በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“ሕዝቤን አጽናኑ”

“ሕዝቤን አጽናኑ”

ምዕራፍ ሠላሳ

“ሕዝቤን አጽናኑ”

ኢሳይያስ 40:​1-​31

1. ይሖዋ እኛን የሚያጽናናበት አንደኛው መንገድ ምንድን ነው?

ይሖዋ ‘የመጽናናት አምላክ’ ነው። እኛን የሚያጽናናበት አንደኛው መንገድ በቃሉ ውስጥ ተመዝግበው እንዲቀመጡ ያደረጋቸው ተስፋዎቹ ናቸው። (ሮሜ 15:​4, 5) ለምሳሌ ያህል የምትወዳቸውን ሰዎች በሞት በምታጣበት ጊዜ እነዚህን ሰዎች በአምላክ አዲስ ዓለም ውስጥ ትንሣኤ እንደሚያገኙ ከሚገልጸው ተስፋ ይበልጥ ሊያጽናናህ የሚችል ምን ነገር ይኖራል? (ዮሐንስ 5:​28, 29) በቅርቡ ክፋትን በማስቆም ምድርን ወደ ገነትነት እንደሚለውጥ ይሖዋ የሰጠው ተስፋስ ቢሆን የሚያጽናና አይደለምን? ወደ መጪዋ ገነት በሕይወት የመሻገርና ሞትን ሳይቀምሱ የመኖር ተስፋ አያጽናናምን?​—⁠መዝሙር 37:​9-11, 29፤ ራእይ 21:​3-5

2. አምላክ የሰጠውን የተስፋ ቃል ልንታመንበት የምንችለው ለምንድን ነው?

2 አምላክ በሰጣቸው ተስፋዎች ላይ በእርግጥ ልንተማመን እንችላለን? አዎን፣ እንችላለን! እነዚህን ተስፋዎች የሰጠው አምላክ ፍጹም የታመነ ነው። ቃሉን ለመፈጸም ችሎታው ያለው ከመሆኑም በላይ ፈቃደኛ ነው። (ኢሳይያስ 55:​10, 11) ይሖዋ ንጹሕ አምልኮን በኢየሩሳሌም መልሶ እንደሚያቋቁም በኢሳይያስ አማካኝነት የተናገረው ቃል ይህንን ጉዳይ የሚያረጋግጥ ጠንካራ ማስረጃ ይሆናል። ይህን ትንቢት መመርመራችን የሰጠውን የተስፋ ቃል በሚፈጽመው አምላክ በይሖዋ ላይ ያለንን እምነት የሚያጠናክርልን በመሆኑ ቀጥሎ ትንቢቱ የሚገኝበትን 40ኛውን የኢሳይያስ ምዕራፍ እንመረምራለን።

የሚያጽናና የተስፋ ቃል

3, 4. (ሀ) ኢሳይያስ የአምላክ ሕዝብ ከጊዜ በኋላ የሚያስፈልገውን ምን የሚያጽናኑ ቃላት መዝግቧል? (ለ) የይሁዳና የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ወደ ባቢሎን በግዞት የሚወሰዱት ለምንድን ነው? በባርነት የሚቆዩትስ ለምን ያህል ጊዜ ነው?

3 ነቢዩ ኢሳይያስ በስምንተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ በኋለኛው ዘመን የሚኖሩት የይሖዋ አገልጋዮች የሚያስፈልጋቸውን የሚያጽናኑ ቃላት መዝግቧል። ኢሳይያስ በቅርቡ በኢየሩሳሌም ላይ ጥፋት እንደሚመጣና አይሁዳውያንም ወደ ባቢሎን እንደሚጋዙ ለንጉሥ ሕዝቅያስ ከተናገረ በኋላ ወዲያው አስከትሎ ተመልሰው ስለ መቋቋማቸው የሚናገረውን የይሖዋ ቃል ጠቅሷል። “አጽናኑ፣ ሕዝቤን አጽናኑ ይላል አምላካችሁ። ለኢየሩሳሌም ልብ ተናገሩ፤ የተቀጠረችበት ወራት እንደ ተፈጸመ፣ ኃጢአትዋም እንደ ተሰረየ፣ ከእግዚአብሔርም እጅ ስለ ኃጢአትዋ ሁሉ ሁለት እጥፍ እንደ ተቀበለች ወደ እርስዋ ጩኹ።”​—⁠ኢሳይያስ 40:​1, 2

4 “አጽናኑ” የሚለው በኢሳይያስ ምዕራፍ 40 መክፈቻ ላይ የሚገኘው ቃል በቀረው የኢሳይያስ መጽሐፍ ውስጥ የሰፈረውን የብርሃንና የተስፋ መልእክት ግሩም በሆነ መንገድ የሚገልጽ ነው። የይሁዳና የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ከሃዲዎች ሆነው በመገኘታቸው ምክንያት በ607 ከዘአበ ወደ ባቢሎን በምርኮ ይወሰዳሉ። ይሁን እንጂ እነዚያ አይሁዳውያን ምርኮኞች ለዘላለም የባቢሎን ባሪያዎች ይሆናሉ ማለት አይደለም። በባርነት የሚቆዩት ኃጢአታቸው ‘እስኪሰረይ’ ብቻ ይሆናል። ይህ ምን ያህል ጊዜ ይወስዳል? ነቢዩ ኤርምያስ እንደተናገረው 70 ዓመት ይፈጃል። (ኤርምያስ 25:​11, 12) ከዚያ በኋላ ግን ይሖዋ ንስሐ የገቡትን ቀሪዎች ከባቢሎን ወደ ኢየሩሳሌም ይመልሳቸዋል። ይሁዳ ባድማ በሆነች በ70ኛው ዓመት ነፃ እንደሚወጡ የተሰጣቸው ተስፋ የሚፈጸምበት ጊዜ እንደደረሰ ማወቃቸው ለምርኮኞቹ ምንኛ የሚያጽናና ይሆናል!​—⁠ዳንኤል 9:​1, 2

5, 6. (ሀ) ከባቢሎን ወደ ኢየሩሳሌም የሚደረገው ረጅም ጉዞ የአምላክ የተስፋ ቃል ፍጻሜውን እንዳያገኝ እንቅፋት የማይሆነው እንዴት ነው? (ለ) አይሁዳውያን ወደ ትውልድ አገራቸው መመለሳቸው በሌሎች ብሔራት ላይ የሚኖረው ተጽዕኖ ምንድን ነው?

