በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከመምህሬ ጋር ልስማማ የምችለው እንዴት ነው?

ከመምህሬ ጋር ልስማማ የምችለው እንዴት ነው?

ምዕራፍ 20

ከመምህሬ ጋር ልስማማ የምችለው እንዴት ነው?

“የሚያዳላ መምህር መታገሥ አልችልም” ትላለች ወጣቷ ቪኪ። እናንተም እንደዚህ እንደሚሰማችሁ አያጠራጥርም። ሆኖም በ1981 በ160,000 ወጣቶች ላይ የተደረገ ጥናት እንዳሳየው 76 በመቶ የሚሆኑት ወጣቶች አስተማሪዎቻቸው አንድ ዓይነት አድልዎ እንደሚያደርጉ ስሞታ አቅርበዋል!

ወጣቶች ከፍተኛ ውጤት አገኝበታለሁ ብለው ላሰቡት ሥራ ዝቅተኛ ውጤት ሲያገኙ ይናደዳሉ። የሚሰጣቸው ቅጣት ከልክ ያለፈ ወይም ተገቢ ያልሆነ ወይም በዘር መድሎ ምክንያት የተሰጣቸው መስሎ ሲታያቸው ቅር ይሰኛሉ። መምህሩ ከሁሉ አብልጦ ለሚወደው ተማሪ የተለየ ትኩረት ሲሰጥ ወይም አድሏዊ አያያዝ ሲያደርግ ይናደዳሉ።

እርግጥ ነው መምህራን የማይሳሳቱ አይደሉም። እነርሱም የየራሳቸው የተለየ ጠባይና ችግር አላቸው፤ እንዲሁም መሠረተ ቢስ የሆነ ጥላቻ ያሳያሉ። ይሁን እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ “በነፍስህ ለቁጣ ችኩል አትሁን” በማለት ያስጠነቅቃል። (መክብብ 7:​9) አስተማሪዎችም ሳይቀሩ ‘በብዙ ነገር ይሰናከላሉ። በቃል የማይሰናከል ማንም ቢኖር እርሱ ሥጋውን ሁሉ ደግሞ ሊገታ የሚችል ፍጹም ሰው ነው።’ (ያዕቆብ 3:​2) እንግዲያስ ባልተረጋገጠ ነገር በመምህራችሁ ላይ ከመፍረድ ልትቆጠቡ አትችሉምን?

ፍሬዲ የተባለ ወጣት መምህሩ “በሁሉም ተማሪዎች ላይ በቁጣ ሲገነፍሉ” ተመለከተ። ፍሬዲ በዘዴ ወደ መምህሩ ቀርቦ ጠየቃቸውና እንዲህ ዓይነት የግልፍተኝነት ጠባይ ያሳዩበትን ምክንያት ተረዳ። “ዛሬ ጧት መኪናዬ አስቸግራኝ ስለነበረ ነው” በማለት መምህሩ ገለጹለት። “ወደ ትምህርት ቤት ስመጣ በጣም ሞቀችብኝና አርፍጄ ሥራ ገባሁ” አሉት።

መምህራንና ከሌሎች አብልጠው የሚወዷቸው ተማሪዎች

መምህራን አብልጠው ለሚወዷቸው ተማሪዎች ስለሚሰጡት የተለየ ሞገስ ምን ሊባል ይቻላል? አንድ መምህር በዓይነቱ ብቸኛ የሆነ ኃላፊነትና የሥራ ሸክም እንዳለበት አስታውሱ። ቢዪንግ አዶለሰንት የተሰኘው መጽሐፍ መምህራን የሚገጥማቸውን “አስቸጋሪ ሁኔታ” ሲገልጽ “አብዛኛውን ጊዜ ሐሳባቸው የተበታተነባቸውን ወጣቶች ትኩረት ለመሳብ ይጥራሉ። . . . ከፊታቸው ተቀምጠው የሚያዳምጧቸው በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ የሚገኙ ወጣቶች ስሜታቸው በጣም ተለዋዋጭ የሆነ፣ ሐሳባቸው በቀላሉ ወደሌላ የሚበታተን፣ ባጠቃላይም በምንም ነገር ላይ ከ15 ደቂቃ በላይ የማተኮር ልማድ የሌላቸው” እንደሆኑ ያስረዳል።

