በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ አሥራ ሦስት

አምላክ ለሰጠህ ሕይወት አድናቆት ይኑርህ

አምላክ ለሰጠህ ሕይወት አድናቆት ይኑርህ

1. ሕይወት የሰጠን ማን ነው?

ይሖዋ “ሕያው አምላክ” ነው። (ኤርምያስ 10:10) እሱ ፈጣሪያችን ሲሆን ሕይወት ሰጥቶናል። መጽሐፍ ቅዱስ ‘አንተ ሁሉንም ነገሮች ፈጥረሃል፤ እንዲሁም ወደ ሕልውና የመጡትም ሆነ የተፈጠሩት በአንተ ፈቃድ ነው’ ይላል። (ራእይ 4:11) ይሖዋ በሕይወት እንድንኖር ይፈልጋል። ሕይወት ከይሖዋ የተገኘ ውድ ስጦታ ነው።—መዝሙር 36:9ን አንብብ።

2. በሕይወታችን ደስተኛ መሆን የምንችለው እንዴት ነው?

2 ይሖዋ፣ እንደ ምግብና ውኃ ያሉ ለሕይወት አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን ሰጥቶናል። (የሐዋርያት ሥራ 17:28) ከሁሉ በላይ ደግሞ በሕይወታችን ደስተኛ እንድንሆን ይፈልጋል። (የሐዋርያት ሥራ 14:15-17) በሕይወታችን ደስተኛ መሆን የምንችለው የአምላክን ትእዛዛት ስንጠብቅ ነው።—ኢሳይያስ 48:17, 18

አምላክ ለሕይወት ያለው አመለካከት

3. ቃየን አቤልን በመግደሉ ይሖዋ ምን እርምጃ ወስዶበታል?

3 መጽሐፍ ቅዱስ፣ የእኛም ሆነ የሌሎች ሰዎች ሕይወት በይሖዋ ፊት ውድ እንደሆነ ይናገራል። ለምሳሌ ያህል፣ የአዳምና የሔዋን ልጅ የሆነው ቃየን በታናሽ ወንድሙ በአቤል ላይ በተቆጣ ጊዜ ይሖዋ ቁጣውን እንዲቆጣጠር አስጠንቅቆት ነበር። ይሁንና ቃየን ማስጠንቀቂያውን አልሰማም፤ በጣም ተቆጥቶ ስለነበር “ወንድሙን አቤልን ደብድቦ ገደለው።” (ዘፍጥረት 4:3-8) በዚህ የተነሳ ይሖዋ ቃየንን ቀጥቶታል። (ዘፍጥረት 4:9-11) ከዚህ መረዳት እንደሚቻለው ቁጣና ጥላቻ መጥፎ ባሕርያት ናቸው፤ እነዚህ ባሕርያት ጠበኛና ጨካኝ ሊያደርጉን ይችላሉ። እንዲህ ያለ ሰው የዘላለም ሕይወት ሊያገኝ አይችልም። (1 ዮሐንስ 3:15ን አንብብ።) ይሖዋን ማስደሰት ከፈለግን ሁሉንም ሰዎች መውደድ ይኖርብናል።—1 ዮሐንስ 3:11, 12

4. አምላክ ለእስራኤላውያን ከሰጣቸው ትእዛዛት መካከል አንዱ ምንድን ነው? ይህስ ምን ያሳያል?

4 በሺዎች የሚቆጠሩ ዓመታት ካለፉ በኋላ፣ ይሖዋ ለሙሴ አሥርቱን ትእዛዛት ሰጥቶት ነበር። ከትእዛዛቱ መካከል “አትግደል” የሚለው ይገኝበታል፤ ይህም ሕይወት፣ በይሖዋ ፊት ውድ እንደሆነ ያሳያል። (ዘዳግም 5:17) አንድ ሰው ሆን ብሎ ሕይወት ካጠፋ ይገደል ነበር።

5. አምላክ ፅንስ ስለማስወረድ ምን አመለካከት አለው?

