በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ወደ ፊት ምን ይጠብቀኝ ይሆን?

ወደ ፊት ምን ይጠብቀኝ ይሆን?

ምዕራፍ 38

ወደ ፊት ምን ይጠብቀኝ ይሆን?

“የኑክሌር ስጋት ያንዣበበበትን መጪ ጊዜ በጣም እፈራዋለሁ።” ይህን ቃል ለአገሩ ከፍተኛ የፖለቲካ ባለ ሥልጣን በጻፈው ደብዳቤ ላይ ያሰፈረው አንድ ጀርመናዊ ወጣት ነበር።

ምናልባት ስለ ወደፊቱ ጊዜ ስታስቡ በኑክሌር ተወንጫፊ መሣሪያ ስትጠፉ ይታያችሁ ይሆናል። አንድ ወጣት “ጥሩ ውጤት ለማምጣት ምን አስጨነቀኝ?” ሲል ጠይቋል። “ዓለም እንደሆነች መጥፋትዋ አይቀር።” በእርግጥም በተማሪዎች ላይ በተደረገ አንድ ጥናት ወጣት ወንዶች ከምንም ነገር በላይ የሚያስፈራቸው የኑክሌር ጦርነት እንደሆነ ሊታወቅ ችሏል። ልጃገረዶች በአንደኛ ደረጃ የሚያስፈራቸው ‘የወላጆቻቸው ሞት’ ሲሆን ለኑክሌር ጦርነት ስጋት ሁለተኛ ደረጃ ሰጥተዋል።

ይሁን እንጂ በአድማሳችን ላይ ያጠላው ጥቁር ደመና የኑክሌር ፍንዳታ ብቻ አይደለም። “የሕዝብ ብዛት፣ የተፈጥሮ ሀብት መመናመን፣ የአካባቢ መበከል፣” ሌሎችም አይቀሬ የሆኑ መቅሠፍቶች የፈጠሩት ስጋት ስመ ጥር የሥነ ልቦና ተመራማሪ የሆኑትን ቢ ኤፍ ስኪነር “የሰው ዘር ሊጠፋ የተቃረበ ይመስላል” ከሚል መደምደሚያ ላይ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል። ቆየት ብለውም “ስለ መጪው ጊዜ ምንም ጥሩ ነገር አይታየኝም። በእርግጥም ችግሮቻችንን ልንፈታ አንችልም” ብለዋል።

ምሁራን የሆኑ ታዛቢዎች እንኳን መጪውን ጊዜ እየተርበተበቱ የሚጠብቁ ከሆነ ብዙ ወጣቶች “ነገ እንሞታለንና እንብላና እንጠጣ” የሚል ዝንባሌ ማሳየታቸው አያስደንቅም። (1 ቆሮንቶስ 15:​32) በእርግጥም መጪው ጊዜ በፖለቲከኞችና በሳይንስ ሊቃውንት ጥረት ላይ የተመካ ከሆነ እውነትም ተስፋ የሚያስቆርጥ ነው። ምክንያቱም ኤርምያስ 10:​23 “የሰው መንገድ ከራሱ እንዳይደለ አውቃለሁ፣ አካሄዱንም ለማቅናት ከሚራመድ ሰው አይደለም” በማለት ይናገራል።

ይህ ጥቅስ የሚናገረው ሰው ራሱን ለማስተዳደር ችሎታ እንደ ሌለው ብቻ አይደለም። ራሱን የማስተዳደር መብት እንደሌለው ያመለክታል። የምድርን የወደፊት ሁኔታ የመቆጣጠር ሥልጣን የለውም። በመሆኑም የሚያደርጋቸው ጥረቶች በሙሉ ውድቅ መሆናቸው አይቀርም። በዚህም ምክንያት ኤርምያስ “ይሖዋ ሆይ፣ አስተካክለኝ፣ ግን በፍርድ ይሁን” በማለት አምላክ ጣልቃ ገብቶ እርምጃ እንዲወስድ ጸልዮአል። (ኤርምያስ 10:​24 አዓት) ይህ ማለት የወደፊቱ የሕይወታችን ሁኔታ የሚወሰነው በፈጣሪያችን ነው ማለት ነው። ታዲያ ይህ የወደፊት ሕይወታችን እንዴት ያለ ይሆናል?