5 ከባቢሎን ወደ ኢየሩሳሌም የሚደረገው ጉዞ ከ800 እስከ 1, 600 ኪሎ ሜትር ይፈጃል። ይህ ለመሄድ በሚመርጡት አቅጣጫ ላይ የተመካ ነው። ረጅሙ ጉዞ የአምላክ የተስፋ ቃል ፍጻሜውን እንዳያገኝ እንቅፋት ይፈጥር ይሆን? በፍጹም! ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “የአዋጅ ነጋሪ ቃል:- የእግዚአብሔርን መንገድ በምድረ በዳ ጥረጉ፣ ለአምላካችንም ጐዳና በበረሀ አስተካክሉ። ሸለቆው ሁሉ ከፍ ይላል፣ ተራራውና ኮረብታውም ሁሉ ዝቅ ይላል፤ ጠማማውም ይቃናል፣ ስርጓጉጡም ሜዳ ይሆናል፤ የእግዚአብሔርም ክብር ይገለጣል፣ ሥጋ ለባሹም ሁሉ በአንድነት ያየዋል፣ የእግዚአብሔር አፍ ይህን ተናግሮአልና።”​—⁠ኢሳይያስ 40:​3-5

6 ብዙውን ጊዜ ምሥራቃውያን ገዥዎች ጉዞ ከመጀመራቸው በፊት ትላልቅ ድንጋዮችን በማንሳት መሸጋገሪያ በመሥራትና አባጣ ጎርባጣውን መሬት በመደልደል መንገድ የሚያዘጋጁ ሰዎችን በፊታቸው ይልኩ ነበር። ወደ አገራቸው ለሚመለሱት አይሁዳውያን ደግሞ አምላክ ራሱ ከፊት ከፊታቸው እየሄደ እንቅፋቱን ሁሉ የሚያስወግድላቸው ያህል ነበር። ደግሞም የይሖዋን ስም የተሸከመ ሕዝብ ከመሆኑም ሌላ ይሖዋ እነርሱን ወደ ትውልድ አገራቸው ለመመለስ የገባውን ቃል መፈጸሙ ለአሕዛብ ሁሉ ክብሩ እንዲገለጥ የሚያደርግ እርምጃ ይሆናል። እነዚያ ብሔራት ወደዱም ጠሉ ይሖዋ የገባውን ቃል የሚፈጽም አምላክ መሆኑን በዓይናቸው ለማየት ይገደዳሉ።

7, 8. (ሀ) በ⁠ኢሳይያስ 40:​3 ላይ የሚገኙት ቃላት በመጀመሪያው መቶ ዘመን እዘአ ፍጻሜያቸውን ያገኙት እንዴት ነው? (ለ) የኢሳይያስ ትንቢት በ1919 ምን ታላቅ ፍጻሜ ነበረው?

7 የዚህ ትንቢት ፍጻሜ በስድስተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ የተከናወነው መልሶ ማቋቋም ብቻ ነው ማለት አይደለም። በአንደኛው መቶ ዘመንም ትንቢቱ ተፈጻሚነት ነበረው። መጥምቁ ዮሐንስ በኢሳይያስ 40:​3 ፍጻሜ መሠረት “በምድረ በዳ የሚጮኽ” ሰው ድምፅ ሆኖ ብቅ ብሏል። (ሉቃስ 3:​1-6) ዮሐንስ የኢሳይያስ ቃላት ለእርሱ እንደሚሠሩ በመንፈስ አነሳሽነት ተናግሯል። (ዮሐንስ 1:​19-23) ከ29 እዘአ አንስቶ ዮሐንስ ለኢየሱስ ክርስቶስ መንገዱን አዘጋጅቷል። * ዮሐንስ አስቀድሞ ያሰማው የነበረው አዋጅ ሕዝቡ ቃል የተገባለትን መሲህ ይሰሙና ይከተሉ ዘንድ በጉጉት እንዲጠባበቁ አነሳስቷቸዋል። (ሉቃስ 1:​13-17, 76) ይሖዋ ንስሐ የሚገቡትን ሰዎች በኢየሱስ አማካኝነት በአምላክ መንግሥት ሥር ብቻ ሊገኝ ወደሚችለው ነፃነት ይኸውም ከኃጢአትና ከሞት ነፃ ወደ መሆን ይመራቸዋል። (ዮሐንስ 1:​29፤ 8:​32) በ1919 የመንፈሳዊ እስራኤል ቀሪዎች ከታላቂቱ ባቢሎን ነፃ ወጥተው ወደ ንጹሕ አምልኮ ሲመለሱ የኢሳይያስ ቃላት ታላቅ ፍጻሜያቸውን አግኝተዋል።

8 ይሁንና በተስፋ ቃሉ የመጀመሪያ ፍጻሜ ተጠቃሚ ስለሚሆኑት በባቢሎን ምርኮ ያሉ አይሁዳውያንስ ምን ማለት ይቻላል? ይሖዋ ወደ ተወደደችው የትውልድ አገራቸው እንደሚመልሳቸው በሰጠው የተስፋ ቃል ሊታመኑ ይችላሉ? እንዴታ! ኢሳይያስ ግልጽ መግለጫዎችንና በዕለት ተዕለት ሕይወት የሚታዩ ምሳሌዎችን በመጠቀም ይሖዋ የገባውን ቃል ይፈጽማል የሚል ሙሉ ትምክህት እንዲኖራቸው የሚያስገድዱ ምክንያቶችን ጠቅሷል።

ቃሉ ዘላለማዊ የሆነ አምላክ

9, 10. ኢሳይያስ የሰውን ሕይወት አላፊ መሆን ከአምላክ “ቃል” ዘላቂነት ጋር ያነጻጸረው እንዴት ነው?

