በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የይሖዋ ቤት ከፍ ከፍ ብሏል

የይሖዋ ቤት ከፍ ከፍ ብሏል

ምዕራፍ አራት

የይሖዋ ቤት ከፍ ከፍ ብሏል

ኢሳይያስ 2:​1-5

1, 2. በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አደባባይ በሚገኝ ግንብ ላይ ተቀርጸው የሚገኙት ቃላት የትኞቹ ናቸው? እነዚህ ቃላት የተወሰዱትስ ከየት ነው?

“ሰይፋቸውንም ማረሻ፣ ጦራቸውንም ማጭድ ለማድረግ ይቀጠቅጣሉ፤ ሕዝብም በሕዝብ ላይ ሰይፍ አያነሣም፣ ሰልፍም ከእንግዲህ ወዲህ አይማሩም።” እነዚህ ቃላት ኒው ዮርክ በሚገኘው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አደባባይ በአንድ ግንብ ላይ ተቀርጸው ይታያሉ። ለአሥርተ ዓመታት የጥቅሱ ምንጭ ሳይገለጽ ቆይቷል። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዓላማ ምድር አቀፍ ሰላም ማስፈን ስለሆነ ጥቅሱን ያመነጩት በ1945 ድርጅቱን የመሠረቱት ሰዎች ናቸው ብሎ መደምደሙ ቀላል ነበር።

2 ይሁን እንጂ በ1975 ከጥቅሱ በታች ኢሳይያስ የሚለው ስም እንዲቀረጽ ተደረገ። ይህም እነዚህ ቃላት በዚህ ዘመን እንዳልተነገሩ ግልጽ የሚያደርግ ነበር። እንዲያውም በዛሬው የኢሳይያስ መጽሐፍ ሁለተኛ ምዕራፍ ውስጥ በትንቢት መልክ የተመዘገቡት ከ2,700 ዓመታት በፊት ነው። ሰላምን የሚያፈቅሩ ሁሉ ኢሳይያስ የተናገራቸው ትንቢቶች ፍጻሜያቸውን የሚያገኙት እንዴትና መቼ እንደሆነ በሺህ ለሚቆጠሩ ዓመታት ሲያስቡ ኖረዋል። ዛሬ ግን እንደዚያ ብሎ መጨነቅ አያስፈልግም። ይህ ጥንታዊ ትንቢት አስገራሚ ፍጻሜውን ሲያገኝ በዓይናችን እያየን ነው።

3. ሰይፋቸውን ማረሻ ለማድረግ የሚቀጠቅጡት አሕዛብ የትኞቹ ናቸው?

3 ሰይፋቸውን ማረሻ ለማድረግ የሚቀጠቅጡት አሕዛብ የትኞቹ ናቸው? ዛሬ ያሉት የፖለቲካ ብሔራትና መንግሥታት እንዳልሆኑ ግልጽ ነው። እነዚህ ብሔራት ጦርነት ለማካሄድና በወታደራዊ ጡንቻ “ሰላምን” ለማስጠበቅ በሚል ሰይፍ ወይም የጦር መሣሪያ መሥራታቸውን ቀጥለዋል። እንዲያውም በእነዚህ ሁሉ ዘመናት የታየው የብሔራት ዝንባሌ ሰይፍን ወደ ማረሻ መቀጥቀጥ ሳይሆን ማረሻን ወደ ሰይፍ መቀጥቀጥ ነው! የኢሳይያስ ትንቢት ፍጻሜውን የሚያገኘው ከሁሉም ብሔራት በተውጣጡ ሰዎች ላይ ሲሆን እነዚህም “የሰላም አምላክ” የሆነውን ይሖዋን የሚያገለግሉ ሰዎች ናቸው።​—⁠ፊልጵስዩስ 4:​9

ወደ ንጹሕ አምልኮ የሚጎርፉ አሕዛብ

4, 5. የኢሳይያስ ምዕራፍ 2 የመክፈቻ ቃላት ስለ ምን ነገር ይተነብያሉ? የእነዚህን ቃላት አስተማማኝነት የሚያረጋግጠውስ ምንድን ነው?

