በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መከራና ግፍ የበዛው ለምንድን ነው?

መከራና ግፍ የበዛው ለምንድን ነው?

ክፍል 6

መከራና ግፍ የበዛው ለምንድን ነው?

1, 2. በሰው ልጅ ላይ ከደረሱት ሁኔታዎች አንጻር ምን ጥያቄዎች ሊነሱ ይችላሉ?

1 ይሁን እንጂ የሁሉ የበላይ የሆነው አካል ፍጹም የሆኑ ሰዎች በምድር ላይ በገነት ለዘላለም እንዲኖሩ ዓላማ ከነበረውና ይህ ዓላማው አሁንም ካልተለወጠ በአሁኑ ጊዜ ገነት የሌለው ለምንድን ነው? ከዚህ ይልቅ የሰው ልጅ ለብዙ መቶ ዘመናት መከራና ግፍ ሲደርስበት የኖረው ለምንድን ነው?

2 ጦርነት፣ የኢምፔሪያሊዝም ወረራ፣ ብዝበዛ፣ ግፍ፣ ድህነት፣ አደጋ፣ በሽታና ሞት ባስከተሏቸው መዘዞች የተነሳ የሰው ልጅ ታሪክ በመከራና ሥቃይ እንደተሞላ ምንም አያጠያይቅም። ንጹሐን በሆኑ ብዙ ሰዎች ላይ ብዙ ዓይነት መጥፎ ነገሮች የሚደርሱት ለምንድን ነው? አምላክ ሁሉን ማድረግ የሚያስችል ኃይል ካለው ይህ ሁሉ መከራ ለብዙ ሺህ ዓመታት እንዲቀጥል የፈቀደው ለምንድን ነው? አምላክ አጽናፈ ዓለምን በጣም ግሩም በሆነ መንገድ የነደፈና በሥርዓት ያደራጀ እንደመሆኑ መጠን በምድር ላይ ዝብርቅና ጥፋት እንዲደርስ ለምን ፈቀደ?

አንድ ምሳሌ

3-5. (ሀ) የሥርዓት አምላክ በምድር ላይ ዝብርቅ እንዲኖር የፈቀደው ለምን እንደሆነ እንድንገነዘብ ሊረዳን የሚችለው የትኛው ምሳሌ ነው? (ለ) ከቀረቡት አማራጮች መካከል ምድር ካለችበት ሁኔታ ጋር የሚመሳሰለው የትኛው ነው?

3 የሥርዓት አምላክ በምድር ላይ ዝብርቅ እንዲኖር የፈቀደው ለምን እንደሆነ ለማስረዳት አንድ ምሳሌ እንጠቀም። በአንድ ጫካ ውስጥ ስትጓዝ አንድ ቤት አገኘህ እንበል። ጠጋ ብለህ ስትመለከት ቤቱ ትርምስምሱ ወጥቷል። መስኮቶቹ ተሰባብረዋል፣ ጣሪያው ተበሳስቷል፣ ከእንጨት የተሠራው በረንዳ ውልቅልቁ ወጥቷል፣ በሩ በአንድ ማጠፊያ ብቻ ተንጠልጥሏል፣ በተጨማሪም የቧንቧው መስመር በሙሉ ከጥቅም ውጪ ሆኗል።

4 እነዚህን ሁሉ ጉድለቶች ስትመለከት ይህን ቤት የነደፈው ጥሩ ችሎታ ያለው ንድፍ አውጪ አይደለም ብለህ ትደመድማለህን? ቤቱ ትርምስምሱ መውጣቱ ይህ ቤት እንዲሁ በአጋጣሚ የተገኘ መሆን አለበት የሚል እምነት ያሳድርብሃልን? ወይም ደግሞ አንድ ሰው የነደፈውና የገነባው መሆን አለበት ብለህ ከደመደምክ ይህ ሰው ችሎታ የሌለውና አሳቢነት የጎደለው እንደሆነ ይሰማሃል?

