በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከጋብቻ በፊት ወሲብ እንድፈጽም ብጠየቅ እንዴት እምቢ ማለት እችላለሁ?

ከጋብቻ በፊት ወሲብ እንድፈጽም ብጠየቅ እንዴት እምቢ ማለት እችላለሁ?

ምዕራፍ 24

ከጋብቻ በፊት ወሲብ እንድፈጽም ብጠየቅ እንዴት እምቢ ማለት እችላለሁ?

ቲን በተባለ መጽሔት ላይ የቀረበ አንድ ብሔር አቀፍ ጥናት የሚበዙት ወጣት አንባቢዎቹ “ወሲብ እንዲፈጽሙ ግፊት ሲደረግባቸው እምቢ የሚባለው እንዴት ነው?” ለሚለው ጥያቄ መልስ ለማግኘት እንደፈለጉ ገልጿል።

መዝሙራዊውም በመዝሙር 119:​9 (አዓት) ላይ እንደሚከተለው በማለት ተመሳሳይ ጥያቄ አቅርቦ ነበር:- “ጎልማሳ መንገዱን በምን ያነጻል?” መልሱ:- “በቃልህ መሠረት ተጠንቅቆ በመኖር ነው።” ይሁን እንጂ እንዲህ ለማድረግ የአእምሮ እውቀት ማግኘት ብቻውን አይበቃም። አንዲት ወጣት “በአእምሯችሁ መጽሐፍ ቅዱስ ከሥነ ምግባር ውጭ ስለሆነ ወሲብ ምን እንደሚል ታውቃላችሁ” በማለት ተናግራለች። “ይሁን እንጂ ልባችሁ እነዚህን ምክንያቶች ወደ አእምሯችሁ ጀርባ መገፍተሩን ይቀጥላል” ብላለች። ስለዚህ መዝሙራዊው ቀጥሎ “አንተን እንዳልበድል፣ ቃልህን በልቤ ሰወርሁ” ብሎ መናገሩ ተገቢ ነበር።​— መዝሙር 119:11

ልባችሁን ጠብቁ

የአምላክን ቃል በልባችሁ ለመሰወር ከሁሉ አስቀድሞ ቅዱሳን ጽሑፎችንና በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረቱ ጽሑፎችን ማንበብና ማጥናት ያስፈልጋችኋል። ይህም የአምላክ ሕጎች ጠቃሚ ስለመሆናቸው እርግጠኛ እንድትሆኑ ሊረዳችሁ ይችላል። በሌላ በኩል ግን የወሲብ ፍላጎት የሚቀሰቅሱ ሐሳቦች የያዙ ነገሮችን ማንበብ፣ ማዳመጥ፣ ወይም መመልከት “ፍትወት” ያነሳሳል። (ቆላስይስ 3:​5) ስለዚህ እንደዚህ ካሉት ነገሮች ፈጽማችሁ ራቁ! በዚህ ፈንታ ንጹሕ የሆኑትን ነገሮች አሰላስሉ።

በተጨማሪም የቅርብ ጓደኞች በንጽሕና በመቆየት ወይም ባለመቆየት ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ እንደሚኖራቸው በጥናት ተረጋግጧል። መዝሙራዊው “እኔ ለሚፈሩህ ሁሉ፣ ትእዛዝህንም ለሚጠብቁ ባልንጀራ ነኝ” በማለት ተናግሯል።​— መዝሙር 119:63

ታዲያ ጓደኞቻችሁ ‘የአምላክን ትእዛዞች ለመጠበቅ’ ከልብ ጥረት የሚያደርጉ ናቸውን? ጆአና የምትባል አንዲት ወጣት የጓደኞች ምርጫን በሚመለከት የሚከተለውን ነገር ታዝባለች:- “ይሖዋን ከሚወዱ ሰዎች ጋር ከሆናችሁ ስለ ሥነ ምግባር በምትነጋገሩበት ጊዜ ልክ እነርሱ እንደሚሰማቸው ዓይነት ስሜት ሊሰማችሁ እንደጀመረ ትገነዘባላችሁ። ለምሳሌ ያህል የጾታ ብልግና አስጸያፊ እንደሆነ ሲናገሩ ብትሰሙ እናንተም እንደዚያው ሊሰማችሁ ይጀምራል። በሌላ በኩል ግን ስለ ጾታ ሥነ ምግባር ደንታ ከሌለው ሰው ጋር ከሆናችሁ ወዲያውኑ እንደ እርሱ ትሆናላችሁ።”​— ምሳሌ 13:20