4 ኢሳይያስ ምዕራፍ 2 በሚከተሉት ቃላት ይጀምራል:- “የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ስለ ይሁዳና ስለ ኢየሩሳሌም ያየው ቃል። በዘመኑም ፍጻሜ [“እንዲህ ሊሆን ይገባል፣” NW] የእግዚአብሔር ቤት ተራራ በተራሮች ራስ ላይ ጸንቶ ይቆማል፣ ከኮረብቶችም በላይ ከፍ ከፍ ይላል፣ አሕዛብም ሁሉ ወደ እርሱ ይሰበሰባሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 2:​1, 2

5 ኢሳይያስ ወደፊት ይሆናል ብሎ የተናገረለት ነገር እንዲሁ ግምታዊ ሐሳብ እንዳልሆነ ልብ በል። ኢሳይያስ እንዲመዘግብ የተነገረው ያለ ጥርጥር ‘ሊሆን የሚገባውን’ ነገር ነው። የይሖዋ ዓላማ ደግሞ ሁሌም ‘ፍጻሜውን እንደሚያገኝ’ የተረጋገጠ ነው። (ኢሳይያስ 55:​11) አምላክ ራሱ የሰጠው የተስፋ ቃል አስተማማኝ መሆኑን ጠበቅ አድርጎ ለመግለጽ ይመስላል በኢሳይያስ ዘመን የኖረው ነቢዩ ሚክያስም በመንፈስ አነሳሽነት በ⁠ኢሳይያስ 2:​2-4 ላይ ከሚገኘው ጋር የሚመሳሰል ትንቢት በመጽሐፉ ውስጥ እንዲያሰፍር አድርጓል።​—⁠ሚክያስ 4:​1-3

6. የኢሳይያስ ትንቢት ፍጻሜውን የሚያገኘው መቼ ነው?

6 የኢሳይያስ ትንቢት ፍጻሜውን የሚያገኘው መቼ ነው? ‘በዘመኑ ፍጻሜ’ ነው። ዘ ኒው ኢንተርናሽናል ቨርሽን “በመጨረሻዎቹ ቀናት” ይላል። የግሪክኛ ቅዱሳን ጽሑፎች ይህ ዘመን ተለይቶ የሚታወቅባቸውን ምልክቶች አስቀድመው ተናግረዋል። ከእነዚህ ምልክቶች መካከል ጦርነት፣ የምድር መንቀጥቀጥ፣ ቸነፈር፣ የምግብ እጥረትና ‘የጊዜው አስጨናቂነት’ ይገኙበታል። * (2 ጢሞቴዎስ 3:​1-5፤ ሉቃስ 21:​10, 11) እንደነዚህ ያሉት ትንቢቶች ፍጻሜያቸውን ማግኘታቸው ‘በዘመኑ ፍጻሜ’ ማለትም በዚህ የነገሮች ሥርዓት የመጨረሻ ቀኖች እንደምንኖር በቂ ማረጋገጫ ነው። እንግዲያው ኢሳይያስ አስቀድሞ በትንቢት የተናገራቸው ነገሮች በዘመናችን ይፈጸማሉ ብለን መጠበቃችን ምክንያታዊ ይሆናል።

አምልኮ የሚካሄድበት ተራራ

7. ኢሳይያስ በሥዕላዊ መንገድ የገለጸው ትንቢት ምንድን ነው?

7 ኢሳይያስ አንድን ትንቢት ሥዕላዊ በሆነ መንገድ በጥቂት ቃላት ቁልጭ አድርጎ ገልጿል። አናቱ ላይ ክብራማ የሆነ ቤት ማለትም የይሖዋ ቤተ መቅደስ የሚገኝበት አንድ ከፍ ያለ ተራራ እናያለን። ይህ ተራራ በዙሪያው ካሉት ኮረብቶችና ተራሮች ሁሉ በላይ ከፍ ያለ ነው። ይሁንና የሚያሸብር ወይም የሚያስፈራ ሳይሆን ማራኪ የሆነ እይታ ያለው ነው። ከሁሉም ብሔራት የተውጣጡ ሰዎች ወደ ይሖዋ ቤት ተራራ ለመውጣት ይጓጓሉ፤ ወደዚያም ይጎርፋሉ። ይህንን ነገር በዓይነ ሕሊናችን መሳል ቀላል ነው። ይሁን እንጂ ትርጉሙ ምንድን ነው?

8. (ሀ) በኢሳይያስ ዘመን ተራሮችና ኮረብቶች ከምን ጋር ይዛመዱ ነበር? (ለ) አሕዛብ ‘ወደ ይሖዋ ቤት ተራራ’ መጉረፋቸው ምን ያመለክታል?

8 በኢሳይያስ ዘመን ኮረብቶችና ተራሮች ብዙውን ጊዜ የሚዛመዱት ከአምልኮ ጋር ነበር። ለምሳሌ ያህል የጣዖት አምልኮ ቦታዎችና የሐሰት አማልክት ቅዱስ ስፍራዎች ሆነው ያገለግላሉ። (ዘዳግም 12:​2፤ ኤርምያስ 3:​6) ይሁን እንጂ የይሖዋ ቤት ወይም ቤተ መቅደስ በኢየሩሳሌም ለሚገኘው የሞሪያ ተራራ ጫፍ ድምቀት ጨምሮለታል። የታመኑ እስራኤላውያን በዓመት ሦስት ጊዜ ወደ ኢየሩሳሌም በመጓዝ እውነተኛውን አምላክ ለማምለክ ወደ ሞሪያ ተራራ ይወጡ ነበር። (ዘዳግም 16:​16) በመሆኑም አሕዛብ ‘ወደ ይሖዋ ቤት ተራራ’ መጉረፋቸው ብዙ ሰዎች ወደ እውነተኛው አምልኮ እየተሰበሰቡ መሆናቸውን የሚያመለክት መግለጫ ነው።

9. ‘የይሖዋ ቤት ተራራ’ ምን ያመለክታል?