5 ጠጋ ብለህ መዋቅሩን ይበልጥ በጥንቃቄ ስትመረምር በመጀመሪያ ግሩም በሆነ መንገድ እንደተገጣጠመና በጥንቃቄ ታስቦበት እንደተሠራ ትገነዘባለህ። ሆኖም አሁን እየፈራረሰ ነው። ጉድለቶቹና ያሉት ችግሮች ምን ሊያመለክቱ ይችላሉ? (1) ባለቤቱ እንደሞተ፤ (2) ጥሩ ችሎታ ያለው ግንበኛ ቢሆንም ቤቱን እንደተወው፤ ወይም ደግሞ (3) ቤቱን ለጊዜው ግዴለሽ ለሆኑ ተከራዮች እንዳከራየው ሊያመለክቱ ይችላሉ። መጨረሻ ላይ የተጠቀሰው ምድር ካለችበት ሁኔታ ጋር የሚመሳሰል ነው።

ችግር የፈጠረው ነገር

6, 7. አዳምና ሔዋን የአምላክን ሕግ ሲጥሱ ምን ደረሰባቸው?

6 የአምላክ ዓላማ ሰዎች እንዲሠቃዩ ወይም እንዲሞቱ እንዳልነበረ የጥንቱ የመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባ ይገልጽልናል። የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን አዳምና ሔዋን የሞቱት አምላክን ስላልታዘዙ ብቻ ነበር። (ዘፍጥረት ምዕራፍ 2 እና 3) የአምላክን ትእዛዝ በጣሱ ጊዜ ፈቃዱን ማድረግ አቆሙ። ከአምላክ ጥበቃ ሥር ወጡ። “የሕይወት ምንጭ” ከሆነው አምላክ ጋር ተቆራረጡ ማለት ነው።​—መዝሙር 36:9

7 ከኃይል ምንጩ ጋር የነበረው ግንኙነት የተቋረጠ አንድ መሣሪያ እየቀዘቀዘ ሄዶ ሥራውን እንደሚያቆም ሁሉ አካላቸውና አእምሯቸው ቀስ በቀስ እየተበላሸ መሄድ ጀመረ። በዚህም ምክንያት አዳምና ሔዋን እያሽቆለቆሉ ሄዱ፣ አረጁ፣ በመጨረሻም ሞቱ። ከዚያ በኋላ ምን ሆነ? ወደመጡበት ተመለሱ:- “አፈር ነህና፣ ወደ አፈርም ትመለ ሳለህ።” አምላክ ሕጉን አለማክበር ሞት እንደሚያስከትል በመግለጽ “ሞትን ትሞታለህ” ብሎ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷቸው ነበር።​—ዘፍጥረት 2:17፤ 3:19

8. የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን የፈጸሙት ኃጢአት ሰብዓዊውን ቤተሰብ የነካው እንዴት ነው?

8 የሞቱት የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን ብቻ አይደሉም፤ ዘሮቻቸው በሙሉ ማለትም መላው የሰው ዘርም የሞት ባሪያ ሆኗል። ይህ የሆነው ለምንድን ነው? በዘር ውርስ ሕግ መሠረት ልጆች የወላጆቻቸውን ባሕርያት ስለሚወርሱ ነው። የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን ልጆች በሙሉ ደግሞ አለፍጽምናንና ሞትን ወርሰዋል። ሮሜ 5:12 እንዲህ ሲል ይገልጽልናል:- “ኃጢአት በአንድ ሰው [የሰው ልጆች አባት በሆነው በአዳም] ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት፣ እንደዚሁም ሁሉ [አለፍጽምናን ማለትም የኃጢአት ዝንባሌዎችን በመውረሳቸው] ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ።” ሰዎች ኃጢአት፣ አለፍጽምናና ሞት ከመጀመሪያው ጀምሮ የነበሩ ነገሮች ስለሚመስሏቸው ተፈጥሮአዊና ሊወገዱ የማይችሉ ነገሮች እንደሆኑ ይሰማቸዋል። ሆኖም የመጀመሪያዎቹ ሰዎች የተፈጠሩት ለዘላለም የመኖር ብቃትና ፍላጎት እንዲኖራቸው ተደርጎ ነው። አብዛኞቹ ሰዎች ሕይወታቸው በሞት ሳቢያ በአጭር የሚቀጭ መሆኑ የሚያበሳጫቸው ለዚህ ነው።

ይህን ያህል ረጅም ጊዜ ለምን አስፈለገ?

9. አምላክ መከራ ለረጅም ጊዜ እንዲቀጥል የፈቀደው ለምንድን ነው?

