በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከዳተኛ ለሆነው የወይን ቦታ ወዮ!

ከዳተኛ ለሆነው የወይን ቦታ ወዮ!

ምዕራፍ ሰባት

ከዳተኛ ለሆነው የወይን ቦታ ወዮ!

ኢሳይያስ 5:​1-30

1, 2. “ወዳጄ” የተከለው ምንድን ነው? ይሁን እንጂ ይህ እንደተጠበቀው ሆኖ ያልተገኘው እንዴት ነው?

“እጅግ ድንቅ ከሆነው የቋንቋው ውበትና መልእክቱን በማስተላለፍ ረገድ ከተንጸባረቀበት የላቀ ችሎታ አንጻር አቻ የማይገኝለት ምሳሌ ነው።” ይህ አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ተንታኝ የ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 5⁠ን የመክፈቻ ቁጥሮች በተመለከተ የሰነዘሩት አስተያየት ነው። ኢሳይያስ የተናገራቸው ቃላት እንደ ሥነ ጥበብ ሥራ ብቻ የሚታዩ ሳይሆኑ አምላክ ለሕዝቡ የሚያደርገውን ፍቅራዊ እንክብካቤ ልብ በሚነካ መንገድ የሚገልጹ ቃላት ናቸው። በሌላ በኩል ደግሞ እነዚሁ ቃላት አምላክ የማይደሰትበትን ነገር በተመለከተ ማስጠንቀቂያ ይሰጡናል።

2 የኢሳይያስ ምሳሌ እንዲህ በማለት ይጀምራል:- “አሁን ስለ ወዳጄና ስለ ወይን ቦታው ለወዳጄ ቅኔ እቀኛለሁ። ለወዳጄ በፍሬያማው ኮረብታ ላይ የወይን ቦታ ነበረው። በዙሪያው ቈፈረ፣ ድንጋዮችንም ለቅሞ አወጣ፣ ምርጥ የሆነውንም አረግ [“ቀይ ወይን፣” NW] ተከለበት፣ በመካከሉም ግንብ ሠራ፣ ደግሞም የመጥመቂያ ጉድጓድ ማሰበት፤ ወይንንም ያፈራ ዘንድ ተማመነ፣ ዳሩ ግን ሆምጣጣ ፍሬ አፈራ።”​—⁠ኢሳይያስ 5:1, 2ከ⁠ማርቆስ 12:​1 ጋር አወዳድር።

ለወይን ቦታው የተደረገ እንክብካቤ

3, 4. የወይን ቦታው ምን ፍቅራዊ እንክብካቤ ተደርጎለታል?

3 ኢሳይያስ ይህን ምሳሌ ቃል በቃል የተቀኘው ያዳምጡት ለነበሩት ሰዎች ሆነም አልሆነ ትኩረታቸውን ስቦ እንደነበር ምንም አያጠራጥርም። አብዛኛዎቹ ከወይን እርሻ ጋር ትውውቅ ስለሚኖራቸው ኢሳይያስ የሰጠው መግለጫ ሕያውና ተጨባጭ ነበር። ዛሬ ያሉት የወይን አትክልተኞች እንደሚያደርጉት ሁሉ የወይን ቦታው ባለቤት የሚተክለው የወይኑን ዘር ሳይሆን “ምርጥ የሆነውን” ወይም ጥራት ያለውን “የቀይ ወይን” ቅጥፍ ወይም ግርንጫፍ ነው። ለወይን ተክል የሚስማማ ዓይነት ቦታ በመሆኑ የወይን ቦታውን “በፍሬያማው ኮረብታ ላይ” ማድረጉ ተገቢ ነው።

4 አንድ የወይን ቦታ ፍሬ እንዲሰጥ ማድረግ ጥረት ይጠይቃል። ኢሳይያስ የወይኑ ቦታ ባለቤት ‘መሬቱን መቆፈሩንና ድንጋዮችንም ለቅሞ ማውጣቱን’ ተናግሯል። ይህ አሰልቺና አድካሚ ሥራ ነው! ‘ግንብ ለመሥራት’ የተጠቀመባቸው ትላልቆቹን ድንጋዮች ሳይሆን አይቀርም። በጥንት ዘመን እንዲህ ዓይነት ግንቦች ማሳውን ከሌቦችና ከእንስሳት ለሚጠብቁት ሰዎች እንደ ማማ ያገለግሉ ነበር። * ከዚህም ሌላ የወይን ቦታውን ለመከለል የድንጋይ ቅጥር ሠርቷል። (ኢሳይያስ 5:​5) አብዛኛውን ጊዜ እንዲህ የሚደረገው በጣም አስፈላጊ የሆነው የላይኛው አፈር ተሸርሽሮ እንዳይወሰድ ለመከላከል ነበር።

5. የወይን ቦታው ጌታ ምን ነገር ለማግኘት ጠብቋል? ይሁን እንጂ ያገኘው ምንድን ነው?

5 የወይኑ ቦታ ባለቤት ለዚህ የወይን ቦታ ይህን ያህል በመድከሙ ፍሬ ያፈራል ብሎ መጠበቁ ተገቢ ነው። ይህንንም በማሰብ የመጥመቂያ ጉድጓድ ምሷል። ይሁን እንጂ ፍሬ ለመሰብሰብ የነበረው ተስፋ እውን ሆኖለታል? አልሆነለትም። እንዲያውም የወይን ቦታው ያፈራው ሆምጣጣ ፍሬ ነበር።

የወይኑ ቦታና ባለቤቱ

6, 7. (ሀ) የወይን ቦታው ጌታ ማን ነው? የወይን ቦታውስ? (ለ) ጌታው ምን ፍርድ እንዲሰጠው ጠይቋል?