9 እርግጥ ዛሬ የአምላክ ሕዝቦች ቃል በቃል በድንጋይ የተሠራ ቤተ መቅደስ ወዳለበት አንድ ተራራ አይሰበሰቡም። በኢየሩሳሌም የነበረው የይሖዋ ቤተ መቅደስ በ70 እዘአ በሮማውያን ሠራዊት ተደምስሷል። ከዚህም በላይ ሐዋርያው ጳውሎስ በኢየሩሳሌም የነበረው ቤተ መቅደስም ሆነ ከዚያ በፊት ሲያገለግል የቆየው የመገናኛው ድንኳን ምሳሌያዊ ጥላ ብቻ እንደነበሩ ግልጽ አድርጓል። ሁለቱም የሚወክሉት አንድን ታላቅ መንፈሳዊ እውነታ ይኸውም ‘በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለችውን እውነተኛይቱን ድንኳን’ ነው። (ዕብራውያን 8:​2) ይህ መንፈሳዊ ድንኳን በኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛዊ መሥዋዕት አማካኝነት ለአምልኮ ወደ ይሖዋ ለመቅረብ የሚያስችል ዝግጅት ነው። (ዕብራውያን 9:​2-10, 23) ከዚሁ ጋር በሚስማማ መንገድ በ⁠ኢሳይያስ 2:​2 ላይ የተገለጸው ‘የይሖዋ ቤት ተራራ’ የሚያመለክተው በጊዜያችን ያለውን ከፍ ያለ ክብር የተጎናጸፈውን የይሖዋ ንጹሕ አምልኮ ነው። ንጹሑን አምልኮ የሚቀበሉ ሰዎች በአምልኮ አንድነት ይሰባሰባሉ እንጂ በአንድ የተወሰነ ስፍራ መሰብሰብ አያስፈልጋቸውም።

የንጹሕ አምልኮ ከፍ ከፍ ማለት

10, 11. የይሖዋ አምልኮ በዘመናችን ከፍ ከፍ ያለው እንዴት ነው?

10 ነቢዩ “የእግዚአብሔር ቤት ተራራ” ወይም ንጹሕ አምልኮ “በተራሮች ራስ ላይ ጸንቶ ይቆማል፣ ከኮረብቶችም በላይ ከፍ ከፍ ይላል” ሲል ተናግሯል። ከኢሳይያስ ዘመን ብዙ ዓመታት ቀደም ብሎ ንጉሥ ዳዊት የቃል ኪዳኑን ታቦት ከባሕር ወለል በላይ 760 ሜትር ከፍታ ላይ ወደሚገኘው የኢየሩሳሌም የጽዮን ተራራ አምጥቶት ነበር። ታቦቱ ተሠርቶ ወደተጠናቀቀውና በሞሪያ ተራራ ላይ ወደሚገኘው ቤተ መቅደስ እስከተወሰደበት ጊዜ ድረስ በዚህ ቦታ ቆይቷል። (2 ሳሙኤል 5:​7፤ 6:​14-19፤ 2 ዜና መዋዕል 3:​1፤ 5:​1-10) ከዚህ አንጻር ሲታይ በኢሳይያስ ዘመን ቅዱሱ ታቦት ቃል በቃል በአካባቢው ከነበሩት ለሐሰት አምልኮ ከሚያገለግሉ ብዙ ኮረብቶች ሁሉ በላይ ከፍ ባለው ቤተ መቅደስ ውስጥ ተቀምጦ ነበር።

11 እርግጥ ነው፣ በመንፈሳዊ ዓይን ሲታይ ለይሖዋ የሚቀርበው አምልኮ በየትኛውም ዘመን ቢሆን ሰዎች ለሐሰት አማልክት ከሚያቀርቡት አምልኮ የላቀ ደረጃ ነበረው። ይሁን እንጂ በዚህ በእኛ ዘመን ይሖዋ አምልኮው ከማንኛውም ንጹህ ያልሆነ አምልኮ ሁሉ በላይ እጅግ ከፍ እንዲል አድርጓል። አዎን፣ ‘ከኮረብቶችና ከተራሮች ሁሉ በላይ’ ከፍ እንዲል አድርጓል። ይሁንና ይህ የሆነው እንዴት ነው? በአብዛኛው ይህ ቃል ፍጻሜውን ያገኘው እርሱን ‘በመንፈስና በእውነት ለማምለክ የሚፈልጉ ሰዎች አንድ ላይ በመሰባሰባቸው’ ነው።​—⁠ዮሐንስ 4:​23

12. ‘የመንግሥት ልጆች’ የተባሉት እነማን ናቸው? ምን የመሰብሰብ ሥራስ ተከናውኗል?