ይሁን እንጂ ብዙውን ጊዜ በንጽሕና መቆየትን ፈተና ላይ የሚጥል ሁኔታ የሚፈጥረው ከተቃራኒ ጾታ ጋር ለመጫወት መቀጣጠርና እርስ በርስ ለመጠናናት ተብሎ የሚደረገው ቅርርብ ነው። በሮበርት ሶርንሰን የተደረገውን ብሔር አቀፍ ጥናት ተመልከቱ። እኚህ ሰው ጥናት ከተደረገባቸው የጾታ ግንኙነት የፈጸሙ ወጣቶች መካከል 56 በመቶዎቹ ወንዶችና 82 በመቶዎቹ ሴቶች ለመጀመሪያ ጊዜ ሩካቤ ሥጋ የፈጸሙት አዘውትረው አብረውት ከሚውሉት ወይም ቢያንስ ቢያንስ በጣም ከሚያውቁትና ከሚወዱት ሰው ጋር መሆኑን ከጥናታቸው ተረድተዋል። ታዲያ ስለ ጋብቻ ለማሰብና ከተቃራኒ ጾታ ጋር እየተቀጣጠራችሁ ለመጫወት ወደሚያስችል ዕድሜ ከደረሳችሁ ምን ማድረግ ይኖርባችኋል? ክብረ ንጽሕናችሁን ጠብቃችሁ ለማግባት ካሰባችሁት ሰው ጋር በሚገባ ለመተዋወቅ የምትችሉት እንዴት ነው?

ለጋብቻ ለመጠናናት ብላችሁ በምትቀራረቡበት ጊዜ የሚያጋጥሙ አደጋዎችን ማስወገድ

መጽሐፍ ቅዱስ “የሰው ልብ ከሁሉ ይልቅ ተንኮለኛ እጅግም ክፉ ነው፤ ማንስ ያውቀዋል?” በማለት ያስጠነቅቃል። (ኤርምያስ 17:​9) አንድ ሰው ተቃራኒ ጾታ ላለው ሌላ ሰው በጣም ጤናማ የሆነ የተፈጥሮ መሳሳብ ሊሰማው ይችላል። ይሁን እንጂ እርስ በርስ ይበልጥ እየተቀራረባችሁ በሄዳችሁ መጠን ያ መሳሳብ እየጨመረ ይሄዳል። ይህ ተፈጥሯዊ የሆነ የመቀራረብ ፍላጎት ደግሞ ልባችሁን ሊያስተው ይችላል። “ከልብ ክፉ አሳብ፣  . . . ዝሙት ይወጣልና” በማለት ኢየሱስ ክርስቶስ ተናግሯል።​— ማቴዎስ 15:​19

ብዙውን ጊዜ አንድ ወንድና አንዲት ሴት የጾታ ግንኙነት ለመፈጸም አቅደው አይነሱም። * አብዛኛውን ጊዜ ይህ ሁኔታ የሚደርሰው ወንዱና ሴቷ በመተቃቀፍ፣ ወይም ደግሞ በመተሻሸት የፍትወት ስሜታቸውን ስለሚቀሰቅሱ ነው። ባል ሳታገባ ልጅ የወለደች አንዲት እናት እንደሚከተለው በማለት ጥፋቷን አምናለች:- “ለእኔና ለማውቃቸው ለብዙዎቹ ሴቶች ልጆች ሁኔታው በየጊዜው ጥቂት በጥቂት ከገደብ አልፎ የመሄድ ጉዳይ ነበር። ከዚያም ሳይታወቃችሁ ድንግልናችሁን ታጣላችሁ። ትንሽ መደባበስ ትጀምሩና ሳታውቁት ልታቆሙ የማትችሉበት ደረጃ ላይ ትደርሳላችሁ።”

ወደ ጾታ ብልግና እንዳትወድቁ ልባችሁ እንዲመራችሁ ከመፍቀድ ይልቅ እናንተ ልባችሁን መምራት ይኖርባችኋል። (ምሳሌ 23:​19) ይህን ልታደርጉ የምትችሉት እንዴት ነው?

