በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 6

ምድር ገነት የምትሆንበት ጊዜ ቀርቧል!

ምድር ገነት የምትሆንበት ጊዜ ቀርቧል!

በአሁኑ ጊዜ እየተፈጸሙ ያሉት መጥፎ ነገሮች ምድር ገነት የምትሆንበት ጊዜ መቅረቡን ያሳያሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ምድር ገነት ከመሆኗ በፊት ሥቃይ የሞላበት ጊዜ እንደሚኖር ይናገራል። አሁን የምንኖረው በዚህ ጊዜ ውስጥ ነው! መጽሐፍ ቅዱስ ይሆናሉ ብሎ ከተናገራቸው ነገሮች መካከል አንዳንዶቹ የሚከተሉት ይገኙበታል:-

ታላላቅ ጦርነቶች። “ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣል።” (ማቴዎስ 24:7) ይህ ትንቢት በትክክል ተፈጽሟል። ከ1914 ጀምሮ ሁለት የዓለም ጦርነቶችና ሌሎች በርካታ ትናንሽ ጦርነቶች ተካሂደዋል። በዚህም ምክንያት በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች አልቀዋል።

የበሽታ መስፋፋት። “በልዩ ልዩ ስፍራ ቸነፈር” ይሆናል። (ሉቃስ 21:11) ይህስ ተፈጽሟል? አዎን። ካንሰር፣ የልብ በሽታ፣ ሳንባ ነቀርሳ፣ ወባ፣ ኤድስና ሌሎች በሽታዎች በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ሕይወት ቀጥፈዋል።

የምግብ እጥረት። በመላው ምድር ላይ ብዙ ሰዎች የሚበሉት በቂ ምግብ የላቸውም። በየዓመቱ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በረሃብ ያልቃሉ። በቅርቡ ምድር ገነት እንደምትሆን የሚያሳይ ይህ ሌላው ምልክት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ “ራብ ይሆናል” ይላል።—ማርቆስ 13:8

የምድር መናወጥ። “የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል።” (ማቴዎስ 24:7) ይህም ቢሆን በጊዜያችን ፍጻሜውን አግኝቷል። ከ1914 ጀምሮ ከአንድ ሚልዮን የሚበልጡ ሰዎች በምድር መናወጥ ሞተዋል።

ክፉ ሰዎች። ሰዎች “ራሳቸውን የሚወዱ . . . ገንዘብን የሚወዱ” ይሆናሉ። “ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ” ይሆናሉ። ልጆች “ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ” ይሆናሉ። (2 ጢሞቴዎስ 3:1-5) በዛሬው ጊዜ እነዚህን የመሰሉ በርካታ ሰዎች እንዳሉ አትስማማም? ለአምላክ አክብሮት የላቸውም፣ እንዲሁም ስለ አምላክ ለመማር ጥረት በሚያደርጉ ሰዎች ላይ ችግር ይፈጥራሉ።

ወንጀል። ከዚህም በተጨማሪ ‘ዓመፅ እየበዛ’ ይሄዳል። (ማቴዎስ 24:12) በአሁኑ ጊዜ ያለው ወንጀል ከዓመታት በፊት ከነበረው የባሰ እንደሆነ ሳትስማማ አትቀርም። በየትኛውም ቦታ የሚኖሩ ሰዎች ዝርፊያና ማጭበርበር ሊፈጸምባቸው ወይም ጉዳት ሊደርስባቸው ይችላል።

እነዚህ ሁሉ የአምላክ መንግሥት መቅረቡን ያሳያሉ። መጽሐፍ ቅዱስ “ይህ ሁሉ መሆኑን ስታዩ የእግዚአብሔር መንግሥት እንደ ቀረበች እወቁ” በማለት ይናገራል። (ሉቃስ 21:31) የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው? በዚህ ምድር ላይ ገነትን የሚያመጣው በሰማይ የሚገኘው የአምላክ መስተዳድር ነው። የሰዎች መንግሥት በአምላክ መንግሥት ይተካሉ።—ዳንኤል 2:44