በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋ ራሳቸውን ከፍ ከፍ የሚያደርጉትን ያዋርዳል

ይሖዋ ራሳቸውን ከፍ ከፍ የሚያደርጉትን ያዋርዳል

ምዕራፍ አምስት

ይሖዋ ራሳቸውን ከፍ ከፍ የሚያደርጉትን ያዋርዳል

ኢሳይያስ 2:​6–4:​1

1, 2. ኢሳይያስ በእርሱ ዘመን ለነበሩት አይሁዳውያን የተናገረው ትንቢታዊ መልእክት የእኛን ትኩረት የሚስብ የሆነው ለምንድን ነው?

ነቢዩ ኢሳይያስ በኢየሩሳሌምና በይሁዳ ሁኔታ በመንገፍገፍ ወደ ይሖዋ አምላክ ዘወር ብሎ እንዲህ ይላል:- “ሕዝብህን የያዕቆብን ቤት ትተሃልና።” (ኢሳይያስ 2:​6ሀ) አምላክ ‘ለራሱ ሕዝብ’ እንዲሆኑለት የመረጣቸውን ሰዎች እንዲተዋቸው ያስገደደው ነገር ምንድን ነው?​—⁠ዘዳግም 14:​2

2 ኢሳይያስ በዘመኑ የነበሩትን አይሁዳውያን ማውገዙ የእኛን ትኩረት በእጅጉ የሚስብ ነገር ነው። ለምን? ምክንያቱም ዛሬ ሕዝበ ክርስትና ያለችበት ሁኔታ ከኢሳይያስ ሕዝብ ጋር የሚመሳሰል ሲሆን ይሖዋ የሚሰጠውም ፍርድ የተለየ አይሆንም። ኢሳይያስ የሚናገረውን በትኩረት መከታተላችን አምላክ ስለሚያወግዘው ነገር ጥርት ያለ ግንዛቤ እንዲኖረን ከማድረጉም በላይ እርሱ ከሚጠላቸው ድርጊቶች እንድንርቅ ይረዳናል። እንግዲያውስ በ⁠ኢሳይያስ 2:​6–4:​1 ላይ ተመዝግበው የሚገኙትን የይሖዋ ትንቢታዊ ቃላት በጉጉት እንመርምር።

በትዕቢት ይሰግዳሉ

3. ኢሳይያስ የተናዘዘው የትኛውን የሕዝቡን ኃጢአት ነው?

3 ኢሳይያስ የሕዝቡን ኃጢአት ሲናዘዝ እንዲህ ብሏል:- “የምሥራቅን ሰዎች አመል ስለ ተሞሉ፣ እንደ ፍልስጤማውያንም ምዋርተኞች ስለ ሆኑ፣ ከባዕድ ልጆችም ጋር ስለ ተባበሩ [“በባዕድ ልጆች ስለ ተጥለቀለቁ፣” NW] ነው።” (ኢሳይያስ 2:​6ለ) ከ800 ዓመታት ገደማ ቀደም ብሎ ይሖዋ ለተመረጠው ሕዝቡ የሚከተለውን ትእዛዝ ሰጥቶ ነበር:- “በእነዚህ ሁሉ ከፊታችሁ የማሳድዳቸው አሕዛብ ሁሉ ረክሰዋልና በእነዚህ ነገሮች ሁሉ አትርከሱ።” (ዘሌዋውያን 18:​24) ይሖዋ የራሱ ርስት እንዲሆኑ የመረጣቸውን ሰዎች በሚመለከት በለዓም እንደሚከተለው ብሎ እንዲናገር አድርጎታል:- “በአምቦች ራስ ላይ ሆኜ አየዋለሁ፣ በኮረብቶችም ላይ ሆኜ እመለከተዋለሁ፤ እነሆ፣ ብቻውን የሚቀመጥ ሕዝብ ነው፣ በአሕዛብም መካከል አይቆጠርም።” (ዘኍልቁ 23:​9, 12) ይሁንና በኢሳይያስ ዘመን የነበሩት የተመረጠ ሕዝብ አባላት በዙሪያቸው ያሉ አሕዛብ በሚያደርጓቸው አጸያፊ ልማዶች ተጠላልፈው በሌላ አባባል ‘የምሥራቅን ሰዎች አመል ተሞልተው’ ነበር። በይሖዋና በቃሉ ላይ ከመታመን ይልቅ ‘እንደ ፍልስጤማውያን ምዋርተኞች ሆነው’ ነበር። ከአሕዛብ የተለዩ መሆናቸው ቀርቶ ምድራቸው ‘በባዕድ ልጆች’ ተጥለቅልቆ ነበር። እነዚህ ደግሞ አምላካዊ ያልሆኑ ድርጊቶችን ወደ አምላክ ሕዝብ ያስገቡ ባዕድ ሰዎች እንደሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም።