ታዲያ አንድ መምህር በትጋት ለሚማር፣ በጥሞና ለሚያዳምጥ ወይም መምህሩን ለሚያከብር ተማሪ ትኩረት ቢሰጥ ያስደንቃልን? እውነት ነው፣ ‘አሽቃባጭ’ የሆኑ ተማሪዎች ከእናንተ ይበልጥ ትኩረት ሲያገኙ ያበሳጫችሁ ይሆናል። ይሁን እንጂ የትምህርት ፍላጎታችሁ ችላ እስካልተባለ ድረስ አንድ ትጉ ተማሪ በመምህሩ ዘንድ ቢወደድ የምትበሳጩት ወይም የምትቀኑት ለምንድን ነው? ከዚህ ይልቅ እናንተም ራሳችሁ ይበልጥ ትጉ ለመሆን ብትጥሩ የተሻለ ይሆናል።

የክፍል ውስጥ ጦርነት

አንድ ተማሪ ስለ መምህሩ ሲናገር “ሁላችንም በእርሱ ላይ ጦርነት እንዳወጅንበት አድርጎ ስለሚያስብ አስቀድሞ ሊዘምትብን ወስኗል። አለአግባብ ሌሎችን የሚጠራጠር ሰው ነው” ብሏል። ይሁን እንጂ ብዙ መምህራን በመጠኑ “ተጠራጣሪ” እንዲሆኑ የሚያስገድዳቸው ምክንያት እንዳላቸው ይሰማቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ እንደተነበየው ያለንበት ጊዜ “የሚያስጨንቅ ዘመን” ስለሆነ ተማሪዎች ብዙውን ጊዜ “ራሳቸውን የማይገዙ፣ ጨካኞች፣ መልካም የሆነውን የማይወዱ” ናቸው። (2 ጢሞቴዎስ 3:​1–3) በመሆኑም ዩ ኤስ ኒውስ ኤንድ ዎርልድ ሪፖርት “በብዙ ከተሞች ውስጥ ባሉ ትምህርት ቤቶች የሚያስተምሩ መምህራን [በተማሪዎች] የሚፈጸመውን የኃይል እርምጃ እየፈሩ ይኖራሉ” ብሏል።

ቀደም ሲል መምህር የነበሩት ሮላንድ ቤትስ መምህራንን በተ መለከተ እንደሚከተለው ብለው ነበር:- “መምህራኑ ፈጽመው ከመሸነፋቸው በፊት ምን ያህል ሊቋቋሟቸው እንደሚችሉ ለማየት [በምሳሌያዊ ሁኔታ] መግፋትና መጎሸም . . . የተፈጥሮ ኃላፊነታቸው እንደሆነ ይሰማቸዋል። . . . አዲሱ መምህራቸው ፈጽሞ ሊሸነፍ የቀረው በጣም ጥቂት መሆኑ ሲሰማቸው ይብሱን ይጎሽሙታል።” እናንተ ወይም የክፍል ጓደኞቻችሁ አንድን መምህር በማበሳጨት ተግባር ተካፍላችሁ ታውቃላችሁን? እንግዲያውስ መምህራችሁ በአጸፌታው እናንተን ለማበሳጨት ቢሞክር አትደነቁ።

መጽሐፍ ቅዱስ “ግፍ ጠቢቡን ያሳብደዋል” ይላል። (መክብብ 7:​7) አንዳንድ መምህራን በአንዳንድ ትምህርት ቤቶች ተንሰራፍቶ በሚገኘው ፍርሃትና አክብሮት የጎደለው ሁኔታ ተገፋፍተው ከልክ ባለፈ መንገድ አጸፋውን የሚመልሱበትና ጥብቅ የሚሆኑበት ምክንያት ሊገባን ይችላል። ዘ ፋምሊ ሃንድቡክ ኦቭ አዶለሰንስ “በጠባያቸው የመምህራቸውን እምነት የሚያንቋሽሹ መስለው የሚታዩ ተማሪዎች . . . አብዛኛውን ጊዜ እነርሱም በምላሹ ይንቋሸሻሉ” በማለት ገልጿል። አዎን፣ የጠላትነት መንፈስ የሚያሳይ መምህር ብዙውን ጊዜ ይህን ጠባዩን የሚያገኘው ከተማሪዎቹ ነው!

