በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“የሰላሙ መስፍን” በጠላቶቹ መካከል ሲገዛ

“የሰላሙ መስፍን” በጠላቶቹ መካከል ሲገዛ

ምዕራፍ 3

“የሰላሙ መስፍን” በጠላቶቹ መካከል ሲገዛ

1, 2. (ሀ) ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ላይ ተሰብስበው ለነበሩ ደቀ መዛሙርቱ ምን የመሰነባበቻ ቃላት ተናገረ? (ለ) ይህስ “የሰላም መስፍን” በመሆን መግዛት ከመጀመሩ በፊት ዓለም ወደ ክርስትና ትለወጣለች ማለት ነውን?

ከ19 መቶ ዘመናት በፊት የወደፊቱ “የሰላም መስፍን” የነበረው ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሰማይ ከማረጉ ጥቂት ቀደም ብሎ የሚከተሉትን የመሰነባበቻ ቃላት ተሰብስበው ለነበሩት ታማኝ ደቀ መዛሙርቱ ተናገረ:- “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው . . . ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው። እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ።”— ማቴዎስ 28:19,20

2 እነዚህ የኢየሱስ ቃላት በ1914 የጀመረው “የነገሮች ሥርዓት መደምደሚያ” ከመምጣቱ በፊት ዓለም በሞላው ወደ ክርስትና እንደሚለወጥ ያሳያሉን? አያሳዩም። ዛሬ በዚህ በ20ኛው መቶ ዘመን መደምደሚያ መዳረሻ ላይ የሰው ዘር ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አዳኝና ሕጋዊ ንጉሥ አድርጎ በመቀበል ወደ እርሱ ከመለወጥ በጣም ርቋል። ይሁን እንጂ ይህ ይሖዋ በመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶች ውስጥ ያስነገረውን ከማከናወን አላዘገየውም። ኢየሱስ ክርስቶስ “የሰላም መስፍን” በመሆን መግዛት ከመጀመሩ በፊት ጠቅላላው የሰው ዘር ዓለም እንዲለወጥ በፍጹም የአምላክ ዓላማ አልነበረም። እንዲያውም ከዚህ በሚቃረን ሁኔታ እርሱ በጠላቶቹ መካከል መግዛት እንደሚጀምር ተተንብዮለት ነበር።

3. ኢየሱስ መዝሙር 110⁠ን መጥቀሱ በጠላቶቹ መካከል እንደሚገዛ የሚያመለክተው እንዴት ነው?

3 በዚህ ምድር ላይ በነበረበት ጊዜም እንኳን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን እውነት ያውቅ ነበር። ሰማዕት ሆኖ ከመሞቱ ከጥቂት ጊዜ በፊት ከሃይማኖታዊ ተቃዋሚዎቹ ጋር ሲከራከር መዝሙር 110⁠ን ጠቀሰ። ስለዚህ ነገር በሉቃስ 20:41-44 ላይ እንዲህ እናነባለን:- “እንዲህም አላቸው ክርስቶስ የዳዊት ልጅ ነው እንዴት ይላሉ? ዳዊት ራሱ በመዝሙራት መጽሐፍ ‘ይሖዋ ጌታዬን ጠላቶችህን ለእግርህ መርገጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ አለው’ ይላል። እንግዲህ ዳዊት ‘ጌታ’ ብሎ ይጠራዋል፣ እንዴትስ ልጁ ይሆናል?”

4–6. (ሀ) ኢየሱስ “የሰላም መስፍን” በመሆን መግዛት ከመጀመሩ በፊት ዓለም በሙሉ ወደ ክርስትና እስኪለወጥ ድረስ መጠበቅ እንደሌለበት መዝሙር ምዕራፍ 2 የሚያመለክተው እንዴት ነው? (ለ) መዝሙር 2:7 በየትኛው ጊዜ ላይ ተፈጽሟል?