4. ብልጽግናና ወታደራዊ ጥንካሬ አይሁዳውያን ይሖዋን እንዲያመሰግኑ ምክንያት ከመሆን ይልቅ እንቅፋት የሆነባቸው እንዴት ነው?

4 ኢሳይያስ በንጉሥ ዖዝያን የግዛት ዘመን ይሁዳ የነበረችበትን የወቅቱን ኢኮኖሚያዊ ብልጽግናና ወታደራዊ ጥንካሬ በማስተዋል እንዲህ ብሏል:- “ምድራቸው በብርና በወርቅ ተሞልታለች፣ ለመዛግብቶቻቸውም ፍጻሜ የለውም፤ ምድራቸውም ደግሞ በፈረሶች ተሞልታለች፣ ለሰረገሎቻቸውም ፍጻሜ የለውም።” (ኢሳይያስ 2:​7) ሕዝቡ ላገኘው ለዚህ ብልጽግናና ወታደራዊ ጥንካሬ የሚያመሰግነው ይሖዋን ነበርን? (2 ዜና መዋዕል 26:​1, 6-15) በፍጹም! ይልቁንም ትምክህታቸውን በሀብት ላይ በመጣል የዚያ ሁሉ ምንጭ ከሆነው ከይሖዋ ርቀዋል። ውጤቱስ? “ምድራቸው ደግሞ በጣዖታት ተሞልታለች፤ ጣዖቶቻቸውም ላደረጉት ለእጃቸው ሥራ ይሰግዳሉ። ታናሹም ሰው ዝቅ ብሎአል፣ ጨዋውም ተዋርዶአል፤ ኃጢአታቸውንም ይቅር አትበላቸው።” (ኢሳይያስ 2:​8, 9) ሕያው ከሆነው አምላክ ፊታቸውን በመመለስ በድን ለሆኑ ጣዖታት ይሰግዳሉ።

5. ለጣዖታት መስገድ የትሕትና ምልክት ያልሆነው ለምንድን ነው?

5 መስገድ የትሕትና መግለጫ ሊሆን ይችላል። ግዑዝ ለሆኑ ነገሮች መስገድ ግን ጣዖት አምላኪውን ‘የሚያዋርድ’ ወይም ክብሩን የሚቀንስበት ከንቱ ተግባር ነው። ይሖዋ እንዲህ ያለውን ኃጢአት እንዴት ይቅር ሊል ይችላል? እነዚህ ጣዖት አምላኪዎች ይሖዋ መልስ እንዲሰጡ ሲጠይቃቸው ምን ያደርጋሉ?

‘ከፍ ያለች ዓይን ትዋረዳለች’

6, 7.(ሀ) ራሳቸውን ከፍ ከፍ የሚያደርጉ ሰዎች በይሖዋ የፍርድ ቀን ምን ይደርስባቸዋል? (ለ) ይሖዋ ቁጣውን የሚገልጸው በምንና በማን ላይ ነው? ለምንስ?