በተጨማሪም በክፍል ውስጥ የሚፈጸሙ ከአግባብ ውጭ የሆኑ ቀልዶች የሚኖራቸውን ውጤት አስቡ። ወጣቷ ቫለሪ ወጣቶች በተተኪ መምህራን ላይ ስለሚያመጡት “አበሳና ፍዳ” ስትናገር ትንገሸገሻለች። ሮላንድ ቤትስ ጨምረው ሲናገሩ “ተተኪ መምህራንን ተማሪዎቻቸው ምሕረት የለሽ በሆነ መንገድ መቆሚያ መቀመጫ ያሳጧቸዋል፤ ብዙውን ጊዜም [በንዴት] ድምፃቸው እስኪሻክር ወይም ክፍሉን ለቀው እስኪወጡ ድረስ ያናድዷቸዋል” ብለዋል። ምንም እንደማይደርስባቸው እርግጠኞች ስለሆኑ አዲስ በመሆኑ ምክንያት ግር ያለውን መምህር ለማበሳጨት በመቻላቸው ይደሰታሉ። ለዚህም ሲሉ በአድማ መልክ መጽሐፎቻቸውን ወይም እርሳሶቻቸውን ወለል ላይ ይጥላሉ። ወይም አስተማሪያቸው ከሚናገረው ነገር አንድም ቃል ሊረዱ እንደማይቸሉ ለማስመሰል ‘ጭጭ’ ይሉ ይሆናል። “ለመቀለድ ብለን ሻጥር እንሠራለን” ይላል ወጣቱ ቦቢ።

ይሁን እንጂ በክፍል ውስጥ ተገቢ ያልሆነ ጠባይ የምታሳዩ ከሆነ ክፉና የጠላትነት መንፈስ የሚያሳይ መምህር ብታፈሩ መደነቅ የለባችሁም። (ከገላትያ 6:​7 ጋር አወዳድሩ።) “ሰዎች ሊያደርጉላችሁ የምትወዱትን ሁሉ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉላቸው” የሚለውን ወርቃማ ሕግ አስታውሱ። (ማቴዎስ 7:​12) በክፍል ውስጥ በሚደረጉ ቀልዶች አትካፈሉ። መምህራችሁ የሚናገረውን ነገር በጥሞና አዳምጡ። ተባባሪዎች ሁኑ። ምናልባት እርሱም ከጊዜ በኋላ ሌላው ቢቀር ተባባሪዎች ለሆናችሁት ለእናንተ የጠላትነት መንፈስ ማሳየቱን ሊቀንስ ይችላል።

አስተማሪዬ አይወደኝም’

አንዳንድ ጊዜ የባሕሪ ግጭት ወይም አንድ ዓይነት አለመግባባት መምህራችሁ በእናንተ ላይ በጠላትነት እንዲነሳ ሊያደርገው ይችላል። ጥያቄ ማብዛታችሁ ከዓመፀኝነት ወይም ደግሞ ገራገር መሆናችሁ ከሞኝነት ሊቆጠርባችሁ ይችላል። መምህራችሁ ከጠላችሁ ደግሞ እናንተን የማሳፈር ወይም የማዋረድ ዝንባሌ ሊኖረው ይችላል። በዚህም ምክንያት በመካከላችሁ ጠላትነት ሊስፋፋ ይችላል።