12 ክርስቶስ ኢየሱስ ‘ስለ ነገሮች ሥርዓት መደምደሚያ’ ሲናገር መላእክት ‘የመንግሥቱን ልጆች’ የሚሰበስቡበት የመከር ወቅት እንደሆነ ጠቅሷል። እነዚህ የመንግሥት ልጆች ከኢየሱስ ጋር በሰማያዊ ክብር የመግዛት መብት ያላቸው ሰዎች ናቸው። (ማቴዎስ 13:​36-43) ከ1919 ወዲህ ይሖዋ ከእነዚህ መካከል ‘ለቀሩት’ ከመላእክት ጋር በመከሩ ሥራ ለመካፈል የሚያስችል ኃይል ሰጥቷቸዋል። (ራእይ 12:​17) በዚህ መሠረት በመጀመሪያ የተሰበሰቡት የመንግሥት ልጆች ማለትም የኢየሱስ ቅቡዓን ወንድሞች ናቸው። ከዚያ እነርሱም በተራቸው ተጨማሪ የመሰብሰብ ሥራ በማከናወኑ ተግባር ይካፈላሉ።

13. ይሖዋ ቅቡዓን ቀሪዎቹን የባረካቸው እንዴት ነው?

13 በዚህ የመከር ወቅት ይሖዋ ቅቡዓን ቀሪዎቹ ቃሉን መጽሐፍ ቅዱስን እንዲያስተውሉና በሥራ ላይ እንዲያውሉ ደረጃ በደረጃ ሲረዳቸው ቆይቷል። ይህም ለንጹሕ አምልኮ ከፍ ከፍ ማለት አስተዋጽኦ አድርጓል። ‘ምድርን ጨለማ አሕዛብንም ድቅድቅ ጨለማ ቢውጣቸውም’ ቅቡዓኑ በይሖዋ ነጽተውና ጠርተው በሰው ዘር መካከል “ብርሃን አብሪዎች” በመሆን እያገለገሉ ነው። (ኢሳይያስ 60:​2፤ ፊልጵስዩስ 2:​15 NW) እነዚህ በመንፈስ የተቀቡ ሰዎች ‘የፈቃዱ ትክክለኛ እውቀት፣ መንፈሳዊ ጥበብና ማስተዋል ሞልቶባቸው’ ‘በአባታቸው መንግሥት እንደ ፀሐይ ያበራሉ።’​—⁠ቆላስይስ 1:​9፤ ማቴዎስ 13:43

14, 15. ‘ከመንግሥት ልጆች’ መሰብሰብ በተጨማሪ ሌላ ምን የመሰብሰብ ሥራ ተከናውኗል? ይህንንስ ሐጌ አስቀድሞ በትንቢት የተናገረው እንዴት ነው?

14 በዚህ ብቻ አላበቃም ሌሎችም ‘ወደ ይሖዋ ቤት ተራራ’ ጎርፈዋል። ኢየሱስ “ሌሎች በጎች” ሲል የጠራቸው እነዚህ ሰዎች ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ ያላቸው ሰዎች ናቸው። (ዮሐንስ 10:​16፤ ራእይ 21:​3, 4) እነዚህ ከ1930ዎቹ አንስቶ በሺዎች ከዚያም በመቶ ሺዎች ብሎም ዛሬ በሚልዮኖች የሚቆጠሩ ሆነዋል! ለሐዋርያው ዮሐንስ በተሰጠው ራእይ ላይ ‘ከሕዝብ፣ ከነገድ፣ ከወገንና ከቋንቋ የተውጣጡ ማንም ሊቆጥራቸው የማይችል እጅግ ብዙ ሰዎች’ መሆናቸው ተገልጿል።​—⁠ራእይ 7:​9