6 የወይኑ ቦታ ባለቤት ማን ነው? የወይኑ ቦታስ ምንድን ነው? የወይኑ ቦታ ባለቤት ራሱ የሚከተለውን በማለት ለእነዚህ ጥያቄዎች መልሱን ይሰጣል:- “አሁንም እናንተ በኢየሩሳሌም የምትኖሩ የይሁዳ ሰዎችም ሆይ፣ በእኔና በወይኑ ቦታዬ መካከል እስኪ ፍረዱ። ለወይኔ ያላደረግሁለት፣ ከዚህ ሌላ አደርግለት ዘንድ የሚገባኝ ምንድር ነው? ወይንን ያፈራል ብዬ ስተማመን ስለ ምን ሆምጣጣ ፍሬ አፈራ? አሁንም በወይኔ ላይ የማደርገውን እነግራችኋለሁ፤ አጥሩን እነቅላለሁ፣ ለማሰማርያም ይሆናል፤ ቅጥሩንም አፈርሳለሁ፣ ለመራገጫም ይሆናል።”​—⁠ኢሳይያስ 5:​3-5

7 አዎን፣ የወይኑ ቦታ ባለቤት ይሖዋ ሲሆን በእርሱና እንደተጠበቀው ሆኖ ባልተገኘው የወይን ቦታው መካከል እንዲፈርዱት በመጠየቅ በችሎት አዳራሽ የተገኘ ያህል ነበር። ታዲያ የወይን ቦታው ምንድን ነው? የወይኑ ቦታ ባለቤት እንዲህ በማለት ያብራራል:- “የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር ወይን ቦታ እርሱ የእስራኤል ቤት ነው፣ የደስታውም አትክልት የይሁዳ ሰዎች ናቸው።”​—⁠ኢሳይያስ 5:​7ሀ

8. ኢሳይያስ ይሖዋን “ወዳጄ” ብሎ መጥራቱ ምን ያመለክታል?

8 ኢሳይያስ የወይኑ ቦታ ባለቤት የሆነውን ይሖዋን “ወዳጄ” በማለት ጠርቶታል። (ኢሳይያስ 5:​1) ኢሳይያስ ቅርበትን በሚያሳይ እንዲህ ዓይነት መግለጫ አምላክን ሊጠራው የቻለው ከእርሱ ጋር የጠበቀ ዝምድና ስለነበረው ብቻ ነው። (ከ⁠ኢዮብ 29:​4 NWመዝሙር 25:​14 የ1980 ትርጉም ጋር አወዳድር።) ይሁን እንጂ ነቢዩ ለአምላክ የነበረው ፍቅር፣ አምላክ ‘ለወይን ቦታው’ ማለትም ራሱ ‘ለተከለው’ ብሔር ካሳየው ፍቅር ጋር ሲወዳደር ከቁጥር አይገባም።​—⁠ከ⁠ዘጸአት 15:​17፤ መዝሙር 80:​8, 9 ጋር አወዳድር።

9. ይሖዋ ብሔሩን ከፍ ያለ ዋጋ እንዳለው የወይን ቦታ አድርጎ የያዘው እንዴት ነው?

9 ይሖዋ ሕዝቡን በከነዓን ምድር ‘በመትከል’ ሕጉንና መመሪያውን ሰጥቷቸዋል። ይህም በሌሎች ብሔራት እንዳይበከሉ እንደ አጥር ሆኖ አገልግሏል። (ዘጸአት 19:​5, 6፤ መዝሙር 147:​19, 20፤ ኤፌሶን 2:​14) ከዚህም በላይ ይሖዋ የሚያስተምሯቸውንና መመሪያ የሚሰጡአቸውን መሳፍንት፣ ካህናትና ነቢያት ሰጥቷቸዋል። (2 ነገሥት 17:​13፤ ሚልክያስ 2:​7፤ ሥራ 13:​20) እስራኤላውያን ወታደራዊ ዛቻ በደረሰባቸው ጊዜ የሚታደጓቸውን ሰዎች አስነስቶላቸዋል። (ዕብራውያን 11:​32, 33) ይሖዋ “ለወይኔ ያላደረግሁለት፣ ከዚህ ሌላ አደርግለት ዘንድ የሚገባኝ ምንድር ነው?” ብሎ መጠየቁ ያለ ምክንያት አልነበረም።

ዛሬ ያለውን የአምላክ የወይን ቦታ ለይቶ ማወቅ

10. ኢየሱስ የወይን ቦታን በተመለከተ ምን ምሳሌ ተናግሯል?