9 አምላክ ሰዎች በራሳቸው መንገድ እንዲሄዱ ይህን ያህል ረጅም ጊዜ የፈቀደው ለምንድን ነው? ለዚህን ያህል ብዙ መቶ ዘመን መከራ እንዲቀጥል የፈቀደው ለምንድን ነው? አንዱ ዐቢይ ምክንያት የሚከተለው አንገብጋቢ የሆነ አከራካሪ ጉዳይ በመነሳቱ ነው:- የመግዛት መብት ያለው ማን ነው? ሰዎችን መግዛት ያለበት አምላክ ነው ወይስ ያለ እርሱ እርዳታ ሰዎች ራሳቸውን ስኬታማ በሆነ መንገድ ማስተዳደር ይችላሉ?

10. ሰዎች ምን ችሎታ ተሰጧቸዋል? ከምን ኃላፊነትስ ጋር?

10 ሰዎች ሲፈጠሩ ነፃ ምርጫ ማለትም የመምረጥ ችሎታ ተሰጥቷቸዋል። አፈጣጠራቸው ከሮቦቶች ወይም ደግሞ አብዛኛውን ጊዜ በተፈጥሮ በውስጣቸው በተቀረጸው ዝንባሌ ከሚመሩት እንስሳት የተለየ ነው። ስለዚህ ሰዎች ማንን ማገልገል እንደሚፈልጉ መምረጥ ይችላሉ። (ዘዳግም 30:19፤ 2 ቆሮንቶስ 3:17) ስለዚህ የአምላክ ቃል የሚከተለውን ምክር ይሰጣል:- “አርነት ወጥታችሁ እንደ እግዚአብሔር ባሪያዎች ሁኑ እንጂ ያ አርነት ለክፋት መሸፈኛ እንዲሆን አታድርጉ።” (1 ጴጥሮስ 2:16) ይሁን እንጂ ሰዎች ምንም እንኳ በጣም ግሩም ስጦታ የሆነውን የመምረጥ ነፃነት ያገኙ ቢሆንም የመረጡት ነገር የሚያስከትለውን ውጤት መቀበል አለባቸው።

11. ከአምላክ ራስን በማግለል በተሳካ ሁኔታ መኖር ይቻል እንደሆነና እንዳልሆነ ማወቅ የሚቻልበት ብቸኛ መንገድ ምንድን ነው?

11 የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን የተሳሳተ ምርጫ አድርገዋል። ራሳቸውን ከአምላክ ለማግለል መርጠዋል። እርግጥ አምላክ የመጀመሪያዎቹን ዓመፀኛ ባልና ሚስት ነፃ ምርጫቸውን አላግባብ ከተጠቀሙ በኋላ ወዲያውኑ ሊያጠፋቸው ይችል ነበር። ሆኖም ይህ እርምጃ አምላክ ሰዎችን ለመግዛት ያለውን መብት በተመለከተ ለተነሣው ጥያቄ እልባት አያስገኝም። የመጀመሪያዎቹ ባልና ሚስት ራሳቸውን ከአምላክ ለማግለል ስለፈለጉ ‘ይህ ምርጫ ደስተኛና ስኬታማ የሆነ ሕይወት ሊያስገኝ ይችላልን?’ ለሚለው ጥያቄ መልስ መገኘት አለበት። ምር​ጫቸው እስከሆነ ድረስ ለዚህ ጥያቄ መልስ እንዲገኝ የግድ የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችንና ልጆቻቸው በራሳቸው መንገድ እንዲሄዱ መፍቀድ ያስ​ፈልጋል። ሰዎች ራሳቸውን ከፈጣሪያቸው በማግለል ስኬታማ በሆነ መንገድ ራሳቸውን ማስተዳደር ይችሉ እንደሆነና እንዳልሆነ ጊዜ የሚያሳየው ነገር ሆነ።

12. ኤርምያስ የሰውን አገዛዝ ውጤት የገለጸው እንዴት ነው? ይህ የሆነውስ ለምንድን ነው?