15 ነቢዩ ሐጌ ይህ ብዙ ሕዝብ እንደሚመጣ ትንቢት ተናግሮ ነበር። እንዲህ ሲል ጽፏል:- “የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና:- ገና አንድ ጊዜ በቅርብ ዘመን እኔ ሰማያትንና ምድርን ባሕርንና የብስንም አናውጣለሁ፤ አሕዛብን ሁሉ አናውጣለሁ፣ በአሕዛብ ሁሉ የተመረጠውም ዕቃ [በንጹሕ አምልኮ ከቆቡዓን ክርስቲያኖች ጋር የሚተባባበሩ ሰዎች] ይመጣል፤ ይህንንም ቤት በክብር እሞላዋለሁ፣ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር።” (ሐጌ 2:​6, 7) አሁንም ቁጥራቸው እያደገ ያለው የእነዚህ እጅግ ብዙ ሰዎችና የቅቡዓን ጓደኞቻቸው መኖር በይሖዋ ቤት የሚቀርበውን ንጹሕ አምልኮ ከፍ ከፍ የሚያደርግ ወይም በሌላ አባባል ለዚያ ክብር የሚጨምር ነው። ከአሁን በፊት ይህን ያህል ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ለእውነተኛው አምላክ በሚቀርብ አምልኮ የተባበሩበት የታሪክ ወቅት ኖሮ አያውቅም። ይህም ለይሖዋና እርሱ ለሾመው ንጉሥ ለኢየሱስ ክርስቶስ ክብር የሚያመጣ ነው። ንጉሥ ሰሎሞን “የንጉሥ ክብር በሕዝብ ብዛት ነው” ሲል ጽፏል።​—⁠ምሳሌ 14:​28

በሰዎች ሕይወት ውስጥ የላቀ ቦታ የተሰጠው አምልኮ

16-18. አንዳንዶች ይሖዋን ተቀባይነት ባለው መንገድ ለማምለክ ሲሉ ምን ለውጦችን አድርገዋል?

16 ንጹሕ አምልኮ በጊዜያችን ከፍ ከፍ በማለቱ ሊወደስ የሚገባው ይሖዋ ነው። ዛሬም ቢሆን ወደ እርሱ የሚመጡ ሰዎች በዚህ ሥራ የመካፈል መብት ያገኛሉ። አንድን ተራራ መውጣት ጥረት እንደሚጠይቅ ሁሉ የአምላክን የጽድቅ የአቋም ደረጃዎች መማርና በሕይወት ውስጥ ተግባራዊ ማድረግም ጥረትን ይጠይቃል። በመጀመሪያው መቶ ዘመን እንደነበሩት ክርስቲያኖች ሁሉ ዛሬ ያሉትም የአምላክ አገልጋዮች ከእውነተኛው አምልኮ ጋር የማይጣጣሙ አኗኗሮችንና ድርጊቶችን ወደ ኋላ ትተዋል። ዝሙት የሚፈጽሙ፣ ጣዖትን የሚያመልኩ፣ አመንዝሮች፣ ሌቦች፣ ስግብግቦች፣ ሰካራሞችና ሌሎችም አኗኗራቸውን በመቀየር በአምላክ ዓይን ‘ታጥበዋል።’​—⁠1 ቆሮንቶስ 6:​9-11

17 እንደሚከተለው ስትል የጻፈችው የአንዲት ወጣት ሁኔታ ለዚህ ዓይነተኛ ምሳሌ ነው:- “ያለ ተስፋ በጭፍን የምመላለስ ሰው ነበርሁ። የፆታ ብልግናና ስካር የሕይወቴ ክፍል ነበር። የአባላዘር በሽታዎች ያዙኝ። አደገኛ ዕፆችን እሸጥ ነበር፤ ስለ ምንም ነገር ግድ አልነበረኝም።” መጽሐፍ ቅዱስን ካጠናች በኋላ ከአምላክ የአቋም ደረጃዎች ጋር ለመስማማት ስትል በሕይወቷ ውስጥ ከፍተኛ ለውጦችን አደረገች። አሁን እንዲህ በማለት ትናገራለች:- “የአእምሮ ሰላም አለኝ፣ ስለራሴ ጥሩ ስሜት ይሰማኛል፣ ስለ ወደፊቱ ጊዜ ተስፋ አግኝቼአለሁ፣ ጥሩ ቤተሰብና ከሁሉ በላይ ደግሞ ከአባታችን ከይሖዋ ጋር ወዳጅነት መመሥረት ችያለሁ።”

18 በይሖዋ ፊት ተቀባይነት ያለው አቋም ካገኘንም በኋላ ቢሆን ሁላችንም በሕይወታችን ውስጥ አንደኛውን ቦታ በመስጠት ንጹሕ የሆነውን አምልኮ ከፍ ከፍ ማድረጋችንን መቀጠል ይኖርብናል። ይሖዋ በሺህ ከሚቆጠሩ ዓመታት በፊት በኢሳይያስ በኩል እንደተናገረው በዛሬው ጊዜ የእርሱን አምልኮ በሕይወታቸው ውስጥ ከምንም ነገር በላይ የሚያስቀድሙ ብዙ ሰዎች እንደሚኖሩ ያለውን ትምክህት ገልጿል። አንተ ከእነርሱ አንዱ ነህን?