ገደብ አብጁ፦ አንድ ወጣት ሰው የሴት ጓደኛው መሳምና መደባበስ እንዲጀምር የምትጠብቅበት ሊመስለው ይችላል። እርስዋ ግን ፈጽሞ ይህን አላሰበች ይሆናል። “እብሪተኛነት ሁከትን ይፈጥራል፤ ምክርን መጠየቅ ግን ብልኅነት ነው።” (ምሳሌ 13:​101980 ትርጉም።) ስለዚህ ተቃራኒ ጾታ ካለው ሰው ጋር ለመጫወት የምትቀጣጠሩ ከሆነ ‘አብራችሁ በመመካከር’ የተቀጣጠራችሁት ሰው ስለ ጉዳዩ ያላችሁን ስሜት እንዲያውቅ አድርጉ። ፍቅርን ለመግለጽ በሚደረጉ ነገሮች ላይ ገደብ ማበጀት ጥበብ ነው። ከዚህም በተጨማሪ አሳሳች ፍንጮችን አትስጡ። የሚያጣብቅ ልብስ መልበስ፣ ሰውነትን ማጋለጥ፣ የወሲብ ስሜት የሚቀሰቅሱ ልብሶች መልበስ ለጓደኛችሁ የተሳሳተ መልእክት ሊያስተላልፉ ይችላሉ።

ፈተና ላይ ከሚጥሉ ሁኔታዎች ራቁ፦ መጽሐፍ ቅዱስ የወንድ ጓደኛዋ ራቅ ወዳሉ ተራራዎች አብራው ሽርሽር እንድትሄድ ስለጋበዛት አንዲት ወጣት ድንግል ይናገራል። ይህን ግብዣ እንዲያቀርብ ያነሳሳው ምን ነበር? በጸደይ ወራት መግቢያ ላይ ባለው ውበት አብረው እንዲደሰቱ ነበር። ይሁን እንጂ የልጃገረዲቱ ወንድሞች ይህን የታሰበውን ሽርሽር ደረሱበትና ተቆጥተው እንዳትሄድ ከለከሏት። ይህን ያደረጉት ለመባለግ ፍላጎት አላት ብለው አስበው ነበርን? በጭራሽ አልነበረም። ይሁን እንጂ በእንዲህ ዓይነቱ ሁኔታ ሥር ሊያጋጥም የሚችለው ፈታኝ ሁኔታ ያለውን ኃይል አሳምረው ያውቁ ነበር። (መኃልየ መኃልይ 1:​6፤ 2:​8–15) እናንተም በተመሳሳይ አብራችሁት ለመጫወት ከቀጠራችሁት ተቃራኒ ጾታ ያለው ሰው ጋር በቤት፣ በአፓርታማ፣ ወይም በቆመ መኪና ውስጥ ብቻችሁን የምትሆኑበትን ወደ ፈተና ሊያመራ የሚችል ሁኔታ ማስወገድ ይኖርባችኋል።

አቅማችሁን እወቁ፦ ከሌሎች ጊዜያት ይበልጥ ወሲባዊ ግንኙነት እንድትፈጽሙ ለሚያነሳሷችሁ ፈታኝ ሁኔታዎች በቀላሉ ልትሸነፉ የምትችሉባቸው ጊዜያት አሉ። ለምሳሌ ያህል የግል ጉዳያችሁ ሳይሳካ ቀርቶ ወይም ከወላጆቻችሁ ጋር አለመግባባት አጋጥሟችሁ አዝናችሁ ይሆናል። ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን እንደዚህ ያለ ብስጭት በሚያጋጥማችሁ ጊዜ ከምንጊዜውም የበለጠ ጠንቃቆች መሆን ይኖርባችኋል። (ምሳሌ 24:​10) በተጨማሪም የአልኮል መጠጦችን በመጠጣት ረገድ ጥንቃቄ አድርጉ። የሚያሰክሩ መጠጦችን በጠጣችሁ ጊዜ የይሉኝታ ስሜታችሁን ልታጡ ትችላላችሁ። “ወይንና አዲስ የወይን ጠጅ ቀናውን አስተሳሰብ ያጠፋል።”​— ሆሴዕ 4:​11 አዓት

