለከቱ አልኮል በመጠጣት ወይም ዕፅ በመውሰድ ራሳቸውን ለማደንዘዝ ይሞክራሉ። ይሁን እንጂ ከእውነታው ለመሸሽ የሚደረግ ጥረት ሁኔታውን ከማባባስ ውጪ የሚፈይደው ነገር የለም። ከመጠን በላይ የሚጠጡ ሰዎች፣ አልኮል ‘እንደ እባብ እንደሚነድፍ፣ እንደ እፉኝትም መርዙን እንደሚረጭ’ በራሳቸው ሕይወት ይመለከታሉ። (ምሳሌ 23:32) በነጠላ ወላጅ በድህነት ያደገችው ማሪያ የተባለች ደቡብ አፍሪካዊት ወጣት “ከእውነታው ለማምለጥ የሚደረግ ጥረት ችግሮችን ከመፍታት ይልቅ የባሰ መዘዝ ያስከትላል” ስትል ተናግራለች።

በእርግጥ አንተ፣ በመጠጣት ወይም ዕፅ በመውሰድ ከችግሩ ለመሸሽ አትሞክር ይሆናል፤ ያም ሆኖ ያለህበት ሁኔታ ምንም የመሻሻል ተስፋ እንደሌለው ሊሰማህ ይችላል። ታዲያ መፍትሔ ከየት ማግኘት ትችላለህ? በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘው ጥበብ ያዘለ ምክር፣ እንደ ካቴና አስሮ ከያዘህ የተስፋ መቁረጥ ስሜት ተላቅቀህ ጤናማ አመለካከት እንድታዳብር የሚረዳ ቁልፍ ሊሆንልህ ይችላል። መጽሐፍ ቅዱስ የሚረዳህ እንዴት እንደሆነ እስቲ እንመልከት።

ያሉህን መልካም ነገሮች ተገንዘብ

ልትወስደው የሚገባው አንዱ ጠቃሚ እርምጃ ስለሌሉህ ነገሮች በማሰብ ከመብሰልሰል ይልቅ ባሉህ ነገሮች ላይ ማተኮር ነው። እንደ መኖሪያ ቤትና አፍቃሪ ቤተሰብ ያሉት ነገሮች ከገንዘብ የበለጠ ዋጋ እንዳላቸው ምንም ጥርጥር የለውም! አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሳሌ “ፍቅር ባለበት ጐመን መብላት፣ ጥላቻ ባለበት የሰባ ፍሪዳ ከመብላት ይሻላል” ይላል። (ምሳሌ 15:17) ክርስቲያን ወጣቶች ደግሞ እንደ ውድ ሀብት ሊያዩት የሚችሉት ለየት ያለ ነገር አላቸው፤ ይህም ‘ከመላው የወንድማማች ማኅበር’ የሚያገኙት ድጋፍ ነው።​—1 ጴጥሮስ 2:17

በተጨማሪም ያሉህን ቁሳዊ ነገሮች አድንቀህ ለመኖር ጥረት ማድረግ ትችላለህ። እርግጥ ነው፣ የምትኖረው መሠረታዊ ነገሮች እንኳ ባልተሟሉበት ደሳሳ ቤት ውስጥ ይሆናል። የምትለብሰውም ያረጁ፣ የነተቡና የተጣፉ ልብሶች ሊሆን ይችላል። እንዲሁም ሁልጊዜ ተመሳሳይ ምግብ መብላት ሰልችቶህ ይሆናል። ሆኖም አምላክን ለማስደሰት ዘመናዊ ልብስ መልበስ ወይም በተንደላቀቀ ቤት ውስጥ መኖር ያስፈልግሃል? በሕይወት ለመኖርም ሆነ ጤናማ ለመሆን በጣም ምርጥ የሆኑ ምግቦችን መመገብ ያስፈልግሃል? እንደ እውነቱ ከሆነ እነዚህ ነገሮች የግድ አያስፈልጉህም። ሐዋርያው ጳውሎስ በዚህ ረገድ ጠቃሚ ትምህርት አግኝቷል። ሀብታም ሆኖ ያውቃል፤ በድህነትም ኖሯል። (ፊልጵስዩስ 4:12) ታዲያ የደረሰበት መደምደሚያ ምንድን ነው? “ምግብ እንዲሁም ልብስና መጠለያ ካለን በእነዚህ ነገሮች ረክተን መኖር ይገባናል” ብሏል።​—1 ጢሞቴዎስ 6:8