10 ኢየሱስ ነፍሰ ገዳይ ስለሆኑት የወይን ገበሬዎች ምሳሌ ሲናገር እነዚህን የኢሳይያስ ቃላት በአእምሮው ይዞ ሊሆን ይችላል:- “የወይን አትክልት የተከለ ባለቤት ሰው ነበረ፤ ቅጥርም ቀጠረለት፣ መጥመቂያም ማሰለት፣ ግንብም ሠራና ለገበሬዎች አከራይቶ ወደ ሌላ አገር ሄደ።” የሚያሳዝነው ገበሬዎቹ ልጁን ሳይቀር በመግደል የወይን ቦታውን ባለቤት ክደውታል። ኢየሱስ ይህ ምሳሌ የሚያመለክተው ሥጋዊ እስራኤላውያንን ብቻ እንዳልሆነ ሲገልጽ እንዲህ ብሏል:- “የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተ [ከሥጋዊ እስራኤላውያን] ትወሰዳለች ፍሬዋንም ለሚያደርግ ሕዝብ ትሰጣለች።”​—⁠ማቴዎስ 21:​33-41, 43

11. በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበረው መንፈሳዊ የወይን ቦታ ምንድን ነው? ይሁን እንጂ ከሐዋርያት ሞት በኋላ ምን ሆኗል?

11 ይህ አዲስ “ሕዝብ” ‘የአምላክ እስራኤል’ ማለትም በድምሩ 144,000 የሚሆኑትን ቅቡዓን ክርስቲያኖች ያቀፈው መንፈሳዊ ሕዝብ ነው። (ገላትያ 6:​16 NW1 ጴጥሮስ 2:​9, 10፤ ራእይ 7:​3, 4) ኢየሱስ እነዚህን ደቀ መዛሙርት ‘በእውነተኛ የወይን ግንድ’ ላይ ከበቀሉ “ቅርንጫፎች” ጋር አወዳድሯቸዋል። የወይን ግንዱ እርሱ ራሱ ነው። ቅርንጫፍ እንደመሆናቸው መጠን ደግሞ ፍሬ ማፍራት ይጠበቅባቸዋል። (ዮሐንስ 15:​1-5) የክርስቶስን ዓይነት ባሕርይ ማንጸባረቅና ‘የመንግሥቱን ምሥራች’ በመስበኩ ሥራ መካፈል ይኖርባቸዋል። (ማቴዎስ 24:​14፤ ገላትያ 5:​22, 23) ይሁን እንጂ አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ከሞቱ በኋላ ‘የእውነተኛው የወይን ግንድ’ ቅርንጫፎች ነን ይሉ ከነበሩት መካከል ብዙዎቹ መልካም ፍሬ ሳይሆን ሆምጣጣ ፍሬ በማፍራት ሐሰተኞች መሆናቸውን አረጋግጠዋል።​—⁠ማቴዎስ 13:​24-30, 38, 39

12. የኢሳይያስ ቃላት ሕዝበ ክርስትናን የሚያወግዙት እንዴት ነው? ለእውነተኛ ክርስቲያኖችስ ምን ትምህርት ይዘዋል?

12 በመሆኑም ኢሳይያስ በይሁዳ ላይ የሰነዘረው ውግዘት ዛሬ በሕዝበ ክርስትናም ላይ ይሠራል። ያሳለፈችውን ታሪክ መለስ ብለን ስንመለከተው ያደረገቻቸው ውጊያዎች፣ የመስቀል ጦርነቶችና ኢንኩዊዝሽኖች ያፈራችው ፍሬ ምን ያህል ጎምዛዛ እንደሆነ የሚያረጋግጡ ናቸው! የሆነ ሆኖ የቅቡዓን ክርስቲያኖችና የተባባሪዎቻቸው ‘እጅግ ብዙ ሰዎች’ እውነተኛ የወይን ቦታ የኢሳይያስን ቃላት መጠበቅ ይኖርባቸዋል። (ራእይ 7:​9) የወይኑን ጌታ ደስ ማሰኘት የሚፈልጉ ከሆነ በግለሰብ ደረጃም ይሁን በቡድን ደረጃ እርሱን ደስ የሚያሰኙትን ፍሬዎች ማፍራት ይኖርባቸዋል።

“ሆምጣጣ ፍሬ”

13. ይሖዋ የወይን ቦታው መጥፎ ፍሬ ስላፈራ ምን ያደርገዋል?

13 ይሖዋ የወይን ቦታውን ለመንከባከብና ለማልማት ይህን ያህል ጥረት በማድረጉ ‘የተወደደ የወይን ቦታ’ እንዲሆን መጠበቁ ተገቢ ነው። (ኢሳይያስ 27:​2) ይሁን እንጂ ጥቅም ላይ የሚውል ፍሬ ከመስጠት ይልቅ “ሆምጣጣ” ማለትም ቃል በቃል ከተወሰደ “የሚሸትት” ወይም “የሚገማ (የበሰበሰ) ፍሬ” አፍርቷል። (ኢሳይያስ 5:​2የአዲሲቱ ዓለም ትርጉም የግርጌ ማስታወሻ፤ ኤርምያስ 2:​21) በመሆኑም ይሖዋ ብሔሩን ለመጠበቅ ያደረገውን “አጥር” እንደሚያፈርስ ተናግሯል። ብሔሩ ‘እንደ ፈረሰ ያህል ሆኖ’ የተተወና ደረቅ መሬት ይሆናል። (ኢሳይያስ 5:​6 NWን አንብብ።) ሙሴ የአምላክን ሕግጋት ሳይጠብቁ ከቀሩ እንደነዚህ ያሉ ሁኔታዎች እንደሚደርሱባቸው አስጠንቅቆ ነበር።​—⁠ዘዳግም 11:​17፤ 28:​63, 64፤ 29:​22, 23

14. ይሖዋ ከብሔሩ የሚጠብቀው ፍሬ ምን ዓይነት ነው? በዚህ ፋንታ ግን ብሔሩ ያፈራው ፍሬ ምን ዓይነት ነው?