አምላክ ለምድር ያለው ዓላማና የወደፊት ሕይወታችሁ

ሰው ከተፈጠረ በኋላ አምላክ ለመጀመሪያዎቹ ሰብዓውያን ባልና ሚስት “ብዙ፣ ተባዙ፣ ምድርንም ሙሉአት፣ ግዙአትም፤ የባሕርንም ዓሦችና የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ግዙአቸው” ብሎ ነበር። (ዘፍጥረት 1:​28) ስለዚህ የሰው ልጅ ምድር አቀፍ በሆነ ገነት ላይ የመኖር ተስፋ ቀርቦለት ነበር።

ይሁን እንጂ የመጀመሪያዎቹ ባልና ሚስት በአምላክ አገዛዝ ላይ ዓመፁ። ሰሎሞን እንደተናገረው “እግዚአብሔር ሰዎችን ቅኖች አድርጎ ሠራቸው፣ . . . እነርሱ ግን ብዙ ብልሃትን ፈለጉ።” (መክብብ 7:​29) የሰው ልጆች ዕቅዶች አጥፊ መሆናቸው ከመረጋገጡም በላይ ለአሁኑ ትውልድ ጉስቁልናና ከምን ጊዜውም የበለጠ ተስፋ አስቆራጭ የሆነ የወደፊት ጊዜ አውርሰውታል።

ታዲያ ይህ ማለት አምላክ ይህችን ምድር የተበከለች፣ በራዲዮአክቲቭ ፍሳሾች የተሞላች፣ ምናልባትም ሕይወት አልባ የሆነች ሉል እንድትሆን ፈጽሞ ይጥላታል ማለት ነውን? በፍጹም እንዲህ ሊሆን አይችልም! እሱ “ምድርን የሠራና ያደረገ ያጸናትም፣ መኖሪያም ልትሆን እንጂ ለከንቱ እንድትሆን ያልፈጠራት አምላክ” ነው። በመሆኑም ለምድር ያቀደው ዓላማ እንደሚፈጸም የተረጋገጠ ነው!​— ኢሳይያስ 45:​18፤ 55:​10, 11

ታዲያ ይህ የሚሆነው መቼና እንዴት ነው? ሉቃስ ምዕራፍ 21ን አውጡና ራሳችሁ አንብቡ። እዚህ ምዕራፍ ላይ ኢየሱስ በዚህ መቶ ዘመን የሰው ልጆችን ሲያሠቃዩ የቆዩትን ችግሮች ተንብዮአል:- እነሱም ዓለም አቀፍ ጦርነቶች፣ የመሬት መንቀጥቀጦች፣ በሽታ፣ የምግብ እጥረት፣ በየቦታው ተስፋፍቶ የሚገኘው ወንጀል ናቸው። እነዚህ ክስተቶች ምን ያመለክታሉ? ኢየሱስ ራሱ “ይህም ሊሆን ሲጀምር ቤዛችሁ ቀርቦአልና አሻቅባችሁ ራሳችሁን አንሡ። . . . ይህ ሁሉ መሆኑን ስታዩ የእግዚአብሔር መንግሥት እንደ ቀረበች እወቁ” በማለት አስረድቷል።​— ሉቃስ 21:​10, 11, 28, 31