4 ስለዚህ በግልጽ እንደሚታየው ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ዳዊት ልጅ በመሆን መግዛት የሚጀምረው ዓለም በመላው ወደ ክርስትና ከተለወጠ በኋላ አይደለም። ከዚያ ይልቅ መግዛት የሚጀምረው በመጨረሻ ላይ ይሖዋ አምላክ በውጊያ ላነገሠው ልጁ የእግር መርገጫ እንዲሆኑ በሚያደርግለት በጠላቶቹ መካከል ነው። መዝሙር ምዕራፍ 2ም እንደዚሁ “የሰላም መስፍን” በመሆን በጠላቶቹ መካከል መግዛት እንደሚጀምር በሚከተሉት ቃላት ያመለክታል:-

5 “አሕዛብ ለምን ያጉረመርማሉ? ወገኖችስ ለምን ከንቱን ይናገራሉ? የምድር ነገሥታት ተነሱ፣ አለቆችም (በይሖዋና አዓት) (በመሲሑ አዓት) ላይ እንዲህ ሲሉ ተማከሩ:- ‘ማሰሪያቸውን እንበጥስ፣ ገመዳቸውን ከእኛ እንጣል።’ በሰማይ የሚኖር እርሱ ይስቃል፣ (ይሖዋ አዓት) ይሳለቅባቸዋል። በዚያን ጊዜም በቁጣው ይናገራቸዋል፣ በመዓቱም ያውካቸዋል። [እንዲህ በማለት] ‘እኔ ግን ንጉሤን ሾምሁ በተቀደሰው ተራራዬ በጸዮን ላይ።”

6 “የይሖዋን ትእዛዝ ልናገር እርሱ እንዲህ አለኝ [ለክርስቶስ] ‘አንተ ልጄ ነህ እኔ ዛሬ ወለድሁህ [ይሖዋ ልጁን ከሞት ባስነሣበትና ለኢየሱስ የዘላለም አባት በሆነበት ጊዜ መዝሙር 2:7 ተፈጽሟል። (ሮሜ 1:4) ለምነኝ፣ አሕዛብን ለርስትህ የምድርንም ዳርቻ ለግዛትህ እሰጥሃለሁ። በብረት በትር ትጠብቃቸዋለህ፣ እንደ ሸክላ ሠሪ ዕቃም ትቀጠቅጣቸዋለህ።’ አሁንም እናንተ ነገሥታት፣ ልብ አድርጉ እናንተ የምድር ፈራጆችም ተገሰጹ። ለይሖዋም በፍርሐት ተገዙ በረዓድም ደስ ይበላችሁ። ልጁን ሳሙት፣ እርሱ እንዳይቆጣና እናንተም ከመንገድ እንዳትጠፉ ቁጣው ፈጥና ትነድዳለችና። በእርሱ የታመኑ ሁሉ ደስ ይበላቸው።”— አዓት

7. ከጴንጠቆስጤ ቀን በኋላ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያት መዝሙር 2⁠ን በመጥቀስ ምን አሉ?

7 በሥራ 4:24-27 መሠረት በ33 እዘአ ከዋለው የጴንጠቆስጤ ዕለት በኋላ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያት በመዝሙር ምዕራፍ ሁለት ላይ ያለውን እንደሚከተለው ጠቅሰው ነበር:- “በአንድ ልብ ሆነው ድምፃቸውን ወደ እግዚአብሔር ከፍ አደረጉ እንዲህም አሉ:- ‘ጌታ ሆይ፣ አንተ ሰማይና ምድሩን ባሕሩንም በእነርሱም የሚኖረውን ሁሉ የፈጠርህ በመንፈስ ቅዱስም በብላቴናህ (በአገልጋይህ) በአባታቸን በዳዊት አፍ አሕዛብ ለምን አጉረመረሙ? ሕዝቡስ ከንቱን ነገር ለምን አሰቡ? የምድር ነገሥታት ተነሱ አለቆችም (በይሖዋና) በተቀባው ላይ አብረው ተከማቹ ብለህ የተናገርህ አምላክ ነህ። በቀባኸው በቅዱሱ ብላቴናህ በኢየሱስ ላይ ሄሮድስና ጴንጤናዊው ጲላጦስ ከአሕዛብና ከእስራኤል ሕዝብ ጋር በዚች ከተማ በእውነት ተሰበሰቡ።”

