በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 70

ዮናስና ትልቁ ዓሣ

ዮናስና ትልቁ ዓሣ

ውኃው ውስጥ ያለውን ሰው ተመልከት። በጣም አስቸጋሪ ሁኔታ ገጥሞታል፤ አይደለም እንዴ? ዓሣው ሊውጠው ነው! ይህ ሰው ማን እንደሆነ ታውቃለህ? ዮናስ ይባላል። ከባድ ችግር ሊያጋጥመው የቻለው እንዴት እንደሆነ እስቲ እንመልከት።

ዮናስ የይሖዋ ነቢይ ነው። ነቢዩ ኤልሳዕ ከሞተ በኋላ ብዙም ሳይቆይ ይሖዋ ዮናስን ‘ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ። በዚያ የሚኖሩት ሰዎች ክፋታቸው በዝቶአልና ሄደህ ስለ ክፋታቸው ንገራቸው’ ብሎ አዘዘው።

ዮናስ ግን መሄድ አልፈለገም። ስለዚህ ከነነዌ ከተማ ርቆ ወደሚገኝ ቦታ በምትሄድ መርከብ ላይ ተሳፈረ። ዮናስ በመሸሹ ይሖዋ አልተደሰተም። ስለዚህ አንድ ኃይለኛ ማዕበል አስነሣ። ማዕበሉ በጣም ኃይለኛ ስለነበረ መርከቢቷ ልትሰጥም ደረሰች። መርከበኞቹ በጣም ስለ ፈሩ እርዳታ ለማግኘት ወደ አምላኮቻቸው ጮኹ።

በመጨረሻ ዮናስ ‘እኔ ሰማይና ምድርን የፈጠረውን አምላክ ይሖዋን አመልካለሁ። አሁን ይሖዋ ያዘዘኝን ትቼ ወደ ሌላ ቦታ እየሄድኩ ነው’ አላቸው። መርከበኞቹ ‘ማዕበሉ እንዲቆም ምን ብናደርግህ ይሻላል?’ ብለው ጠየቁት።

ዮናስ ‘ወደ ባሕሩ ጣሉኝ፤ ባሕሩም እንደ ቀድሞው ጸጥ ይልላችኋል’ አላቸው። መርከበኞቹ ይህን ማድረግ አልፈለጉም፤ ይሁን እንጂ ማዕበሉ እየጨመረ ሲሄድ በመጨረሻ ዮናስን ከመርከቡ አውጥተው ወደ ባሕሩ ጣሉት። ማዕበሉ ወዲያውኑ አቆመ፤ ባሕሩም እንደ ቀድሞው ጸጥ አለ።

ዮናስ ውኃው ውስጥ ሲሰጥም አንድ ትልቅ ዓሣ ዋጠው። ይሁን እንጂ አልሞተም። ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት በዓሣው ሆድ ውስጥ ነበር። ዮናስ ይሖዋን ታዝዞ ወደ ነነዌ ባለመሄዱ በጣም አዘነ። ምን እንዳደረገ ታውቃለህ?

ዮናስ ይሖዋ እንዲረዳው ጸለየ። ከዚያም ይሖዋ ዓሣው ዮናስን በደረቅ ምድር ላይ እንዲተፋው አደረገው። ከዚያ በኋላ ዮናስ ወደ ነነዌ ሄደ። ይህ ሁኔታ ይሖዋ ያዘዘውን ሁሉ ማድረጋችን ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ አያስተምረንም?

የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የዮናስ መጽሐፍ