9 በመጀመሪያ ደረጃ ተመልሰው እንደሚቋቋሙ የተነገረው የአምላክ ቃል ዘላለማዊ ነው። ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ጩኽ የሚል ሰው ቃል፤ ምን ብዬ ልጩኽ? አልሁ። ሥጋ ለባሽ ሁሉ ሣር ነው፣ ክብሩም ሁሉ እንደ ምድረ በዳ አበባ ነው። የእግዚአብሔር እስትንፋስ ይነፍስበታልና ሣሩ ይደርቃል አበባውም ይረግፋል፤ በእውነት ሕዝቡ ሣር ነው። ሣሩ ይደርቃል አበባውም ይረግፋል፣ የአምላካችን ቃል ግን ለዘላለም ጸንታ ትኖራለች።”​—⁠ኢሳይያስ 40:​6-8

10 እስራኤላውያን ሣር ለዘላለም የሚቆይ ነገር እንዳልሆነ አሳምረው ያውቃሉ። በበጋ ወራት ኃይለኛ የሆነው የፀሐይ ሙቀት ሲመታው አረንጓዴ የነበረው ሣር ይደርቅና ቡናማ ይሆናል። በአንዳንድ መልኩ ሲታይ የሰው ልጅ ሕይወትም እንደ ሣር ጊዜያዊ ነው። (መዝሙር 103:​15, 16፤ ያዕቆብ 1:​10, 11) ኢሳይያስ እያነጻጸረ የሚናገረው የሰውን ሕይወት አላፊነት ከአምላክ “ቃል” ማለትም ከተገለጠው ዓላማው ዘላቂነት ጋር ነው። አዎን፣ “የአምላካችን ቃል” ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል። አምላክ አንዴ የተናገረውን ቃሉን የሚሽር ወይም እንዳይፈጸም ሊያግድ የሚችል አንዳች ነገር አይኖርም።​—⁠ኢያሱ 23:​14

11. ይሖዋ በጽሑፍ በሰፈረው ቃሉ ውስጥ ያለውን የተስፋ ቃል ይፈጽማል ብለን ልንታመንበት የምንችለው ለምንድን ነው?

11 ዛሬ ስለ ዓላማው የሚገልጸውን የይሖዋ ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በጽሑፍ መልክ ሰፍሮ እናገኘዋለን። ባለፉት መቶ ዘመናት መጽሐፍ ቅዱስ መራራ ተቃውሞ የገጠመው ሲሆን ደፋር የሆኑ ተርጓሚዎችና ሌሎች ሰዎች መጽሐፉን ጠብቀው ለማቆየት ሲሉ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ ጥለዋል። ይሁን እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ እስካሁን ድረስ ተጠብቆ የቆየው በእነርሱ ጥረት ብቻ ነው ማለት አይደለም። ሊመሰገን የሚገባው ቃሉን የሚጠብቀው ‘ሕያውና ዘላለማዊ የሆነው አምላክ’ ይሖዋ ነው። (1 ጴጥሮስ 1:​23-25) እስቲ አስበው:- ይሖዋ ቃሉ ጸንቶ እንዲኖር ካደረገ በቃሉ ውስጥ ያለውን ተስፋ አይፈጽምም ብለን የምንጠራጠርበት ምክንያት ይኖራል?

በጎቹን በርኅራኄ የሚይዝ ኃያል አምላክ

12, 13. (ሀ) ተመልሶ ስለመቋቋም የተነገረው የተስፋ ቃል ሊታመን የሚችለው ለምንድን ነው? (ለ) በግዞት ለነበሩት አይሁዳውያን ምን ምሥራች ነበረ? እርግጠኞች ሊሆኑ የሚችሉትስ ለምንድን ነው?

12 ኢሳይያስ ተመልሶ ስለመቋቋም የተሰጠው የተስፋ ቃል እምነት ሊጣልበት የሚችል መሆኑን የሚያሳይ ሁለተኛ ምክንያት ይጠቅሳል። የተስፋ ቃሉን የሰጠው አምላክ ሕዝቡን በርኅራኄ የሚይዝ ኃያል አምላክ ነው። ኢሳይያስ እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “የምስራች የምትነግሪ ጽዮን ሆይ [“ለጽዮን የምስራች የምትነግሪ ሆይ፣” NW ]፣ ከፍ ወዳለው ተራራ ውጪ፤ የምስራች የምትነግሪ ኢየሩሳሌም ሆይ፣ [“ለኢየሩሳሌም የምስራች የምትነግሪ ሆይ፣” NW ] ድምፅሽን በኃይል አንሺ፤ አንሺ፣ አትፍሪ፤ ለይሁዳም ከተሞች:- እነሆ፣ አምላካችሁ! ብለሽ ንገሪ። እነሆ፣ ጌታ እግዚአብሔር እንደ ኃያል [“በኃይልም፣” የአዲሲቱ ዓለም ትርጉም የግርጌ ማስታወሻ ] ይመጣል ክንዱም ስለ እርሱ ይገዛል፤ እነሆ፣ ዋጋው ከእርሱ ጋር ደመወዙም በፊቱ ነው። መንጋውን እንደ እረኛ ያሰማራል፣ ጠቦቶቹን በክንዱ ሰብስቦ በብብቱ ይሸከማል፣ የሚያጠቡትንም በቀስታ ይመራል።”​—⁠ኢሳይያስ 40:​9-11

13 በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን ሴቶች በጦር ሜዳ ስለተገኘው ድል ወይም ሊመጣ ስላለው የተሻለ ነገር ምሥራች በመዘመር በተገኘው ውጤት የተሰማቸውን ደስታ መግለጻቸው የተለመደ ነገር ነበር። (1 ሳሙኤል 18:​6, 7፤ መዝሙር 68:​111980 ትርጉም ) ኢሳይያስ አይሁዳውያኑ ምርኮኞች ያላንዳች ፍርሃት ከተራራ ጫፍ ላይ በጩኸት የሚነገር ምሥራች እንደሚጠብቃቸው በትንቢታዊ መልክ መናገሩ ነበር። ይህም ይሖዋ ሕዝቡን ወደ ተወደደችው ኢየሩሳሌም መመለሱ ነው! ይሖዋ “በኃይል” ስለሚመጣ እርግጠኛ ሆነው ሊጠብቁ ይችላሉ። በመሆኑም የገባውን ቃል እንዳይፈጽም ሊያግደው የሚችል ነገር አይኖርም።