የመዝሙር ምዕራፍ 2 ዋነኛ ፍፃሜ

8. (ሀ) መዝሙር 2:1,2 የመጀመሪያ ተፈጻሚነቱን ያገኘው መቼ ነበር? (ለ) መዝሙር ምዕራፍ 2 ዋነኛ ተፈጻሚነቱን ያገኘው ከመቼ ጀምሮ ነው?

8 በመጀመሪያው መቶ ዘመን 33ኛው ዓመት የመዝሙር 2:1,2⁠ን ትንቢታዊ ቃላት የመጀመሪያ ፍጻሜ ተመልክቶአል። ይህም በምድር ላይ ሰው ከነበረው ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር በተያያዘ ሁኔታ ነበር። እርሱም በመጥምቁ ዮሐንስ በተጠመቀበት ጊዜ በይሖዋ አምላክ ቅዱስ መንፈስ ተቀብቶ ነበር። ሆኖም መዝሙር 2 ዋነኛ ፍጻሜውን ያገኘው በ1914 ከተፈጸመው የአሕዛብ ዘመናት ወዲህ ነው። (ሉቃስ 21:24) በ607 ከዘአበ የኢየሩሳሌም ከተማ በመጀመሪያ ከጠፋችበት ጊዜ የሚጀምሩት “የተወሰኑት የአሕዛብ ዘመናት” በ1914 እንደተፈጸሙ በበቂ ሁኔታ ተረጋግጧል። * በዚያን ጊዜ ለዚህ ዓለም ብሔራት፣ ሕዝበ ክርስቲያን ነን ለሚሉት ብሔራት ጭምር የሞት ደወል ተደውሏል።

9. በዳዊት ንጉሣዊ መስመር ከተወከለው የአምላክ መንግሥት ጋር በተያያዘ ሁኔታ በመጀመሪያው የኢየሩሳሌም ጥፋት ወቅት ምን ነገር ተፈጸመ?

9 ኢየሩሳሌም በመጀመሪያ በባቢሎናውያን በጠፋችበት ጊዜ በንጉሥ ዳዊት ንጉሣዊ መስመር የተወከለውና በእስራኤል ሕዝብ ላይ ይገዛ የነበረው የይሖዋ አምላክ መንግሥት ወደ ፍጻሜው መጥቶአል። ከዚያን ጊዜ ወዲህ ሥጋዊ አይሁዳውያን ከንጉሥ ዳዊት መስመር በሆነ ንጉሥ አልተገዙም። ይሁን እንጂ ባንተ የትውልድ መስመር ዘላለማዊ መንግሥት አቋቍማለሁ በማለት ይሖዋ ቃል ኪዳን ባደረገለት በዳዊት ዘር የሚመራው የልዑሉ አምላክ መንግሥት በምድር ላይ ለዘላለም ተቋርጦ የሚቀር አልነበረም።

10, 11. (ሀ) በነቢዩ ሕዝቅኤል በኩል አምላክ የዳዊትን ዙፋን በሚመለከት ምን አለ? (ለ) የዳዊትን ዙፋን ለመውረስ “ሕጋዊ መብት ያለው” ሆኖ የመጣው ማን ነው? (ሐ) እርሱስ ራሱን እንደ ሕጋዊ ወራሽ አድርጎ ባቀረበ ጊዜ የተሰበሰቡት ብዙ አይሁዳውያን ምን አሉ?