በቁርጠኝነት እምቢ በሉ፦ አንድ ወንድና አንዲት ሴት ስሜታቸው ተጋግሎ አደገኛ በሆነ ሁኔታ እንደተቀራረቡ በሚገነዘቡበት ጊዜ ምን ማድረግ ይችላሉ? ከሁለት አንዳቸው ሁኔታውን ሊለውጥ የሚችል ነገር መናገር ወይም ማድረግ ይኖርባቸዋል። ዴብራ አብራው ለመጫወት ከቀጠረችው ሰው ጋር ብቻዋን ሳለች “እናውራ” ብሎ መኪናውን ጭር ባለ ቦታ አቆመ። ስሜታቸው እየተለወጠ ሲመጣ ዴብራ ለሰውየው “ይህ መተሻሸት አይደለም እንዴ? ማቆም የለብንም?” አለችው። ይህም የነበሩበትን የተጋጋለ ሁኔታ ለወጠው። እሱም ወዲያውኑ ወደ ቤቷ ወሰዳት። እንደዚህ በመሰሉት ሁኔታዎች እምቢ ማለት ምናልባት ከዚህ በፊት ማድረግ ከነበረባችሁ ነገር ሁሉ የከበደ ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ ለወሲባዊ ግንኙነት የተሸነፈች አንዲት የ20 ዓመት ሴት እንደተናገረችው “ትታችሁ ካልሄዳችሁ በኋላ ይቆጫችኋል!” ብላለች።

ታዛቢ አስከትሉ፦ አብራችሁ ለመጫወት በምትቀጣጠሩበት ጊዜ ተገቢ ያልሆነ ነገር እንዳታደርጉ ሊጠብቃችሁ የሚችል ታዛቢ ማስከተል በአንዳንድ ሰዎች ጊዜ እንዳለፈበት ነገር ተደርጎ ቢታይም እስከ አሁን ድረስ ጠቃሚ ሆኖ ተገኝቷል። አንዳንድ ተጓዳኝ ወንዶችና ሴቶች “እምነት ሊጣልብን የማንችል ያስመስላል” በማለት ቅሬታቸውን ያሰማሉ። ምናልባት ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ ራስን ማመኑስ ጥበብ ነውን? ምሳሌ 28:​26 (አዓት) ግልጽ በሆነ መንገድ “በገዛ ልቡ የሚታመን ሰው ሞኝ ነው፤ በጥበብ የሚመላለስ ሰው ግን ከጉዳት ያመልጣል” በማለት ይናገራል። ስለዚህ ከተቃራኒ ጾታ ጋር ለመጫወት በምትቀጣጠሩበት ጊዜ አንድ ታዛቢ አስከትላችሁ በመሄድ በጥበብ ተመላለሱ። ዴብራ ስትናገር “ታዛቢ አስከትሎ የሚመጣን ሰው በእርግጥ አከብራለሁ። እኔ ንጽሕናዬን ለመጠበቅ ፍላጎት ያለኝን ያህል እሱም ንጽሕናውን ለመጠበቅ ፍላጎት ያለው መሆኑን አውቃለሁ” በማለት ገልጻለች። “ታዛቢ ማስከተሉ ምንም ችግር የለውም። ምክንያቱም ለብቻችን የምንነጋገረው ነገር ካለ ገለል ብለን ልንነጋገር እንችላለን። እንዲህ ማድረጉ የሚያስገኘው ጥበቃ እንደፈለግን ለመሆን ባለመቻላችን ከሚደርስብን ችግር እጅግ ይሻላል” በማለት አክላ ተናግራለች።

ከአምላክ ጋር ወዳጅነት መመሥረት

ከሁሉ በላይ ከአምላክ ጋር የተቀራረበ ወዳጅነት መመሥረት፣ እርሱ ስሜት ያለው እውን የሆነ አካል እንደሆነ ማወቅ አምላክን የሚያስቀይመውን ጠባይ እንድታስወግዱ ይረዳችኋል። ስላሉባችሁ ችግሮች ለይታችሁ ለእርሱ በመናገር ልባችሁን ማፍሰስ ከእርሱ ጋር ይበልጥ ያቀራርባችኋል። በንጽሕና ለመቆየት የሚፈልጉ ብዙ ወንዶችና ሴቶች በስሜት በተጋጋሉበት ወቅት አስፈላጊውን ብርታት እንዲሰጣቸው በመጠየቅ አብረው ወደ አምላክ ጸልየዋል።