14. (ሀ) ይሖዋ ሕዝቡን የሚመራበትን የርኅራኄ መንገድ ኢሳይያስ በምሳሌ ያስረዳው እንዴት ነው? (ለ) እረኞች በጎቻቸውን በርኅራኄ እንደሚይዙ የሚያሳየው የትኛው መግለጫ ነው? (ገጽ 405 ላይ የሚገኘውን ሣጥን ተመልከት።)

14 ይሁን እንጂ ይህ ኃያል አምላክ ርኅሩኅም ነው። ይሖዋ ሕዝቡን ወደ ትውልድ አገራቸው እንዴት እንደሚመራቸው ኢሳይያስ ግሩም አድርጎ ይገልጻል። ይሖዋ ጠቦቶቹን ሰብስቦ “በብብቱ” እንደሚሸከም አፍቃሪ እረኛ ነው። እዚህ ላይ “በብብቱ” የሚለው መግለጫ አጣፍቶ የሚለብሰውን ጨርቅ የሚያመለክት እንደሆነ ከሁኔታው መረዳት ይቻላል። አንዳንድ ጊዜ እረኞች ከሌሎቹ እኩል መሄድ የማይችሉትን አዲስ የተወለዱ ግልገሎች የሚሸከሟቸው እዚህ ውስጥ ነው። (2 ሳሙኤል 12:​3) ከእረኝነት ጋር የተያያዘው እንዲህ ያለው ልብ የሚነካ መግለጫ በግዞት ለነበረው ሕዝብ የይሖዋን ፍቅራዊ አሳቢነት የሚያረጋግጥ እንደነበር ጥርጥር የለውም። በእርግጥም ደግሞ እንዲህ ያለው ኃያልና ርኅሩኅ አምላክ የገባውን ቃል እንደሚፈጽም እምነት ሊጣልበት ይችላል!

15. (ሀ) ይሖዋ ‘በኃይል’ የመጣው መቼ ነው? ‘ስለ እርሱ የሚገዛው ክንዱ’ ማን ነው? (ለ) በድፍረት ሊታወጅ የሚገባው ምሥራች የትኛው ነው?

15 የኢሳይያስ ቃላት ለዘመናችንም የሚሆን ትንቢታዊ ትርጉም ያዘሉ ናቸው። በ1914 ይሖዋ ‘በኃይል’ መጥቶ በሰማይ መንግሥቱን አቋቁሟል። ‘ስለ እርሱ የሚገዛው ክንዱ’ የተባለው ይሖዋ በሰማያዊ ዙፋን ያስቀመጠው ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በ1919 ይሖዋ በምድር የነበሩትን ቅቡዓን አገልጋዮቹን ከታላቂቱ ባቢሎን ግዞት ነፃ በማውጣት ሕያውና እውነተኛ የሆነውን አምላክ አምልኮ ሙሉ በሙሉ መልሶ የማቋቋሙን ተግባር አስጀምሯል። ከዳር እስከ ዳር ይሰማ ዘንድ ይህ ምሥራች ተራራ ጫፍ ላይ ሆኖ የመጮህ ያህል በድፍረት ሊታወጅ ይገባል። እንግዲያው ይሖዋ አምላክ እውነተኛውን አምልኮ በዚህች ምድር ላይ መልሶ እንዳቋቋመ ድምፃችንን ከፍ አድርገን ለሌሎች በድፍረት እንናገር!

16. ይሖዋ ዛሬ ሕዝቡን የሚመራው እንዴት ነው? ይህስ ምሳሌ የሚሆነው እንዴት ነው?

16 በ⁠ኢሳይያስ 40:​10, 11 ላይ የሚገኙት ቃላት በዛሬው ጊዜ ላለነው ሰዎች ተጨማሪ ጠቀሜታም አላቸው። ይሖዋ ሕዝቦቹን የሚመራበትን የርኅራኄ አያያዝ መመርመር የሚያጽናና ነው። አንድ እረኛ ከሌሎች እኩል መሄድ የማይችሉትን ጨምሮ እያንዳንዱ በግ ምን እንደሚያስፈልገው እንደሚያውቅ ሁሉ ይሖዋም እያንዳንዱ የታመነ አገልጋዩ ያለበትን የአቅም ገደብ ይገነዘባል። ከዚህም በተጨማሪ ርኅሩኁ እረኛ ይሖዋ ለክርስቲያን እረኞች ግሩም ምሳሌ ይሆናል። ሽማግሌዎች ይሖዋ ራሱ ያሳየውን ፍቅራዊ አሳቢነት በመኮረጅ መንጋውን በርኅራኄ መያዝ ይኖርባቸዋል። ይሖዋ ‘በገዛ ልጁ ደም በዋጀው’ መንጋ ውስጥ ለሚገኝ ለእያንዳንዱ አባል ምን እንደሚሰማው ዘወትር ማስታወስ ይኖርባቸዋል።​—⁠ሥራ 20:​28

በኃይሉና በጥበቡ አቻ የሌለው

17, 18. (ሀ) አይሁዳውያኑ ግዞተኞች ተመልሰው እንደሚቋቋሙ በተሰጠው የተስፋ ቃል ላይ ትምክህት ሊኖራቸው የሚችለው ለምንድን ነው? (ለ) ኢሳይያስ ያነሳቸው የሚያስፈሩ ጥያቄዎች የትኞቹ ናቸው?

17 የአምላክ ኃይልና ጥበብ አቻ የማይገኝለት በመሆኑ ግዞተኞቹ አይሁዳውያን ተመልሰው እንደሚቋቋሙ በተሰጠው የተስፋ ቃል ሊተማመኑ ይችላሉ። ኢሳይያስ እንዲህ ይላል:- “ውኆችን በእፍኙ የሰፈረ፣ ሰማይንም በስንዝር የለካ፣ የምድርንም አፈር በመስፈርያ ሰብስቦ የያዘ፣ ተራሮችን በሚዛን ኮረብቶችንም በሚዛኖች የመዘነ ማን ነው? የእግዚአብሔርን መንፈስ ያዘዘ፣ ወይስ አማካሪ ሆኖ ያስተማረው ማን ነው? ወይስ ከማን ጋር ተመካከረ? ወይስ ማን መከረው? የፍርድንም መንገድ ማን አስተማረው? እውቀትንስ ማን አስተማረው? የማስተዋልንስ መንገድ ማን አሳየው?”​—⁠ኢሳይያስ 40:​12-14