የይሖዋን መንገድ የተማረ ሕዝብ

19, 20. የአምላክ ሕዝብ ስለ ምን ነገር ተምሯል? ደግሞስ የት?

19 ኢሳይያስ በዛሬው ጊዜ እውነተኛውን አምልኮ ስለሚቀበሉ ሰዎች የሚነግረን ተጨማሪ ነገር አለ። እንዲህ ይላል:- “ሕግ ከጽዮን የእግዚአብሔርም ቃል ከኢየሩሳሌም ይወጣልና ብዙዎች አሕዛብ ሄደው:- ኑ፣ ወደ እግዚአብሔር ተራራ፣ ወደ ያዕቆብ አምላክ ቤት እንውጣ፤ እርሱም መንገዱን ያስተምረናል፣ በጎዳናውም እንሄዳለን ይላሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 2:​3

20 ይሖዋ ሕዝቡ እንደ ጠፋ በግ እንዲባዝን አይፈቅድም። ከዚህ ይልቅ መንገዶቹን እንዲማሩ ሲል በመጽሐፍ ቅዱስና በመጽሐፍ ቅዱሳዊ ጽሑፎች አማካኝነት ‘ሕጉን’ እንዲሁም ‘ቃሉን’ ይነግራቸዋል። ይህን እውቀት ማግኘታቸው ‘በመንገዱ እንዲሄዱ’ ያስታጥቃቸዋል። በአድናቆት በተሞላ ልብ በመነሳሳትና ከመለኮታዊ መመሪያዎች ጋር በመስማማት እርስ በርሳቸው ስለ ይሖዋ መንገዶች ይወያያሉ። በትላልቅ የአውራጃ ስብሰባዎች እንዲሁም በመንግሥት አዳራሾችና በመኖሪያ ቤቶች ውስጥ በትናንሽ ቡድኖች ሆነው ስለ ይሖዋ መንገዶች ለማዳመጥና ለመማር አንድ ላይ ይሰበሰባሉ። (ዘዳግም 31:​12, 13) በዚህ መንገድ እርስ በርስ ለመበረታታት እንዲሁም ለፍቅርና ለመልካም ሥራ ለመነቃቃት ይሰበሰቡ የነበሩትን የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖች ምሳሌ ይኮርጃሉ።​—⁠ዕብራውያን 10:​24, 25

21. የይሖዋ አገልጋዮች የሚካፈሉት በየትኛው ሥራ ነው?

21 ሌሎችም ከፍ ወዳለው የይሖዋ አምላክ አምልኮ ‘እንዲወጡ’ ይጋብዛሉ። ይህንን ማድረጋቸው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከማረጉ ጥቂት ቀደም ብሎ ለደቀ መዛሙርቱ ከሰጠው ትእዛዝ ጋር ምንኛ የሚስማማ ነው! እንዲህ ብሏቸው ነበር:- “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፣ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው።” (ማቴዎስ 28:​19, 20) የይሖዋ ምሥክሮች በሚያገኙት መለኮታዊ ድጋፍ በመታገዝ በታዛዥነት በምድር ዙሪያ ሰዎችን እያስተማሩና እያጠመቁ ደቀ መዛሙርት በማድረግ ላይ ናቸው።

ሰይፍ ወደ ማረሻ

22, 23. ኢሳይያስ 2:​4 የሚተነብየው ስለ ምን ነገር ነው? አንድ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ባለ ሥልጣን ይህን ጉዳይ በሚመለከት ምን ብለዋል?

22 አሁን ደግሞ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አደባባይ በሚገኘው ግንብ ላይ የተቀረጹትን ቃላት ጭምር ወደያዘው ቁጥር እንምጣ። ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “በአሕዛብም መካከል ይፈርዳል፣ በብዙ አሕዛብም ላይ ይበይናል፤ ሰይፋቸውንም ማረሻ፣ ጦራቸውንም ማጭድ ለማድረግ ይቀጠቅጣሉ፤ ሕዝብም በሕዝብ ላይ ሰይፍ አያነሳም፣ ሰልፍም ከእንግዲህ ወዲህ አይማሩም።”​—⁠ኢሳይያስ 2:​4