የወደፊት ሕይወታችሁ ብሩሕ እንዲሆን የሚያስችለው ይህ መንግሥት ብቻ ነው። በቀላል አነጋገር መንግሥቱ መስተዳድር ወይም አምላክ ምድርን የሚገዛበት መሣሪያ ነው። ይህ ንጉሣዊ መስተዳድር ምድርን ከሰው ልጆች ቁጥጥር መንጭቆ ያወጣል። (ዳንኤል 2:​44) “ምድርን የሚያጠፉት” ሰዎች ራሳቸው በአምላክ እጅ ይጠፋሉ። ምድርንና የሰው ልጆችን በሰው መጥፎ አስተዳደር ምክንያት ከደረሰው ከፍተኛ በደል ነጻ ያወጣል።​— ራእይ 11:​18፤ መክብብ 1:​4

ምድር በአምላክ መንግሥት አስተዳደር ሥር አስተማማኝ ሰላም አግኝታ ቀስ በቀስ ከዳር እስከ ዳር ገነት ትሆናለች። (ሉቃስ 23:​43) ፍጹም የሆነ ሥነ ምሕዳራዊ (ኢኮሎጂያዊ) ሚዛን ይኖራል። በሰውና በአራዊት መካከልም እንኳን ሳይቀር ፍጹም ስምምነት ይኖራል። (ኢሳይያስ 11:​6–9) ጦርነትና የጦር መሣሪያዎች ይጠፋሉ። (መዝሙር 46:​8, 9) ወንጀል፣ ረሀብ፣ የቤት እጥረት፣ በሽታ፣ ሞትም እንኳን ሳይቀር ይጠፋሉ። የምድር ነዋሪዎች “በብዙ ሰላም ደስ ይላቸዋል።”​— መዝሙር 37:​10, 11፤ 72:​16፤ ኢሳይያስ 65:​21, 22፤ ራእይ 21:​3, 4

የአምላክን ተስፋዎች ‘መፈተን’

የወደፊት ተስፋችሁ በምድር ላይ በገነት ለዘላለም መኖር ሊሆን ይችላል! ይሁን እንጂ ይህ ሐሳብ ማራኪ መስሎ ቢሰማችሁም ምናልባት ጥሩ ሰዎች ሁሉ ወደ ሰማይ ይሄዳሉ የሚለውን እምነት ለመተው አስቸጋሪ ሊሆንባችሁ ወይም ደግሞ በራሱ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ጥርጣሬ ይኖራችሁ ይሆናል። በይሖዋ ምሥክሮች መካከል ያሉ አንዳንድ ወጣቶችም እንኳን ሳይቀሩ እምነታቸው አንዳንድ ጊዜ በሚያስደነግጥ ሁኔታ ሲዋዥቅ ያገኙታል። ለምሳሌ ያህል ሚሸል ምሥክሮች የሆኑ ወላጆች ያሳደጓት ልጅ ናት። መጽሐፍ ቅዱስ እውነተኛ ነው ብሎ መቀበል ለእርሷ ሌሊቱ ሲያልፍ ቀን እንደሚመጣ የመቀበልን ያህል ቀላል ነበር። ይሁን እንጂ አንድ ቀን በመጽሐፍ ቅዱስ የማምነው ለምንድን ነው የሚል ሐሳብ መጣባት። “እስከዚያ ጊዜ ድረስ በመጽሐፍ ቅዱስ አምን የነበረው እናትና አባቴ ስላመኑበት ብቻ ነው ብዬ እገምታለሁ” ብላለች።

መጽሐፍ ቅዱስ “ያለ እምነትም [አምላክን] ደስ ማሰኘት አይቻልም” ይላል። (ዕብራውያን 11:​6) ሆኖም እምነት እናትና አባታችሁ ስላላቸው ብቻ ሊኖራችሁ የሚችል ነገር አይደለም። የወደፊት ሕይወታችሁ ዋስትና ያለው እንዲሆን ከፈለጋችሁ በጠንካራ ማስረጃ ላይ የተመሠረተ፣ “ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ” እምነት መገንባት አለባችሁ። (ዕብራውያን 11:​1) መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚገልጸው ‘ሁሉንም መፈተን’ ወይም ዘ ሊቪንግ ባይብል “የተባለው ነገር ሁሉ እውነት መሆኑን ፈትናችሁ አረጋግጡ” እንደሚለው ማድረግ አለባችሁ።​— 1 ተሰሎንቄ 5:​21

