በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከዳተኛነትን የሚመለከት የማስጠንቀቂያ ትምህርት

ከዳተኛነትን የሚመለከት የማስጠንቀቂያ ትምህርት

ምዕራፍ አሥራ ስምንት

ከዳተኛነትን የሚመለከት የማስጠንቀቂያ ትምህርት

ኢሳይያስ 22:​1-25

1. ዙሪያዋን በተከበበች አንዲት ጥንታዊ ከተማ ውስጥ መገኘት ምን ሊመስል ይችላል?

ዙሪያዋን በተከበበች አንድ የጥንት ከተማ ውስጥ ብትሆን ሁኔታው ምን ሊመስል እንደሚችል አስብ። ከከተማዋ ቅጥር ውጭ ብርቱና ጨካኝ የሆነ የጠላት ሠራዊት ሰፍሯል። ከዚህ ቀደም ሌሎች ከተሞችን እንዳንበረከከ ታውቃለህ። አሁን ደግሞ አንተ ያለህባትን ከተማ በቁጥጥሩ ሥር ለማስገባትና ለመበዝበዝ እንዲሁም ነዋሪዎቿን ለማስነወርና ለመጨፍጨፍ ቆርጦ ተነስቷል። ይህን የጠላት ሠራዊት ፊት ለፊት በውጊያ መግጠም የማይታሰብ ነገር ነው። እንዳይገቡ ያግዳቸዋል ብለህ ተስፋ የምታደርገው አንድ ነገር ቢኖር የከተማዋ ቅጥር ብቻ ነው። በቅጥሩ ላይ አሻግረህ ስትመለከት ደግሞ የጠላት ሠራዊት የሠራውን የከበባ ቅጥር ታያለህ። ከዚህም በላይ መከላከያዎቻችሁን መደርመስ የሚችል መርግ የሚወረውሩበት መሣሪያ አላቸው። ቅጥሩን የሚያፈርሱበትን መሣሪያቸውን፣ መወጣጫ መሰላላቸውን፣ ቀስተኞቻቸውንና ሠረገሎቻቸውን እንዲሁም የሠራዊታቸውን ጭፍራ ትመለከታለህ። እንዴት የሚያስፈራ ነው!

2. በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 22 ላይ የተገለጸው ከበባ የተከሰተው መቼ ነው?

2 በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 22 ላይ በኢየሩሳሌም ላይ ስለተፈጸመ ተመሳሳይ ከበባ እናነባለን። ይህ የሆነው መቼ ነው? እዚህ ላይ የተገለጹት ነገሮች ሁሉ ፍጻሜያቸውን ያገኙበት ከበባ ይህ ነው ብሎ ለይቶ መናገር ያስቸግራል። ከሁኔታው ለመረዳት እንደሚቻለው ትንቢቱ ኢየሩሳሌም የሚገጥሟት የተለያዩ ከበባዎች አጠቃላይ ገጽታ ምን እንደሚመስል የሚጠቁም እንዲሁም ከፊታቸው ሊጠብቃቸው ስለሚችለው ነገር በጥቅሉ የሚያስጠነቅቅ ነው ቢባል ይቀላል።

3. የ⁠ኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ኢሳይያስ ለገለጸው ከበባ የሰጡት ምላሽ ምን ነበር?

3 ኢሳይያስ በገለጸው ዓይነት ከበባ ወቅት የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ምን ያደርጉ ይሆን? የአምላክ የቃል ኪዳን ሕዝብ እንደመሆናቸው መጠን ይሖዋ እንዲታደጋቸው ወደ እርሱ እየጮሁ ይሆን? የለም፣ እንዲያውም ዛሬ አምላክን እናመልካለን የሚሉ ሰዎች የሚያሳዩትን ዓይነት ጥበብ የጎደለው ዝንባሌ እያሳዩ ነው።

የተከበበች ከተማ

4. (ሀ) ‘የራእይው ሸለቆ’ የተባለችው ማን ናት? ይህ ስም የተሰጣትስ ለምንድን ነው? (ለ) የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች የነበራቸው መንፈሳዊ ሁኔታ ምን ይመስላል?

4 በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 21 ላይ ሦስቱም የፍርድ መልእክቶች ሲጀምሩ “ሸክም” የሚለውን ቃል ተጠቅመዋል። (ኢሳይያስ 21:​1, 11, 13) ኢሳይያስ ምዕራፍ 22⁠ም የሚጀምረው በተመሳሳይ መንገድ ነው:- “ስለ ራእይ ሸለቆ የተነገረ ሸክም። እናንተ ሁላችሁ ወደ ሰገነት መውጣታችሁ ምን ሆናችኋል?” (ኢሳይያስ 22:​1) ‘የራእይ ሸለቆ’ የተባለችው ኢየሩሳሌም ነች። ከተማዋ ከፍ ያለ ቦታ ላይ የምትገኝ ብትሆንም በትላልቅ ተራሮች የተከበበች በመሆኗ ሸለቆ ተብላለች። ከተማዋ ‘ከራእይ’ ጋር የተያያዘችው በዚያ የተገለጡ ብዙ መለኮታዊ ራእይዎች በመኖራቸው ነው። ከዚህ የተነሣ የከተማዋ ነዋሪዎች የይሖዋን ቃል መታዘዝ ይኖርባቸዋል። እነርሱ ግን በተቃራኒው እርሱን ችላ ብለው በሐሰት አምልኮ ተጠላልፈዋል። አምላክ ከተማዋን የከበበውን የጠላት ኃይል እንደ መሣሪያ በመጠቀም ይህን አስቸጋሪ የሆነውን ሕዝቡን ሊቀጣ ነው።​—⁠ዘዳግም 28:​45, 49, 50, 52

5. ሕዝቡ ወደ ሰገነታቸው የወጡት ለምን ሳይሆን አይቀርም?