6 ኢሳይያስ እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “ከእግዚአብሔር ማስደንገጥና ከግርማው ክብር የተነሣ ወደ ድንጋይ ዋሻ ግባ፣ በመሬትም ውስጥ ተሸሸግ።” (ኢሳይያስ 2:​10) ሆኖም ሁሉን ቻይ ከሆነው ከይሖዋ ሊሸሽጋቸው የሚችል ምንም ዓይነት የድንጋይ ዋሻ ወይም ጠንካራ መከላከያ አይኖርም። ፍርዱን ለማስፈጸም በሚመጣበት ጊዜ “ከፍ ያለችውም የሰው ዓይን ትዋረዳለች፣ የሰዎችም ኩራት ትወድቃለች፣ በዚያም ቀን እግዚአብሔር ብቻውን ከፍ ከፍ ይላል።”​—⁠ኢሳይያስ 2:​11

7 “የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር ቀን” እየመጣ ነው። በዚህ ጊዜ የአምላክ ቁጣ “በትዕቢተኛውና በኩራተኛው ሁሉ ላይ ከፍ ባለውም ላይ ይሆናል፣ እርሱም ይዋረዳል፤ ደግሞም በረጅሙ ከፍ ባለውም በሊባኖስ ዝግባ ሁሉ ላይ፣ በረጅሙም ተራራ ሁሉ ላይ፣ ከፍ ባለውም ኮረብታ ሁሉ ላይ፣ በረጅሙም ግንብ ሁሉ ላይ፣ በተመሸገውም ቅጥር ሁሉ ላይ፣ በተርሴስም መርከብ ሁሉ ላይ፣ በሚያማምሩ ጣዖታቱም ሁሉ ላይ ይሆናል።” (ኢሳይያስ 2:​12-16) አዎን፣ የሰው ልጆች መኩራሪያ ሆኖ የቆመ የትኛውም ድርጅትም ሆነ አምላካዊ አክብሮት የሌለው እያንዳንዱ ግለሰብ በይሖዋ የቁጣ ቀን የእጁን ያገኛል። በዚህ መንገድ “ሰውም ሁሉ ይዋረዳል፣ የሰውም ኩራት ይወድቃል፣ በዚያም ቀን እግዚአብሔር ብቻ ከፍ ከፍ ይላል።”​—⁠ኢሳይያስ 2:​17

8. አስቀድሞ የተነገረው የፍርድ ቀን በ607 ከዘአበ በኢየሩሳሌም ላይ የመጣው እንዴት ነው?

8 አስቀድሞ በትንቢት የተነገረለት የፍርድ ቀን በአይሁዳውያን ላይ የመጣው በ607 ከዘአበ የባቢሎኑ ንጉሥ ናቡከደነፆር ኢየሩሳሌምን ባጠፋበት ጊዜ ነበር። ነዋሪዎቹ የተወደደችው ከተማቸው በእሳት ስትጋይ፣ ዕጹብ ድንቅ የሆኑት ሕንጻዎቻቸው ሲፈራርሱና ግዙፍ ቅጥሯ ሲደረማመስ ተመልክተዋል። የይሖዋም ቤተ መቅደስ ወደመ። ‘በሠራዊት ጌታ በእግዚአብሔር ቀን’ መዝገባቸውም ሆነ ሠረገሎቻቸው ምንም ሊፈይዱ አልቻሉም። ጣዖቶቻቸውስ? ኢሳይያስ “ጣዖቶቻቸውም ሁሉ ፈጽመው ይጠፋሉ” ሲል አስቀድሞ የተናገረው ትንቢት በትክክል ተፈጽሟል። (ኢሳይያስ 2:​18) መሳፍንቱንና ኃያላኖቻቸውን ጨምሮ አይሁዳውያን ወደ ባቢሎን በምርኮ ተወስደዋል። ኢየሩሳሌም ገና የ70 ዓመት ባድማነት ይጠብቃት ነበር።

9. የሕዝበ ክርስትና ሁኔታ በኢሳይያስ ዘመን ከነበሩት ከይሁዳና ከኢየሩሳሌም ሁኔታ ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው?