ችግረኛ በሆነ ቤተሰብ ውስጥ ያደገው ኤልድሬድ የተባለ ደቡብ አፍሪካዊ “የቤተሰባችን ገቢ በጣም አነስተኛ እንደሆነና የፈለግነውን ሁሉ ማግኘት እንደማንችል በመገንዘብ ያለንበትን ሁኔታ ተቀብለን እንኖር ነበር” በማለት ተናግሯል። ኤልድሬድ የትምህርት ቤት ሱሪው በተቀደደ ቁጥር እናቱ ስለምትጥፈው ሱሪው የተለጣጠፈ እንደነበር ያስታውሳል። “የልጆቹን ፌዝ መቻል ነበረብኝ። ይሁን እንጂ ዋናው ነገር ልብሳችን ንጹሕና ሊለበስ የሚችል መሆኑ ነበር” በማለት ኤልድሬድ በግልጽ ተናግሯል።

ለራስህ ጥሩ ግምት ይኑርህ

የ11 ዓመቱ ጄምስ ከእናቱና ከእህቱ ጋር የሚኖረው ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ጆሃንስበርግ አቅራቢያ በሚገኝ ትርኪምርኪ ሰፈር ውስጥ ነበር። ቤተሰቡ ምንም ዓይነት ንብረት አልነበራቸውም ማለት ይቻላል። ያም ሆኖ ጄምስ እንደ ትልቅ ሀብት የሚቆጠር ነገር ይኸውም ጊዜና ጉልበት ነበረው፤ ይህንንም ሌሎችን ለመርዳት ማዋል ያስደስተው ነበር። ጄምስ ሁልጊዜ ቅዳሜና እሁድ፣ በአካባቢው የሚሠራውን የይሖዋ ምሥክሮች የመንግሥት አዳራሽ በመገንባቱ ሥራ በፈቃደኝነት ይካፈል ነበር። በዚህ ሥራ መካፈሉ ጊዜው አሰልቺ እንዳይሆንበት የረዳው ከመሆኑም ሌላ ጠቃሚ ነገር እንዳከናወነ እንዲሰማው ብሎም ለራሱ ጥሩ ግምት እንዲኖረው አድርጎታል። “በአዳራሹ ግንባታ ሥራ ስካፈል ውዬ ወደ ቤቴ ስመለስ በውስጤ ይህ ነው የማልለው እርካታ ይሰማኛል!” ሲል ተናግሯል።

ልታከናውነው የምትችለው ሌላው ጠቃሚ ተግባር ደግሞ ከቤት ወደ ቤት የሚካሄደው መጽሐፍ ቅዱስን የማስተማር ሥራ ነው። (ማቴዎስ 24:14) የይሖዋ ምሥክሮች የሆኑ ወጣቶች በዚህ ሥራ አዘውትረው ይካፈላሉ። እንዲህ ማድረጋቸው ወደፊት የተሻለ ሕይወት እንደሚመጣ ለሰዎች ተስፋ የሚሰጥ ከመሆኑም ሌላ እነዚህ ወጣቶች ለራሳቸው ያላቸው አክብሮት ከፍ እንዲል ይረዳቸዋል። እርግጥ ነው፣ በዚህ ሥራ ሲካፈሉ ገንዘብ አይከፈላቸውም። ይሁንና ኢየሱስ በጥንቷ የሰምርኔስ ጉባኤ ለሚገኙት ክርስቲያኖች የላከውን መልእክት አስታውስ። እነዚህ ክርስቲያኖች በቁሳዊ ነገሮች ረገድ በጣም ድሆች ነበሩ። ያም ቢሆን በመንፈሳዊ ጠንካሮች ስለነበሩ ኢየሱስ “መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ፤ ይሁንና ሀብታም ነህ” ብሏቸዋል። በፈሰሰው የኢየሱስ ደም እንደሚያምኑ በተግባር በማሳየታቸው የማይጠፋ ሕይወትን አክሊል ስለሚያገኙ የላቀ ሀብት ይኖራቸዋል።​—ራእይ 2:9, 10

