በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋን በመተማመን ተጠባበቁ

ይሖዋን በመተማመን ተጠባበቁ

ምዕራፍ ሃያ ሦስት

ይሖዋን በመተማመን ተጠባበቁ

ኢሳይያስ 30:​1-​33

1, 2. (ሀ) ኢሳይያስ ምዕራፍ 30 የያዘው ምንድን ነው? (ለ) ቀጥሎ የምንመረምራቸው ጥያቄዎች የትኞቹ ናቸው?

በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 30 ላይ ክፉዎችን በተመለከተ ስለተነገረ ተጨማሪ የፍርድ መልእክት እናነባለን። የሆነ ሆኖ ይህኛው የኢሳይያስ ትንቢት ክፍል የይሖዋን አስደሳች ባሕርያት ጎላ አድርጎ የሚገልጽ ነው። እንዲያውም የይሖዋ ባሕርያት ጉልህ ሆነው ከመቀመጣቸው የተነሣ መገኘቱን ዓይተን የተጽናናን፣ መመሪያ የሚሰጠውን ድምፁን ያዳመጥንና ፈዋሽ የሆነው እጁ የዳሰሰን ያህል ይሰማናል።​—⁠ኢሳይያስ 30:​20, 21, 26

2 ያም ሆኖ ግን የኢሳይያስ አገር ሰዎች ማለትም ከሃዲ የሆኑት የይሁዳ ነዋሪዎች ወደ ይሖዋ ለመመለስ አሻፈረን ብለዋል። ይልቁንም ትምክህታቸውን የጣሉት በሰዎች ላይ ነው። ስለዚህ ነገር ይሖዋ ምን ይሰማዋል? ይህኛው የኢሳይያስ ትንቢት ክፍል ዛሬ ያሉት ክርስቲያኖች ይሖዋን በመተማመን እንዲጠባበቁ የሚረዳቸውስ እንዴት ነው? (ኢሳይያስ 30:​18) እስቲ እንመልከት።

ለአደጋ የሚዳርግ የሞኝነት አካሄድ

3. ይሖዋ ያጋለጠው የትኛውን ሴራ ነው?

3 ለተወሰነ ጊዜ የይሁዳ መሪዎች በአሦር ቀንበር ሥር ላለመውደቅ በምሥጢር ሲያሴሩ ቆይተዋል። ይሁን እንጂ ይሖዋ ይህን ነገር ይመለከት ነበር። አሁን ይህን ሴራቸውን ያጋልጣል:- “ለዓመፀኞች ልጆች ወዮላቸው! ይላል እግዚአብሔር፤ ከእኔ ዘንድ ያልሆነን ምክር ይመክራሉ፣ ኃጢአትንም በኃጢአት ላይ ይጨምሩ ዘንድ ከመንፈሴ ዘንድ ያልሆነውን ቃል ኪዳን ያደርጋሉ። . . . ወደ ግብጽ እንዲወርዱ ይሄዳሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 30:​1, 2

4. ዓመፀኛ የሆነው የአምላክ ሕዝብ ግብጽን በአምላክ ቦታ ያስቀመጠው እንዴት ነው?

4 እነዚህ ሴረኛ መሪዎች ዕቅዳቸው እንደተጋለጠ ሲያውቁ ምንኛ ይደነግጡ ይሆን! ከግብጽ ጋር ጥምረት ለመፍጠር ወደዚያ መጓዝ አሦርን የሚያስቆጣ እርምጃ ብቻ ሳይሆን በይሖዋ አምላክ ላይም ማመፅ ነው። በንጉሥ ዳዊት ዘመን ብሔሩ መሸሸጊያ ያደረገው ይሖዋን ሲሆን ‘በክንፎቹም ጥላ ታምነዋል።’ (መዝሙር 27:​1፤ 36:​7) አሁን ግን ‘የፈርዖንን ኃይል’ መሸሸጊያቸው ‘የግብጽንም ጥላ መታመኛቸው አድርገዋል።’ (ኢሳይያስ 30:​2) ግብጽን በአምላክ ቦታ አስቀምጠዋል! እንዴት ያለ ከዳተኝነት ነው!​—⁠ኢሳይያስ 30:​3-5ን አንብብ።

5, 6. (ሀ) ከግብጽ ጋር ኅብረት መፍጠር ለአደጋ የሚዳርግ ስህተት የሆነው ለምንድን ነው? (ለ) አሁን ወደ ግብጽ የሚደረገው ጉዞ ሞኝነት እንደሆነ የሚያሳየው ከዚህ ቀደም የአምላክ ሕዝብ ያደረገው የትኛው ጉዞ ነው?