18 እነዚህ በግዞት ላይ የነበሩት አይሁዳውያን ሊያሰላስሉባቸው የሚገቡ አክብሮታዊ ፍርሃት የሚያሳድሩ ጥያቄዎች ናቸው። ሥጋ ለባሽ የሆነው ሰው የአንድን ትልቅ ባሕር ሞገድ ሊያስቆም ይችላልን? እንዴት አድርጎ! ይሁንና በይሖዋ ፊት ምድርን የሸፈኗት ባሕሮች በመዳፉ ላይ እንዳለች አንድ ጠብታ ናቸው። * ደካማ የሆኑ ሰዎች ከዋክብት የሞሉበትን ሰፊ ሰማይ መለካት ወይም የምድርን ተራሮችና ኮረብቶች መመዘን ይችላሉን? በፍጹም። ይሖዋ ግን ሰው አንድን ነገር በስንዝር ማለትም ከአውራ ጣቱ እስከ ትንሿ ጣቱ ጫፍ ድረስ ባለው ርቀት መለካት እንደሚችል ሁሉ በቀላሉ ሊለካቸው ይችላል። አምላክ ተራሮችንና ኮረብቶችን በሚዛን ሊለካቸው የሚችል ያህል ነው። ከሰዎች መካከል እጅግ ጠቢብ የሚባሉት እንኳ ቢሆኑ አሁን ስላለውም ሁኔታ ይሁን ወደፊት ስለሚመጣው ነገር እንዲህ አድርግ ብለው አምላክን ሊያማክሩት ይችላሉን? በፍጹም አይችሉም!

19, 20. የይሖዋን ታላቅነት ጎላ አድርጎ ለመግለጽ ኢሳይያስ ምን ስዕላዊ መግለጫ ተጠቅሟል?

19 በምድር ስላሉት ኃያላን ብሔራትስ ምን ለማለት ይቻላል? አምላክ የተስፋ ቃሉን እንዳይፈጽም ሊገቱት ይችሉ ይሆን? ኢሳይያስ ብሔራትን እንደሚከተለው ብሎ በመግለጽ መልስ ይሰጣል:- “እነሆ፣ አሕዛብ በገንቦ እንዳለች ጠብታ ናቸው፣ በሚዛንም እንዳለ ትንሽ ትቢያ ተቈጥረዋል፤ እነሆ፣ ደሴቶችን እንደ ቀላል ነገር ያነሣል። ሊባኖስ ለማንደጃ እንስሶችዋም ለሚቃጠል መሥዋዕት አይበቁም። አሕዛብ ሁሉ በፊቱ እንዳልነበሩ ናቸው፤ ከምናምን እንደሚያንሱ፣ እንደ ከንቱ ነገርም ይቈጥራቸዋል።”​—⁠ኢሳይያስ 40:​15-17

20 ብሔራት በጠቅላላ በይሖዋ ፊት በገንቦ እንዳለች ጠብታ ናቸው። ምንም ለውጥ እንደማያመጣ በሚዛን ላይ እንዳለ ደቃቅ ትቢያ ከመሆን አያልፉም። * አንድ ሰው ትልቅ መሠዊያ ገንብቶ የሊባኖስን ተራሮች የሸፈኑትን ዛፎች ሁሉ ማገዶ ቢያደርግና በተራራው ላይ የሚዘዋወሩትን እንስሳት ሁሉ መሥዋዕት አድርጎ ቢያቀርባቸው እንኳ ለይሖዋ የሚበቃ አይሆንም። ኢሳይያስ እስካሁን የተጠቀመባቸው መግለጫዎች ሁሉ በቂ ስላልሆኑ ሌላ የበለጠ ጠንከር ያለ መግለጫ በመጠቀም ብሔራት ሁሉ በይሖዋ ዓይን “ከምንም ያነሱ” ናቸው ብሏል።​—⁠ኢሳይያስ 40:​17ኒው ሪቫይዝድ ስታንዳርድ ቨርሽን

21, 22. (ሀ) ይሖዋ አቻ የሌለው መሆኑን ኢሳይያስ ጎላ አድርጎ የገለጸው እንዴት ነው? (ለ) ሕያው የሆነው የኢሳይያስ መግለጫ ወደ ምን መደምደሚያ ያደርሰናል? (ሐ) ነቢዩ ኢሳይያስ ሳይንሳዊ ትክክለኛነቱ የተረጋገጠ ምን ነገር ተናግሯል? (ገጽ 412 ላይ የሚገኘውን ሣጥን ተመልከት።)

21 ኢሳይያስ፣ ይሖዋ አቻ የማይገኝለት አምላክ መሆኑን ይበልጥ ጠበቅ አድርጎ ለመግለጽ ሲል ከወርቅ፣ ከብር ወይም ከእንጨት አማልክት የሚሠሩትን ሰዎች የሞኝነት ድርጊት ማጋለጡን ይቀጥላል። እንዲህ ያለ ማንኛውም ጣዖት ‘በምድር ክበብ ላይ የሚቀመጠውን ’ እና ነዋሪዎቿን የሚመለከተውን አምላክ ይወክላል ብሎ ማሰብ ምንኛ ሞኝነት ይሆናል!​—⁠ኢሳይያስ 40:​18-24ን አንብብ።

22 ይህ ሁሉ የማያሻማ መግለጫ ወደ አንድ መደምደሚያ ያደርሰናል። በኃይሉና በጥበቡ አቻ የማይገኝለት አምላክ ይሖዋ የገባውን ቃል እንዳይፈጽም የሚያግደው አንዳች ነገር የለም። ኢሳይያስ የተናገራቸው ቃላት ወደ ትውልድ አገራቸው ለመመለስ ይናፍቁ የነበሩትን በባቢሎን ግዞተኛ የሆኑ አይሁዳውያን ምንኛ አጽናንተዋቸውና አበረታተዋቸው መሆን ይኖርበታል! ዛሬ እኛም ይሖዋ ወደፊት እንደሚፈጸሙ ቃል የገባልን ነገሮች እውን እንደሚሆኑ እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን።

“እነዚህን የፈጠረ ማን ነው?”