23 ይህንን ማድረግ ቀላል አይሆንም። በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና የባሕል ድርጅት ዋና ዲሬክተር የሆኑት ፍሬድሪኮ ሜየር በአንድ ወቅት እንዲህ ብለዋል:- “ምስልና ድምፅ በሚያስተላልፉ መሣሪያዎች አማካኝነት የጦርነትን ዘግናኝ ገጽታ ዘወትር የምናየውና የምንሰማው ቢሆንም ይህ ለብዙ መቶ ዘመናት ሲገነባ የኖረውን የከባድ መሣሪያዎች ቴክኖሎጂ መስፋፋት ሊገታው የቻለ አይመስልም። ዛሬ ያለው ትውልድ ‘ሰይፍን ወደ ማረሻ’ የመቀየርና ይህ ነው ከማይባል ዘመን በፊት የጀመረውን የጦርነት አባዜ በሰላም የመተካት እጅግ በጣም አስቸጋሪ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ተግባር ከፊቱ ይጠብቀዋል። ይህን ተግባር ከዳር ማድረስ ‘የምድር ነዋሪዎች’ ሊያከናውኑት ከሚችሉት ከማንኛውም ተግባር ሁሉ የላቀ ከመሆኑም ሌላ ለልጆቻችን የምናወርሰው ከሁሉ የተሻለ ቅርስ ነው።”

24, 25. የኢሳይያስ ቃላት ፍጻሜያቸውን የሚያገኙት በማን ላይ ነው? በምንስ መንገድ?

24 በአጠቃላይ ሲታይ ብሔራት ይህን የላቀ ግብ ዳር ሊያደርሱት በፍጹም አይችሉም። ይህ ከአቅማቸው በላይ የሆነ ነገር ነው። የኢሳይያስ ቃላት ፍጻሜያቸውን ያገኙት ከብዙ ብሔራት በተውጣጡና በንጹህ አምልኮ በተሰባሰቡ ግለሰቦች ላይ ነው። ይሖዋ ከእነዚህ ሰዎች ጋር ‘እርቅ ፈጥሯል።’ ሕዝቡ እንዴት እርስ በርሳቸው ተስማምተው በሰላም መኖር እንደሚችሉ አስተምሯቸዋል። በእርግጥም ደግሞ በዚህ በተከፋፈለና ጥላቻ በነገሠበት ዓለም ውስጥ ‘ሰይፋቸውን ማረሻ፣ ጦራቸውን ማጭድ ለማድረግ ቀጥቅጠዋል።’ እንዴት?

25 በመጀመሪያ ደረጃ ብሔራት በሚያደርጉት ጦርነት የትኛውንም ወገን ደግፈው አይቆሙም። ኢየሱስ ከመሞቱ ትንሽ ቀደም ብሎ የታጠቁ ሰዎች ሊይዙት መጥተው ነበር። ጴጥሮስ በጌታው ላይ የተቃጣውን ጥቃት ለመከላከል ሰይፉን በመዘዘ ጊዜ ኢየሱስ “ሰይፍ የሚያነሡ ሁሉ በሰይፍ ይጠፋሉና ሰይፍህን ወደ ስፍራው መልስ” ብሎታል። (ማቴዎስ 26:​52) ከዚያ ጊዜ አንስቶ የኢየሱስን ፈለግ የሚከተሉ ሁሉ በሙሉ ሰይፋቸውን ወደ ማረሻ በመለወጥ እንደነርሱ ሰብዓዊ ፍጡራን የሆኑትን ሰዎች ለመግደል መሣሪያ ከማንሳትም ሆነ ለጦርነት የሚደረጉ ሌሎች ጥረቶችን ከመደገፍ ሲቆጠቡ ኖረዋል። ‘ከሰው ሁሉ ጋር ባላቸው ግንኙነት ሰላምን ተከትለዋል።’​—⁠ዕብራውያን 12:​14

የሰላምን መንገድ መከተል

26, 27. የአምላክ ሕዝብ ‘ሰላምን የሚከተለውና የሚሻው’ እንዴት ነው? አንድ ምሳሌ ስጥ።

26 የአምላክ ሕዝቦች ሰላም በጦርነት ለመሳተፍ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ብቻ የተወሰነ አይደለም። ከ230 በሚበልጡ አገሮች ውስጥ የሚገኙና ስፍር ቁጥር ከሌላቸው ቋንቋዎችና ባሕሎች የተውጣጡ ቢሆኑም እርስ በርሳቸው ሰላም አላቸው። ኢየሱስ በመጀመሪያው መቶ ዘመን ለደቀ መዛሙርቱ “እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ፣ ደቀ መዛሙርቴ እንደሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ” ሲል ለደቀ መዛሙርቱ የተናገራቸው ቃላት በእነርሱ ላይ ዘመናዊ ፍጻሜያቸውን አግኝተዋል። (ዮሐንስ 13:​35) ዛሬ ያሉ ክርስቲያኖች “ሰላም ፈጣሪዎች” ናቸው። (ማቴዎስ 5:​9 የአዲሲቱ ዓለም ትርጉም የግርጌ ማስታወሻ) ‘ሰላምን ይሻሉ፣ ይከተሉትማል።’ (1 ጴጥሮስ 3:​11) ‘የሰላም አምላክ’ የሆነው ይሖዋ ይደግፋቸዋል።​—⁠ሮሜ 15:​33