5 ኢሳይያስ ወደ ግብጽ የሚደረገው ጉዞ እንዲሁ ድንገተኛ ጉብኝት ይሆን ለሚለው ጥያቄ መልስ መስጠት የፈለገ ይመስል የሚከተለውን ተጨማሪ ዝርዝር መግለጫ ሰጥቷል:- “በደቡብ ስላሉ እንስሶች የተነገረ ሸክም። ተባትና እንስት አንበሳ እፉኝትም ነዘር እባብም በሚወጡባት በመከራና በጭንቀት ምድር በኩል ብልጥግናቸውን በአህዮች ጫንቃ ላይ መዛግብቶቻቸውንም በግመሎች ሻኛ ላይ እየጫኑ . . . ይሄዳሉ።” (ኢሳይያስ 30:​6) በግልጽ ለመረዳት እንደሚቻለው ጉዞው በሚገባ የታሰበበት ነው። ተጓዦቹ ውድ የሆኑ ሸቀጦች የጫኑባቸውን ግመሎቻቸውንና አህዮቻቸውን አሰልፈው የሚያገሱ አናብስትና መርዘኛ እባቦች በሞሉበት ምድረ በዳ አቋርጠው ወደ ግብጽ ይጓዛሉ። በመጨረሻም ተጓዦቹ ያሰቡት ቦታ ደርሰው የያዙትን ውድ ሀብት ለግብጻውያኑ ያስረክባሉ። በእነርሱ ቤት የግብጽን ከለላ በዋጋ መግዛታቸው ነው። ይሁን እንጂ ይሖዋ እንዲህ ይላል:- “ወደማይጠቅሙአቸው ሕዝብ ይሄዳሉ። የግብጽ እርዳታ ከንቱና ምናምን ነው፤ ስለዚህ ስሙን:- በቤት የሚቀመጥ ረዓብ ብዬ ጠርቼዋለሁ።” (ኢሳይያስ 30:​6, 7) “ረዓብ” የተባለው ‘የባሕር ውስጥ ዘንዶ’ ግብጽን ያመለክታል። (ኢሳይያስ 51:​9, 10) የማትሰጠው ዓይነት የተስፋ ቃል የለም። ነገር ግን አንዱንም አትፈጽምም። ይሁዳ ከእርሷ ጋር ወዳጅነት መፍጠሯ ለጥፋት የሚዳርግ ከባድ ስህተት ነው።

6 ኢሳይያስ ስለ መልእክተኞቹ ጉዞ ሲገልጽ አድማጮቹ በሙሴ ዘመን የተደረገውን ተመሳሳይ ጉዞ ያስታውሱ ይሆናል። የቀድሞ አባቶቻቸው በዚሁ ‘የሚያስፈራ ምድረ በዳ’ ተጉዘዋል። (ዘዳግም 8:​14-16) ይሁን እንጂ በሙሴ ዘመን እስራኤላውያን በዚህ መንገድ የተጓዙት ከግብጽ ባርነት ነፃ በወጡ ጊዜ ነበር። አሁን ግን መልእክተኞቹ ወደ ግብጽ የሚሄዱት የእነርሱ ተገዥ ለመሆን ነው። እንዴት ያለ ሞኝነት ነው! እኛም መንፈሳዊ ነፃነታችንን በባርነት በመለወጥ ተመሳሳይ የሆነ የቂልነት ውሳኔ እንዳናደርግ እንጠንቀቅ!​—⁠ከ⁠ገላትያ 5:​1 ጋር አወዳድር።

የነቢዩ መልእክት የገጠመው ተቃውሞ

7. ይሖዋ ለይሁዳ የሰጠውን ማስጠንቀቂያ ኢሳይያስ እንዲጽፈው ያደረገው ለምንድን ነው?

7 ኢሳይያስ የተናገረውን መልእክት “ለሚመጣውም ዘመን ለዘላለም እንዲሆን” በጽሑፍ እንዲያሰፍረው ይሖዋ ነግሮታል። (ኢሳይያስ 30:​8) ይሖዋ በእርሱ መታመንን ትተው ከሰዎች ጋር ማበርን በመረጡ ሰዎች አለመደሰቱ ዛሬ ያለውን የእኛን ትውልድ ጨምሮ ወደፊት ለሚመጡት ትውልዶች ትምህርት እንዲሆን ሲባል ተመዝግቦ መቀመጥ አለበት። (2 ጴጥሮስ 3:​1-4) ይሁን እንጂ በጽሑፍ መስፈሩ በወቅቱም አስፈላጊ የሆነበት ምክንያት ነበር። “ዓመፀኛ ወገንና የእግዚአብሔርን ሕግ ለመስማት የማይወድዱ የሐሰት ልጆች ናቸውና።” (ኢሳይያስ 30:​9) ሕዝቡ የአምላክን ምክር ችላ ብሎ ነበር። በመሆኑም ከጊዜ በኋላ ተገቢው ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው እንደነበር እንዳይክዱ ተጽፎ መቀመጥ ነበረበት።​—⁠ምሳሌ 28:​9፤ ኢሳይያስ 8:​1, 2

8, 9. (ሀ) የይሁዳ መሪዎች የይሖዋን ነቢያት ለማበላሸት የሞከሩት በምን መንገድ ነው? (ለ) ኢሳይያስ እንደማይፈራ ያሳየው እንዴት ነው?

