በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 3

የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት

የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት

በዚህ ሥዕል ላይ ምን ለየት ያለ ነገር ትመለከታለህ? አዎ፣ እዚህኛው ሥዕል ላይ ሰዎች ይታያሉ። እነዚህ ሰዎች የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት ናቸው። ማን ፈጠራቸው? አምላክ ነው። ስሙ ማን እንደሆነ ታውቃለህ? ስሙ ይሖዋ ነው። ወንዱ አዳም ሴቲቱ ደግሞ ሔዋን ተባሉ።

ይሖዋ አምላክ አዳምን የፈጠረው እንደሚከተለው ነው። ከምድር አፈር ወስዶ ፍጹም የሆነ የሰው አካል ሠራበት። ቀጥሎም በሰውዬው አፍንጫ እፍ አለበት፤ አዳምም ሕያው ሆነ።

ይሖዋ አምላክ ለአዳም አንድ ሥራ ሰጠው። ለሁሉም ዓይነት እንስሳት ስም እንዲያወጣላቸው ነገረው። አዳም እን​ስሶቹን ለረጅም ጊዜ አይቷቸው ሊሆን ስለሚችል ለእያንዳንዳቸው ከሁሉ የተሻለ ተስማሚ ስም ሊያወጣላቸው ይችላል። አዳም ለእንስሶቹ ስም ሲያወጣላቸው አንድ ነገር ማስተዋል ጀመረ። ይህ ነገር ምን እንደሆነ ታውቃለህ?

ሁሉም እንስሳት ጥንድ ጥንድ ነበሩ። ወንድና ሴት ዝሆኖች እንዲሁም ወንድና ሴት አንበሶች ነበሩ። አዳም ግን ጓደኛ የምትሆነው ሴት አልነበረችውም። ስለዚህ ይሖዋ አዳም ከባድ እንቅልፍ እንዲወስደው አደረገ። ከዚያ በኋላ ከጎኑ አንድ አጥንት ወሰደ። ይሖዋ በዚህ አጥንት በመጠቀም ለአዳም ሴት ፈጠረለት፤ እርሷም ሚስቱ ሆነች።

በዚህ ጊዜ አዳም እንዴት ተደስቶ ይሆን! በተጨማሪም ሔዋን በዚህ ውብ የአትክልት ቦታ ውስጥ የመኖር አጋጣሚ በማግኘቷ እንዴት ተደስታ ይሆን! አሁን ልጆች ወልደው አብረው በደስታ መኖር ይችላሉ።

ይሖዋ አዳምና ሔዋን ለዘላለም እንዲኖሩ ይፈልግ ነበር። መላዋን ምድር ልክ እንደ ኤደን የአትክልት ስፍራ ውብ እንዲያደርጓት ፈልጎ ነበር። አዳምና ሔዋን ይህ ሥራ ሲሰጣቸው እንዴት ተደስተው ይሆን! አንተ ምድርን ውብ የአትክልት ስፍራ በማድረጉ ሥራ ብትካፈል ትደሰት ነበር? ይሁን እንጂ የአዳምና የሔዋን ደስታ ዘላቂ አልሆነም። እስቲ ይህ የሆነበት ምክንያት ምን እንደሆነ እንመልከት