5 ‘የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች በሙሉ ወደ ሰገነታቸው’ መውጣታቸውን ልብ በል። ጥንት የእስራኤላውያን ቤቶች ጣራ ጠፍጣፋ ስለነበረ ቤተሰቡ አብዛኛውን ጊዜ አንድ ላይ ይሰበሰብበታል። ኢሳይያስ በዚህ ወቅት ወደ ሰገነት የወጡበትን ምክንያት በተመለከተ ምንም ያለው ነገር የለም። ይሁን እንጂ አገላለጹ በነገሩ አለመደሰቱን ያሳያል። እንግዲያው ሰገነት ላይ የወጡት የሐሰት አማልክቶቻቸውን ለመለማመን ሳይሆን አይቀርም። ኢየሩሳሌም በ607 ከዘአበ ከመጥፋቷ በፊት በነበሩት ዓመታት እንዲህ ዓይነት ልማድ ነበራቸው።​—⁠ኤርምያስ 19:​13፤ ሶፎንያስ 1:​5

6. (ሀ) በኢየሩሳሌም ውስጥ ምን ዓይነት ሁኔታ ነግሦ ነበር? (ለ) አንዳንዶች የፈነጠዙት ለምንድን ነው? ይሁንና ምን ይጠብቃቸዋል?

6 ኢሳይያስ እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “ጩኸትና ፍጅት የተሞላብሽ ከተማ፣ ደስታ ያለሽ ከተማ ሆይ፣ በአንቺ ውስጥ የተገደሉት በሰይፍ የተገደሉ አይደሉም፣ በሰልፍም የሞቱ አይደሉም።” (ኢሳይያስ 22:​2) ብዙ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ወደ ከተማዋ በመጉረፋቸው ከተማዋ ተተረማምሳለች። በጎዳና ላይ የሚሄዱትም ሰዎች ይንጫጫሉ እንዲሁም ተሸብረዋል። አንዳንዶች ግን ምናልባት አስተማማኝ ሁኔታ እንዳላቸው ወይም ስጋቱ እንዳለፈ ስለተሰማቸው ሊሆን ይችላል ፈንጥዘዋል። * ይሁን እንጂ በዚህ ጊዜ መፈንጠዝ ሞኝነት ነው። ብዙዎቹ የከተማዋ ነዋሪዎች በሰይፍ ስለት ከመገደል የከፋ አሟሟት ይጠብቃቸዋል። ዙሪያዋን የተከበበች ከተማ ከውጭ ምግብ ማግኘት የምትችልበት መንገድ ሁሉ ይዘጋል። በከተማዋ ውስጥ ያለው ክምችት እየተመናመነ ይሄዳል። ረሃቡና መጨናነቁ ለወረርሽኝ በር ይከፍታል። ከዚህ የተነሣ በኢየሩሳሌም ያሉ ብዙዎች በረሃብና በቸነፈር ይሞታሉ። ይህ ነገር በ607 ከዘአበ እና በ70 እዘአ ተከስቷል።​—⁠2 ነገሥት 25:​3፤ ሰቆቃወ ኤርምያስ 4:​9, 10 *

7. በከበባው ወቅት የኢየሩሳሌም ገዥዎች ምን ያደርጋሉ? ምንስ ይደርስባቸዋል?

7 በዚህ ቀውጢ ወቅት የኢየሩሳሌም ገዥዎች ምን ዓይነት አመራር ይሰጡ ይሆን? ኢሳይያስ እንዲህ በማለት መልሱን ይሰጣል:- “አለቆችሽ ሁሉ በአንድነት ሸሹ፣ ያለ ቀስትም ተማረኩ፤ ከሩቅ ሸሽተው ከአንቺ ዘንድ የተገኙት ሁሉ በአንድነት ታሰሩ።” (ኢሳይያስ 22:​3) አለቆችና ኃያላኑ ለመሸሽ ሲሞክሩ ተይዘዋል! ምንም ቀስት መገተር ሳያስፈልግ ተማርከው እንደ አስረኛ ተነድተዋል። ይህ የሆነው በ607 ከዘአበ ነው። የኢየሩሳሌም ቅጥር ከተደረመሰ በኋላ ንጉሥ ሴዴቅያስ በምሽት ከኃያላኑ ጋር ሸሸ። ይህንን ያወቁት ጠላቶቹ ተከታትለው ኢያሪኮ ሜዳ ላይ ደረሱባቸው። ኃያላኑ ተበታተኑ። ሴዴቅያስን ይዘው ዓይኑን ካጠፉት በኋላ በመዳብ እግር ብረት አስረው እየጎተቱ ወደ ባቢሎን ወሰዱት። (2 ነገሥት 25:​2-7) ከዳተኝነቱ ያስከተለበት እንዴት ያለ የሚያሳዝን ውጤት ነው!