8 ቀጥሎ ደግሞ ኢሳይያስ የሕዝቡን የዓመፀኝነት ዝንባሌ የሚያሳይ ምሳሌ ጠቅሷል። “ባለ ራእዮችን:- አትመልከቱ ይላሉ፣ ነቢያትንም:- ጣፋጩንና አታላዩን ነገር እንጂ ቅኑን ነገር አትንገሩን።” (ኢሳይያስ 30:​10) የይሁዳ መሪዎች የታመኑት ነቢያት ‘ቅን የሆነውን’ ማለትም ትክክለኛውን ነገር መናገራቸውን አቁመው “ጣፋጩንና አታላዩን” ወይም ሐሰት የሆነውን ነገር እንዲነግሯቸው በማዘዝ ጆሮአቸውን እንዲያክኩላቸው ፈልገዋል። እነርሱ የሚፈልጉት የሚያወድሳቸውን እንጂ የሚያወግዛቸውን ሰው አልነበረም። እንደ እነርሱ አስተሳሰብ ከሆነ የሚጥማቸውን ነገር የማይናገር ማንኛውም ነቢይ ‘ከመንገድ ፈቀቅ ማለትና ከጎዳናውም ዘወር ማለት’ አለበት። (ኢሳይያስ 30:​11ሀ) አንድም ለእነርሱ ጆሮ የሚጥም ነገር መናገር አለዚያም ጨርሶ ስብከቱን ማቆም አለበት!

9 የኢሳይያስ ተቃዋሚዎች “የእስራኤልንም ቅዱስ ከእኛ ዘንድ አስወግዱ” ሲሉ አጥብቀው ጠይቀዋል። (ኢሳይያስ 30:​11ለ) ኢሳይያስ ‘የእስራኤል ቅዱስ’ በሆነው አምላክ በይሖዋ ስም መናገሩን ያቁም ማለታቸው ነው! ከፍ ያለው የይሖዋ የአቋም ደረጃ እነርሱ ያሉበትን የረከሰ ሁኔታ የሚያጋልጥባቸው በመሆኑ ይህ የይሖዋ ማዕረግ ራሱ ያስቆጣቸዋል። ኢሳይያስ ምን ምላሽ ይሰጥ ይሆን? “የእስራኤል ቅዱስ እንዲህ ይላል” በማለት ተናግሯቸዋል። (ኢሳይያስ 30:​12ሀ) ኢሳይያስ ያለምንም ማመንታት ተቃዋሚዎቹ ለመስማት የጠሏቸውን ቃላት በመጠቀም ተናግሯል። ምንም አልፈራም። ለእኛ እንዴት ያለ ግሩም ምሳሌ ነው! ክርስቲያኖች የአምላክን መልእክት በማወጅ ረገድ ፈጽሞ አቋማቸውን ማላላት አይገባቸውም። (ሥራ 5:​27-29) እንደ ኢሳይያስ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል’ በማለት ማወጃቸውን ይቀጥላሉ!

ማመፅ የሚያስከትለው ውጤት

10, 11. የይሁዳ ዓመፅ የሚያስከትለው ውጤት ምን ይሆናል?

10 ይሁዳ የአምላክን ቃል አሻፈረኝ ብላለች፣ በሐሰት እንዲሁም “ጠማማ” በሆነ ነገር ታምናለች። (ኢሳይያስ 30:​12ለ) ውጤቱ ምን ይሆናል? ይሖዋ ከሕልውና ውጭ ያደርጋቸዋል እንጂ እነርሱ እንደተመኙት ሁኔታውን ችላ ብሎ አያልፈውም! ኢሳይያስ በምሳሌ በማስደገፍ እንዳስረዳው ይህ መጠነ ሰፊ ጥፋት የሚመጣባቸው በድንገት ይሆናል። የሕዝቡ ዓመፀኝነት “አዘብዝቦ ለመፍረስ እንደ ቀረበ፣ አፈራረሱም ፈጥኖ ድንገት እንደሚመጣ እንደ ረጅም ቅጥር” ይሆናል። (ኢሳይያስ 30:​13) ከፍ ብሎ የተሠራ አንድ ቅጥር ማዘብዘብ ከጀመረ የኋላ ኋላ ቅጥሩን እንዳለ ይዞት እንደሚወድቅ ሁሉ በኢሳይያስ ዘመን የነበሩት ሰዎች እየጨመረ የሚሄድ ዓመፅም ብሔሩ እንዲጠፋ ምክንያት ይሆናል።

11 ኢሳይያስ ሌላ ምሳሌ በመጠቀም መጪው ጥፋት ሙሉ በሙሉ የሚያወድም እንደሆነ ይገልጻል:- “የሸክለኛ ማድጋ እንደሚሰበር ይሰብረዋል፣ ሳይራራም ያደቅቀዋል፤ ከስባሪውም እሳት ከማንደጃ የሚወስዱበት ወይም ውኃ ከጉድጓድ የሚቀዱበት ገል አይገኝም።” (ኢሳይያስ 30:​14) በይሁዳ ላይ የሚደርሰው ጥፋት ሙሉ በሙሉ የሚያወድም ከመሆኑ የተነሣ ዋጋ ያለው አንድም ነገር አይተርፍም። ከምድጃ ላይ እሳት የሚጫርበት ወይም ከጉድጓድ ውኃ የሚጨለፍበት ገል እንኳ አይገኝም። መጨረሻቸው ምንኛ የሚያሳፍር ይሆናል! ዛሬም በእውነተኛው አምልኮ ላይ በሚያምፁ ሰዎች ላይ የሚመጣው ጥፋት ከዚህ ባልተለየ መልኩ ድንገተኛና ሙሉ በሙሉ የሚያወድም ይሆናል።​—⁠ዕብራውያን 6:​4-8፤ 2 ጴጥሮስ 2:​1

ይሖዋ ያቀረበውን ጥሪ አልተቀበሉም

12. የይሁዳ ሰዎች ከጥፋት ማምለጥ የሚችሉት እንዴት ነው?