12 የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊ የሆነው ኤርምያስ ውጤቱ ምን እንደሚሆን አውቆ ነበር። በኃያሉ የአምላክ ቅዱስ መንፈስ ወይም አንቀሳቃሽ ኃይል መሪነት እንዲህ ሲል ሐቁን ጽፏል:- “አቤቱ፣ የሰው መንገድ ከራሱ እንዳይደለ አውቃለሁ፣ አካሄዱንም ለማቅናት ከሚራመድ ሰው አይደለም። አቤቱ፣ ቅጣኝ።” (ኤርምያስ 10:23, 24) ሰዎች የአምላክ ሰማያዊ ጥበብ አመራር የግድ እንደሚያስፈልጋቸው ተገንዝቦ ነበር። ይህ የሆነው ለምንድን ነው? በአጭሩ አምላክ ሰዎች ከእሱ አመራር ውጪ ስኬታማ በሆነ መንገድ እንዲኖሩ አድርጎ ስላልፈጠራቸው ነው።

13. ባለፉት ብዙ ሺህ ዓመታት የሰው ልጅ አገዛዝ ያስከተላቸው ውጤቶች በማያሻማ መንገድ ያረጋገጡት ነገር ምንድን ነው?

13 የሰው ልጅ በገዛባቸው ብዙ ሺህ ዓመታት የተገኙት ውጤቶች የሰው ልጆች የራሳቸውን ጉዳዮች ከፈጣሪያቸው ውጪ በራሳቸው መምራት እንደማይችሉ በማያሻማ መንገድ አረጋግጧል። ያደረጉት ሙከራ ላስከተለው አስከፊ ውጤት ተጠያቂዎቹ ራሳቸው ናቸው። መጽሐፍ ቅዱስ ይህን ቁልጭ አድርጎ ገልጾታል:- “[አምላክ] ሥራውም ፍጹም ነው፤ መንገዱም ሁሉ የቀና ነው፤ የታመነ አምላክ፣ ክፋትም የሌለበት፣ እርሱ እውነተኛና ቅን ነው። እነርሱ ረከሱ፤ ልጆቹም አይደሉም፤ ነውርም አለባቸው።”​—ዘዳግም 32:4, 5

አምላክ በቅርቡ ጣልቃ ይገባል

14. አምላክ በሰው ልጆች ጉዳዮች ውስጥ ጣልቃ የሚገባበትን ጊዜ ከዚህ በኋላ የማያዘገየው ለምንድን ነው?

14 አምላክ የሰው ልጅ አገዛዝ ስኬታማ እንዳልሆነ ለብዙ መቶ ዘመናት በሚገባ በተግባር እንዲታይ ያደረገ በመሆኑ አሁን በሰው ልጅ ጉዳዮች ውስጥ ጣልቃ በመግባት መከራን፣ ሐዘንን፣ በሽታንና ሞትን ያስቀራል። አምላክ ሰዎች በሳይንስ፣ በኢንዱስትሪ፣ በሕክምናና በሌሎች መስኮች ከፍተኛ የእድገት ደረጃዎቻቸው ላይ እንዲደርሱ የፈቀደ በመሆኑ ከዚህ በኋላ ሰዎች ከፈጣሪያቸው ራሳቸውን አግልለው በራሳቸው ሰላም የሰፈነበት ገነታዊ ዓለም ማምጣት ይችሉ እንደሆነና እንዳልሆነ እንዲያሳዩ ሌሎች ብዙ መቶ ዘመናት መፍቀድ አያስፈልገውም። እንዲህ ዓይነት ዓለም ማምጣት አልቻሉም፤ ደግሞም አይችሉም። ከአምላክ ራሳቸውን ማግለላቸው ያተረፈው ነገር ቢኖር አስቀያሚ፣ አስከፊና ቀሳፊ የሆነ ዓለም ነው።

15. የትኛውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር መከተል ይኖርብናል?

15 የሰውን ልጅ ለመርዳት ይፈልጉ የነበሩ ቅን ልብ ያላቸው ገዥዎች የነበሩ ቢሆንም እንኳ ጥረቶቻቸው አልሰመሩም። በዛሬው ጊዜ በየትኛውም ሥፍራ ያለው ሁኔታ የሰውን ልጅ አገዛዝ ውድቀት ያሳያል። መጽሐፍ ቅዱስ “ማዳን በማይችሉ በሰው ልጆችና በአለቆች አትታመኑ” የሚል ምክር የሚሰጠው ለዚህ ነው።​—መዝሙር 146:3

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 24, 25 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ቅን ልብ ያላቸው የዓለም ገዥዎች እንኳ ሰላም የሰፈነበት ገነታዊ ዓለም ማምጣት አልቻሉም