14 አምላክ ብሔሩ መልካም ፍሬ እንዲያፈራ ይጠብቅበታል። በኢሳይያስ ዘመን የኖረው ሚክያስ እንዲህ ሲል ተናግሯል:- “እግዚአብሔርም ከአንተ ዘንድ የሚሻው ምንድር ነው? ፍርድን ታደርግ ዘንድ፣ ምሕረትንም ትወድድ ዘንድ፣ ከአምላክህም ጋር በትሕትና ትሄድ ዘንድ አይደለምን?” (ሚክያስ 6:​8፤ ዘካርያስ 7:​9) ይሁን እንጂ ብሔሩ የይሖዋን ማሳሰቢያ ሳይሰማ ቀረ። [አምላክ] ፍርድን ተስፋ ያደርግ ነበር፣ እነሆም፣ [“ሕግ ማፍረስ፣” NW] ደም ማፍሰስ ሆነ፤ ጽድቅንም ይተማመን ነበር፣ እነሆም፣ ጩኸት ሆነ።” (ኢሳይያስ 5:7ለ) ሙሴ ከሃዲ የሆነው ብሔር “ከሰዶም ወይን” መርዛም የሆነ የወይን ፍሬ እንደሚያፈራ ተንብዮ ነበር። (ዘዳግም 32:​32) ከዚህ አንጻር ከአምላክ ሕግ የራቁት ግብረ ሰዶምን ጨምሮ የፆታ ብልግና በመፈጸምም እንደነበር ግልጽ ነው። (ዘሌዋውያን 18:​22) “ሕግ ማፍረስ” የሚለው መግለጫ “ደም ማፍሰስ” ተብሎም ሊተረጎም ይችላል። እንዲህ ያለው ጭካኔ የተሞላበት ድርጊት የተጨቆኑት ሰዎች ‘እንዲጮኹ’ ቢያደርግ ምንም አያስገርምም። ይህ ጩኸት ደግሞ ወደ ወይኑ ጌታ ጆሮ ደርሷል።​—⁠ከ⁠ኢዮብ 34:​28 ጋር አወዳድር።

15, 16. እውነተኛ ክርስቲያኖች እስራኤል ያፈራችውን ዓይነት መጥፎ ፍሬ ከማፍራት ሊርቁ የሚችሉት እንዴት ነው?

15 ይሖዋ ‘ጽድቅንና ፍርድን የሚወድድ’ አምላክ ነው። (መዝሙር 33:​5) አይሁዳውያንን እንዲህ ሲል አዝዟቸዋል:- “በፍርድ ዓመፃ አታድርጉ፤ ለድሀ አታድላ፣ ባለ ጠጋውንም አታክብር፤ ነገር ግን ለባልንጀራህ በእውነት ፍረድ።” (ዘሌዋውያን 19:​15) እንግዲያው ለሰዎች ያለንን ግምት እንደ ዘር፣ ዕድሜ፣ ሀብት ወይም ድህነት ያሉት ነገሮች እንዲያዛቡብን ባለመፍቀድ ከሌሎች ጋር ባለን ግንኙነት ከአድልዎ ልንርቅ ይገባል። (ያዕቆብ 2:​1-4) በተለይ በበላይ ተመልካችነት የሚያገለግሉ ሁሉ ‘ወደ አንድ ወገን ያዘነበለ አመለካከት እንዳያድርባቸው’ መጠንቀቃቸውና ፍርድ ከመስጠታቸው በፊት የጉዳዩን ግራና ቀኝ ለመመልከት መጣራቸው በጣም አስፈላጊ ነው።​—⁠1 ጢሞቴዎስ 5:​21፤ ምሳሌ 18:​13

16 ከዚህም ሌላ በዚህ ዓመፀኛ በሆነ ዓለም ውስጥ የሚኖሩ ክርስቲያኖች በቀላሉ ለአምላክ የአቋም ደረጃዎች አሉታዊ አመለካከት ወይም የዓመፅ ዝንባሌ ሊያዳብሩ ይችላሉ። ይሁን እንጂ እውነተኛ ክርስቲያኖች የአምላክን ሕግጋት ‘ለመታዘዝ ዝግጁ’ መሆን ይኖርባቸዋል። (ያዕቆብ 3:​17 NW) ‘ክፉ በሆነው በአሁኑ ዓለም’ ውስጥ የሚፈጸመው የፆታ ብልግናና ዓመፅ ቢኖርም ‘እንደ ጥበበኞች እንጂ ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንዴት እንደሚመላለሱ በጥንቃቄ መጠበቅ’ ይኖርባቸዋል። (ገላትያ 1:​4፤ ኤፌሶን 5:​15) ልቅ ከሆነው የፆታ አመለካከት ለመራቅ ይፈልጋሉ። እንዲሁም አለመግባባቶች ሲነሱ ‘ያለ ንዴት፣ ቁጣ፣ ጩኸትና መሳደብ’ ችግራቸውን መፍታት ይኖርባቸዋል። (ኤፌሶን 4:​31) እውነተኛ ክርስቲያኖች ጽድቅን በመኮትኮት ለአምላክ ክብር ከማምጣታቸውም ሌላ የእርሱን ሞገስ ያገኛሉ።

ስግብግብነት የሚያስከፍለው ዋጋ

17. በኢሳይያስ የመጀመሪያ ወዮታ የተወገዘው ክፉ ድርጊት ምንድን ነው?