12 ሆኖም ኢሳይያስ መልእክቱን ይነግራቸው የነበሩት ሰዎች ከጥፋቱ መዳን የሚችሉበት መንገድ አልነበረም ማለት አይደለም። መዳን የሚችሉበት መንገድ ነበረ። ነቢዩ ይህን ጉዳይ ሲያብራራ እንዲህ ብሏል:- “የእስራኤል ቅዱስ፣ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና:- በመመለስና በማረፍ ትድናላችሁ፤ በጸጥታና በመታመን ኃይል ይሆንላችኋል።” (ኢሳይያስ 30:​15ሀ) ሕዝቡ “በማረፍ” ወይም በሌላ አባባል ከሰብዓዊ ወገኖች ጋር አብረው የመዳን ዋስትና ለማግኘት ከመጣር በመታቀብ እንዲሁም “በፀጥታ በመታመን” ማለትም ለፍርሃት እጃቸውን ሳይሰጡ በአምላክ የማዳን ኃይል እንደሚታመኑ በማረጋገጥ እምነት እንዳላቸው ካሳዩ ይሖዋ እነርሱን ለማዳን ዝግጁ ነው። ኢሳይያስ “እናንተ ግን እምቢ አላችሁ” ብሏቸዋል።​—⁠ኢሳይያስ 30:​15ለ የ1980 ትርጉም

13. የይሁዳ መሪዎች ትምክህታቸውን የጣሉት በምን ነገር ላይ ነበር? እንዲህ ያለውስ ትምክህት ተገቢ ነውን?

13 ከዚያም ኢሳይያስ እንዲህ በማለት ያብራራል:- “ነገር ግን:- በፈረስ ላይ ተቀምጠን እንሸሻለን እንጂ እንዲህ አይሆንም አላችሁ፣ ስለዚህም ትሸሻላችሁ፤ ደግሞም:- በፈጣን ፈረስ ላይ እንቀመጣለን አላችሁ፣ ስለዚህም የሚያሳድዱአችሁ ፈጣኖች ይሆናሉ።” (ኢሳይያስ 30:​16) የይሁዳ ሰዎች መዳናቸው በይሖዋ ላይ ሳይሆን በፈጣን ፈረሶች የተመካ እንደሆነ አድርገው አስበዋል። (ዘዳግም 17:​16፤ ምሳሌ 21:​31) ይሁን እንጂ ነቢዩ ጠላቶቻቸው ስለሚያገኟቸው ይህ ትምክህታቸው ሕልም ብቻ እንደሆነ በመናገር መልስ ሰጥቷል። ቁጥራቸው የቱንም ያህል ትልቅ ቢሆን የሚያመጣው ለውጥ የለም። “ከአንድ ሰው ዛቻ የተነሣ ሺህ ሰዎች ይሸሻሉ፤ . . . ከአምስት ሰዎች ዛቻ የተነሣ ትሸሻላችሁ።” (ኢሳይያስ 30:​17) የይሁዳ ሠራዊት ሽብር ላይ ስለሚወድቅ እፍኝ በማይሞሉ ጠላቶቻቸው ጩኸት ይሸሻል። * በመጨረሻ “በተራራ ራስ ላይ እንዳለ ምሰሶ፣ በኮረብታም ላይ እንዳለ ምልክት” ሆነው የሚተርፉት ጥቂት ቀሪዎች ብቻ ይሆናሉ። (ኢሳይያስ 30:​17) ኢየሩሳሌም በ607 ከዘአበ ስትጠፋ ልክ በትንቢቱ መሠረት የተረፉት ጥቂት ቀሪዎች ብቻ ናቸው።​—⁠ኤርምያስ 25:​8-11

በኩነኔ መሐል የተገኘ ማጽናኛ

14, 15. በ⁠ኢሳይያስ 30:​18 ላይ የሚገኙት ቃላት ለጥንቶቹ የይሁዳ ነዋሪዎችም ሆነ ዛሬ ላሉት እውነተኛ ክርስቲያኖች ማጽናኛ የሚሰጡት እንዴት ነው?

14 እነዚህ ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገቡ ቃላት በኢሳይያስ አድማጮች ጆሮ እያቃጨሉ እያለ የመልእክቱ ቃና ይቀየራል። የአደጋው ስጋት በበረከት ተስፋ ይተካል። “እግዚአብሔርም የፍርድ አምላክ ነውና ስለዚህ እግዚአብሔር ይራራላችሁ ዘንድ ይታገሣል፣ ይምራችሁም ዘንድ ከፍ ከፍ ይላል [“ይነሣል፣” NW]፤ እርሱን በመተማመን የሚጠባበቁ ሁሉ ብፁዓን [“ደስተኞች፣” NW] ናቸው።” (ኢሳይያስ 30:​18) እንዴት የሚያበረታታ አነጋገር ነው! ይሖዋ ልጆቹን ለመርዳት የሚጓጓ ርኅሩኅ አባት ነው። ምሕረት ሲያሳይ ደስ ይለዋል።​—⁠መዝሙር 103:​13፤ ኢሳይያስ 55:​7