መከራው ያስከተለው ሐዘን

8. (ሀ) ኢየሩሳሌም ጥፋት እንደሚደርስባት የሚናገረውን ትንቢት በተመለከተ ኢሳይያስ ምን ተሰምቶታል? (ለ) በኢየሩሳሌም የሚታየው ትዕይንት ምን ይመስላል?

8 ይህ ትንቢት ኢሳይያስን በጥልቅ ነክቶታል። እንዲህ ይላል:- “ፊታችሁን ከእኔ ዘንድ አርቁ፤ መራራ ልቅሶ አለቅሳለሁ፤ ስለ ሕዝቤ ሴት ልጅ ጥፋት ታጽናኑኝ ዘንድ አትድከሙ።” (ኢሳይያስ 22:​4) ኢሳይያስ በትንቢት በተነገረው የሞዓብና የባቢሎን የወደፊት ዕጣም አዝኖ ነበር። (ኢሳይያስ 16:​11፤ 21:​3) አሁን ደግሞ በገዛ ሕዝቡ ላይ የሚመጣውን መዓት ሲያስበው የሚሰማው ሐዘንና ሰቆቃ የባሰ ነው። ሊጽናናም አልቻለም። ለምን? “ከሠራዊት ጌታ ከእግዚአብሔር ዘንድ የድንጋጤና የመረገጥ የድብልቅልቅም ቀን፣ የቅጥርም መፍረስ ወደ ተራራም መጮኽ በራእይ ሸለቆ ውስጥ ሆኖአል።” (ኢሳይያስ 22:​5) ኢየሩሳሌም ድብልቅልቅ ትላለች። ሕዝቡ የሚይዘውና የሚጨብጠው ጠፍቶት ወዲያና ወዲህ ይቅበዘበዛል። ጠላት የከተማዋን ቅጥር ደርምሶ መግባት ሲጀምር ‘ወደ ተራራ ይጮኻሉ።’ ይህ ማለት የከተማዋ ነዋሪዎች በሞሪያ ተራራ ላይ በሚገኘው ቅዱስ መቅደሱ ውስጥ ወዳለው አምላክ ይጮኻሉ ማለት ነውን? ምናልባት ሊሆን ይችላል። ታማኝነት ከጎደለው አካሄዳቸው አንጻር ሲታይ ግን በፍርሃት ተውጠው የሚያሰሙት ጩኸት ከአካባቢው ተራሮች ጋር ተጋጭቶ ከማስተጋባት ያለፈ የሚፈይደው ነገር አይኖርም።

9. ኢየሩሳሌምን ስጋት ላይ የጣላትን ሠራዊት ሁኔታ ግለጽ።

9 ኢየሩሳሌምን ስጋት ላይ የጣላት ምን ዓይነት ጠላት ነው? ኢሳይያስ እንዲህ ይለናል:- “ኤላምም ከሰረገለኞችና ከፈረሰኞች ጋር ሆኖ አፎቱን ተሸከመ፣ ቂርም ጋሻውን ገለጠ።” (ኢሳይያስ 22:​6) ጠላቶቻቸው በሚገባ የታጠቁ ናቸው። ኮሮጆዎቻቸውን ፍላጻ የሞሉ ቀስተኞች አሏቸው። ጦረኞቹ ጋሻዎቻቸውን ለውጊያው እያዘጋጁ ነው። ሠረገሎችና ለውጊያ የሰለጠኑ ፈረሶች አሉ። ሠራዊቱ ዛሬ የፋርስ ባሕረ ሰላጤ ከሚባለው አካባቢ በስተ ሰሜን ከምትገኘው ከኤላም እንዲሁም ከኤላም አጠገብ የምትገኝ ቦታ እንደሆነች ከምትገመተው ከቂር የተውጣጡ ወታደሮችን ያቀፈ ነው። እነዚህ አገሮች መጠቀሳቸው ወራሪዎቹ በጣም ሩቅ ከሆነ ቦታ መምጣታቸውን የሚጠቁም ነው። በተጨማሪም በሕዝቅያስ ዘመን ኢየሩሳሌምን ስጋት ላይ ከጣላት ሠራዊት መካከል የኤላማውያን ቀስተኞች ሊኖሩ እንደሚችሉ የሚጠቁም ነው።

ለመከላከል የተደረጉ ሙከራዎች

10. ለከተማዋ መጥፎ የሚሆነው ምን ከሆነ ነው?

10 ኢሳይያስ በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ ሲገልጽ እንዲህ ብሏል:- “መልካሞቹንም ሸለቆችሽን ሰረገሎች ሞሉባቸው፣ ፈረሰኞችም መቆሚያቸውን በበር ላይ አደረጉ። የይሁዳንም መጋረጃ ገለጠ።” (ኢሳይያስ 22:​7, 8ሀ) ከኢየሩሳሌም ውጭ ያለውን ሜዳ ሠረገሎችና ፈረሶች ያጨናነቁት ሲሆን በከተማዋ በሮች ላይ ጥቃት ለመሰንዘር ቦታ ቦታቸውን ይዘዋል። የሚገለጠው ‘የይሁዳ መጋረጃ’ ምንድን ነው? የከተማዋ በር ሳይሆን አይቀርም። የከተማዋ በር ተያዘ ማለት ከተማዋን የሚከላከሉት ሰዎች አበቃላቸው ማለት ይሆናል። * ይህ የመከላከያ መጋረጃ ሲገለጥ ከተማዋ ለወራሪዎቹ ክፍት ትሆናለች።

11, 12. የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ምን የመከላከል እርምጃ ወስደዋል?