5 አምላክ ፅንስ ስለማስወረድ ምን አመለካከት አለው? በማህፀን ውስጥ ያለ ፅንስም እንኳ በይሖዋ ፊት ውድ ነው። ይሖዋ ለእስራኤላውያን በሰጠው ሕግ ላይ አንድ ሰው በአንዲት ነፍሰ ጡር ሴት ላይ ጉዳት ቢያደርስና በማህፀኗ ውስጥ ያለው ፅንስ ቢሞት ይህ ሰው በሞት እንዲቀጣ አዟል። (ዘፀአት 21:22, 23ን አንብብ፤ መዝሙር 127:3) ይህም ፅንስ ማስወረድ ተገቢ እንዳልሆነ ያሳየናል።—ተጨማሪ ሐሳብ 28⁠ን ተመልከት።

6, 7. ለሕይወት አክብሮት እንዳለን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

6 ለራሳችንም ሆነ ለሌሎች ሕይወት አክብሮት እንዳለን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው? የእኛንም ሆነ የሌሎችን ሕይወት አደጋ ላይ ሊጥል የሚችል ነገር ባለማድረግ ነው። በመሆኑም ትንባሆ ማጨስ፣ ጫት መቃም ወይም ዕፅ መውሰድ አይኖርብንም፤ ምክንያቱም እነዚህ ነገሮች ሰውነታችንን ሊጎዱ እንዲሁም ለሞት ሊዳርጉን ይችላሉ።

7 ሕይወታችንም ሆነ ሰውነታችን የአምላክ ስጦታ ስለሆነ እሱ በሚፈልገው መንገድ ልንጠቀምበት ይገባል። በመሆኑም ሰውነታችንን በአግባቡ መያዝ ይኖርብናል። እንዲህ የማናደርግ ከሆነ በአምላክ ፊት የረከስን እንሆናለን። (ሮም 6:19፤ 12:1፤ 2 ቆሮንቶስ 7:1) ሕይወትን እንደ ውድ ነገር የማንመለከት ከሆነ ሕይወት ለሰጠን ለይሖዋ የምናቀርበው አምልኮ ተቀባይነት አይኖረውም። እርግጥ ነው፣ መጥፎ ልማዶችን መተው ቀላል አይደለም፤ ሆኖም ሕይወትን እንደ ውድ ነገር በመመልከት እነዚህን ልማዶች ለመተው ጥረት የምናደርግ ከሆነ ይሖዋ ይረዳናል።

8. የራሳችንንም ሆነ የሌሎችን ሕይወት አደጋ ላይ እንዳንጥል ምን ማድረግ ይኖርብናል?

8 ሕይወት ውድ ስጦታ እንደሆነ ተመልክተናል። ይሖዋ፣ በተቻለ መጠን የራሳችንንም ሆነ የሌሎችን ሕይወት አደጋ ላይ የሚጥል ነገር ከማድረግ እንደምንቆጠብ ይተማመናል። መኪና፣ ሞተር ብስክሌት ወይም ሌላ ተሽከርካሪ ስንነዳ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እናደርጋለን። በተጨማሪም አደገኛ ከሆኑና ዓመፅ ከሚንጸባረቅባቸው ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች እንርቃለን። (መዝሙር 11:5) እንዲሁም በመኖሪያ ቤታችን ውስጥ ሕይወትን አደጋ ላይ ሊጥሉ የሚችሉ ነገሮች እንዳይኖሩ እንጠነቀቃለን። ይሖዋ እስራኤላውያንን እንዲህ ሲል አዟቸው ነበር፦ “አዲስ ቤት በምትሠራበት ጊዜ አንድ ሰው ከጣሪያህ ላይ ወድቆ በቤትህ ላይ የደም ዕዳ እንዳታመጣ በጣሪያህ ዙሪያ መከታ [ወይም ከለላ] ሥራ።”—ዘዳግም 22:8

9. ይሖዋ ከእንስሳት ጋር በተያያዘ ምን እንድናደርግ ይጠብቅብናል?

9 ይሖዋ እንስሳትንም እንኳ እንድንንከባከብ ይፈልጋል። እርግጥ ነው፣ ምግብና ልብስ ለማግኘት እንዲሁም ሕይወታችንን ከአደጋ ለመጠበቅ ስንል እንስሳትን መግደል እንችላለን። (ዘፍጥረት 3:21፤ 9:3፤ ዘፀአት 21:28) ይሁንና ለመዝናናት ስንል ብቻ በእንስሳት ላይ የጭካኔ ድርጊት መፈጸም አሊያም መግደል ተገቢ አይሆንም።—ምሳሌ 12:10

ሕይወት ቅዱስ በመሆኑ ከፍ አድርገህ ልትመለከተው ይገባል

10. ደም ሕይወትን እንደሚወክል የሚያሳየው ምንድን ነው?