መጽሐፍ ቅዱስ እውነት መሆኑን ለራሳችሁ ማረጋገጥ

በመጀመሪያ መጽሐፍ ቅዱስ በእርግጥ “የአምላክ መንፈስ ያለበት መጽሐፍ” መሆን አለመሆኑን ማረጋገጥ ያስፈልጋችሁ ይሆናል። (2 ጢሞቴዎስ 3:​16) ይህን ማድረግ የምትችሉት እንዴት ነው? ሁሉን ከሚችለው አምላክ በስተቀር ያለ አንዳች መሳሳት ‘ከመጀመሪያ መጨረሻውን መናገር’ የሚችል ማንም የለም። (ኢሳይያስ 43:​9፤ 46:​10) አምላክ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተደጋጋሚ ከመጀመሪያ መጨረሻውን ተናግሯል። በሉቃስ 19:​41–44 እና 21:​20, 21 ላይ ስለ ኢየሩሳሌም ውድቀት የተመዘገቡትን ትንቢቶች አንብቡ። ወይም ደግሞ ስለ ባቢሎን ውድቀት በኢሳይያስ 44:​27, 28 እና 45:​1–4 ላይ የሚናገረውን ትንቢት አንብቡ። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ እነዚህ ክንውኖች የተናገራቸው ትንቢቶች አላንዳች መሳሳት በትክክል የተፈጸሙ መሆናቸውን ዓለማዊ ታሪክ ያረጋግጣል! የ14 ዓመቷ ጃኒን “ከትንቢቶቹ አንዳንዶቹን ከመረመርኩ በኋላ መጽሐፍ ቅዱስ የተነበያቸውን ነገሮች በሙሉ ከመፈጸማቸው አስቀድሞ እንዴት በትክክል እንደተናገረ ስመለከት በጣም ተገርሜያለሁ!” ብላለች።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ትክክለኛነት፣ ሐቀኝነት፣ ግልጽነትና እርስ በርሱ የማይጋጭ መሆኑ በመጽሐፍ ቅዱስ ለማመን ተጨማሪ ምክንያቶች ናቸው። * ይሁን እንጂ የይሖዋ ምሥክሮች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጧቸው ማብራሪያዎች ትክክለኛ መሆናቸውን እንዴት ታውቃላችሁ? የጥንቷ ቤርያ ነዋሪዎች ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ የሰጠውን ማብራሪያ ያለ አንዳች ጥያቄ በጭፍን አልተቀበሉም። ከዚህ ይልቅ ‘ነገሩ እንደዚሁ ይሆንን? እያሉ ቅዱሳን መጻሕፍትን ዕለት ዕለት መረመሩ።’​— ሥራ 17:​11

እኛም በተመሳሳይ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች ጥልቅ ጥናት እንድታደርጉ አጥብቀን እንመክራችኋለን። ወደ ዘላለም ሕይወት የሚመራ እውቀት የተሰኘው (በኒው ዮርክ የመጠበቂያ ግንብ መጽሐፍ ቅዱስና ትራክት ማኅበር የተዘጋጀ) መጽሐፍ እነዚህን የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች ግልጽ በሆነ መንገድ ያብራራል። ወላጆቻችሁ የይሖዋ ምሥክሮች ከሆኑ ለሚኖሯችሁ ማናቸውም ጥያቄዎች መልስ እንድታገኙ ሊረዷችሁ እንደሚችሉ ጥርጥር የለውም። “በዚህ ረገድ ምንም ዓይነት ችግር ካለባችሁ ለወላጆቻችሁ አትደብቋቸው” በማለት ጃኔል የተባለች አንዲት ወጣት ሴት ትመክራለች። “ለማመን አስቸጋሪ የሆነ ነገር ካጋጠማችሁ ጠይቁ።” (ምሳሌ 15:​22) ከጊዜ በኋላ ይሖዋ በእርግጥ ምሥክሮቹን ስለ መጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች አስደናቂ ማስተዋል በመስጠት እንደባረካቸው እንደምትገነዘቡ አያጠራጥርም!