10 ኢየሩሳሌም ለመጀመሪያ ጊዜ ከመጥፋቷ ከጥቂት ጊዜ በፊት ይሖዋ ነቢዩን ሕዝቅኤልን ለንጉሥዋ የሚከተሉትን ቃላት እንዲነግረው አነሳሳው:- “አንተ ቀንህ የደረሰብህ፣ የኃጢአትህ ቀጠሮ ጊዜ የደረሰብህ፣ ርኩስ ኃጢአተኛ የእስራኤል አለቃ ሆይ፣ ጌታ (ይሖዋ አዓት) እንዲህ ይላል:- መጠምጠሚያውን አውልቅ፣ ዘውዱንም አርቅ፤ ይህ እንዲህ አይሆንም፤ የተዋረደውን ከፍ አድርግ፣ ከፍ ያለውንም አዋርድ። ባድማ፣ ባድማ፣ ባድማ አደርጋታለሁ፤ ‘ፍርድ ያለው (ሕጋዊ መብት ያለው አዓት) እስኪመጣ ድረስ ይህች ደግሞ አትሆንም፣ ለእርሱም እሰጣታለሁ።’”— ሕዝቅኤል 21:25–27

11 ‘ሕጋዊ መብት ያለው’ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆኖ ተገኝቷል። ከዳዊት የትውልድ መስመር የመጣ መሆኑም በማቴዎስ 1:1–16 እና በሉቃስ 3:23–31 ተመዝግቦ ይገኛል። በአብዛኛው “የዳዊት ልጅ” ተብሎ ይጠራ ነበር። ትንቢቱን ለመፈጸም በአህያ ውርንጭላ ላይ እየጋለበ በድል ወደ ኢየሩሳሌም በገባበት ቀን እርሱንና ሐዋርያቱን ተከትለው የሄዱት የአይሁድ ሕዝቦች በደስታ ተውጠው:- “(ማዳን) ለዳዊት ልጅ (በይሖዋ አዓት) ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፣ ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ይጮሁ ነበር።— ማቴዎስ 21:9

“የዳዊት ልጅ” በሰማይ በዙፋን ላይ ተቀመጠ

12. የአሕዛብ ዘመናት በ1914 ሲፈጸሙ ኢየሱስ ክርስቶስ የዳዊት ዘላለማዊ ወራሽ በመሆን ዙፋን ላይ የተቀመጠው የት ነበር?

12 በዳዊት ቤተሰብ እጅ የነበረውን የአምላክን መንግሥት አሕዛብ በእግራቸው የረገጡባቸው 2520 ዓመታት በ1914 ተፈጽመዋል። በዚያን ጊዜም “የዳዊት ልጅ” የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ንጉሥ ሆኖ የሚሾምበት ጊዜ መጣ። ይህም የሆነው በምድራዊ ዙፋን ላይ ሳይሆን በጣም ከፍተኛ በሆኑት በሰማያት ውስጥ በይሖዋ አምላክ ቀኝ ነበር!— ዳንኤል 7:9,10,13,14

13. (ሀ) 1914 የአሕዛብ ዘመናት መጨረሻ እንደሚሆን አስቀድሞ ሲገለጽ የነበረው ከየትኛው ጊዜ ጀምሮ ነው? በእነማን አማካኝነትስ? (ለ) የምድር መንግሥታት ዙፋን ላይ ለተቀመጠው አዲስ ንጉሥ ለ“ዳዊት ልጅ” የነበራቸው ዝንባሌ ምን ነበር?

13 ይህ ከፍተኛ የሆነ ቀን ከመጠበቂያ ግንብ የመጽሐፍ ቅዱስና የትናንሽ ጽሑፎች ማኅበር ጋር የቅርብ ግንኙነት በነበራቸው ሰዎች ከ1876 ጀምሮ አስቀድሞ ተጠቍሞ ነበር። ይሁን አንጂ የምድር መንግሥታት፣ ሕዝበ ክርስቲያን ነን የሚሉ መንግሥታት ጭምር የበላይ ገዥነታቸውን አዲስ ለተሾመው “የዳዊት ልጅ” የሚያስረክቡበት ጊዜ መድረሱን ለመቀበል ፈቃደኞች አልሆኑም። የይሖዋ አምላክ የእግር መርገጫ በሆነችው በመላዋ ምድር ላይ ከአምላክ የተሰጠውን የበላይ ገዥነት መብት እንደያዘ አልተቀበሉም። (ማቴዎስ 5:35) ሕጋዊ የሆነውን ንጉሥ በግልጽ አንቀበልም ማለታቸውን በአንደኛው የዓለም ጦርነት ውስጥ በመግባት አረጋግጠዋል።