17 ቁጥር 8 ላይ ኢሳይያስ ይሖዋ የተናገረውን ቃል መጥቀስ ያቆማል። ይሁዳ ያፈራችውን “ሆምጣጣ ፍሬ” በማውገዝ ከስድስቱ ወዮታዎች መካከል የመጀመሪያ የሆነውን ይናገራል:- “ስፍራ እስከማይቀር ድረስ እናንተም በምድር ላይ ብቻችሁን እስክትቀመጡ ድረስ፣ ቤትን ከቤት ጋር ለሚያያይዙ እርሻንም ከእርሻ ጋር ለሚያቀራርቡ ወዮላቸው! የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር በጆሮዬ እንዲህ አለ:- በእውነት ብዙ ታላቅና መልካም ቤት ባድማ ይሆናል፣ የሚቀመጥበትም አይገኝም። ከወይኑ ቦታ አሥር ጥማድ በሬ ካረሰው አንድ የባዶስ መስፈሪያ ብቻ ይወጣል፤ አንድ የቆሮስ መስፈሪያ ዘር አንድ የኢፍ መስፈሪያ ብቻ ይሰጣል።”​—⁠ኢሳይያስ 5:​8-10

18, 19. በኢሳይያስ ዘመን የኖሩት ሰዎች ይሖዋ ስለ ርስት የሰጠውን መመሪያ ችላ ያሉት እንዴት ነው? ውጤቱስ ምን ይሆናል?

18 በጥንቷ እስራኤል መሬት ሁሉ የይሖዋ ነበር። እያንዳንዱ ቤተሰብ ከአምላክ ያገኘው ርስት የነበረው ሲሆን ይህን ማከራየት ወይም በብድር መስጠት ካልሆነ በስተቀር ምድሪቱን ‘ለዘለቄታው’ መሸጥ አይቻልም ነበር። (ዘሌዋውያን 25:​23) ይህ ሕግ ርስትን በሞኖፖል መያዝን የመሳሰሉትን የግፍ ድርጊቶች የሚከላከል ነበር። እንዲሁም ቤተሰቦች ወደ ድህነት አራንቋ እንዳይገቡ ጠብቋቸዋል። ይሁን አንጂ በይሁዳ የነበሩ አንዳንዶች በስግብግብነት አምላክ ስለ ርስት ያወጣውን ሕግ ይጥሱ ነበር። ሚክያስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “በእርሻው ላይ ይመኛሉ፣ በግዴታም ይይዙታል፤ በቤቶችም ላይ ይመኛሉ፣ ይወስዱአቸውማል፤ ሰውንና ቤቱን፣ ሰውንና ርስቱንም ይነጥቃሉ።” (ሚክያስ 2:​2) ሆኖም ምሳሌ 20:​21 “በመጀመሪያ ፈጥኖ [“በስግብግብነት፣” NW] የተከማቸ ርስት ፍጻሜው አይባረክም” በማለት ያስጠነቅቃል።

19 ይሖዋ እነዚህ ስግብግብ ሰዎች አላግባብ ያጋበሱትን ሃብት እንደሚገፍፋቸው ተናግሯል። አላግባብ የነጠቁት ቤት ‘የሚቀመጥበት አይኖርም።’ የቋመጡለትም ምድር የሚያፈራው ፍሬ እጅግ አነስተኛ ብቻ ይሆናል። ይህ እርግማን እንዴትና መቼ ፍጻሜውን እንደሚያገኝ ተለይቶ የተጠቀሰ ነገር የለም። ቢያንስ ግን በከፊል ወደፊት በባቢሎን ምርኮ ወቅት የሚመጣባቸውን ነገር የሚጠቅስ ይመስላል።​—⁠ኢሳይያስ 27:​10

20. ዛሬ ያሉ ክርስቲያኖች አንዳንድ እስራኤላውያን ካሳዩት የስስት ዝንባሌ መራቅ የሚችሉት እንዴት ነው?

20 ዛሬ ያሉ ክርስቲያኖች በዚያ ዘመን የነበሩ አንዳንድ እስራኤላውያን ያሳዩትን የአልጠግብ ባይነት ባሕርይ ሊጸየፉት ይገባል። (ምሳሌ 27:​20) ለቁሳዊ ነገሮች የተጋነነ ግምት መስጠት ከጀመርን ቀስ ብለን ደግሞ ያለ ምንም ይሉኝታ በተሳሳተ መንገድ ገንዘብ ወደ ማሳደድ ዞር ልንል እንችላለን። አንድ ሰው አጠያያቂ በሆኑ የንግድ ሥራዎች ወይም በአጭር ጊዜ ሃብታም ያደርጋሉ በሚባሉ የማይጨበጡ ዕቅዶች ውስጥ እጁን ሊያስገባ ይችላል። “ባለጠጋ ለመሆን የሚቸኩል ግን ሳይቀጣ አይቀርም።” (ምሳሌ 28:​20) እንግዲያው ባለን ነገር መርካቱ ምንኛ አስፈላጊ ነው!​—⁠1 ጢሞቴዎስ 6:​8

አጠያያቂ መዝናኛ ያለው አደጋ

21. በኢሳይያስ ሁለተኛ ወዮታ የተወገዘው ኃጢአት ምንድን ነው?