15 እነዚህ ተስፋ ሰጪ ቃላት በ607 ከዘአበ በኢየሩሳሌም ላይ ከደረሰው ጥፋት እንዲተርፉ አምላክ ምሕረቱን ላሳያቸው የአይሁድ ቀሪዎችና በ537 ከዘአበ ወደ ተስፋይቱ ምድር ለተመለሱት ጥቂቶች ይሠራሉ። ይሁን እንጂ ነቢዩ የተናገራቸው ቃላት ዛሬ ያሉትን ክርስቲያኖችም የሚያጽናኑ ናቸው። ይሖዋ ክፉውን ዓለም ለማጥፋት ስለ እኛ ‘እንደሚነሳ’ የሚያስታውሱን ናቸው። የታመኑ አምላኪዎች “የፍርድ አምላክ” የሆነው ይሖዋ ፍትሕ ከሚጠይቀው በላይ የሰይጣን ዓለም ዕድሜ በአንድ ቀን እንኳ እንዲራዘም እንደማይፈቅድለት እርግጠኞች ናቸው። በመሆኑም ‘እርሱን በመተማመን የሚጠባበቁ’ ደስተኞች የሚሆኑበት ብዙ ምክንያት አላቸው።

ይሖዋ ለጸሎታቸው መልስ በመስጠት ሕዝቡን ያጽናናል

16. ይሖዋ ተስፋ የቆረጡትን የሚያጽናናው እንዴት ነው?

16 ይሁንና አንዳንዶች መዳናቸው እንዳሰቡት ቶሎ ባለመምጣቱ የተስፋ መቁረጥ ስሜት ያድርባቸው ይሆናል። (ምሳሌ 13:​12፤ 2 ጴጥሮስ 3:​9) የይሖዋን ለየት ያለ ባሕርይ ጎላ አድርገው ከሚገልጹት ከሚከተሉት የኢሳይያስ ቃላት ማጽናኛ እንዲያገኙ ምኞታችን ነው። “በኢየሩሳሌም ውስጥ በጽዮን የምትኖሩ ሕዝብ ሆይ፣ ከእንግዲህ ወዲህ አታለቅስም፤ በጩኸትም ድምፅ ይራራልሃል፣ በሰማህም ጊዜ ይመልስልሃል።” (ኢሳይያስ 30:​19) ኢሳይያስ ቁጥር 18 ላይ ‘እናንተ’ እያለ ሲናገር ቆይቶ ቁጥር 19 ላይ ‘አንተ’ በማለት ፍቅራዊ በሆነ መንገድ ተናግሯል። ይሖዋ የተጨነቁትን ሰዎች ሲያጽናና የእያንዳንዱን ሰው ጉዳይ በግለሰብ ደረጃ ይመለከታል። አባት እንደመሆኑ መጠን ተስፋ የቆረጠ ልጁን ‘ለምን እንደ ወንድምህ ብርቱ አትሆንም’ አይለውም። (ገላትያ 6:​4) ይልቁንም እያንዳንዳቸውን በጥሞና ያዳምጣል። እንዲያውም ‘መልስ የሚሰጠው እንደሰማ ወዲያውኑ ነው።’ እንዴት የሚያጽናና ነው! ተስፋ የቆረጡ ሰዎች ወደ ይሖዋ በመጸለይ በእጅጉ ብርታት ሊያገኙ ይችላሉ።​—⁠መዝሙር 65:​2

የአምላክን ቃል እያነበባችሁ መንገዱን የሚመራችሁን ድምፅ ተከተሉ

17, 18. በአስቸጋሪ ጊዜያት ሳይቀር ይሖዋ መመሪያ የሚሰጠው እንዴት ነው?

17 ኢሳይያስ ንግግሩን በመቀጠል አድማጮቹን መከራ እንደሚመጣ ያስታውሳቸዋል። ሕዝቡ “የጭንቀትን እንጀራና የመከራን ውኃ” ይቀበላሉ። (ኢሳይያስ 30:​20ሀ) በከበባው ወቅት የሚደርስባቸው መከራና ጭቆና የእንጀራና የውኃ ያህል የተለመደ ነገር ይሆናል። ያም ሆኖ ግን ይሖዋ ቅን ልብ ያላቸውን ሰዎች ለመታደግ ዝግጁ ነው። [“ታላቅ፣” NW] አስተማሪህ እንግዲህ ከአንተ አይሰወርም፤ ዓይኖችህ ግን [“ታላቅ፣” NW] አስተማሪህን ያያሉ፣ ወደ ቀኝም ወደ ግራም ፈቀቅ ብትል ጆሮችህ በኋላህ:- መንገዱ ይህች ናት በእርስዋም ሂድ የሚለውን ቃል ይሰማሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 30:​20ለ, 21 *

