በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 41

የነሐስ እባብ

የነሐስ እባብ

በእንጨቱ ላይ የተጠመጠመው እባብ እውነተኛ እባብ ይመስላል? እውነተኛ እባብ አይደለም። ከነሐስ የተሠራ እባብ ነው። ሕዝቡ እባቡን ማየት እንዲችሉና ሕይወታቸው እንዲተርፍ ሙሴ በእንጨት ላይ እንዲሰቅለው ይሖዋ አዝዞት ነበር። መሬት ላይ የሚታዩት ሌሎቹ እባቦች ግን እውነተኛ እባቦች ናቸው። ሰዎቹ እባቦቹ ስለነደፏቸው ታመዋል። ለምን እንደሆነ ታውቃለህ?

እስራኤላውያን በአምላክና በሙሴ ላይ በማጉረምረማቸው የተነሳ ነው። ‘በዚህ ምድረ በዳ እንድንሞት ከግብፅ ምድር ያወጣችሁን ለምንድን ነው? በዚህ ቦታ ምግብም ሆነ ውኃ የለም። ይህ መና እንደሆነ ሰልችቶናል’ በማለት አጉረመረሙ።

ይሁን እንጂ መናው ጥሩ ምግብ ነበር። ይሖዋ በተአምር የሰጣቸው ምግብ ነበር። ይሖዋ ተአምር በመሥራት ውኃም ሰጥቷቸዋል። ቢሆንም ሕዝቡ አምላክ ላደረገላቸው እንክብካቤ አመስጋኞች አልነበሩም። ስለዚህ ይሖዋ እስራኤላውያንን ለመቅጣት እነዚህን መርዘኛ እባቦች ላከ። እባቦቹ ነደፏቸውና ብዙዎቹ ሞቱ።

በመጨረሻም ሕዝቡ ወደ ሙሴ መጡና ‘በይሖዋና በአንተ ላይ በማጉረምረም በድለናል። እነዚህን እባቦች እንዲያስወግድልን ወደ ይሖዋ ጸልይልን’ አሉት።

ሙሴ ለሕዝቡ ጸለየ። ይሖዋም ሙሴ ይህን የነሐስ እባብ እንዲሠራ አዘዘው። በእንጨት ላይ እንዲሰቅለውና የተነደፈ ሁሉ ወደዚህ እባብ መመልከት እንዳለበት ነገረው። ሙሴም አምላክ እንዳለው አደረገ። የተነደፉት ሰዎችም የነሐሱን እባብ በመመልከት ዳኑ።

ከዚህ የምንማረው አንድ ትምህርት አለ። ሁላችንም በእነዚህ እባቦች የተነደፉት እስራኤላውያን ከነበሩበት ሁኔታ ጋር በሚመሳሰል ሁኔታ ሥር እንገኛለን። ሁላችንም በሞት ጥላ ሥር ነን። በአካባቢህ ያለውን ሁኔታ ተመልከት፤ ሰዎች ሲያረጁ፣ ሲታመሙና ሲሞቱ ትመለከታለህ። ይህ ሊሆን የቻለው የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት አዳምና ሔዋን ይሖዋን አንታዘዝም በማለታቸው ነው፤ እኛ ደግሞ የእነርሱ ልጆች ነን። ይሁን እንጂ ይሖዋ ለዘላለም መኖር የምንችልበትን መንገድ አዘጋጀ።

ይሖዋ ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ምድር ላከው። ብዙ ሰዎች ኢየሱስን መጥፎ ሰው እንደሆነ አድርገው በማሰብ በእንጨት ላይ ሰቀሉት። ይሁን እንጂ ይሖዋ ኢየሱስን የሰጠው እኛን ለማዳን ነው። በእርሱ ከተማመንና እርሱን ከተከተልነው የዘላለም ሕይወት ልናገኝ እንችላለን። ይሁን እንጂ ስለዚህ ጉዳይ ሌላም የምንማረው ነገር ይኖራል።