ብሩህ ተስፋ ይኑርህ

ሀብታምም ሆንክ ድሃ ከይሖዋ ጋር የጠበቀ ግንኙነት መመሥረት ትችላለህ። መጽሐፍ ቅዱስ “ባለጠጋና ድኻ የሚጋሩት ነገር፣ እግዚአብሔር የሁላቸውም ፈጣሪ መሆኑ ነው” ይላል። (ምሳሌ 22:2) በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት የይሖዋ ምሥክሮች ይህንን ሐቅ መገንዘባቸው ድህነትን ተቋቁመው ለመኖር ረድቷቸዋል። ሰዎች ደስተኞች መሆናቸው የተመካው ቁሳዊ ሀብት በማግኘታቸው ላይ ሳይሆን እሱን ለማገልገል የሚፈልጉትን ሁሉ ከሚቀበለው ከይሖዋ አምላክ ጋር ወዳጅነት በመመሥረታቸው ላይ መሆኑን እነዚህ ወጣቶች ተገንዝበዋል። ወደፊት ሰዎች ከድህነት አረንቋ የሚላቀቁበት አዲስ ዓለም እንደሚመጣ አምላክ ተስፋ ሰጥቷል።​—2 ጴጥሮስ 3:13፤ ራእይ 21:3, 4

እስከዚያ ጊዜ ድረስ ግን ያሉህን ነገሮች በአግባቡ ተጠቀምባቸው። ብሩህ ተስፋ ይኑርህ። መንፈሳዊ ሀብት አከማች። (ማቴዎስ 6:19-21) ድህነትን ልትቋቋመው እንደምትችል ተፈታታኝ ሁኔታ አድርገህ ተመልከተው!

ቁልፍ ጥቅስ

“አንድ ሰው ሀብታም ቢሆንም እንኳ ሕይወቱ በንብረቱ ላይ የተመካ [አይደለም]።”​—ሉቃስ 12:15

ጠቃሚ ምክር

ቁማር ከመጫወት፣ ከማጨስ እንዲሁም የአልኮል መጠጥ ከመጠን በላይ ከመጠጣት ተቆጠብ። ሌሎች የቤተሰብህ አባላት እንዲህ ዓይነት ልማድ ካላቸው በምግባርህ ጥሩ ምሳሌ ለመሆን ጥረት አድርግ።

ይህን ታውቅ ነበር . . . ?

የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች በተግባር ማዋልህ ያለህበት ሁኔታ ምንም ይሁን ምን ባለህ ነገር ረክተህ እንድትኖር ሊረዳህ ይችላል።​—ፊልጵስዩስ 4:12, 13፤ 1 ጢሞቴዎስ 6:8፤ ዕብራውያን 13:5

ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

አሉኝ የምላቸው ነገሮች ․․․․․

በእነዚህ ነገሮች ተጠቅሜ ሌሎችን ለመርዳት እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

ምን ይመስልሃል?

● “ድሃ” ለሚለው ቃል የሚሰጠው ፍቺ አንጻራዊ ነው የምንለው ለምንድን ነው?

● ከእውነታው ለመሸሽ ሲባል እንደ ዕፅና የአልኮል መጠጥ ያሉ ነገሮችን መውሰድ ጥበብ የጎደለው አካሄድ ነው የምንለው ለምንድን ነው?

● ድህነትን ለመቋቋም ምን ዓይነት ጠቃሚ እርምጃዎች መውሰድ ትችላለህ?