18 ይሖዋ “ታላቅ አስተማሪ” ነው። በአስተማሪነቱ አቻ የለውም። ይሁንና ሰዎች እርሱን ‘ሊያዩትና’ ‘ሊሰሙት’ የሚችሉት እንዴት ነው? ይሖዋ ቃላቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተመዘገበው ነቢያቱ አማካኝነት ራሱን ይገልጣል። (አሞጽ 3:​6, 7) ዛሬ የታመኑ አምላኪዎች መጽሐፍ ቅዱስን ሲያነብቡ የአምላክ አባታዊ ድምፅ የሚሄዱበትን መንገድ የሚነግራቸውና በዚያ መንገድ መመላለስ ይችሉ ዘንድ ጎዳናቸውን እንዲያስተካክሉ አጥብቆ የሚያሳስባቸው ያህል ነው። ይሖዋ በመጽሐፍ ቅዱስ ገጾችና “ታማኝና ልባም ባሪያ” በሚያዘጋጃቸው መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጽሑፎች አማካኝነት ሲናገር እያንዳንዱ ክርስቲያን በጥንቃቄ ማዳመጥ ይኖርበታል። (ማቴዎስ 24:​45-47) እያንዳንዱ ሰው ‘ሕይወቱ ነውና’ መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ መትጋት አለበት።​—⁠ዘዳግም 32:​46, 47፤ ኢሳይያስ 48:​17

ወደፊት የሚገኙትን በረከቶች አስቡ

19, 20. የታላቁን አስተማሪ ድምፅ የሚታዘዙ ሰዎች ምን በረከት ተዘጋጅቶላቸዋል?

19 ለታላቁ አስተማሪ ድምፅ ምላሽ የሚሰጡ ሰዎች የተቀረጹ ምስሎቻቸውን እንደ አስጸያፊ ነገር በመቁጠር ያስወግዷቸዋል። (ኢሳይያስ 30:​22ን አንብብ።) ከዚያ በኋላ ጥሩ ምላሽ የሰጡት ሰዎች ግሩም በረከቶችን ያገኛሉ። እነዚህ በረከቶች በኢሳይያስ 30:​23-26 ላይ የተገለጹ ሲሆን አይሁዳውያን ቀሪዎች በ537 ከዘአበ ከምርኮ ሲመለሱ የመጀመሪያ ፍጻሜያቸውን ካገኙት አስደሳች የመልሶ መቋቋም ትንቢቶች ጋር የተያያዙ ናቸው። በዛሬው ጊዜ ይህ ትንቢት መሲሁ አሁን ባለው መንፈሳዊ ገነትም ሆነ ወደፊት ቃል በቃል በምትመጣው ገነት ውስጥ የሚያመጣውን ድንቅ በረከት እንድናስተውል ይረዳናል።

20 “በምድርም ለተዘራው ዘርህ ዝናብ ይሰጣል፣ ከምድርም ፍሬ የሚወጣ እንጀራ ወፍራምና ብዙ [“የሰባና በቅባት የራሰ፣” NW] ይሆናል። በዚያም ቀን ከብቶችህ በሰፊ መስክ ይሰማራሉ፤ መሬትንም የሚያርሱ በሬዎችና አህዮች በመንሽና በወንፊት የነጻውን ጨው ጨው የሚለውን ገፈራ ይበላሉ።” (ኢሳይያስ 30:​23, 24) ዕለታዊ ምግባቸው “የሰባና በቅባት የራሰ” እንጀራ ማለትም ገንቢ በሆኑ ንጥረ ነገሮች የዳበረ ምግብ ይሆናል። የምድሪቱ ፍሬ እጅግ የተትረፈረፈ ከመሆኑ የተነሣ እንስሳቱ ሳይቀሩ እንደ ልብ ይመገባሉ። ከብቶቹ የሚመገቡት አልፎ አልፎ ብቻ ያገኙ የነበረውን “ጨው ጨው የሚለውን ገፈራ” ይሆናል። ለሰው ምግብነት ለሚያገለግል እህል እንደሚደረገው ሁሉ ይህ የከብቶች ምግብም ‘በመንሽ ተበጥሯል።’ ኢሳይያስ የታመኑ ሆነው በተገኙት ሰዎች ላይ ይሖዋ የሚያፈስሰው በረከት እጅግ የተትረፈረፈ እንደሚሆን በምሳሌ ለማስረዳት የሰጠው ዝርዝር መግለጫ እንዴት ደስ የሚል ነው!

21. የሚመጣው በረከት ምን ያህል የተሟላ እንደሆነ ግለጽ።

21 “በረጅሙ ተራራ ሁሉ ከፍ ባለውም ኮረብታ ሁሉ ላይ ወንዞችና የውኃ ፈሳሾች ይሆናሉ።” (ኢሳይያስ 30:​25) * ኢሳይያስ የይሖዋ በረከት ምን ያህል የተሟላ እንደሆነ ጎላ አድርጎ ለማሳየት ተስማሚ መግለጫ ተጠቅሟል። የውኃ እጥረት አይኖርም። ውድ ነገር የሆነው ውኃ በረባዳማ መሬቶች ላይ ብቻ ሳይሆን በየተራራው ሁሉ ‘በረጅሙ ተራራና ከፍ ባለው ኮረብታ ሁሉ’ ላይ ሳይቀር ይፈስሳል። አዎን፣ ረሃብ የተረሳ ነገር ይሆናል። (መዝሙር 72:​16) ከዚያም ነቢዩ ትኩረቱን ከተራራም በላይ ከፍ ወዳሉ ነገሮች ያዞራል። “እግዚአብሔርም የሕዝቡን ስብራት በጠገነ ዕለት፣ መቅሠፍቱ የቈሰለውንም በፈወሰ ዕለት፣ የጨረቃ ብርሃን እንደ ፀሐይ ብርሃን፣ የፀሐይም ብርሃን እንደ ሰባት ቀን ብርሃን ሰባት እጥፍ ይሆናል።” (ኢሳይያስ 30:​26) ለዚህ ድንቅ ትንቢት ይህ እንዴት ያለ አስደሳች መደምደሚያ ነው! የአምላክ ክብር በሙሉ ኃይሉ ደማቅ ሆኖ ይበራል። ለታመኑት የአምላክ አገልጋዮች የተዘጋጁት በረከቶች ከዚያ ቀደም ከታየው ሁሉ በበለጠ መጠን ሰባት እጥፍ ሆነው ይፈስሳሉ።