መጽሐፍ ቅዱስ “ለማንም ስለ ክፉ ፈንታ ክፉን አትመልሱ፤ . . . ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ” ይላል። (ሮሜ 12:​17, 18) መምህራችሁን ላለማስቆጣት ጥረት አድርጉ። አስፈላጊ ካልሆነ ፍጥጫ ራቁ። መምህራችሁ በእናንተ ላይ ቅር ለመሰኘት ምክንያት የሚሆን ነገር እንዲያገኝባችሁ አታድርጉ። እንዲያውም የወዳጅነት መንፈስ ለማሳየት ሞክሩ። ‘የወዳጅነት መንፈስ? ለእርሱ?’ ብላችሁ ትጠይቁ ይሆናል። አዎን፣ ወደ ክፍል በምትገቡበት ጊዜ ለመምህራችሁ አክብሮት የተሞላበት ሰላምታ በመስጠት የታረመ ጠባይ አሳዩ። ሳታቋርጡ የትሕትና ጠባይና፣ አልፎ አልፎም ፈገግታ ማሳየታችሁ መምህራችሁ ስለ እናንተ የነበረውን አስተያየት እንዲለውጥ ሊያደርገው ይችላል።​— ከሮሜ 12:​20, 21 ጋር አወዳድሩ።

እርግጥ ነው፣ ፈገግ የሚያደርግ ሁኔታ ሳይኖር ሁልጊዜ አለ ምክንያት ፈገግ ልትሉ አትችሉም። ይሁን እንጂ መክብብ 10:​4 “ትዕግሥት ታላቁን ኃጢአት ጸጥ ያደርጋልና የገዢ [ወይም ሥልጣን ያለው ሰው] ቁጣ [አንተን ለመቅጣት] የተነሣብህ እንደ ሆነ ስፍራህን አትልቀቅ” በማለት ይመክራል። ‘የለዘበች መልስ ቁጣን የምትመልስ’ መሆኗንም አስታውሱ።​— ምሳሌ 15:​1

ከዚህ የበለጠ ማርክ ሊሰጠኝ ይገባ ነበር’

ይህ በተደጋጋሚ የሚሰማ ስሞታ ነው። ስለ ችግሩ ከመምህራችሁ ጋር ለመነጋገር ሞክሩ። ነቢዩ ናታን ንጉሥ ዳዊት የፈጸመውን ከባድ በደል እንዲያጋልጥ የተሰጠውን አስቸጋሪ ሥራ በብልሃትና በድፍረት እንዴት እንደፈጸመ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። ናታን ለንጉሡ እንዲናገር የተላከውን ወቀሳ ለማንም እየለፈለፈ ወደ ቤተ መንግሥቱ ዘው ብሎ አልገባም። ከዚህ ይልቅ ወደ ንጉሡ በዘዴ ቀረበ።​— 2 ሳሙኤል 12:1–7

እናንተም በተመሳሳይ በትሕትናና በእርጋታ ወደ መምህራችሁ ቀረብ ብላችሁ ለመናገር ትችላላችሁ። መምህር የነበሩት ብሩስ ዌበር “ተማሪ የሚያሳየው ዓመፀኝነት አንድን መምህር እልከኛ እንዲሆን ያደርገዋል። ያዙኝ ልቀቁኝ እያላችሁ ብትደነፉ ወይም ከፍተኛ በደል ተፈጽሞብኛልና እበቀላለሁ ብላችሁ ብትዝቱ የትም አትደርሱም” ብለዋል። ከዚህ ይልቅ በሳል በሆነ መንገድ ለመቅረብ ሞክሩ። ምናልባትም መምህራችሁ የተጠቀመበትን የማርክ አሰጣጥ ዘዴ እንዲያስረዳችሁ በመጠየቅ ልትጀምሩ ትችሉ ይሆናል። ከዚያም፣ ይላሉ ዌበር “መጥፎ አገማገም እንደተደረገባችሁ በመናገር ፈንታ የአሠራር ስህተት ወይም የድምር ስህተት የተደረገባችሁ መሆኑን ለማረጋገጥ ልትሞክሩ ትችላላችሁ። የአስተማሪያችሁን የራሱን የማርክ አሰጣጥ ዘዴ ተጠቀሙ፤ በውጤታችሁ ላይ ስህተት ተሠርቷል የምትሉበትን ቦታ ለመምህራችሁ አሳዩ።” ማርካችሁ ባይለወጥም እንኳን በሳል አቀራረባችሁ የመምህራችሁን አድናቆት ሊያተርፍላችሁ ይችላል።