14. (ሀ) አንደኛው የዓለም ጦርነት ሲፈነዳ ከመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ጋር ለተባበሩት ክርስቲያኖች ብሔራት ምን ዓይነት ዝንባሌ እንዳላቸው አሳዩ? (ለ) ከዚህ አንጻር ሲታይ የዓለም ሁኔታ የሚያሳየው ነገር ምንድን ነው?

14 በጦርነቱ ተሳታፊ መንግሥታት ውስጥ የነበሩትና ከመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ጋር የቅርብ ግንኙነት መሥርተው ራሳቸውን የወሰኑት ክርስቲያኖች ከደም አፍሳሽነት ነፃ ለመሆን የወሰዱትን ቁርጥ አቋም እንዲተው ለማድረግ ከባድ ተጽዕኖ ደረሰባቸው። እነርሱ በዚያን ጊዜ የክርስቲያናዊ ገለልተኝነትን ግዴታ ሙሉ በሙሉ አልተረዱትም ነበር። የዳዊት ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ “የነገሮችን ሥርዓት መደምደሚያ” በሚመለከት ለደቀመዛሙርቱ የተናገረው ትንቢት መከራን አክሎ በእነርሱ ላይ ተፈጸመ:- “ስለ ስሜም በአሕዛብ ሁሉ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ።” (ማቴዎስ 24:9) ይህ ጥላቻ ከአንደኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ አላባራም። ከእነዚህ ትርጉም ካላቸው የዘመናዊ ታሪክ እውነታዎች አንፃር የዓለም ሁኔታ ምን ያመለክታል? ይህ የሚያመለክተው “የሰላሙ መስፍን” በዚሁ ምድር ላይ በጠላቶቹ መካከል እየገዛ መሆኑን ነው!

15. በሰማይ ላይ ጦርነት በተከፈተ ጊዜ በሰይጣንና በአጋንንታዊ ጭፍሮቹ ላይ ምን ደረሰባቸው? የውጊያው ውጤቶች በየትኛው ዓመት ላይ መደምደሚያ ላይ ደርሰው መሆን ይኖርበታል?

15 ጠላቶቹ በሰማይና በምድር ላይ ቢኖሩም እንኳን ሁሉን የሚችለው አምላክ ተስፋ የተደረገው መሲሐዊ መንግሥት እርሱ በወሰነው ጊዜ እንዲወለድ አድርጎታል። ራዕይ 12:1–9 በሰማያት ውስጥ ወንዱ ልጅ ማለትም መንግሥቱ ከይሖዋ ሚስት መሰል ድርጅት ማሕጸን ከወጣ በኋላ ወዲያውኑ በሰማይ ጦርነት እንደተከፈተ ያሳያል። ቅዱስ የሆኑት ሰማያት ከዚያ በኋላ ለምሳሌያዊው ዘንዶ ለሰይጣን ዲያብሎስና ለአጋንንታዊ መላእክቱ መኖሪያ መሆናቸውን አቆሙ። በዚህ ለሰብዓዊ ዓይኖች ሊታይ በማይችለው ጦርነት ንጉሣዊ ኃይል የተቀበለው “የዳዊት ልጅ” በድል አድራጊነት ተዋግቶ ሰይጣን ዲያብሎስንና አጋንንታዊ ጭፍሮቹን ከሰማያት በመጣል በምድራችን አካባቢ እንዲወሰኑ አድርጎአቸዋል። ይህ የሰይጣናዊ ኃይሎች መዋረድ አንደኛው የዓለም ጦርነት ወደ ፍጻሜው በመጣበት ዓመት በ1918 ላይ ሙሉ በሙሉ እንደ ተፈጸመ ከሁኔታዎች መረዳት ይቻላል።