11 አሁን ደግሞ ኢሳይያስ ሕዝቡ ራሳቸውን ከጠላት ለመከላከል ባደረጉት ጥረት ላይ ያተኩራል። መጀመሪያ የመጣላቸው ነገር በጦር መሣሪያ መጠቀም ነበር! “በዚያም ቀን በዱር ቤት የነበረውን የጦር ዕቃ ተመለከትህ፣ የዳዊትም ከተማ ፍራሾች እንደ በዙ አይታችኋል፣ የታችኛውንም ኩሬ ውኃ አከማችታችኋል።” (ኢሳይያስ 22:​8ለ, 9) በዱር ቤት በነበረው የጦር ግምጃ ቤት ውስጥ መሣሪያዎች ተከማችተው ነበር። ይህን የጦር ግምጃ ቤት የገነባው ሰሎሞን ነው። የተገነባው ከሊባኖስ በመጣ ዝግባ ስለነበር “የሊባኖስ የዱር ቤት” ሊባል በቅቷል። (1 ነገሥት 7:​2-5) ግድግዳዎቹ ተሰንጥቀው ክፍተት እንደፈጠሩ አስተውለዋል። ሕዝቡ ውኃ በማከማቸት ትልቅ ግምት የሚሰጠው አንድ የመከላከል እርምጃ ወስደዋል። የሕዝቡን ሕይወት ለማቆየት ውኃ አንገብጋቢ ነገር ነው። አንድ ከተማ ያለ ውኃ ልትቆም አትችልም። ያም ሆኖ ግን ይሖዋ ነፃ እንዲያወጣቸው እርሱን ስለመፈለጋቸው የተጠቀሰ አንድም ነገር እንደሌለ ልብ በል። ከዚህ ይልቅ የተመኩት ራሳቸው ባላቸው ነገር ነበር። እኛም ተመሳሳይ ስህተት እንዳንሠራ እንጠንቀቅ!​—⁠መዝሙር 127:​1

12 በከተማዋ ቅጥር ላይ ክፍተቶች ለመድፈን ምን ያደርጉ ይሆን? “የኢየሩሳሌምን ቤቶች ቈጠራችሁ፣ ቅጥሩንም ለማጥናት ቤቶችን አፈረሳችሁ።” (ኢሳይያስ 22:​10) ክፍተቶቹን ለመድፈን የሚያስችል ቁሳቁስ ለማግኘት የትኛው ቢፈርስ እንደሚሻል ለመወሰን ቤቶች ተገምግመዋል። ይህም የጠላት ኃይል ቅጥሩን ሙሉ በሙሉ እንዳይቆጣጠረው ለመከላከል የተደረገ ጥረት ነው።

እምነት የለሽ ሕዝብ

13. ሕዝቡ በቂ ውኃ እንዲኖር ለማድረግ የሞከረው እንዴት ነው? ይሁን እንጂ ማንን ረስተው ነበር?

13 “በአሮጌው ኩሬ ላለው ውኃ በሁለቱ ቅጥር መካከል መከማቻ ሠራችሁ፤ ይህን ያደረገውን ግን አልተመለከታችሁም፣ ቀድሞ የሠራውንም አላያችሁም።” (ኢሳይያስ 22:​11) እዚህ ላይና ኢሳይያስ 22 ቁጥር 9 ላይ የተጠቀሰው ውኃ ለማከማቸት የተደረገ ጥረት ንጉሥ ሕዝቅያስ ከተማዋን ከወራሪው የአሦር ኃይል ለመከላከል ሲል የወሰደውን እርምጃ ያስታውሰናል። (2 ዜና መዋዕል 32:​2-5) ይሁን እንጂ በዚህ የኢሳይያስ ትንቢት ውስጥ የተጠቀሱት የከተማዋ ነዋሪዎች ጨርሶ እምነት የለሽ ናቸው። የከተማዋን መከላከያ ሲያጠናክሩ ከሕዝቅያስ ፍጹም በተለየ መልኩ ስለ ፈጣሪያቸው አንዳች አላሰቡም።

14. ይሖዋ የማስጠንቀቂያ መልእክት ቢያስነግርም ሕዝቡ ምን ጥበብ የጎደለው ዝንባሌ አሳይቷል?