ፕሬንቲስ የተባለ ወጣት “አንዳንድ ጊዜ የዓለም ሁኔታ በጣም ያሳዝነኛል። እንደ ራእይ 21:​4 የመሰሉትን ጥቅሶች ሳነብ ግን ተስፋ የማደርገው ነገር አገኛለሁ” ይላል። አዎን፣ በአምላክ ተስፋዎች ላይ ጠንካራ እምነት ማሳደር ስለ ሕይወት ያላችሁን አመለካከት እንደሚለውጠው የተረጋገጠ ነው። መጪውን ጊዜ በትካዜ ሳይሆን በደስታና በጉጉት ትጠብቃላችሁ። የአሁኑ ሕይወታችሁ ትርጉም የሌለውና ሕይወታችሁን ለጥቂት ጊዜ ለማቆየት የሚደረግ መፍጨርጨር ሳይሆን ‘እውነተኛውን ሕይወት አጥብቃችሁ ትይዙ ዘንድ ለወደፊቱ ለራሳችሁ መልካም መሠረት ለመጣል’ የሚያስችል ይሆንላችኋል።​— 1 ጢሞቴዎስ 6:​19

ይሁን እንጂ ወደዚህ “እውነተኛ ሕይወት” ለመድረስ የመጽሐፍ ቅዱስን ትምህርቶች ተምሮ ከማመን ሌላ ተጨማሪ ነገር ማድረግ ያስፈልጋልን?

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.20 የመጽሐፍ ቅዱስን እውነተኝነት በሚመለከት ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ከቅዱሳን ጽሑፎች እየጠቀሱ ማመራመር የተሰኘውን (በኒው ዮርክ የመጠበቂያ ግንብ መጽሐፍ ቅዱስ እና ትራክት ማኅበር የተዘጋጀ) መጽሐፍ ገጽ 58–68 ተመልከቱ።

የመወያያ ጥያቄዎች

◻ ወጣቶች የወደፊት ሕይወታቸውን በሚመለከት ምን ስጋቶች አሏቸው?

◻ አምላክ ለምድር የነበረው የመጀመሪያ ዓላማ ምን ነበር? የአምላክ ዓላማ እንዳልተለወጠ እርግጠኞች ለመሆን የምንችለው ለምንድን ነው?

◻ የአምላክ መንግሥት አምላክ ለምድር የነበረውን ዓላማ በመፈጸም ረገድ ምን ሚና ይጫወታል?

◻ የመጽሐፍ ቅዱስን ትምህርቶች እውነተኝነት መመርመር አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? ይህንንስ ማድረግ የምትችሉት እንዴት ነው?

◻ መጽሐፍ ቅዱስ በአምላክ መንፈስ መሪነት የተጻፈ መሆኑን ለራሳችሁ ማረጋገጥ የምትችሉት እንዴት ነው?

[በገጽ 306 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“ስለ መጪው ጊዜ ምንም ጥሩ ነገር አይታየኝም። በእርግጥም ችግሮቻችንን ልንፈታ አንችልም።” —የሥነ ልቦና ተመራማሪ ቢ ኤፍ ስኪነር

[በገጽ 307 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የመሬት ፈጣሪ የሰው ልጅ ፕላኔታችንን እንዲያጠፋት አይፈቅድም

[በገጽ 309 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ስለ መጽሐፍ ቅዱስ እውነተኝነት ራሳችሁን አሳምናችኋልን?