[በገጽ 168 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

ከድህነት ማምለጥ የምችልበት መንገድ እንደሌለ ቢሰማኝም የሚያስፈልጉኝን ነገሮች ለማግኘት ስል ከወንበዴዎች ቡድን ጋር መቀላቀል ወይም መስረቅ በፍጹም መፍትሔ እንደማይሆን ተገንዝቤ ነበር። እንደነዚህ ያሉትን ነገሮች ያደርጉ የነበሩ አብዛኞቹ እኩዮቼ በአሁኑ ጊዜ ሕይወታቸው ተበላሽቷል ወይም የመጠጥና የዕፅ ሱሰኞች ሆነዋል አሊያም እስር ቤት ገብተዋል።”​—ጆርጅ

[በገጽ 164 ላይ የሚገኝ ሣጥን/​ሥዕል]

የመልመጃ ሣጥን

ውጭ አገር መሄድ ይኖርብኛል?

አንዳንድ ወጣቶች ወደ ውጭ አገር መሄድ የሚፈልጉት ለራሳቸው የሚሆን ገንዘብ ለማግኘት አሊያም ወላጆቻቸውን ለመርዳት በማሰብ ነው። ሌሎች ደግሞ የውጭ አገር ቋንቋ ለመማር፣ ተጨማሪ ትምህርት ለማግኘት ወይም በቤት ውስጥ ካለው ችግር ለመሸሽ ሲሉ ወደ ሌላ አገር ይሄዳሉ። አንዳንድ ክርስቲያን ወጣቶች፣ ሰባኪዎች ይበልጥ ወደሚያስፈልጉባቸው አገሮች ሄደዋል። ወደ ውጭ አገር መሄድ ከባድ ውሳኔ ስለሆነ በቁም ነገር ልታስብበት ይገባል። በመሆኑም ወደ ሌላ አገር ለመሄድ ካሰብክ ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች አንብብና አሰላስልባቸው። የቀረቡትን ጥያቄዎች ካሰብክባቸው በኋላ መልስህን በወረቀት ላይ ጻፍ። ከዚያም ጉዳዩን በጸሎት አስበህበት ውሳኔ አድርግ።

□ ከሕግ አንጻር ምን የሚጠበቅብኝ ነገር አለ?​—ሮም 13:1

□ ወደ ሌላ አገር መሄድ የሚጠይቅብኝ አጠቃላይ ወጪ ምን ያህል ነው?​—ሉቃስ 14:28

□ በውጭ አገር ስኖር የሚያስፈልጉኝን ነገሮች ማሟላት እንደምችል እርግጠኛ እንድሆን የሚያደርጉኝ ምን ነገሮች እያከናወንኩ ነው?​—ምሳሌ 13:4

□ በውጭ አገር የሚኖሩ የጎለመሱ ሰዎችን ምክር ጠይቄያለሁ?​—ምሳሌ 1:5

□ ወላጆቼ ስለዚህ ጉዳይ ምን ይሰማቸዋል?​—ምሳሌ 23:22

□ ወደ ሌላ አገር ለመሄድ የፈለግሁት ለምንድን ነው?​—ገላትያ 6:7, 8

□ በምሄድበት አገር ከሌሎች ጋር አብሬ የምኖር ከሆነ እነዚህ ሰዎች ጥሩ መንፈሳዊ ልማድ እንዲኖረኝ ያበረታቱኛል?​—ምሳሌ 13:20

□ ከሥነ ምግባር አንጻር ምን ችግሮች ሊያጋጥሙኝ ይችላሉ? ምን መንፈሳዊ ወይም አካላዊ ጉዳትስ ሊደርስብኝ ይችላል?​—ምሳሌ 5:3, 4፤ 27:12፤ 1 ጢሞቴዎስ 6:9, 10

□ ካሉት እውነታዎች አንጻር ውጭ አገር በመሄዴ ምን ጥቅሞች እንደማገኝ ይሰማኛል?​—ምሳሌ 14:15

[በገጽ 167 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር፣ እንደ ካቴና አስሮ ከያዘህ የተስፋ መቁረጥ ስሜት እንድትላቀቅ የሚረዳ ቁልፍ ሊሆንልህ ይችላል