10 ደም ሕይወትን ስለሚወክል በይሖዋ ፊት ቅዱስ ነው። ቃየን አቤልን ከገደለው በኋላ ይሖዋ ቃየንን “የወንድምህ ደም ከምድር ወደ እኔ እየጮኸ ነው” ብሎት ነበር። (ዘፍጥረት 4:10) የአቤል ደም ሕይወቱን ይወክላል። ቃየን አቤልን በመግደሉ ይሖዋ ቀጥቶታል። በኖኅ ዘመን ከተከሰተው የጥፋት ውኃ በኋላም ይሖዋ ደም ሕይወትን እንደሚወክል ተናግሯል። ይሖዋ፣ ኖኅና ቤተሰቡ የእንስሳትን ሥጋ እንዲበሉ ፈቅዶላቸዋል። “በሕይወት የሚንቀሳቀስ እያንዳንዱ እንስሳ ምግብ ይሁናችሁ። የለመለመውን ተክል እንደሰጠኋችሁ ሁሉ እነዚህን በሙሉ ሰጥቻችኋለሁ” ብሏቸዋል። ነገር ግን ይሖዋ “ሕይወቱ ማለትም ደሙ በውስጡ ያለበትን ሥጋ ብቻ አትብሉ” ሲል አዟቸዋል። (ዘፍጥረት 1:29፤ 9:3, 4) ደም ነፍስን ወይም ሕይወትን ስለሚወክል ይሖዋ ሥጋን ከነደሙ እንዳይበሉ ከልክሏል።

11. አምላክ ደምን በተመለከተ ለእስራኤል ብሔር ምን ትእዛዝ ሰጥቷል?

11 ይሖዋ፣ ኖኅንና ቤተሰቡን ደም እንዳይበሉ ከነገራቸው ከ800 ዓመታት ገደማ በኋላ ሕዝቦቹን በድጋሚ እንዲህ ሲል አዘዛቸው፦ “አንድ እስራኤላዊ ወይም በመካከላችሁ የሚኖር አንድ የባዕድ አገር ሰው ለመብልነት የተፈቀደ እንስሳ ወይም ወፍ አድኖ ቢይዝ ደሙን ያፍሰው፤ አፈርም ያልብሰው።” ከዚያም “ደም አትብሉ” አላቸው። (ዘሌዋውያን 17:13, 14) ይሖዋ በዚህ ጊዜም ቢሆን፣ ሕዝቦቹ ደምን እንደ ቅዱስ ነገር አድርገው እንዲመለከቱት ይፈልግ ነበር። ሥጋውን እንጂ ደሙን መብላት አይችሉም ነበር። የአንድን እንስሳ ሥጋ ለመብላት በቅድሚያ ደሙን መሬት ላይ ማፍሰስ ነበረባቸው።

12. ክርስቲያኖች ለደም ምን አመለካከት አላቸው?

12 ኢየሱስ ከሞተ ከተወሰኑ ዓመታት በኋላ ሐዋርያትና በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ የነበሩ ሽማግሌዎች በኢየሩሳሌም ተሰብስበው ነበር፤ ሐዋርያትና ሽማግሌዎች የተሰበሰቡት፣ ለእስራኤላውያን ከተሰጡት ሕጎች መካከል ክርስቲያኖች ሊታዘዟቸው የሚገቡት የትኞቹን እንደሆነ ለመወሰን ነው። (የሐዋርያት ሥራ 15:28, 29ን አንብብ፤ 21:25) ይሖዋ፣ ለደም ያለው አመለካከት እንዳልተለወጠና ደምን እንደ ቅዱስ ነገር ሊመለከቱት እንደሚገባ እንዲገነዘቡ ረድቷቸዋል። የጥንቶቹ ክርስቲያኖች ደም አይበሉም፣ አይጠጡም እንዲሁም ደሙን ሳያፈስሱ ሥጋውን አይበሉም ነበር። እንዲህ ማድረግ ጣዖት ከማምለክና የሥነ ምግባር ብልግና ከመፈጸም የማይተናነስ ኃጢአት ነበር። ከዚያ ጊዜ አንስቶ እውነተኛ ክርስቲያኖች ደም ላለመብላትም ሆነ ላለመጠጣት ቆራጥ አቋም ወስደዋል። ዛሬም ቢሆን ይሖዋ ደምን እንደ ቅዱስ ነገር አድርገን እንድንመለከተው ይፈልጋል።

13. ክርስቲያኖች ደምን ለሕክምና የማይወስዱት ለምንድን ነው?