ፍርድና ደስታ

22. የታመኑት ሰዎች ከሚያገኙት በረከት በተቃራኒ ይሖዋ ለክፉዎች ምን አዘጋጅቶላቸዋል?

22 ኢሳይያስ መልእክቱን የሚናገርበት የድምፅ ቃና እንደገና ይቀየራል። የአድማጮቹን ትኩረት ማግኘት የፈለገ ይመስል“እነሆ” በማለት ይጀምራል። “የእግዚአብሔር ስም ከሚነድድ ቁጣ ከሚትጐለጐልም ጢስ ጋር ከሩቅ ይመጣል፤ ከንፈሮቹም ቁጣን የሞሉ ናቸው፣ ምላሱም እንደምትበላ እሳት ናት።” (ኢሳይያስ 30:​27) እስከዚህ ጊዜ ድረስ ይሖዋ የሕዝቡ ጠላቶች የራሳቸውን ጎዳና ሲከተሉ እጁን ጣልቃ ሳያስገባ ቆይቷል። አሁን ግን ወደፊት እንደሚገሰግስ ወዠብ ፍርዱን ለማስፈጸም ወደ እነርሱ እየተጠጋ ነው። “እስትንፋሱም አሕዛብን በአጥፊ ወንፊት ሊነፋቸው እንደሚያጥለቀልቅ እስከ አንገትም እንደሚደርስ ወንዝ ነው፣ በሕዝብም መንጋጋ የሚያስት ልጓም ይሆናል።” (ኢሳይያስ 30:​28) የአምላክ ሕዝብ ጠላቶች ‘በሚያጥለቀልቅ ወንዝ’ ተከብበው ‘በወንፊት እንደሚነፉ’ ያህል ይወዘወዛሉ እንዲሁም ‘በልጓም’ ይጎተታሉ። አዎን፣ ይጠፋሉ።

23. ዛሬ ላሉት ክርስቲያኖች “የልብ ደስታ” ምክንያት የሚሆነው ነገር ምንድን ነው?

23 ኢሳይያስ አንድ ቀን ወደ ምድራቸው ስለሚመለሱት የታመኑ አምላኪዎች አስደሳች ሁኔታ ሲገልጽ እንደገና የንግግሩን ቃና ይለውጣል። “ዝማሬ በተቀደሰች የዐውደ ዓመት ሌሊት እንደሚሆን ዝማሬ ይሆንላችኋል፤ ወደ እግዚአብሔርም ተራራ ወደ እስራኤል አምባ ይመጣ ዘንድ እንቢልታ ይዞ እንደሚሄድ ሰው የልብ ደስታ ይሆንላችኋል።” (ኢሳይያስ 30:​29) በዛሬው ጊዜ ያሉ እውነተኛ ክርስቲያኖችም በሰይጣን ዓለም ላይ ስለሚወሰደው የፍርድ እርምጃ፣ ‘የመዳናችን አምባ’ የሆነው ይሖዋ ለእነርሱ ስለሚያደርግላቸው ጥበቃ እንዲሁም ስለ መጪው የመንግሥቱ በረከቶች ሲያስቡ በተመሳሳይ ‘የልብ ደስታ” ይሞላሉ።​—⁠መዝሙር 95:​1 NW

24, 25. የኢሳይያስ ትንቢት በአሦር ላይ ስለሚደርሰው ፍርድ ጎላ አድርጎ የሚገልጸው እንዴት ነው?

24 ኢሳይያስ ስለዚህ ደስታ ከገለጸ በኋላ ስለ ፍርድ መልእክት ወደሚናገረው ጭብጥ መለስ በማለት የአምላክ ቁጣ የሚወርደው በማን ላይ እንደሆነ ይገልጻል። “እግዚአብሔርም ክቡር ድምፁን ያሰማል፣ የክንዱንም መውረድ በሚነድድ ቁጣውና በምትበላ እሳት ነበልባል በዐውሎ ነፋስም በወጨፎም በበረዶ ጠጠርም ይገልጣል። አሦርም በበትር ከመታው ከእግዚአብሔር ድምፅ የተነሣ ይደነግጣል።” (ኢሳይያስ 30:​30, 31) ኢሳይያስ በዚህ ሥዕላዊ መግለጫ አማካኝነት አምላክ በአሦር ላይ የሚወስደውን የፍርድ እርምጃ ጠበቅ አድርጎ ገልጿል። አሦር በአምላክ ፊት ቆሞ ‘የክንዱን መውረድ’ እያየ በፍርሃት እንደሚርድ ያህል ይሆናል።