23. አይሁዳውያን ግዞተኞች የሚበረታቱበት ምን ምክንያት ነበራቸው? አሁን ይሖዋ ስለ ራሱ ጠበቅ አድርጎ የሚገልጸው ነገር ምንድን ነው?

23 አይሁዳውያን ምርኮኞች የሚበረታቱበት ሌላም ምክንያት ነበር። ነፃ እንደሚወጡ ቃል የገባላቸው የሁሉ ነገር ፈጣሪና የታላቅ ኃይል ምንጭ የሆነው አምላክ ነው። ይህን ከፍተኛ ችሎታውን ጎላ አድርጎ ለመግለጽ ይሖዋ በፍጥረት ሥራው በተንጸባረቀው ችሎታው ላይ እንዲያተኩሩ ያደርጋል:- “እንግዲህ እተካከለው ዘንድ በማን መሰላችሁኝ? ይላል ቅዱሱ። ዓይናችሁን ወደ ላይ አንሥታችሁ ተመልከቱ፤ እነዚህን የፈጠረ ማን ነው? ሠራዊታቸውን በቁጥር የሚያወጣ እርሱ ነው፣ ሁሉንም በየስማቸው ይጠራቸዋል፤ በኃይሉ ብዛትና በችሎቱ ብርታት አንድስ እንኳ አይታጣውም።”​—⁠ኢሳይያስ 40:​25, 26

24. ይሖዋ ስለ ራሱ ሲናገር አቻ የሌለው መሆኑን ያስረዳው እንዴት ነው?

24 የእስራኤል ቅዱስ እየተናገረ ያለው ስለ ራሱ ነው። ይሖዋ አቻ የሌለው መሆኑን ሲገልጽ የሰማይን ከዋክብት እንዲመለከቱ ተናግሯል። ሠራዊቱን እንደሚያዝዝ አንድ የጦር አዛዥ ይሖዋም ከዋክብቱን ያዝዛቸዋል። አንድ ላይ ሊሰበስባቸው ቢፈልግ እንኳ ‘አንዳቸውም አይጠፉበትም።’ የከዋክብቱ ቁጥር ሕልቆ መሳፍርት የሌለው ቢሆንም እያንዳንዳቸውን በግል ስማቸውም ወይም እንደ ስም ባለው ስያሜያቸው ይጠራቸዋል። እነርሱም መሪያቸው ‘ታላቅ ኃይል’ ያለውና ‘ብርቱ’ በመሆኑ እንደ ታዛዥ ወታደር በሥርዓት ቦታቸውን ጠብቀው ይመላለሳሉ። በመሆኑም አይሁዳውያን ግዞተኞች እርግጠኛ የሚሆኑበት ምክንያት ነበራቸው። ከዋክብትን የሚያዝዘው ፈጣሪ አገልጋዮቹን ለመደገፍ አያንስም።

25. በ⁠ኢሳይያስ 40:​26 ላይ ተመዝግቦ ለሚገኘው መለኮታዊ ጥሪ ምላሽ የምንሰጠው እንዴት ሊሆን ይችላል? ከምንስ ውጤት ጋር?

25 በኢሳይያስ 40:​26 ላይ ተመዝግቦ የሚገኘውን “ዓይናችሁን ወደ ላይ አንሥታችሁ ተመልከቱ” የሚለውን መለኮታዊ ጥሪ ሊቃወም የሚችል ማን አለ? ከዘመናዊው የከዋክብት ጥናት ግኝቶች የተነሣ በከዋክብት የተሞላው ሰማይ አስፈሪ ግርማ ያለው መሆኑ ከኢሳይያስ ዘመን ይበልጥ ዛሬ ግልጽ ሆኗል። ከፍተኛ ኃይል ባላቸው ቴሌስኮፖቻቸው የሰማይን አካል የሚመለከቱት ተመራማሪዎች ሊታይ የሚችለው አጽናፈ ዓለም እስከ 125 ቢልዮን የሚገመቱ ጋላክሲዎችን እንደያዘ ይገምታሉ። ከእነዚህ መካከል አንዱ ብቻ እንኳ ማለትም ሚልክዌይ የተባለው ጋላክሲ በአንዳንድ ግምቶች መሠረት ከ100 ቢልዮን የሚበልጡ ከዋክብት ይዟል! እንዲህ ያለውን ነገር ማወቃችን ለፈጣሪ አክብሮት እንዲያድርብንና ተስፋ በሰጠበት ቃሉ ላይ ሙሉ ትምክህት እንዲኖረን የሚያደርግ ነው።

26, 27. በባቢሎን የነበሩት ግዞተኞች ስሜት የተገለጸው እንዴት ነው? ምን ነገርስ ማወቅ አስፈልጓቸው ነበር?

26 ይሖዋ አይሁዳውያኑ ግዞተኞች በምርኮ በሚቆዩባቸው ረጅም ዓመታት መንፈሳቸው ሊዳከም እንደሚችል ስላወቀ ኢሳይያስ የሚከተሉትን የማረጋገጫ ቃላት አስቀድሞ እንዲጽፍ አድርጓል:- “ያዕቆብ ሆይ፣ እስራኤልም ሆይ:- መንገዴ ከእግዚአብሔር ተሰውራለች ፍርዴም ከአምላኬ አልፋለች ለምን ትላለህ? ለምንስ እንዲህ ትናገራለህ? አላወቅህምን? አልሰማህምን? እግዚአብሔር የዘላለም አምላክ፣ የምድርም ዳርቻ ፈጣሪ ነው፤ አይደክምም፣ አይታክትም፣ ማስተዋሉም አይመረመርም።”​—⁠ኢሳይያስ 40:​27, 28