21 ቀጥሎ ደግሞ ኢሳይያስ ሁለተኛውን ወዮታ ይገልጻል:- “ስካርን ለመከተል በጥዋት ለሚማልዱ፣ የወይን ጠጅም እስኪያቃጥላቸው እስከ ሌሊት ድረስ ለሚዘገዩ ወዮላቸው! መሰንቆና በገና ከበሮና እምቢልታም የወይን ጠጅም በግብዣቸው አለ፤ የእግዚአብሔርን ሥራ ግን አልተመለከቱም፣ እጁም ያደረገችውን አላስተዋሉም።”​—⁠ኢሳይያስ 5:​11, 12

22. በእስራኤል ውስጥ ራስን አለመግዛት የተንጸባረቀው እንዴት ነው? ይህስ በብሔሩ ላይ የሚያስከትለው ውጤት ምንድን ነው?

22 ይሖዋ “ደስተኛ አምላክ” ስለሆነ አገልጋዮቹ ሚዛናዊ በሆነ መንገድ በመዝናናታቸው አይከፋም። (1 ጢሞቴዎስ 1:​11) ይሁን እንጂ ተድላን የሚያሳድዱት እነዚህ ሰዎች ገደብ የላቸውም! መጽሐፍ ቅዱስ ‘ብዙውን ጊዜ የሚሰክሩ ሰዎች በሌሊት ይሰክራሉ’ በማለት ይገልጻል። (1 ተሰሎንቄ 5:​7) ሆኖም በትንቢቱ ላይ የተጠቀሱት ፈንጠዝያ ወዳዶች በመጠጥ መራጨት የሚጀምሩት ገና ቀኑ ሲጠባ ሲሆን እስከ ምሽት ድረስ መጠጣታቸውን ይቀጥላሉ! ጨርሶ አምላክ ያለና በድርጊታቸውም ተጠያቂ የሚያደርጋቸው መስሎ አይታያቸውም። ኢሳይያስ እንደነዚህ ያሉት ሰዎች የወደፊት ዕጣቸው የጨለመ መሆኑን ተንብዮአል:- “ስለዚህ ሕዝቤ ወደ ምርኮ ሄዱ፣ ጌታን አላወቁትምና፤ ከበርቴዎቻቸውም ተራቡ፣ ሕዝባቸውም ተጠሙ።” (ኢሳይያስ 5:13) በእውነተኛው እውቀት መሠረት ለመመላለስ አሻፈረኝ በማለታቸው ትንሽ ትልቅ ሳይል የአምላክ የቃል ኪዳን ሕዝብ ወደ ሲኦል ይወርዳል።​—⁠ኢሳይያስ 5:​14-17ን አንብብ።

23, 24. ክርስቲያኖች ገደብ ማበጀት ወይም ልከኝነትን ማንጸባረቅ የሚጠበቅባቸው እንዴት ነው?

23 “ፈንጠዝያ” ወይም “ቅጥ ያጣ ጭፈራ” በመጀመሪያው መቶ ዘመን በነበሩ አንዳንድ ክርስቲያኖች ዘንድም የነበረ ችግር ነው። (ገላትያ 5:​21 ባይንግተን፤ 2 ጴጥሮስ 2:​13) በመሆኑም ዛሬም ጭምር አንዳንድ ራሳቸውን የወሰኑ ክርስቲያኖች ማኅበራዊ ግብዣዎችን በተመለከተ ጥበብ የጎደለው ውሳኔ ማድረጋቸው ምንም አያስገርምም። የአልኮል መጠጦች በገፍ መቅረባቸው አንዳንዶች እንዲጮሁና ከጣሪያ በላይ እንዲንጫጩ አድርጓቸዋል። (ምሳሌ 20:​1 NW) ያለልክ በወሰዱት መጠጥ ተገፋፍተው ሥነ ምግባር የጎደለው ድርጊት የፈጸሙ አሉ። እንዲሁም አንዳንዶቹ ግብዣዎች ሌሊቱን ሙሉ በመዝለቃቸው በሚቀጥለው ቀን ለሚደረገው ክርስቲያናዊ እንቅስቃሴ እንቅፋት እስከመሆን ደርሰዋል።

24 ይሁን እንጂ ሚዛናዊ የሆኑ ክርስቲያኖች በመዝናኛ ምርጫቸው ረገድ መልካም ፍሬዎችን ያፈራሉ እንዲሁም ገደብ በማበጀት ልከኝነትን ያንጸባርቃሉ። “በቀን እንደምንሆን በአገባብ እንመላለስ፤ በዘፈንና [“በፈንጠዝያና፣” NW] በስካር አይሁን” የሚለውን በ⁠ሮሜ 13:​13 ላይ የሚገኘውን የጳውሎስን ምክር ይከተላሉ።

ኃጢአትን መጥላትና እውነትን ማፍቀር

25, 26. ኢሳይያስ በሦስተኛውና በአራተኛው ወዮታ ያጋለጠው የእስራኤላውያን ክፉ አስተሳሰብ የትኛው ነው?