14 ኢሳይያስ እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “በዚያም ቀን የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ወደ ልቅሶና ወደ ዋይታ ራስን ወደ መንጨትና ማቅንም ወደ መልበስ ጠራ። እነሆም፣ ሐሤትና ደስታ በሬውንና በጉንም ማረድ ሥጋንም መብላት የወይን ጠጅንም መጠጣት ሆነዋል፤ እናንተ:- ነገ እንሞታለንና እንብላ እንጠጣ ብላችኋል።” (ኢሳይያስ 22:​12, 13) የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች በይሖዋ ላይ በፈጸሙት ዓመፅ ምንም አልተጸጸቱም። አላለቀሱም፣ ፀጉራቸውን አልነጩም ወይም ንስሐ መግባታቸውን ለማሳየት ማቅ አልለበሱም። እንደዚያ ቢያደርጉ ኖሮ ይሖዋ ከመጪው አሰቃቂ መከራ ሊጠብቃቸው ይችል ነበር። ከዚያ ይልቅ ራሳቸውን በተድላ አስጠምደው ነበር። ዛሬም በአምላክ የማያምኑ ብዙ ሰዎች የሚያሳዩት ዝንባሌ ተመሳሳይ ነው። የትንሣኤም ሆነ ወደፊት ገነት በምትሆነው ምድር ላይ የመኖር ምንም ዓይነት ተስፋ ስለሌላቸው “ነገ እንሞታለንና እንብላና እንጠጣ” በሚል ራስን የማዝናናት ስሜት ብቻ ተውጠዋል። (1 ቆሮንቶስ 15:​32) እንዴት ያለ አስተዋይነት የጎደለው አስተሳሰብ ነው! ዘላቂ ተስፋ ሊኖራቸው የሚችለው በይሖዋ ቢታመኑ ብቻ ነበር!​—⁠መዝሙር 4:​6-8፤ ምሳሌ 1:​33

15. (ሀ) ይሖዋ በኢየሩሳሌም ላይ ያስነገረው የፍርድ መልእክት ምንድን ነው? ይህንን ፍርዱን የሚያስፈጽመውስ ማን ነው? (ለ) ሕዝበ ክርስትና ከኢየሩሳሌም ጋር የሚመሳሰል ዕጣ የሚገጥማት ለምንድን ነው?

15 የተከበቡት የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ከእንግዲህ ደህንነት የሚባል ነገር አይኖራቸውም። ኢሳይያስ እንዲህ ይላል:- “የሠራዊት ጌታ ይሖዋ ይህን ነገር በጆሮዬ አሰማኝ:- እስክትሞቱ ድረስ ይህ በደል በእውነት አይሰረይላችሁም ይላል የሠራዊት ጌታ ይሖዋ።” (ኢሳይያስ 22:​14 NW) ሕዝቡ ልበ ደንዳና በመሆኑ ይቅርታ አያገኝም። ያለ ምንም ጥርጥር ከፊታቸው የሚጠብቃቸው ሞት ነው። ይህ ፍጹም እርግጠኛ የሆነ ነገር ነው። ይህን የተናገረው ሉዓላዊ ገዢ የሆነው የሠራዊት ጌታ ይሖዋ ነው። ኢሳይያስ በተናገራቸው ትንቢታዊ ቃላት ፍጻሜ መሠረት ከዳተኛ በሆነችው ኢየሩሳሌም ላይ ሁለት ጊዜ ጥፋት ደርሶባታል። መጀመሪያ በባቢሎናውያን ከዚያም በሮማውያን ሠራዊት ተደምስሳለች። በተመሳሳይ አምላክን እናመልካለን ብለው ቢናገሩም በሥራቸው የሚክዱት አባላት ያሏት ከዳተኛዋ ሕዝበ ክርስትናም ጥፋት ይጠብቃታል። (ቲቶ 1:​16) በአምላክ የጽድቅ መንገዶች የሚሳለቁትን ሌሎች የዓለም ሃይማኖቶች ጨምሮ የሕዝበ ክርስትና ኃጢአት “እስከ ሰማይ ድረስ ደርሷል።” እንደ ከሃዲዋ ኢየሩሳሌም ሁሉ የእነርሱም በደል ሊሠረይ የማይችል ከባድ በደል ነው።​—⁠ራእይ 18:​5, 8, 21

ራስ ወዳድ መጋቢ

16, 17. (ሀ) ቀጥሎ የይሖዋ ማስጠንቀቂያ የሚደርሰው ማን ነው? ለምንስ? (ለ) ሳምናስ ልቡ ትልቅ ነገር ይመኝ ስለነበር ምን ይደርስበታል?

16 አሁን ደግሞ ነቢዩ ትኩረቱን ከዳተኛ ከሆነው ሕዝብ በመመለስ ከዳተኛ ወደሆነ ግለሰብ ዘወር ይላል። ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል:- በቤቱ ውስጥ ወደ ተሾመው ወደዚህ አዛዥ ወደ ሳምናስ ሂድ እንዲህም በለው:- መቃብር በዚህ ያስወቀርህ፣ ከፍ ባለው ስፍራ መቃብር ያሠራህ፣ በድንጋይም ውስጥ ለራስህ መኖርያ ያሳነጽህ በዚህ ምን አለህ? በዚህስ በአንተ ዘንድ ማን አለ?”​—⁠ኢሳይያስ 22:​15, 16