ለወላጆቻችሁ አሳውቁ

ይሁንና አንዳንድ ጊዜ ከመምህራችሁ ጋር መነጋገሩ ብቻ ፍሬ ቢስ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ ያህል የሱዛንን ተሞክሮ ውሰዱ። ባለ ማዕረግ ተማሪ በመሆኗ ከአስተማሪዎቿ አንዷ በጣም አነስተኛ ማርክ ስትሰጣት ደነገጠች። ችግሩ ምን ነበር? ሱዛን የይሖዋ ምሥክር ነች። አስተማሪዋም ራስዋ እንዳመነችው በዚህ ምክንያት ትጠላት ነበር። “ነገሩ በእርግጥ የሚያበሳጭ ነበር” ትላለች ሱዛን፤ “እናም ምን ማድረግ እንዳለብኝ ግራ ገብቶኝ ነበር።”

ሱዛን ስትናገር “እንደምንም ብዬ ተደፋፈርኩና ስለዚህች መምህር ለእናቴ [ነጠላ ወላጅ ናት] ነገርኳት። እርስዋም ‘እሺ እንግዲህ፣ ምናልባት መምህርሽን ማነጋገር እችል ይሆናል’ አለችኝ። ከዚያም እናቴ የወላጆች ቀን በሚከበርበት ዕለት ሄደችና ችግሩ ምን እንደሆነ መምህሯን ጠየቀቻት። እናቴ ትናደዳለች ብዬ ፈርቼ ነበር፤ ግን አልተናደደችም። መምህሬን ያነጋገረቻት ረጋ ብላ ነበር” ትላለች። አስተማሪዋም ሱዛንን ሌላ አስተማሪ እንዲያስተምራት ዝግጅት አደረገችላት።

በእርግጥ በዚህ ረገድ የሚነሱ ግጭቶች በሙሉ እንዲህ ያለ ጥሩ እልባት ላያገኙ ይችላሉ። አንዳንድ ጊዜም ችላችሁ ከማለፍ በቀር ምንም መፍትሔ ላይኖረው ይችላል። ይሁን እንጂ ይህን የትምህርት ዘመን ከመምህራችሁ ጋር ተቻችላችሁ በሰላም ካሳለፋችሁ በመጪው ዓመት ከአዳዲስ የክፍል ጓደኞችና ከአዳዲስ መምህራን ጋር አዲስ ጅምር ልታደርጉ ትችላላችሁ።

የመወያያ ጥያቄዎች

◻ አድልዎ የሚያደርግባችሁን መምህር እንዴት ልትመለከቱ ትችላላችሁ?

◻ ብዙውን ጊዜ መምህራን ትኩረታቸውን በሙሉ ለሚወዷቸው ተማሪዎች የሚሰጡት ለምንድን ነው?

◻ አሰልቺ መስሎ ከሚታያችሁ መምህር ትምህርት ልታገኙ የምትችሉት እንዴት ነው?

◻ አንዳንድ መምህራን ለተማሪዎቻቸው የጥላቻ መንፈስ ያላቸው መስለው የሚታዩት ለምንድን ነው?

◻ ወርቃማውን ሕግ በክፍል ውስጥ ልትሠሩበት የምትችሉት እንዴት ነው?

◻ በማርክ አሰጣጥ ወይም በአያያዝ አድልዎ የተደረገባችሁ መስሎ ቢታያችሁ ምን ልታደርጉ ትችላላችሁ?

[በገጽ 158 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

መምህሩ ለሚወደው ተማሪ ትኩረት መስጠቱ ብዙውን ጊዜ ሌሎቹን ቅር ያሰኛል

[በገጽ 163 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“በብዙ ከተሞች ባሉ ትምህርት ቤቶች የሚያስተምሩ መምህራን በተማሪዎቻቸው የኃይል እርምጃ እንዳይፈጸምባቸው እየፈሩ ይኖራሉ።”​—ዩ ኤስ ኒውስ ኤንድ ወርልድ ሪፖርት

[በገጽ 160, 161 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

‘መምህሬ ስልችት ያደርገኛል!’