ዲያብሎስ ቦታውን በማጣቱ ጦርነት ከፈተ

16, 17. (ሀ) ከቦታው ዝቅ የተደረገው ሰይጣን ዲያብሎስ ጦርነት የከፈተው በማን ላይ ነው? (ለ) ይህንንስ ጦርነት ለማካሄድ በእነማን ይጠቀማል?

16 ቦታውን ያጣው ምሳሌያዊው ዘንዶ ሰይጣን ዲያብሎስ በተለይ በአሁኑ ጊዜ ሚስት መሰል በሆነችው የይሖዋ አምላክ ድርጅት ላይ ተቆጥቶአል። (ራዕይ 12:17) ስለዚህም እርሷ መንፈሳዊት እናታቸው ለመሆንዋ ማረጋገጫ ባላቸው በመንፈስ በተወለዱት ቀሪዎችና ራሳቸውን የወሰኑ ክርስቲያኖች ላይ ጭካኔ የተሞላበት ጦርነት አድርጓል።— ገላትያ 4:26

17 ሰይጣን ከቅቡዓን ቀሪዎች ጋር ስለ መንግሥቱ መወለድ ምስክር በመሆን በታዛዥነት በሚሰሩት ‘በሌሎች በጎችም’ ላይ ጦርነት ከፍቷል። (ዮሐንስ 10:16) በአሁኑ ጊዜ ሰይጣን ከቦታቸው ዝቅ በተደረጉትና በምድር ዙሪያ በተኰለኰሉት አጋንንታዊ ኃይሎች ብቻ ሳይሆን በድርጅቱ ምድራዊ ክፍል እየተጠቀመ በቀሪዎቹና በ“ሌሎች በጎች” ላይ ውጊያ ያካሄዳል።

18. (ሀ) ዲያብሎስ ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ በቅቡዓን ቀሪዎችና በጓደኞቻቸው ላይ ጦርነት ቢከፍትም እነርሱ ምን የመከላከያ ኃይል አላቸው? (ለ) የትኛው “የሰላሙ መስፍን” አገዛዝ ገጽታ ነው ወደ ፍጻሜ የደረሰው?

18 ‘የሰላሙ መስፍን’ በዚህ ምድር ላይ በጠላቶቹ መካከል መግዛቱ አሁን ሊያከትም ተቃርቧል። ሁኔታውንም እጅግ በጣም ጥሩ በሆነ ጥንቃቄ ይዞታል። ቅዱስ የሆኑት ታዛዥ መላእክቱም ንጉሣዊ ትእዛዙን ለመቀበልና በፍጥነት ለመፈጸም ዝግጁ ሆነው ቀንና ሌሊት በተጠንቀቅ ቆመዋል። እነርሱም ‘የሰላሙ መስፍን’ በጠላቶቹ መካከል በሚገዛበት በዚህ በፍጥነት እያጠረ በሚሄደው ጊዜ ውስጥ የመንግሥቱን ጉዳዮች ማከናወናቸውን ሲቀጥሉ ለቅቡዓን ቀሪዎቹና ለጓደኞቻቸው ማለትም የ“ሌሎች በጎች” ክፍል ለሆኑት “እጅግ ብዙ ሰዎች” ተከላካይ ኃይል ሆነው ያገለግላሉ።— ራእይ 7:9

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.8  የበለጠ ማብራሪያ ለማግኘት በመጠበቂያ ግንብ፣ በመጽሐፍ ቅዱስና በትራክት ማኅበር የታተመውን በምድር ላይ በገነት ለዘላለም መኖር ትችላለህ የሚባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 16 አንቀጽ 14–21 ተመልከት

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]