17 ሳምናስ ‘በቤቱ ውስጥ’ ምናልባትም በንጉሥ ሕዝቅ​ያስ ቤት ሳይሆን አይቀርም ‘መጋቢ ሆኖ ተሾሟል።’ ይህ ማለት ከንጉሡ ቀጥሎ ከፍተኛ ሥልጣን ያለው ሰው ነበር ማለት ነው። ከእርሱ ብዙ ይጠበቃል። (1 ቆሮንቶስ 4:​2) ይሁንና በአንደኛ ደረጃ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው የብሔሩ ጉዳይ ሆኖ ሳለ ሳምናስ የሚያሳድደው የራሱን ክብር ነበር። ከፍ ባለ አለት ላይ ከንጉሥ ባልተናነሰ ክብር የተቀናጣ መቃብር እያሠራ ነው። ይሖዋ ይህንን ነገር በማስተዋል ኢሳይያስ በመንፈስ ተነሳስቶ ይህን ታማኝ ያልሆነ መጋቢ እንዲያስጠነቅቀው አድርጓል:- “እነሆ፣ እግዚአብሔር በኃይል ወርውሮ ይጥልሃል፣ አጠንክሮም ይጨብጥሃል። ጠቅልሎም ያንከባልልሃል ወደ ሰፊይቱም ምድር እንደ ኳስ ይጥልሃል፤ አንተ የጌታህ ቤት እፍረት! በዚያ ትሞታለህ በዚያም የክብርህ ሰረገላዎች ይሆናሉ። ከአዛዥነት ሥራህ አሳድድሃለሁ፣ ከሹመትህም ትሻራለህ።” (ኢሳይያስ 22:​17-19) ሳምናስ ባንጸባረቀው ራስ ወዳድነት ምክንያት በኢየሩሳሌም ውስጥ ተራ መቃብር እንኳ አይኖረውም። ይልቁንም እንደ ኳስ ተንከባልሎ ሩቅ በሚገኝ አገር ይሞታል። ይህ ነገር በአምላክ ሕዝብ መካከል ሥልጣን ላላቸው ሁሉ ትልቅ ማስጠንቀቂያ ይሆናል። ሥልጣንን አላግባብ መጠቀም የነበረውን የሥልጣን ደረጃ ወደ ማጣት ምናልባትም ጨርሶ ከሥልጣን ወደ መባረር ሊያደርስ ይችላል።

18. ሳምናስን የሚተካው ማን ነው? ይህ ሰው የሳምናስን የመጋቢነት መጎናጸፊያና የዳዊትን ቤት መክፈቻ ይቀበላል ማለት ምን ማለት ይሆናል?

18 ይሁንና ሳምናስ ከሥልጣኑ የሚወገደው እንዴት ነው? ይሖዋ በኢሳይያስ አማካኝነት እንዲህ ሲል ሁኔታውን ግልጽ አድርጓል:- “በዚያም ቀን ባሪያዬን የኬልቅያስን ልጅ ኤልያቄምን እጠራለሁ፣ መጐናጸፊያህንም አለብሰዋለሁ፣ በመታጠቂያህም አስታጥቀዋለሁ፣ ሹመትህንም በእጁ አሳልፌ እሰጠዋለሁ፤ በኢየሩሳሌምም ለሚኖሩ ለይሁዳም ቤት አባት ይሆናል። የዳዊትንም ቤት መክፈቻ በጫንቃው ላይ አኖራለሁ፤ እርሱም ይከፍታል የሚዘጋም የለም፤ እርሱም ይዘጋል የሚከፍትም የለም።” (ኢሳይያስ 22:​20-22) በሳምናስ ፋንታ ኤልያቄም የመጋቢነት መጎናጸፊያና የዳዊት ቤት መክፈቻ ይሰጠዋል። መጽሐፍ ቅዱስ “መክፈቻ” የሚለውን ቃል ሥልጣንን፣ መስተዳድርን ወይም ኃይልን ለማመልከት ይጠቀምበታል። (ከማቴዎስ 16:​19 ጋር አወዳድር።) በጥንት ዘመን መክፈቻ የተሰጠው አንድ የንጉሥ አማካሪ የቤተ መንግሥቱን የተለያዩ ክፍሎች ሊቆጣጠርና የንጉሡን አገልጋዮች ሳይቀር የመምረጥ ሥልጣን ሊኖረው ይችላል። (ከ⁠ራእይ 3:​7, 8 ጋር አወዳድር።) በመሆኑም የመጋቢነት ኃላፊነት ትልቅ ቦታ ሲሆን ማንም ይሁን ማን በዚህ ኃላፊነት ቦታ የሚያገለግል ከሆነ ብዙ ይጠበቅበታል። (ሉቃስ 12:​48) ሳምናስ ለማገልገል ብቃቱ ያለው ሰው ሊሆን ይችላል። ነገር ግን የታመነ ሆኖ ባለመገኘቱ ምክንያት ይሖዋ በሌላ ሰው ይተካዋል።

ሁለት ምሳሌያዊ ችንካሮች

19, 20. (ሀ) ኤልያቄም ለሕዝቡ በረከት የሆነው እንዴት ነው? (ለ) በሳምናስ መታመናቸውን የሚቀጥሉ ሰዎች ምን ያገኛሉ?

