በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 38

አሥራ ሁለቱ ሰላዮች

አሥራ ሁለቱ ሰላዮች

እነዚህ ሰዎች የተሸከሙትን ፍራፍሬ ተመልከት። የወይን ዘለላው በጣም ትልቅ ነው። በጣም ከባድ ከመሆኑ የተነሳ ሁለት ሰዎች በእንጨት ላይ አድርገው ተሸክመውታል። በለሶቹንና ሮማኖቹንም ተመልከት። እነዚህ የሚያምሩ ፍራፍሬዎች የመጡት ከየት ነው? ከከነዓን ምድር ነው። ከነዓን በአንድ ወቅት አብርሃም፣ ይስሐቅና ያዕቆብ ይኖሩበት የነበረ ቦታ መሆኑን አስታውስ። ይሁን እንጂ በዚያ ቦታ ተከስቶ በነበረው ረሃብ ምክንያት ያዕቆብ ቤተሰቡን ይዞ ወደ ግብፅ ተጓዘ። አሁን ከ216 ዓመታት ገደማ በኋላ ሙሴ እስራኤላውያንን ወደ ከነዓን ምድር መልሶ እየወሰዳቸው ነው። በምድረ በዳው ውስጥ ወደሚገኝ ቃዴስ ተብሎ ወደሚጠራ ቦታ ደረሱ።

በከነዓን ምድር መጥፎ የሆኑ ሰዎች ይኖሩ ነበር። ስለዚህ ሙሴ 12 ሰላዮችን እንዲህ ብሎ ላካቸው:- ‘በዚያ ቦታ ምን ያህል ሰዎች እንደሚኖሩና ምን ያህል ኃይለኞች እንደሆኑ መርምሩ። ምድሪቱ ጥሩ እህል የምታበቅል መሆንና አለመሆኗን አረጋግጡ። ስትመለሱም ጥቂት ፍራፍሬ ይዛችሁ ኑ።’

ሰላዮቹ ወደ ቃዴስ ሲመለሱ ‘በጣም ጥሩ አገር ነው’ ብለው ለሙሴ ነገሩት። ሙሴ ይህን ማረጋገጥ እንዲችል የምድሪቱን ፍሬ አሳዩት። ይሁን እንጂ አሥሩ ሰላዮች ‘በዚያ ምድር የሚኖሩት ሰዎች ትልልቆችና ኃይለኞች ናቸው። ምድሪቱን ለመውሰድ ከሞከርን ይገድሉናል’ አሉ።

እስራኤላውያን ይህን ሲሰሙ በጣም ፈሩ። ‘በግብፅ ምድር ሳለን ወይም በዚሁ በምድረ በዳ ሳለን ብንሞት ይሻለን ነበር። በውጊያ ላይ እንሞታለን፤ ሚስቶቻችንና ልጆቻችንም ይማረካሉ። በሙሴ ፋንታ አንድ አዲስ መሪ እንምረጥና ወደ ግብፅ እንመለስ!’ አሉ።

ይሁን እንጂ ከሰላዮቹ መካከል ሁለቱ በይሖዋ በመተማመን ሕዝቡን ለማረጋጋት ሞከሩ። እነዚህ ሰላዮች ኢያሱና ካሌብ ይባላሉ። ‘አትፍሩ። ይሖዋ ከእኛ ጋር ነው። ምድሪቱን ያለ ምንም ችግር እንወርሳታለን’ አሏቸው። ይሁን እንጂ ሕዝቡ አልተቀበሏቸውም። እንዲያውም ኢያሱንና ካሌብን ለመግደል ፈለጉ።

ይህም ይሖዋን በጣም አስቆጣው፤ ሙሴን እንዲህ አለው:- ‘ከ20 ዓመት ዕድሜ ጀምሮ ከዚያም በላይ የሆነ ሰው ሁሉ ወደ ከነዓን ምድር አይገባም። በግብፅም ሆነ በምድረ በዳ የፈጸምኩትን ተአምራት አይተዋል፤ ያም ሆኖ በእኔ አልታመኑም። ስለዚህ የመጨረሻው ሰው እስኪሞት ድረስ ለ40 ዓመታት በምድረ በዳ ይቅበዘበዛሉ። ኢያሱና ካሌብ ብቻ ወደ ከነዓን ምድር ይገባሉ።’