13 እንዲህ ሲባል ታዲያ ክርስቲያኖች ለሕክምናም ቢሆን ደም አይወስዱም ማለት ነው? አዎ፣ አይወስዱም። ይሖዋ ደምን እንዳንበላም ሆነ እንዳንጠጣ አዞናል። አንድ ሐኪም የአልኮል መጠጥ እንዳትጠጣ ቢያዝህ መጠጡን በደም ሥርህ ትወስዳለህ? እንዲህ እንደማታደርግ የታወቀ ነው! በተመሳሳይም ደምን እንዳንበላም ሆነ እንዳንጠጣ የተሰጠን ትእዛዝ ደምን ለሕክምና አለመውሰድንም ይጨምራል።—ተጨማሪ ሐሳብ 29⁠ን ተመልከት።

14, 15. ክርስቲያኖች ለሕይወት ምን አመለካከት አላቸው? ሕይወታቸውን ለማራዘም ሲሉ የአምላክን ሕግ ይጥሳሉ? አብራራ።

14 ይሁንና አንድ ሐኪም ደም ካልወሰድክ ትሞታለህ ቢልህስ? አምላክ ደምን በተመለከተ የሰጠውን ትእዛዝ መታዘዝ ወይም አለመታዘዝ ለእያንዳንዱ ሰው የተተወ ውሳኔ ነው። ክርስቲያኖች አምላክ ለሰጣቸው ሕይወት አድናቆት አላቸው። በመሆኑም ከባድ የጤና ችግር ሲያጋጥመን አማራጭ የሕክምና ዘዴዎችን ለመጠቀም ጥረት እናደርጋለን፤ ይሁንና ሕይወታችንን ለማትረፍ ስንል ደም አንወስድም።

15 ጤንነታችንን ለመጠበቅ ከፍተኛ ጥረት እናደርጋለን፤ ሆኖም ደም ሕይወትን ስለሚወክልና ሕይወት ደግሞ በአምላክ ፊት ውድ ስለሆነ ደም አንወስድም። የአምላክን ትእዛዝ በመጣስ ሕይወታችንን ለማራዘም ከመጣር ይልቅ ለይሖዋ ትእዛዝ ቅድሚያ እንሰጣለን። ኢየሱስ “ሕይወቱን ማዳን የሚፈልግ ሁሉ ያጣታልና፤ ለእኔ ሲል ሕይወቱን የሚያጣ ሁሉ ግን ያገኛታል” ብሏል። (ማቴዎስ 16:25) ይሖዋን ስለምንወደው እሱን መታዘዝ እንፈልጋለን። ይሖዋ ለእኛ ከሁሉ የተሻለው ነገር ምን እንደሆነ ያውቃል፤ በመሆኑም እኛም ልክ እንደ ይሖዋ ሕይወትን ውድና ቅዱስ ነገር እንደሆነ አድርገን እንመለከተዋለን።—ዕብራውያን 11:6

16. የአምላክ አገልጋዮች አምላክ ደምን በተመለከተ የሰጠውን ሕግ የሚታዘዙት ለምንድን ነው?

16 የአምላክ ታማኝ አገልጋዮች ደምን በተመለከተ የሰጠውን ሕግ ለመታዘዝ ቁርጥ ውሳኔ አድርገዋል። ደም ከመብላትም ሆነ ከመጠጣት እንዲሁም ደምን ለሕክምና ከመውሰድ ይቆጠባሉ። * ይሁንና ሕይወታቸውን ለማዳን ሌሎች አማራጭ የሕክምና ዘዴዎችን ይጠቀማሉ። ሕይወትንና ደምን የፈጠረው አምላክ ለእነሱ የተሻለውን ነገር እንደሚያውቅ እርግጠኞች ናቸው። አንተስ አምላክ ለአንተ የተሻለውን ነገር እንደሚያውቅ ይሰማሃል?