19 በመጨረሻም ይሖዋ ምሳሌያዊ አገላለጽ በመጠቀም ሥልጣኑ ከሳምናስ ወደ ኤልያቄም ማሸጋገሩን እንዲህ በማለት ይገልጻል:- “በታመነም ስፍራ [ኤልያቄምን] እንደ ችንካር እተክለዋለሁ፣ ለአባቱም ቤት የክብር ዙፋን ይሆናል። የአባቱንም ቤት ክብር ሁሉ ልጆቹንም የልጅ ልጆቹንም፣ ከጽዋ ዕቃ ጀምሮ እስከ ማድጋ ዕቃ ድረስ፣ ታናናሹን ዕቃ ሁሉ ይሰቅሉበታል። በዚያ ቀን፣ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፣ በታመነው ስፍራ የተተከለው ችንካር [ሳምናስ] ይወልቃል፤ ተሰብሮም ይወድቃል፣ በእርሱም ላይ የተሰቀለው ሸክም ይጠፋል፤ እግዚአብሔር ተናግሮአልና።”​—⁠ኢሳይያስ 22:​23-25

20 በእነዚህ ቁጥሮች ላይ የተጠቀሰው የመጀመሪያው ችንካር ኤልያቄም ነው። ለአባቱ የኬልቅያስ ቤት “የክብር ዙፋን” ይሆናል። ሳምናስ እንዳደረገው የአባቱን ቤት ክብር አያዋርድም ወይም አያሰድብም። ኤልያቄም የቤቱ ዕቃ ሁሉ የሚሰቀልበት አስተማማኝ መንጠልጠያ ማለትም የንጉሡ አገልጋዮች ሁሉ የሚታመኑበት ሰው ይሆናል። (2 ጢሞቴዎስ 2:​20, 21) ከዚህ በተቃራኒው ደግሞ ሁለተኛው ችንካር የሚያመለክተው ሳምናስን ነው። አስተማማኝ መስሎ ቢታይም ከቦታው ይወገዳል። እርሱን ተስፋ የሚያደርጉ ሁሉ ይወድቃሉ።

21. በዘመናችን እንደ ሳምናስ በሌላ የተተካው ማን ነው? ለምንስ? ደግሞስ የተተካው በማን ነው?

21 አምላክን እናመልካለን ከሚሉት ሰዎች መካከል የአገልግሎት መብት የሚያገኙ ሁሉ ይህን መብታቸውን ሌሎችን ለማገልገልና ይሖዋን ለማስከበር ሊጠቀሙበት እንደሚገባ ሳምናስ የገጠመው ነገር ማሳሰቢያ ይሆነናል። ራሳቸውን ለማበ​ልጸግ ወይም ዝናን ለማትረፍ ሊጠ​ቀሙበት አይገባም። ለምሳሌ ያህል ሕዝበ ክርስትና የኢየሱስ ክርስቶስ ምድራዊ ወኪል ሆና የተሾመች መጋቢ እንደሆነች አድርጋ ለረጅም ዘመን ራሷን ስታስተዋውቅ ኖራለች። ይሁን እንጂ ሳምናስ የራሱን ክብር ብቻ በማሳደድ የአባቱን ቤት እንዳዋረደ ሁሉ የሕዝበ ክርስትና መሪዎችም ለራሳቸው ሃብትና ሥልጣን በማሳደድ ለፈጣሪ ኃፍረት ሆነዋል። በመሆኑም በ1918 ፍርድ ‘በአምላክ ቤት’ ሲጀምር ይሖዋ ሕዝበ ክርስትናን አስወግዷታል። በዚህ ጊዜ ሌላ መጋቢ ይኸውም “ታማኝና ልባም መጋቢ” ብቅ ብሎ በኢየሱስ ምድራዊ ቤተሰብ ላይ ተሾሟል። (1 ጴጥሮስ 4:​17፤ ሉቃስ 12:​42-44) ይህ ቡድን የዳዊትን ቤት ንጉሣዊ “መክፈቻ” የመሸከም ብቃት ያለው ሆኖ ተገኝቷል። የተለያየ ኃላፊነት ያላቸው ቅቡዓን ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ምግብ ለማግኘት የሚተማመኑበት ወይም በሌላ አባባል እንደተለያየ ዓይነት ዕቃ የሚንጠለጠሉበት አስተማማኝ ድጋፍ ሆኖላቸዋል። ‘ሌሎች በጎችም’ እንዲሁ ‘በጥንቷ ኢየሩሳሌም ደጆች ውስጥ እንደነበሩት መጻተኞች’ የሚደገፉት የኤልያቄም ዘመናዊ አምሳያ በሆነው በዚህ “ችንካር” ነው።​—⁠ዮሐንስ 10:​16፤ ዘዳግም 5:​14

22. (ሀ) ሳምናስ በሌላ መጋቢ መተካቱ ወቅታዊ የነበረው ለምንድን ነው? (ለ) በዘመናችን ‘ታማኝና ልባም መጋቢ’ መሾሙ ወቅታዊ የሆነው ለምንድን ነው?