25 አሁን ደግሞ ኢሳይያስ ሦስተኛውንና አራተኛውን ወዮታ ሲናገር አዳምጥ:- “በደልን በምናምንቴ ገመድ፣ ኃጢአትንም በሰረገላ ማሰሪያ ወደ ራሳቸው ለሚስቡ:- እናይ ዘንድ ይቸኩል፣ ሥራውንም ያፋጥን፤ እናውቃትም ዘንድ የእስራኤል ቅዱስ ምክር ትቅረብ፣ ትምጣ ለሚሉ ወዮላቸው! ክፉውን መልካም መልካሙን ክፉ ለሚሉ፣ ጨለማውን ብርሃን ብርሃኑንም ጨለማ ለሚያደርጉ፣ ጣፋጩን መራራ መራራውንም ጣፋጭ ለሚያደርጉ ወዮላቸው!”​—⁠ኢሳይያስ 5:​18-20

26 ይህ ኃጢአትን ልማድ ስላደረጉ ሰዎች የተሰጠ እንዴት ያለ ሕያው መግለጫ ነው! ከሚጎትተው ሰረገላ ጋር እንደታሠረ እንስሳ ከኃጢአት ጋር ተቆራኝተዋል። እነዚህ ኃጢአተኞች መጪውን የፍርድ ቀን አይፈሩም። ‘የአምላክ ሥራ በፍጥነት ይምጣ’ በማለት ያፌዛሉ! ለአምላክ ሕግ ከመታዘዝ ይልቅ “ክፉውን መልካም መልካሙንም ክፉ” በማለት ነገሮችን ያጣምማሉ።​—⁠ከ⁠ኤርምያስ 6:​15፤ 2 ጴጥሮስ 3:​3-7 ጋር አወዳድር።

27. ዛሬ ያሉ ክርስቲያኖች የእስራኤላውያኑን ዓይነት ዝንባሌ ከማሳየት ሊርቁ የሚችሉት እንዴት ነው?

27 ዛሬ ያሉ ክርስቲያኖች እንዲህ ያለውን ዝንባሌ ፈጽመው ማስወገድ ይኖርባቸዋል። ለምሳሌ ያህል ዝሙትንና ግብረ ሰዶምን ክፋት እንደሌላቸው ነገሮች አድርጎ የተቀበለው ዓለም ያለውን አመለካከት ይቃወማሉ። (ኤፌሶን 4:​18, 19) አንድ ክርስቲያን ከባድ ኃጢአት ወደ መፈጸም የሚመራ ‘የተሳሳተ ጎዳና’ ሊከተል እንደሚችል አይካድም። (ገላትያ 6:​1 NW) በጉባኤው ውስጥ ያሉ ሽማግሌዎች በኃጢአት የወደቁትንና እርዳታ የሚያስፈልጋቸውን ለማገዝ ዝግጁ ናቸው። (ያዕቆብ 5:​14, 15) በጸሎትና በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ በተመሠረተ ምክር በመታገዝ በመንፈሳዊ ማገገም ይቻላል። አለዚያ ግን ‘የኃጢአት ባሪያ’ ሆኖ የመቅረት አደጋ አለ። (ዮሐንስ 8:​34) ክርስቲያኖች በይሖዋ ፊት “ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ” ሆነው ለመገኘት ይጥራሉ እንጂ በአምላክ አይዘብቱም ወይም የፍርድ ቀን እንደሚመጣ አይዘነጉም።​—⁠2 ጴጥሮስ 3:​14፤ ገላትያ 6:​7, 8

28. በመጨረሻዎቹ የኢሳይያስ ወዮታዎች ላይ የተወገዙት ኃጢአቶች የትኞቹ ናቸው? ዛሬ ያሉ ክርስቲያኖችስ ከዚህ መራቅ የሚችሉት እንዴት ነው?

28 ኢሳይያስ እነዚህን የመጨረሻ ወዮታዎች አክሎ መናገሩ ተገቢ ነው:- “በዓይናቸው ጥበበኞች በነፍሳቸውም አስተዋዮች ለሆኑ ወዮላቸው! የወይን ጠጅ ለመጠጣት ኃያላን የሚያሰክረውንም ለማደባለቅ ጨካኞች ለሆኑ፤ በደለኛውን ስለ ጉቦ ጻድቅ ለሚያደርጉ፣ የጻድቁንም ጽድቅ ለሚያስወግዱበት ወዮላቸው!” (ኢሳይያስ 5:21-23) እነዚህ ቃላት የተነገሩት በምድሪቱ መሳፍንት ሆነው ለሚያገለግሉት ሰዎች እንደነበር ከሁኔታው ለመረዳት ይቻላል። በዛሬው ጊዜ ሽማግሌዎች “በነፍሳቸው አስተዋዮች” መስለው ከመታየት ይርቃሉ። ከሌሎች ሽማግሌዎች የሚሰጣቸውን ምክር በትሕትና ይቀበላሉ፤ እንዲሁም ድርጅታዊ መመሪያዎችን በጥብቅ ይከተላሉ። (ምሳሌ 1:​5፤ 1 ቆሮንቶስ 14:​33) በአልኮል አጠቃቀማቸው ረገድ ልከኞች ሲሆኑ ከየትኛውም የጉባኤ ኃላፊነታቸው በፊት የአልኮል መጠጥ አይወስዱም። (ሆሴዕ 4:​11) በተጨማሪም ሽማግሌዎች አድሏዊ መስለው እንዳይታዩ እንኳን ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደርጋሉ። (ያዕቆብ 2:​9) ከሕዝበ ክርስትና ካህናት ምንኛ የተለዩ ናቸው! ከእነዚህ ካህናት መካከል ብዙዎቹ ሐዋርያው ጳውሎስ በ⁠ሮሜ 1:​18, 26, 27፤ በ⁠1 ቆሮንቶስ 6:​9, 10 እንዲሁም በ⁠ኤፌሶን 5:​3-5 ላይ ከሰጠው ምክር ፍጹም በተቃራኒ በመካከላቸው ያሉ ታላላቅና ባለጠጋ ሰዎችን ኃጢአት ይሸፋፍኑላቸዋል።

29. ከእስራኤላውያን የተውጣጣውን የይሖዋ የወይን ቦታ ምን አስከፊ ፍጻሜ ይጠብቀዋል?