ይሖዋ ደምን ለምን ዓላማ ብቻ እንዲውል ፈቅዶ ነበር?

17. ይሖዋ እስራኤላውያን ደምን እንዲጠቀሙ የፈቀደው ለምን ዓላማ ብቻ ነበር?

17 ይሖዋ ለሙሴ በሰጠው ሕግ ላይ እስራኤላውያንን እንዲህ ብሏቸዋል፦ “የሥጋ ሕይወት ያለው በደሙ ውስጥ ነው፤ ለራሳችሁም ማስተሰረያ እንዲሆን [ወይም ምሕረት እንድታገኙ] እኔ ራሴ ደሙን ለእናንተ ስል ለመሠዊያው ሰጥቼዋለሁ፤ ምክንያቱም . . . የሚያስተሰርየው ደሙ ነው።” (ዘሌዋውያን 17:11) እስራኤላውያን ኃጢአት በሚሠሩበት ጊዜ መሥዋዕት የሚሆን እንስሳ በካህኑ ፊት ያቀርቡ ነበር፤ ካህኑ ደግሞ የእንስሳውን ደም በቤተ መቅደሱ ውስጥ ባለው መሠዊያ ላይ ይረጨዋል፤ በዚህ መንገድ እስራኤላውያን የይሖዋን ይቅርታ ማግኘት ይችሉ ነበር። ይሖዋ፣ እስራኤላውያን ደምን እንዲጠቀሙ የፈቀደው ለዚህ ዓላማ ብቻ ነበር።

18. ኢየሱስ የከፈለው መሥዋዕት ምን አጋጣሚ ከፍቶልናል?

18 ኢየሱስ ወደ ምድር በመጣበት ጊዜ የኃጢአት ይቅርታ እንድናገኝ ሲል ሕይወቱን ወይም ደሙን መሥዋዕት አድርጎ ሰጥቷል፤ በመሆኑም የእንስሳ መሥዋዕት እንዲቀርብ የሚያዘው ሕግ ቀርቷል። (ማቴዎስ 20:28፤ ዕብራውያን 10:1) ይሖዋ፣ የኢየሱስ ሕይወት በጣም ውድ ከመሆኑ የተነሳ ከሞት ካስነሳው በኋላ ኢየሱስ በከፈለው መሥዋዕት አማካኝነት የሰው ልጆች በሙሉ ለዘላለም መኖር የሚችሉበት አጋጣሚ እንዲያገኙ አድርጓል።—ዮሐንስ 3:16፤ ዕብራውያን 9:11, 12፤ 1 ጴጥሮስ 1:18, 19

ለሕይወትና ለደም አክብሮት እንዳለህ ማሳየት የምትችለው እንዴት ነው?

19. “ከሰው ሁሉ ደም ንጹሕ” ለመሆን ምን ማድረግ ይኖርብናል?

19 ይሖዋ ሕይወትን የመሰለ ውድ ነገር ስለሰጠን በጣም አመስጋኞች ነን! በመሆኑም ሰዎች በኢየሱስ ካመኑ ለዘላለም መኖር እንደሚችሉ መንገር እንፈልጋለን። ለሰዎች ፍቅር ስላለን ሕይወት ማግኘት የሚችሉበትን መንገድ እንዲያውቁ ለመርዳት የተቻለንን ጥረት እናደርጋለን። (ሕዝቅኤል 3:17-21) እንዲህ ካደረግን ልክ እንደ ሐዋርያው ጳውሎስ “ከሰው ሁሉ ደም ንጹሕ [ነኝ]፤ . . . ምክንያቱም የአምላክን ፈቃድ ሁሉ ለእናንተ ከመንገር ወደኋላ አላልኩም” ብለን መናገር እንችላለን። (የሐዋርያት ሥራ 20:26, 27) ስለ ይሖዋ ለሌሎች እንሰብካለን፤ እንዲሁም ሕይወት በእሱ ፊት ምን ያህል ውድ እንደሆነ እንናገራለን፤ እንዲህ በማድረግ ለሕይወትም ሆነ ለደም ከፍተኛ አክብሮት እንዳለን እናሳያለን።

^ አን.16 ደም መውሰድን በተመለከተ ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀውን ‘ከአምላክ ፍቅር አትውጡ’ የተባለውን መጽሐፍ ከገጽ 77-79 ተመልከት።