22 ኤልያቄም ሳምናስን የተካው ሰናክሬምና ጭፍሮቹ ኢየሩሳሌምን ስጋት ላይ በጣሉበት ጊዜ ነበር። በተመሳሳይም ‘ታማኝና ልባም የሆነው መጋቢ’ የተሾመው ሰይጣንና የእርሱ ኃይሎች ‘በአምላክ እስራኤል’ እንዲሁም ከእነርሱ ጋር በሚተባበሩት ሌሎች በጎች ላይ የመጨረሻ ጥቃት ለመሰንዘር ሲንቀሳቀሱ ወደ መደምደሚያው በሚመጣው የፍጻሜ ዘመን ውስጥ ነው። (ገላትያ 6:​16) በሕዝቅያስ ዘመን እንደሆነው ሁሉ ይህ ጥቃት የጽድቅ ጠላቶች የሆኑት ወገኖች ሲደመሰሱ ያበቃል። የታመኑት የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች አሦር በይሁዳ ላይ ካካሄደችው ወረራ ሕይወታቸውን እንዳተረፉ ሁሉ ‘በታመነ ሥፍራ በተተከለው ችንካር’ ማለትም በታመነው መጋቢ ላይ የሚደገፉ ሁሉ ሕይወታቸውን ያድናሉ። እንግዲያው ተቀባይነት ባጣችው “ችንካር” በሕዝበ ክርስትና ላይ አለመታመን ምንኛ ጥበብ ነው!

23. ሳምናስ በመጨረሻ ምን ሆኗል? ከዚህስ ምን ልንማር እንችላለን?

23 ታዲያ ሳምናስስ ምን ይጠብቀዋል? እርሱን በተመለከተ በ⁠ኢሳይያስ 22:​18 ላይ ተመዝግቦ የሚገኘው ትንቢት ፍጻሜውን ያገኘው እንዴት እንደሆነ የሚገልጽ ምንም የተመዘገበ ነገር የለም። ራሱን ከፍ ከፍ አድርጎ በኋላ መዋረዱ ከሕዝበ ክርስትና ጋር ያመሳስለዋል። ይሁንና ከተሰጠው ተግሳጽ ትምህርት አግኝቶ ሊሆን ይችላል። በዚህ ረገድ ግን ከሕዝበ ክርስትና ጋር ፈጽሞ አይመሳሰልም። አሦራዊው ራፋስቂስ ኢየሩሳሌም እጅዋን እንድትሰጥ በጠየቀ ጊዜ ከእርሱ ጋር ለመነጋገር የሄደውን ልዑካን የመራው አዲሱ የሕዝቅያስ መጋቢ ኤልያቄም ነበር። ይሁን እንጂ ሳምናስ የንጉሡ ጸሐፊ ሆኖ አብሮት ሄዷል። ከሁኔታው ለመረዳት እንደሚቻለው ሳምናስ በንጉሡ ቤት ማገልገሉን ቀጥሎ ነበር። (ኢሳይያስ 36:​2, 22) በአምላክ ድርጅት ውስጥ የነበራቸውን የኃላፊነት ቦታ ለሚያጡ ሰዎች ይህ እንዴት ያለ ግሩም ትምህርት ነው! ከመመረርና ቅር ከመሰኘት ይልቅ ይሖዋ በፈቀደው በማንኛውም ቦታ እርሱን ማገልገላቸውን መቀጠላቸው ጥበብ ይሆናል። (ዕብራውያን 12:​6) እንዲህ በማድረግ ሕዝበ ክርስትና ከሚጠብቃት መዓት ይድናሉ። ለዘላለምም የአምላክን ሞገስና በረከት ያገኛሉ።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.6 በ66 እዘአ ኢየሩሳሌምን ከብቦ የነበረው የሮማ ሠራዊት ወደኋላ ሲያፈገፍግ ብዙ አይሁዳውያን በደስታ ፈንጥዘው ነበር።

^ አን.6 የመጀመሪያው መቶ ዘመን ታሪክ ጸሐፊ የነበረው ጆሴፈስ እንዳለው ከሆነ በ70 እዘአ በኢየሩሳሌም ከነበረው እጅግ ጽኑ ረሃብ የተነሣ ሰዎች ቆዳ፣ እርጥብ ሣር እና ድርቆሽ በልተዋል። አንዲት እናትም የገዛ ልጅዋን ጠብሳ እንደበላች ሪፖርት ተደርጓል።

^ አን.10 ወይም ደግሞ ‘የይሁዳ መጋረጃ’ የሚለው መግለጫ የሚያመለክተው ከተማዋን ለመከላከል የሚያስችልን ሌላ ዝግጅት ምናልባትም ጦር መሣሪያ የሚከማችበትንና ወታደሮች የሚጠብቁበት ምሽግ ሊሆን ይችላል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 231 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሴዴቅያስን ሲሸሽ ይዘው ዓይኑን አጥፍተውታል

[በገጽ 232 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በኢየሩሳሌም እንዳሉ ዙሪያቸውን የተከበቡት አይሁዳውያን ተስፋቸው ጨልሞ ነበር

[በገጽ 239 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሕዝቅያስ ኤልያቄምን ‘በአስተማማኝ ስፍራ እንዳለ ችንካር’ አድርጎታል

[በገጽ 241 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ብዙ የሕዝበ ክርስትና መሪዎች እንደ ሳምናስ ሃብት በማካበት ለፈጣሪ ኃፍረት ሆነዋል

[በገጽ 242 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በዘመናችን በኢየሱስ ቤተሰቦች ላይ አንድ ታማኝ መጋቢ ቡድን ተሾሟል