በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 89

ኢየሱስ ቤተ መቅደሱን አጸዳ

ኢየሱስ ቤተ መቅደሱን አጸዳ

ኢየሱስ በጣም የተናደደ ይመስላል፤ አይመስልም እንዴ? ኢየሱስ በጣም የተናደደው ለምን እንደሆነ ታውቃለህ? ኢየሩሳሌም ውስጥ በሚገኘው የአምላክ ቤተ መቅደስ ውስጥ የነበሩት እነዚህ ሰዎች በጣም ስግብግቦች ስለነበሩ ነው። አምላክን ለማምለክ ወደዚህ ቦታ ከሚመጡት ሰዎች ላይ ብዙ ገንዘብ ለማትረፍ ይሞክሩ ነበር።

በሥዕሉ ላይ የሚታዩትን ኮርማዎች፣ በጎችና እርግቦች ተመለከትካቸው? ሰዎቹ እነዚህን እንስሳት በዚሁ በቤተ መቅደሱ ውስጥ ይሸጡ ነበር። ለምን እንደሆነ ታውቃለህ? እስራኤላውያን ለአምላክ መሥዕዋት አድርገው የሚያቀርቧቸው እንስሳትና አዕዋፍ ይፈልጉ ስለነበረ ነው።

የአምላክ ሕግ በሚለው መሠረት አንድ እስራኤላዊ ኃጢአት ከሠራ ለአምላክ መሥዋዕት ማቅረብ ነበረበት። እስራኤላውያን መሥዋዕት የሚያቀርቡባቸው ሌሎች ጊዜያትም ነበሩ። ይሁን እንጂ አንድ እስራኤላዊ ለአምላክ መሥዋዕት አድርጎ የሚያቀርባቸውን ወፎችና እንስሳት ማግኘት የሚችለው ከየት ነበር?

አንዳንድ እስራኤላውያን ራሳቸው ወፎችና እንስሳት ነበሯቸው። ስለዚህ እነዚህን መሥዋዕት አድርገው ማቅረብ ይችሉ ነበር። ይሁን እንጂ ብዙዎቹ እስራኤላውያን የራሳቸው እንስሳት ወይም ወፎች አልነበሯቸውም። ሌሎቹ ደግሞ የሚኖሩበት ቦታ ከኢየሩሳሌም በጣም ስለሚርቅ የራሳቸውን እንስሳ ይዘው ወደ ቤተ መቅደሱ መምጣት አይችሉም። ስለዚህ ሰዎቹ እዚህ ይመጡና የሚፈልጓቸውን እንስሳት ወይም ወፎች ይገዛሉ። ይሁን እንጂ እነዚህ ሰዎች ሕዝቡን ብዙ ገንዘብ ይጠይቋቸው ነበር። ሕዝቡን ያጭበረብሩ ነበር። ከዚህም በላይ በዚህ በአምላክ ቤተ መቅደስ ውስጥ መሸጥ አልነበረባቸውም።

ኢየሱስን ያስቆጣው ይህ ነበር። ስለዚህ ጠረጴዛዎቹን ከነገንዘቡ ገለባብጦ ሳንቲሞቻቸውን በታተናቸው። በተጨማሪም በገመድ ጅራፍ ሠራና እንስሳቱን በሙሉ ከቤተ መቅደሱ አስወጣቸው። ርግቦች ይሸጡ የነበሩትን ሰዎች ‘ርግቦቹን ከዚህ አውጡ! የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት’ ሲል አዘዛቸው።

ከኢየሱስ ተከታዮች መካከል አንዳንዶቹ ኢየሩሳሌም ውስጥ በሚገኘው በዚህ ቤተ መቅደስ ውስጥ አብረውት ነበሩ። ኢየሱስ ያደረገውን ነገር ሲመለከቱ በጣም ተደነቁ። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የአምላክን ልጅ አስመልክቶ ‘ለአምላክ ቤት ያለው ፍቅር እንደ እሳት ያቃጥለዋል’ ተብሎ የተጻፈበት ቦታ ትዝ አላቸው።

ኢየሱስ በማለፍ በዓል ላይ ለመገኘት እዚህ ኢየሩሳሌም ውስጥ በነበረበት ወቅት ብዙ ተአምራትን ፈጽሟል። ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ይሁዳን ለቆ ወጣና ወደ ገሊላ ለመመለስ ጉዞ ጀመረ። ይሁን እንጂ እግረ መንገዱን ወደ ሰማርያ አውራጃ ጎራ ብሎ ነበር። እዚያ ምን እንደተፈጸመ እስቲ እንመልከት