9 የሕዝበ ክርስትና ሁኔታ በኢሳይያስ ዘመን ከነበሩት ከኢየሩሳሌምና ከይሁዳ ሁኔታ ጋር ምንኛ ተመሳሳይ ነው! ሕዝበ ክርስትና ከዚህ ዓለም ብሔራት ጋር የጠበቀ ወዳጅነት መሥርታለች። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቀንደኛ ደጋፊ ከመሆኗም ሌላ ቤቷን በጣዖታትና ቅዱስ ጽሑፋዊ ባልሆኑ ልማዶች ሞልታለች። ተከታዮቿም ፍቅረ ነዋይ የተጠናወታቸውና በወታደራዊ ኃይል የሚታመኑ ናቸው። ደግሞስ ቀሳውስቶቻቸውን ከፍተኛ ማዕረግ የሚገባቸው ሰዎች እንደሆኑ አድርገው በመመልከት በተለያዩ የማዕረግና የክብር ስያሜዎች ያቆላምጧቸው የለምን? ራሷን እንዲህ ከፍ ከፍ ያደረገችው ሕዝበ ክርስትና እንዳልነበረች የምትሆንበት ጊዜ ይመጣል። ግን መቼ?

እያንዣበበ ያለው “የእግዚአብሔር ቀን”

10. ሐዋርያው ጳውሎስና ሐዋርያው ጴጥሮስ የተናገሩት ስለ የትኛው ‘የይሖዋ ቀን’ ነው?

10 ቅዱሳን ጽሑፎች በጥንቷ ኢየሩሳሌምና ይሁዳ ላይ ከመጣው የፍርድ ቀን እጅግ የላቀ ትርጉም ስለሚኖረው “የእግዚአብሔር ቀን” ይናገራሉ። ሐዋርያው ጳውሎስ በመንፈስ ተነሳስቶ ‘የይሖዋን ቀን መምጣት’ በዙፋን ላይ ከተቀመጠው ከኢየሱስ ክርስቶስ መገኘት ጋር በማዛመድ ተናግሯል። (2 ተሰሎንቄ 2:​1, 2) ጴጥሮስ ደግሞ ይህንን ቀን ‘ጽድቅ ከሚኖርበት አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር’ መቋቋም ጋር አያይዞ ገልጾታል። (2 ጴጥሮስ 3:​10-13) ይህ ቀን ይሖዋ ሕዝበ ክርስትናን ጨምሮ በመላው ክፉ የነገሮች ሥርዓት ላይ እርምጃ የሚወስድበት ቀን ነው።

11. (ሀ) መጪውን ‘የይሖዋ ቀን’ ‘የሚችለው ማን ነው?’ (ለ) ይሖዋን መጠጊያችን ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