ይሖዋ እንደዚህ የመሰለ ጸሎት ለሚያቀርቡለት ሰዎች “ከተለመደው በላይ የሆነ ኃይል” በልግስና በመስጠት ጸሎታቸውን ይመልስላቸዋል። (2 ቆሮንቶስ 4:​7 አዓት) በእርግጥ እናንተም የበኩላችሁን ማድረግ ይኖርባችኋል። ሆኖም በአምላክ እርዳታና በረከት የጾታ ብልግና እንድትፈጽሙ ለሚደረግባችሁ ተጽእኖና ፈተና እምቢ ማለት እንደሚቻል እርግጠኞች ሁኑ።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.12 አንድ ጥናት እንደገለጸው ድርጊቱ ቅጽበታዊና አስቀድሞ ያልታቀደ መሆኑን 60 በመቶ የሚሆኑት ሴቶች ተናግረዋል።

የመወያያ ጥያቄዎች

◻ ወሲብን በሚመለከት የይሖዋን ሕጎች በልባችሁ ለመሰወር እንድትችሉ የሚረዷችሁና እናንተ ልታደርጓቸው የምትችሏቸው አንዳንድ ነገሮች ምንድን ናቸው?

◻ ከጋብቻ በፊት የጾታ ግንኙነት ስለ መፈጸም ያላችሁ አመለካከት በጓደኞቻችሁ ሊነካ የሚችለው እንዴት ነው?

◻ ከተቃራኒ ጾታ ጋር ለመጫወት በምትቀጣጠሩበት ጊዜ ጥንቃቄ ማድረግ አስፈላጊ እንደሆነ የሚሰማችሁ ለምንድን ነው?

◻ ለጋብቻ ለመጠናናት ብለው የሚቀራረቡ ወንዶችና ሴቶች ወደ ጾታ ብልግና እንዳይወድቁ ራሳቸውን ለመጠበቅ ሊያደርጓቸው የሚችሉ አንዳንድ ነገሮች ምንድን ናቸው?

[በገጽ 193 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“ትንሽ መደባበስ ትጀምሩና . . .”

[በገጽ 194 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

ለጋብቻ ለመጠናናት ብላችሁ በምትቀራረቡበት ጊዜ ራሳችሁን ከሌሎች ሰዎች ባለመነጠል የጾታ ብልግና ከመፈጸም ራቁ

[በገጽ 195 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

ተቃራኒ ጾታ ያላቸው ወጣቶች እየተቀጣጠሩ በሚጫወቱበት ጊዜ በንጽሕና መቆየት

ወደ መተሻሸትና መደባበስ ሊያመሩ ከሚችሉ ሁኔታዎች ራቁ

በቡድን መሃል ሆናችሁ ለመጫወት ተቀጣጠሩ አለዚያም ታዛቢ አስከትሉ

ጭውውታችሁ በሚያንጹ ነገሮች ላይ ያተኮረ እንዲሆን አድርጉ

ከመጀመሪያው ተጓዳኛችሁ በፍቅር መግለጫዎች ረገድ ሊኖር ስለሚገባው ገደብ ያላችሁን አመለካከት እንዲያውቅ/እንድታውቅ አድርጉ

አለባበሳችሁ ልከኝነትን የሚያንጸባርቅ ይሁን፣ ተገቢ ያልሆነ ስሜት የሚቀሰቅሱ ተግባሮችን አስወግዱ

ንጽሕናሽ አደገኛ ሁኔታ ላይ ሊወድቅ እንደተቃረበ ከተሰማሽ ወደ ቤት እንዲወስድሽ ጠይቂ

የ“ደህና እደሩ” ስንብታችሁን ከማስረዘም ተቆጠቡ

አታምሹ

[ሥዕል]

ጥናታዊ ቅርርብ የሚያደርጉ ተጓዳኞች ከሌሎች ሰዎች እንዲነጠሉ በማያደርጓቸው ነገሮች አብረው ለመካፈል ዕቅድ ሊያወጡ ይችላሉ

[ገጽ 196 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሁኔታው በጣም “የተጋጋለ” ከሆነ እምቢ ለማለት ድፍረት ይኑራችሁ! ይህንን ስትሉም ከምር መሆኑ ይታወቅ!