25 ነቢዩ እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “እግዚአብሔር በላዩ የሚያወርድበት የታዘዘበቱ የበትር ድብደባ ሁሉ በከበሮና በመሰንቆ ይሆናል፤ በጦርነትም ክንዱን አንሥቶ ይዋጋቸዋል። ከቀድሞም ጀምሮ የማቃጠያ ስፍራ [“ቶፌት፣” NW] ተዘጋጅታለች፣ ለንጉሥም ተበጅታለች፤ ጥልቅና ሰፊም አድርጎአታል፤ እሳትና ብዙ ማገዶ ተከምሮአል፤ የእግዚአብሔርም እስትንፋስ እንደ ዲን ፈሳሽ ያቃጥለዋል።” (ኢሳይያስ 30:​32, 33) በሄኖም ሸለቆ የምትገኘው ቶፌት እዚህ ላይ የተጠቀሰችው በእሳት እንደምትቃጠል ምሳሌያዊ ቦታ ሆና ነው። ኢሳይያስ የአሦር መጨረሻው ወደዚያ መጣል መሆኑን በመግለጽ በዚህ ብሔር ላይ የሚመጣውን ድንገተኛና ሙሉ በሙሉ የሚያወድም ጥፋት ጎላ አድርጎ ገልጿል።​—⁠ከ⁠2 ነገሥት 23:​10 ጋር አወዳድር።

26. (ሀ) ይሖዋ በአሦር ላይ ያስነገረው ፍርድ በዘመናችን ምን ተፈጻሚነት አለው? (ለ) ዛሬ ያሉ ክርስቲያኖች ይሖዋን በመተማመን የሚጠባበቁት እንዴት ነው?

26 ይህ የፍርድ መልእክት የተነገረው በአሦር ላይ ቢሆንም የኢሳይያስ ትንቢት ያዘለው ትርጉም በዚህ ብቻ የሚወሰን አይደለም። (ሮሜ 15:​4) ይሖዋ ሕዝቡን የሚጨቁኑትን ሰዎች ለማጥለቅለቅ፣ ለመወዝወዝና በልጓም ይዞ ለመጎተት ዳግም ይመጣል። (ሕዝቅኤል 38:​18-23፤ 2 ጴጥሮስ 3:​7፤ ራእይ 19:​11-21) ያ ቀን በቶሎ እንዲመጣ እንመኛለን! እስከዚያው ድረስ ግን ክርስቲያኖች ነፃ የሚወጡበትን ቀን በናፍቆት መጠበቃቸውን ይቀጥላሉ። በኢሳይያስ ምዕራፍ 30 ላይ ተመዝግበው በሚገኙት ግልጽ የሆኑ ቃላት ላይ በማሰላሰል ብርታት ያገኛሉ። እነዚህ ቃላት የአምላክ አገልጋዮች የጸሎትን መብት እንደ ውድ ነገር እንዲመለከቱ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት እንዲተጉ እንዲሁም በመጪው የመንግሥቱ በረከቶች ላይ እንዲያሰላስሉ የሚያበረታቱ ናቸው። (መዝሙር 42:​1, 2፤ ምሳሌ 2:​1-6፤ ሮሜ 12:​12) በዚህ መንገድ የኢሳይያስ ቃላት ሁላችንም ይሖዋን በመተማመን እንድንጠባበቅ ይረዱናል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.13 ይሁዳ የታመነች ሆና ብትገኝ ኖሮ ነገሩ የተገላቢጦሽ ይሆን እንደነበር አትዘንጋ።​—⁠ዘሌዋውያን 26:​7, 8

^ አን.17 መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ይሖዋ “ታላቅ አስተማሪ” ተብሎ የተጠራበት ቦታ ይህ ብቻ ነው።

^ አን.21 የ⁠ኢሳይያስ 30:​25 የቀረው ክፍል “በታላቅም እልቂት ቀን ግንቦች በወደቁ ጊዜ” ይላል። የዚህ ትንቢት የመጀመሪያ ፍጻሜ የባቢሎንን ውድቀት የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። ይህ ደግሞ እስራኤላውያን በ⁠ኢሳይያስ 30:​18-26 ላይ የተጠቀሱትን በረከቶች እንዲያገኙ በር የከፈተ እርምጃ ነው። (አንቀጽ 19ን ተመልከት።) እነዚህ በረከቶች በአዲሱ ዓለም ውስጥ የላቀ ፍጻሜያቸውን እንዲያገኙ በር የሚከፍተውን የአርማጌዶን የጥፋት እርምጃም ሊያመለክት ይችላል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 305 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በሙሴ ዘመን እስራኤላውያን ከግብጽ ሲያመልጡ በኢሳይያስ ዘመን ደግሞ ይሁዳ እርዳታ ፍለጋ ወደ ግብጽ ሄዳለች

[በገጽ 311 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

“ከፍ ባለውም ኮረብታ ሁሉ ላይ ወንዞችና የውኃ ፈሳሾች ይሆናሉ”

[በገጽ 312 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሖዋ “ከሚነድድ ቁጣ ከሚትጎለጎልም ጢስ ጋር” ይመጣል