29 ኢሳይያስ ይህንን ትንቢታዊ መልእክት የሚደመድመው ‘የይሖዋን ሕግ የጣሉትና’ የጽድቅ ፍሬ ማፍራት የተሳናቸው ሰዎች መጨረሻቸው አስከፊ እንደሚሆን በመግለጽ ነው። (ኢሳይያስ 5:​24፤ ሆሴዕ 9:​16፤ ሚልክያስ 4:​1) እንዲህ ይላል:- [ይሖዋ] ለአሕዛብም [“ለአንድ ታላቅ ብሔር፣” NW] በሩቅ ምልክትን ያቆማል፣ ከምድርም ዳርቻ በፉጨት ይጠራቸዋል፤ እነሆም፣ እየተጣደፉ ፈጥነው ይመጣሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 5:​26፤ ዘዳግም 28:​49፤ ኤርምያስ 5:​15

30. በይሖዋ ሕዝቦች ላይ “አንድ ታላቅ ሕዝብ” የሚጠራው ማን ነው? ውጤቱስ ምን ይሆናል?

30 በጥንት ዘመን አንድ ረጅም እንጨት ከፍ ያለ ቦታ ላይ ይተከልና ሕዝቡ ወይም ሠራዊቱ ወደዚያ እንዲሰባሰብ ‘ምልክት’ ሆኖ ያገለግል ነበር። (ከ⁠ኢሳይያስ 18:​3፤ ኤርምያስ 51:​27 ጋር አወዳድር።) አሁን ግን በስም ያልተጠቀሰውን ይህን “ታላቅ ብሔር” ፍርዱን ለማስፈጸም ሲል የሚሰበስበው ይሖዋ ራሱ ነው። * ‘በፉጨት ይጠራዋል’ ማለትም ሊቆጣጠራቸው እንደሚገባ በማሰብ ወደ ባዘኑት ሕዝቦቹ እንዲመጣ ትኩረቱን ይስበዋል ማለት ነው። ከዚያም ነቢዩ እንደ አንበሳ ያለው ይህ ድል አድራጊ በፍጥነት ስለሚያመጣው አስፈሪ ጥፋት ሲገልጽ ‘ንጥቂያውን’ ማለትም የአምላክን ብሔር ‘እንደሚይዝና’ በምርኮ ‘እንደሚወስደው’ ተናግሯል። (ኢሳይያስ 5:​27-30ሀን አንብብ።) ይህ በይሖዋ ሕዝብ ምድር ለሚኖሩት ሰዎች እንዴት የሚያሳዝን ነገር ነው! “ወደ ምድርም ቢመለከቱ፣ እነሆ፣ ጨለማና መከራ አለ፤ ብርሃንም በደመናዎችዋ ውስጥ ጨልሞአል።”​—⁠ኢሳይያስ 5:​30ለ

31. እውነተኛ ክርስቲያኖች ከእስራኤላውያን በተውጣጣው የይሖዋ የወይን ቦታ ላይ ከደረሰው ዓይነት ቅጣት መራቅ የሚችሉት እንዴት ነው?

31 አዎን፣ አምላክ ያን ያህል በፍቅር ተንከባክቦ የተከለው የወይን ቦታ ምድረ በዳ ማለትም ለጥፋት የሚገባ ሆኗል። የኢሳይያስ ቃላት ዛሬ ይሖዋን ለሚያገለግሉ ሁሉ የሚያስተላልፉት ትምህርት እንዴት ጠንካራ ነው! የአምላክ ሕዝቦች ለይሖዋ ክብርና ለራሳቸውም መዳን ሲሉ የጽድቅ ፍሬ ብቻ ለማፍራት የሚጣጣሩ እንዲሆኑ ምኞታችን ነው!

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.4 አንዳንድ ምሁራን ከድንጋይ ግንብ ይልቅ በሰፊው የተለመዱት እንደ ዳስ ወይም ጎጆ ያሉት በቀላል ወጪ የሚሠሩ ጊዜያዊ ነገሮች ነበሩ የሚል እምነት አላቸው። (ኢሳይያስ 1:​8) በመካከሉ የተሠራው ግንብ የወይኑ ቦታ ባለቤት ለዚህ “የወይን ቦታ” ምን ያህል የተለየ ጥረት እንዳደረገለት የሚያሳይ ነው።

^ አን.30 ኢሳይያስ በሌሎች ትንቢቶች ውስጥ ባቢሎን የይሖዋን የጥፋት ፍርድ የሚያስፈጽም ብሔር እንደሆነ ገልጿል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 83 ላይ የሚገኝ የሥዕል መግለጫ]

ከሚጎትተው ሰረገላ ጋር እንደታሠረ እንስሳ ኃጢአተኛውም ከኃጢአት ጋር ተቆራኝቷል

[በገጽ 85 ላይ የሚገኝ ባለ ሙሉ ገጽ ሥዕል]