11 ነቢዩ ኢዩኤል “የእግዚአብሔር ቀን ቀርቧልና ለቀኑ ወዮ! እርሱም ሁሉን ከሚችል አምላክ ዘንድ እንደ ጥፋት ይመጣል” ሲል ተናግሯል። ይህ “ቀን” ቅርብ ከመሆኑ አንጻር ሲታይ እያንዳንዱን ሰው የሚያሳስበው ነገር በዚህ አስፈሪ ጊዜ መሸሸጊያ ማግኘቱ ሊሆን አይገባምን? ኢዩኤል “ማንስ ይችለዋል?” ሲል ጠይቋል። “እግዚአብሔር ግን ለሕዝቡ መሸሸጊያ . . . ይሆናል” በማለት ራሱ መልሱን ሰጥቷል። (ኢዩኤል 1:​15፤ 2:​11፤ 3:​16) ይሖዋ አምላክ ትዕቢተኛ ለሆኑና ትምክህታቸውን በሀብት፣ በወታደራዊ ኃይል እንዲሁም በሰው ሠራሽ አማልክት ላይ ላደረጉ ሰዎች መሸሸጊያ ይሆናልን? በፍጹም ሊሆን አይችልም! አምላክ ተመሳሳይ ስህተት በመፈጸማቸው የራሱን የተመረጠ ሕዝብ እንኳ ትቷል። ሁሉም የአምላክ አገልጋዮች ‘ጽድቅንና ትሕትናን’ መፈለጋቸውና ለይሖዋ አምልኮ በሕይወታቸው ምን ቦታ እንደሰጡት በቁም ነገር ማሰባቸው ምንኛ አንገብጋቢ ነው!​—⁠ሶፎንያስ 2:​2, 3

“ለፍልፈልና ለሌሊት ወፍ”

12, 13. ጣዖት አምላኪዎች ጣዖቶቻቸውን ‘ለፍልፈልና ለሌሊት ወፍ’ መጣላቸው ተገቢ የሆነው ለምንድን ነው?

12 በታላቁ የይሖዋ ቀን ጣዖት አምላኪዎች ጣዖቶቻቸውን የሚመለከቷቸው እንዴት ይሆናል? ኢሳይያስ እንዲህ በማለት መልሱን ይሰጣል:- “እግዚአብሔርም ምድርን ያናውጥ ዘንድ በተነሣ ጊዜ ሰዎች ከማስደንገጡና ከግርማው ክብር የተነሣ ወደ ድንጋይ ዋሻና ወደ ምድር ንቃቃት ውስጥ ይገባሉ። በዚያም ቀን ሰው . . . የብሩንና የወርቁን ጣዖቶቹን ለፍልፈልና ለሌሊት ወፍ ይጥላል። እግዚአብሔርም ምድርን ያናውጥ ዘንድ በተነሣ ጊዜ ከማስደንገጡና ከግርማው ክብር የተነሣ ወደ ድንጋይ ዋሻና ወደ ተሰነጠቁ ዓለቶች ውስጥ ይገባሉ። እስትንፋሱ በአፍንጫው ያለበትን ሰው ተዉት፤ እርሱ ስለ ምን ይቆጠራል?” ​—⁠ኢሳይያስ 2:​19-22

13 ፍልፈል የሚኖረው መሬት ውስጥ ጉድጓድ ቆፍሮ ሲሆን የሌሊት ወፍ ደግሞ ጎጆዋን የምትሠራው ጨለማና ገለልተኛ በሆነ ዋሻ ውስጥ ነው። ከዚህም በላይ በርካታ ቁጥር ያላቸው የሌሊት ወፍ ጎጆዎች በተሠሩበት አካባቢ መጥፎ ሽታና ከፍተኛ መጠን ያለው የኩስ ክምችት ይኖራል። ጣዖታቱ እንዲህ ዓይነት ቦታ መጣላቸው ተገቢ ነው። የሚገባቸውም እንዲህ ያለ የጨለማና የቆሻሻ ቦታ ነው። ሰዎቹም ቢሆኑ በይሖዋ የፍርድ ቀን መሸሸጊያ ለማግኘት የሚፈልጉት በድንጋይ ዋሻዎችና በተሰነጠቁ ዓለቶች ውስጥ ነው። በመሆኑም የጣዖታቱም ሆነ የአምላኪዎቻቸው ዕጣ ፈንታ አንድ ዓይነት ይሆናል። ልክ ኢሳይያስ በትንቢት እንደተናገረው ግዑዝ ጣዖታት በ607 ከዘአበ አምላኪዎቻቸውንም ሆነ ኢየሩሳሌምን ከናቡከደነፆር እጅ መታደግ ሳይችሉ ቀርተዋል።

14. ይሖዋ በዓለም የሐሰት ሃይማኖት ግዛት ላይ ፍርድ በሚሰጥበት በመጪው ቀን ዓለማዊ አስተሳሰብ ያላቸው ሰዎች ምን ያደርጋሉ?