27 ኢሳይያስ ከትውልድ አገራቸው በመቶዎች የሚቆጠሩ ኪሎ ሜትሮች ርቀው በባቢሎን የሚገኙት ግዞተኞች ስሜት ምን እንደሚመስል የሚገልጹትን ይሖዋ የተናገራቸውን ቃላት መዝግቧል። አንዳንዶች ‘መንገዳቸውን’ ማለትም የሚገፉትን አስቸጋሪ የሕይወት ጎዳና አምላክ እንደማያይ ወይም እንደማያውቅ አድርገው ያስቡ ይሆናል። ለሚደርስባቸው የፍትሕ መጓደል ይሖዋ ግዴለሽ እንደሆነ አድርገው ያስባሉ። ከራሳቸው የግል ተሞክሮም ይሁን ከሌሎች በመስማት የሚያውቋቸውን ነገሮች እንደገና አስታውሷቸዋል። ይሖዋ ሕዝቡን ነፃ ለማውጣት ችሎታውም ፈቃደኛነቱም አለው። እርሱ ዘላለማዊ አምላክና የመላዋ ምድር ፈጣሪ ነው። የፍጥረት ሥራውን ሲያከናውን የተጠቀመበት ኃይሉ አሁንም አለ። ኃያሏ ባቢሎንም ብትሆን ከአቅሙ በላይ አይደለችም። እንዲህ ያለው አምላክ አቅም አጥቶ ለሕዝቡ ማድረግ የሚሳነው ነገር አይኖርም። የይሖዋን አሠራር ሙሉ በሙሉ እንረዳለን ብለውም መጠበቅ አይኖርባቸውም። የእርሱ ሐሳብ ወይም ማስተዋሉ ከአእምሮአቸው በላይ ነው።

28, 29. (ሀ) ይሖዋ ደካሞችን እንደሚረዳ ሕዝቡን ያሳሰባቸው እንዴት ነው? (ለ) ይሖዋ ለሕዝቡ ኃይል የሚሰጠው እንዴት እንደሆነ ለማስረዳት የተጠቀሰው ምሳሌ ምንድን ነው?

28 ይሖዋ ትካዜ ላይ ለወደቁት ግዞተኞች በኢሳይያስ አማካኝነት ማበረታቻ መስጠቱን ይቀጥላል:- “ለደካማ ኃይልን ይሰጣል፣ ጉልበት ለሌለውም ብርታትን ይጨምራል። ብላቴኖች ይደክማሉ ይታክቱማል፣ ጐበዛዝቱም ፈጽሞ ይወድቃሉ፤ እግዚአብሔርን በመተማመን የሚጠባበቁ ግን ኃይላቸውን ያድሳሉ፤ እንደ ንስር በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፣ አይታክቱም፤ ይሄዳሉ፣ አይደክሙም።”​—⁠ኢሳይያስ 40:​29-31

29 ይሖዋ ለደከሙት ኃይልን ስለመስጠት ሲናገር ግዞተኞቹ ወደ ትውልድ አገራቸው መመለስ የሚጠይቅባቸውን አስቸጋሪ ጉዞ በአእምሮው ይዞ ሊሆን ይችላል። ይሖዋ ለእርዳታ ወደ እርሱ የሚመጡትን የደከሙ ሰዎች መደገፍ ባሕርይው እንደሆነ ያስታውሳቸዋል። ብርቱ የሚባሉት ሰዎች ማለትም ‘ብላቴኖችና’ ‘ጎበዛዝት’ እንኳ በድካም ሊታክቱና ሊወድቁ ይችላሉ። ይሁንና ይሖዋ በእርሱ ለሚታመኑት ሰዎች ለመሮጥና ለመራመድ የሚያስችላቸውን ኃይል ይሰጣቸዋል። ያለ ፋታ ለሰዓታት ማንዣበብ የሚችለው የንስር ወፍ የሚያደርገው ብዙም ድካም የማይጠይቅ መስሎ የሚታይ በረራ ይሖዋ ለአገልጋዮቹ እንዴት ኃይል እንደሚሰጣቸው በጉልህ የሚያስረዳ ምሳሌ ይሆናል። * አይሁዳውያኑ ግዞተኞች እንዲህ ያለውን መለኮታዊ ድጋፍ የማግኘት ተስፋ ስላላቸው ተስፋ የሚቆርጡበት ምክንያት የለም።

30. ዛሬ ያሉ እውነተኛ ክርስቲያኖች ከኢሳይያስ ምዕራፍ 40 የመደምደሚያ ቁጥሮች ማጽናኛ ማግኘት የሚችሉት እንዴት ነው?

30 የ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 40 የመጨረሻ ቁጥሮች በዚህ ክፉ የነገሮች ሥርዓት የመጨረሻ ቀናት ውስጥ ለሚኖሩት እውነተኛ ክርስቲያኖች ጥሩ መጽናኛ ይዘዋል። ተስፋ እንድንቆርጥ ሊያደርጉን የሚችሉ ብዙ ተጽእኖዎችና ችግሮች ባሉበት በዚህ ጊዜ በጽናት የምንቋቋማቸውን መከራዎችና የሚደርስብንን የፍትሕ መጓደል አምላክ እንደሚመለከት ማወቃችን የሚያጽናና ነው። ‘ለጥበቡ ቁጥር የሌለው’ የሁሉ ነገር ፈጣሪ የወሰነው ጊዜ ሲደርስ በራሱ መንገድ የፍትሕ መጓደሉን እንደሚያስተካክለው እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን። (መዝሙር 147:​5, 6) እስከዚያው ድረስም ለመጽናት የምንታገለው ብቻችንን አይደለም። ምንጩ የማይነጥፈው ይሖዋ በፈተና ወቅት ለአገልጋዮቹ ብርታት አልፎ ተርፎም ‘ከወትሮው የበለጠ ኃይል’ ሊሰጣቸው ይችላል።​—⁠2 ቆሮንቶስ 4:​7 NW 

31. የኢሳይያስ ትንቢት በባቢሎን በግዞት ለነበሩት አይሁዳውያን ያዘለው ብርሃን የሚፈነጥቅ ተስፋ ምን ነበር? እኛስ ስለ ምን ነገር ሙሉ በሙሉ እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን?