ዘ ፋምሊ ሃንድቡክ ኦቭ አዶለሰንስ የተሰኘው መጽሐፍ “አንዳንድ ጥናቶች አብዛኞቹ ጎረምሳ ተማሪዎች አስተማሪዎቻቸውን አሰልቺ ናቸው ወይም የተጨዋችነት ጠባይ ይጎድላቸዋል እያሉ እንደሚተቿቸው ያሳያሉ” ይላል። ፈጥኖም ይሁን ዘግይቶ እናንተም ምክንያቱን ባታውቁትም ‘እያዛጋችሁ እንባችሁ እስኪፈስ’ ድረስ የሚያሰለች መምህር ያጋጥማችሁ ይሆናል። ታዲያ ምን ልታደርጉ ትችላላችሁ?

በቅርቡ የተደረገ አንድ ሙከራ በአፍላ ጉርምስና የዕድሜ ክልል የሚገኝ አንድ ወጣት ኢንዱስትሪ ነክ፣ የአካል ማሰልጠኛና ሙዚቃ የመሳሰሉትን ትምህርቶች በሚማርበት ጊዜ የሚያሳየው የትኩረት ደረጃ ከፍተኛ እንደሆነ አረጋግጧል። ይሁን እንጂ ቋንቋና ታሪክን በመሳሰሉት ትምህርቶች ላይ የሚታየው የትኩረት ደረጃ በጣም ዝቅተኛ ነው።

የአካል ማሠልጠኛ ወይም የሙዚቃ መምህራን ከቀለም ትምህርት መምህራን የበለጠ ተሰጥዎ አላቸው ማለት ነውን? ላይሆን ይችላል። በግልጽ እንደሚታየው ብዙ ተማሪዎች ስለ ቀለም ትምህርቶች አሉታዊ አመለካከት አላቸው። ተማሪዎች አንድ ትምህርት አሰልቺ ነው ብለው አስቀድመው ከወሰኑ የሶቅራጥስን የመሰለ የማስተማር ችሎታ ያለው መምህርም እንኳን ትኩረታቸውን ለመሳብ ሊያዳግተው ይችላል! ታዲያ መስተካከል ያለበት ለአንዳንድ ትምህርቶች ያላችሁ አፍራሽ አስተሳሰብ ይሆን? ስለምትማሩት ነገር ተጨማሪ ፍላጎት እንዲያድርባችሁ ማድረግ በትምህርት ላይ የሚያጋጥማችሁን መሰላቸት ሊያስወግድላችሁ ይችላል።

አንዳንድ ጊዜ ጥሩ የትምህርት ፍላጎት ያላቸው ተማሪዎችም እንኳን ቢሆኑ “መጥፎ” መምህር አጋጠመን ብለው ያማርራሉ። ይሁን እንጂ “ጥሩ” መምህር እንዴት ያለ ነው? አንዲት ወጣት ልጃገረድ “የሒሳብ አስተማሪዬ ተጫዋች ስለሆነች እወዳታለሁ” ብላለች። አንድ ልጅ ደግሞ የእንግሊዝኛ መምህሩ ‘ብዙ ቀልዶች ስለሚናገር’ አመስግኖታል።

ይሁን እንጂ አንድ መምህር ተወዳጅና አዝናኝ መሆኑ አንድ ጠንካራ ጎን ቢሆንም ‘ለማስተማር የሚበቃ’ ለመሆኑ ምትክ ሊሆን አይችልም። (2 ጢሞቴዎስ 2:​2) መጽሐፍ ቅዱስ እዚህ ላይ የሚናገረው ስለ መንፈሳዊ ብቃት ቢሆንም አንድ መምህር የሚያስተምረውን ትምህርት ማወቅ ያለበት መሆኑን ያጎላል።