27 ሰላም ፈጣሪዎች መሆንን የተማሩ ሰዎችን በተመለከተ ግሩም ምሳሌዎችን መጥቀስ ይቻላል። አንድ ወጣት ቀደም ሲል የነበረውን ሕይወት በተመለከተ እንደሚከተለው ሲል ጽፏል:- “የደረሰብኝ መጥፎ ተሞክሮ ራስን መከላከል እንድማር ምክንያት ሆኖኛል። በሕይወቴም ቁጡና ኃይለኛ ሆንኩ። የሚቀናኝ መደባደብ ነበር። በየዕለቱ በጎረቤቴ ከሚገኙ የተለያዩ ልጆች ጋር እደባደብ ነበር። አንዳንድ ጊዜ በቡጢ፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ በድንጋይና በጠርሙስ ሳይቀር እደባደባለሁ። ያደግሁት በጣም ዓመፀኛ ሆኜ ነበር።” ይሁን እንጂ ከጊዜ በኋላ ‘ወደ ይሖዋ ቤት ተራራ’ እንዲወጣ የቀረበለትን ግብዣ ተቀበለ። የአምላክን መንገድ በመማር ሰላም ወዳድ የአምላክ አገልጋይ ሆኗል።

28. ክርስቲያኖች ሰላምን ለመከተል ምን ማድረግ ይችላሉ?

28 አብዛኞቹ የይሖዋ አገልጋዮች ይህን ዓይነት የዓመፀኛነት አካሄድ የሚከተሉ አልነበሩም። ያም ሆኖ በአንጻራዊ ሁኔታ ቀላል መስለው በሚታዩት ደግነትና ይቅር ባይነት ማሳየትን እንዲሁም ለሌሎች ማሰብን በመሳሰሉት ነገሮች ረገድ ከሌሎች ጋር ባላቸው ግንኙነት ሰላም እንዲሰፍን ለማድረግ ይጥራሉ። ፍጽምና የሌላቸው ሰዎች ቢሆኑም እንኳ “ማንም በባልንጀራው ላይ የሚነቅፈው ነገር ካለው ይቅር ተባባሉ” የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር ሥራ ላይ ለማዋል ይጥራሉ።​—⁠ቆላስይስ 3:​13

የሰላም ተስፋ

29, 30. የምድር የወደፊት ዕጣ ምንድን ነው?

29 ይሖዋ በዚህ ‘የዘመን ፍጻሜ’ አስገራሚ ሥራ አከናውኗል። ከሁሉም ብሔራት እርሱን ለማገልገል የሚፈልጉ ሰዎችን አሰባስቧል። በእርሱ የሰላም መንገድ መጓዝንም አስተምሯቸዋል። ከመጪው ‘ታላቅ መከራ’ በሕይወት የሚያልፉትና ጦርነት ለዘላለም ወደሚወገድበት አዲስ ዓለም የሚገቡት ሰዎች እነዚህ ናቸው።​—⁠ራእይ 7:​14

30 ከዚያ በኋላ ሰይፍ ማለትም የጦር መሣሪያ አይኖርም። መዝሙራዊው “የእግዚአብሔርን ሥራ፣ በምድር ያደረገውንም ተአምራት እንድታዩ ኑ። እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ጦርነትን ይሽራል፤ ቀስትን ይሰብራል፣ ጦርንም ይቆርጣል፣ በእሳትም ጋሻን ያቃጥላል” ሲል ጽፏል። (መዝሙር 46:​8, 9) ከዚህ ተስፋ አንጻር ሲታይ ኢሳይያስ “እናንተ የያዕቆብ ቤት ሆይ፣ ኑ፣ በእግዚአብሔር ብርሃን እንሂድ” ሲል የሰጠው ጥብቅ ማሳሰቢያ ዛሬም ከዚያ ዘመን ያልተናነሰ ጠቀሜታ አለው። (ኢሳይያስ 2:​5) አዎን፣ የይሖዋ አምላክ ብርሃን ዛሬ መንገዳችንን እንዲያበራልን እንፍቀድለት። ይህን ካደረግን ለዘላለም በመንገዱ መሄድ እንችላለን።​—⁠ሚክያስ 4:​5

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.6 በይሖዋ ምሥክሮች ከተዘጋጀው ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? የተባለ መጽሐፍ “የምንኖረው ‘በመጨረሻው ዘመን’ ውስጥ ነው?” የሚለውን 9ኛ ምዕራፍ ተመልከት።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]