31 በስድስተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ በባቢሎን ስለነበሩት አይሁዳውያን ግዞተኞች አስብ። በመቶዎች የሚቆጠሩ ኪሎ ሜትሮች ርቃ የምትገኘው ኢየሩሳሌም ባድማ ሆናና ቤተ መቅደሷም ፈራርሶ ነበር። የኢሳይያስ ትንቢት ይሖዋ ወደ ትውልድ አገራቸው እንደሚመልሳቸው የሚገልጽ ብርሃን የሚፈነጥቅና ተስፋ የሚሰጥ የሚያጽናና ተስፋ ይዞላቸዋል! በ537 ከዘአበ ይሖዋ ሕዝቡን ወደ ትውልድ አገራቸው በመመለስ የተስፋ ቃሉን የሚፈጽም አምላክ መሆኑን አሳይቷል። እኛም በይሖዋ ላይ ሙሉ እምነት ሊኖረን ይችላል። በኢሳይያስ ትንቢት ውስጥ ግሩም ሆኖ የተገለጸው የመንግሥቱ ተስፋ እውን ይሆናል። ይህ በእርግጥም ለመላው የሰው ዘር ብርሃን የሚፈነጥቅ ምሥራች ነው!

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.7 ኢሳይያስ የተናገረው የይሖዋን መንገድ ስለ ማዘጋጀት ነው። (ኢሳይያስ 40:​3) ወንጌሎች ደግሞ ይህንኑ ትንቢት የሚጠቅሱት መጥምቁ ዮሐንስ ለኢየሱስ ክርስቶስ መንገድ በማዘጋጀት ካከናወነው ሥራ ጋር በማያያዝ ነው። የክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን ጽሑፎችን በመንፈስ አነሳሽነት የጻፉት ሰዎች ትንቢቱን በዚህ መልክ የተጠቀሙበት ኢየሱስ አባቱን ስለሚወክልና በእርሱም ስም ስለመጣ ነው።​—⁠ዮሐንስ 5:​43፤ 8:​29

^ አን.18 “አጠቃላዩ የውቂያኖሶች መጠነቁስ (mass) 1.35 ኳንቲሊየን (1.35 x 1018) ሜትሪክ ቶን ወይም ከጠቅላላው የምድር መጠነቁስ 1/4400 እንደሚሆን” ይገመታል።​—⁠ኢንካርታ 97 ኢንሳይክሎፔዲያ

^ አን.20 ዚ ኤክሲፖዚተርስ ባይብል ኮሜንታሪ እንዲህ ይላል:- “በምሥራቃውያን የገበያ ቦታ በሚካሄደው ንግድ ፈሳሽ ነገሮች በሚለኩበት ገንቦ ውስጥ ያለችውን ትንሽ የውኃ ጠብታ ወይም ደግሞ ሥጋ አሊያም ፍራፍሬ ሲመዘን በሚዛን ላይ የሚኖረውን ትቢያ ከግምት ውስጥ የሚያስገባ የለም።”

^ አን.29 ንስር ብዙም ኃይል ሳይጠይቅበት ከፍ ብሎ እየተንሳፈፈ ይቆያል። ይህንን የሚያደርገው ሙቅ አየር ወደ ላይ የሚወጣባቸውን መስመሮች ወይም ቴርማልስ በመከተል ነው።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 404, 405 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

ይሖዋ አፍቃሪ እረኛ ነው

ኢሳይያስ በጎቹን በብብቱ አቅፎ ከሚይዝ እረኛ ጋር በማወዳደር ስለ ይሖዋ ተናግሯል። (ኢሳይያስ 40:​10, 11) ኢሳይያስ ይህን ምሳሌ የሰጠው በእረኞች የዕለት ተዕለት ልማድ ላይ ተመርኩዞ እንደነበር ግልጽ ነው። በመካከለኛው ምሥራቅ የሄርሞን ተራራ ላይ ያሉ እረኞችን በቅርብ የተከታተለ አንድ ታዛቢ እንዲህ ብሏል:- “እያንዳንዱ እረኛ ሁኔታቸውን ለማወቅ መንጋውን በቅርብ ይከታተላል። አዲስ የተወለደ ግልገል ሲያገኝ እናቷን ለመከተል አቅሙ ስለማይኖራት በካባው . . . ማጣፊያ ውስጥ ይይዛታል። እቅፉ ሲሞላ ደግሞ እናታቸውን መከተል እስኪችሉ ድረስ በእግራቸው እያንጠለጠለ ትከሻቸው ላይ ይሸከማቸዋል አለዚያም ቅርጫት ወይም ከረጢት ውስጥ አድርጎ በአህያ ጀርባ ላይ ይጭናቸዋል።” የምናገለግለው አምላክ ለሕዝቡ እንዲህ ያለ ርኅራኄ የተሞላበት አሳቢነት የሚያሳይ መሆኑን ማወቃችን የሚያጽናና አይደለምን?

[በገጽ 412 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

የምድር ቅርጽ ምን ዓይነት ነው?

በጥንት ዘመን አብዛኛው ሰው የሚያስበው ምድር ጠፍጣፋ እንደሆነች ነበር። በስድስተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ መጀመሪያ ላይ ግሪካዊው ፈላስፋ ፓይታጎረስ ምድር ሉል መሆን አለባት የሚል ጽንሰ ሐሳብ አፈለቀ። ያም ሆኖ ግን ፓይታጎረስ ይህንን ጽንሰ ሐሳብ ከማፍለቁ ሁለት መቶ ዓመታት ቀደም ብሎ ነቢዩ ኢሳይያስ አስገራሚ በሆነ ግልጽነትና እርግጠኝነት “እርሱ በምድር ክበብ ላይ ይቀመጣል” ሲል ተናግሯል። (ኢሳይያስ 40:​22፣ በሰያፍ የጻፍነው እኛ ነን።) እዚህ ላይ “ክበብ” ተብሎ የተተረጎመው ኩግ የሚለው የዕብራይስጥ ቃል “ሉል” ተብሎም ሊተረጎም ይችላል። የሚያስገርመው ደግሞ ከየትኛውም አቅጣጫ ክብ ሆኖ የሚታየው የሉል ቅርጽ ያለው ነገር ብቻ ነው። * በዚህ መንገድ ነቢዩ ኢሳይያስ በዘመኑ ከነበረ ግምታዊ ሐሳብ የጸዳና ከትክክለኛ ሳይንስ ጋር የሚጣጣም ሐሳብ መዝግቧል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.72 ምድር ጥፍጥፍ ሉልመሳይ (oblate spheroid) ነች ለማለት ይቻላል። በዋልታዎቿ አካባቢ በተወሰነ መጠን ጠፍጣፋ ቅርጽ አላት።

[በገጽ 403 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

መጥምቁ ዮሐንስ “በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ” ነበር