የሚያሳዝነው ግን እውቀትና ደስ የሚል ባሕርይ ሁልጊዜ አንድ ላይ የማይገኙ መሆናቸው ነው። ለምሳሌ ያህል ሐዋርያው ጳውሎስ በአምላክ ቃል አስተማሪነቱ ከፍተኛ ብቃት ነበረው። ሆኖም በጳውሎስ ዘመን የነበሩ አንዳንድ ክርስቲያኖች “ሰውነቱ ግን ሲታይ ደካማ ነው፣ ንግግሩም የተናቀ ነው” በማለት ስሞታ አሰምተዋል። ጳውሎስ መልስ ሲሰጥ “በአነጋገሬ ያልተማርሁ [ችሎታ የሌለኝ] ብሆን እንኳ፣ በእውቀት ግን እንዲህ አይደለሁም” ብሏል። (2 ቆሮንቶስ 10:​10፤ 11:​6) አንዳንድ ሰዎች ጳውሎስ አሉበት የተባሉትን ጉድለቶች ብቻ ተመልክተው የተናገረውን ነገር ንቀው ከነበረ ጠቃሚ እውቀት ሳያገኙ ቀርተዋል። ወደ ትምህርት ቤታችሁ ስንመጣም ይህንን ዓይነት ስህተት ከመፈጸም ተቆጠቡ! ስለዚህ መምህራችሁን “መጥፎ” ነው ብላችሁ ከማንኳሰሳችሁ በፊት ‘የሚያስተምረውን ነገር ያውቃልን? ከእርሱ ልማር እችላለሁን?’ ብላችሁ ራሳችሁን ጠይቁ።

ጥሩ ተናጋሪ ላልሆነ መምህር ከወትሮው የበለጠ ትኩረት መስጠት ሊኖርባችሁ ይችላል። ሐሳባችሁ እርሱ በሚናገረው ላይ እንዲያተኩር ለማድረግ ማስታወሻ ለመውሰድ ሞክሩ። ክፍል ውስጥ አሰልቺ የሆነባችሁን ትምህርት እቤታችሁ ተጨማሪ ጥናት በማድረግ አሟሉት።

ራሳቸው መምህርት የሆኑት ባርባራ ማየር እንደሚከተለው በማለት ያክላሉ:- “ምን ያህል እንደ ደጋገሙት ለማስታወስ እስከማይችሉ ድረስ አንዱን ትምህርት ብዙ ጊዜ ደጋግመው ያስተማሩ መምህራን የሚያስተምሩትን ትምህርት የመሰልቸት ባሕርይ ሊታይባቸው ይችላል።” ታዲያ አሰልቺ የሆነባችሁን የትምህርት ክፍለ ጊዜ ሕያው ለማድረግ ምን ልታደርጉ ትችላላችሁ? “ለለውጥ ያህል እጃችሁን አውጡና ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ጠይቁ። . . . መምህራችሁ የሚያውቀውን ሁሉ እንዲነግራችሁ አድርጉ።” መምህሩ በዚህ ቅር ይሰኛልን? ጥያቄ የምታቀርቡት አክብሮት በተሞላበት መንገድ ከሆነ ቅር አይሰኝም። (ቆላስይስ 4:​6) ማየር ሲናገሩ “እንዲህ ብታደርጉ መምህራችሁ ላይ ላዩን ከሚያስተምረው የበለጠ ጠለቅ ያለ ዝግጅት አድርጎ እንደሚመጣ ትገነዘባላችሁ” ይላሉ።

ለማወቅ መጓጓት ከአንዱ ወደሌላው የሚተላለፍ ስሜት ነው። ስለዚህ ለመማር ያላችሁ ፍላጎት ለመምህራችሁ ንቃት ይጨምርለት ይሆናል። እርግጥ መምህራችሁ በጣም ከፍተኛ ለውጥ ያደርጋል ብላችሁ አትጠብቁ። በተጨማሪም በግድ ልትታገሷቸው የሚገቡ አንዳንድ ትምህርቶች ሊኖሯችሁ ይችላሉ። ይሁን እንጂ ጥሩ አድማጮች ከሆናችሁና የሚሰጠውን ትምህርት ለመከታተል ፍላጎት ካላችሁ አሰልቺ ከሆነ መምህርም እንኳ ትምህርት ልታገኙ ትችላላችሁ።

[በገጽ 162 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በትምህርት ቤት እየጨመረ የሚሄደው የዓመፅ ማዕበል የመምህርነትን ሥራ አስቸጋሪ አድርጎታል

[በገጽ 164 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

አንድ ዓይነት የፍትሕ መጓደል እንደተፈጸመባችሁ ከተሰማችሁ በአክብሮት ወደ መምህራችሁ ቀርባችሁ ተነጋገሩ