በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 7

ለዘመናችን ማስጠንቀቂያ የሚሆን ጥንት የተፈጸመ ታሪክ

ለዘመናችን ማስጠንቀቂያ የሚሆን ጥንት የተፈጸመ ታሪክ

ይሖዋ ክፉ ሰዎች ገነትን እንዲያበላሹ አይፈቅድም። በዚያ የሚኖሩት ወዳጆቹ የሆኑት ብቻ ናቸው። ክፉ ሰዎች ምን ይደርስባቸዋል? መልሱን ለማግኘት ስለ ኖኅ የሚናገረውን እውነተኛ ታሪክ ተመልከት። ኖኅ ይኖር የነበረው ከብዙ ሺህ ዓመታት በፊት ነው። ኖኅ የይሖዋን ፈቃድ ለማድረግ ሁልጊዜ ይጥር የነበረ ጥሩ ሰው ነው። ይሁን እንጂ በምድር ላይ ይኖሩ የነበሩት ሌሎች ሰዎች መጥፎ ድርጊት ይፈጽሙ ነበር። ስለዚህ ይሖዋ እነዚህን ክፉ ሰዎች በሙሉ ለማጥፋት የውኃ መጥለቅለቅ እንደሚያመጣ ለኖኅ ነገረው። የጎርፍ መጥለቅለቁ በሚሆንበት ጊዜ እርሱና ቤተሰቡ እንዳይሞቱ መርከብ እንዲሠራ ለኖኅ ነገረው።—ዘፍጥረት 6:9-18

ኖኅና ቤተሰቡ መርከብ ሠሩ። ኖኅ የጎርፍ መጥለቅለቅ እንደሚመጣ ሰዎችን አስጠንቅቆ ነበር። ሰዎቹ ግን አልሰሙትም። መጥፎ ነገር መሥራታቸውን ቀጠሉ። መርከቡ ተሠርቶ ካለቀ በኋላ ኖኅ እንስሳትን ወደ መርከቡ አስገባ፣ በመጨረሻም እርሱና ቤተሰቡም ገቡ። ከዚያም ይሖዋ ኃይለኛ ዝናብ አወረደ። ዝናቡ 40 ቀንና 40 ሌሊት ዘነበ። ውኃው ምድርን በሙሉ አጥለቀለቀ።—ዘፍጥረት 7:7-12

ክፉዎቹ ሰዎች ሕይወታቸውን አጡ፤ ኖኅና ቤተሰቡ ግን ዳኑ። ይሖዋ ኖኅንና ቤተሰቡን ከውኃው መጥለቅለቅ አድኖ ከክፋት በጸዳች ምድር ላይ እንዲኖሩ አደረጋቸው። (ዘፍጥረት 7:22, 23) ይሖዋ ትክክል የሆነውን ለማድረግ ፈቃደኛ የማይሆኑ ሰዎችን በድጋሚ የሚያጠፋበት ጊዜ እንደሚመጣ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። ጥሩ ሰዎች አይጠፉም። ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም ይኖራሉ።—2 ጴጥሮስ 2:5, 6, 9

ዛሬ ብዙ ሰዎች መጥፎ ነገሮችን ይሠራሉ። ዓለም በችግር ተሞልታለች። ይሖዋ ሰዎችን እንዲያስጠነቅቁ ምሥክሮቹን በተደጋጋሚ ቢልክም ብዙዎቹ የይሖዋን ቃል ለመስማት አይፈልጉም። መንገዳቸውን መለወጥ አይፈልጉም። አምላክ ትክክልና ስህተት ስለሆኑ ነገሮች የሚናገረውን ለመቀበል አይፈልጉም። እነዚህ ሰዎች ምን ይደርስባቸዋል? አንድ ቀን አካሄዳቸውን ይቀይሩ ይሆን? ብዙዎቹ የሚለወጡ ዓይነት አይደሉም። ክፉ ሰዎች የሚጠፉበትና ዳግመኛ በሕይወት የማይኖሩበት ጊዜ እየመጣ ነው።—መዝሙር 92:7

ምድር አትጠፋም፤ እንዲያውም ገነት ትሆናለች። የአምላክ ወዳጅ የሚሆኑ ሁሉ ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም ይኖራሉ።—መዝሙር 37:29