14 በሕዝበ ክርስትናና በዓለም የሐሰት ሃይማኖት ግዛት ውስጥ በታቀፉት ሌሎች ክፍሎች ላይ በሚመጣው የይሖዋ የፍርድ ቀን ሰዎች ምን ያደርጋሉ? በምድር ዙሪያ የሚያዩት ነገር እየተባባሰ የሚሄድ ብቻ ስለሚሆን አብዛኛዎቹ ጣዖቶቻቸው ከንቱ መሆናቸውን እንደሚገነዘቡ እሙን ነው። በእነዚህም ፋንታ መንፈሳዊ ካልሆኑ ምድራዊ ድርጅቶች ምናልባትም በራእይ ምዕራፍ 17 ላይ የተገለጸውን “ቀይ አውሬ” ማለትም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን ከመሳሰሉ ወገኖች መሸሸጊያና ጥበቃ ለማግኘት ይጥሩ ይሆናል። ሕዝበ ክርስትና ዋነኛ ክፍል የሆነችላትን የዓለም የሐሰት ሃይማኖት ድርጅት ማለትም ታላቂቱ ባቢሎንን የሚያጠፏት የዚህ ምሳሌያዊ አውሬ “አሥር ቀንዶች” ናቸው።​—⁠ራእይ 17:​3, 8-12, 16, 17

15. በፍርዱ ቀን ይሖዋ ብቻውን ‘ከፍ ከፍ የሚለው’ እንዴት ነው?

15 ታላቂቱ ባቢሎንን የማጥፋቱንና የማቃጠሉን ሥራ የሚያከናውኑት ምሳሌያዊዎቹ አሥር ቀንዶች ቢሆኑም ፍርዱን ያስተላለፈው ይሖዋ ነው። ራእይ 18:​8 ታላቂቱ ባቢሎንን በሚመለከት እንዲህ ይላል:- “ስለዚህ በአንድ ቀን ሞትና ኀዘን ራብም የሆኑ መቅሠፍቶችዋ ይመጣሉ፣ በእሳትም ትቃጠላለች፤ የሚፈርድባት እግዚአብሔር ብርቱ ነውና።” ስለዚህ የሰውን ልጅ ከሐሰት ሃይማኖት ቁጥጥር ሥር ነፃ በማውጣቱ የሚመሰገነው ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ይሖዋ ነው። ኢሳይያስ እንደተናገረው “በዚያም ቀን እግዚአብሔር ብቻውን ከፍ ከፍ ይላል። የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር ቀን [ነውና]።”​—⁠ኢሳይያስ 2:​11ለ, 12ሀ

‘መንገዳችሁን ያጠፉባችሁ መሪዎቹ ናቸው’

16. (ሀ) የሰብዓዊው ኅብረተሰብ ‘ድጋፍና ብርታት’ ምን ምን ነገሮችን ያካትታል? (ለ) የኢሳይያስ ሕዝብ የኅብረተሰቡ ‘ድጋፍና ብርታት’ በመጥፋቱ የሚሰቃየው እንዴት ነው?

16 የሰው ልጅ ኅብረተሰብ የተረጋጋ ሕይወት እንዲመራ ካስፈለገ ‘ድጋፍና ብርታት’ ማግኘት ያስፈልገዋል። ይህም ማለት እንደ ምግብና ውኃ ያሉትን መሠረታዊ ነገሮችና ከሁሉ በላይ ደግሞ ሕዝቡን ለመምራትና ማኅበራዊ ሥርዓትን ለማስጠበቅ ብቃት ያላቸው እንዲሁም እምነት የሚጣልባቸው መሪዎች ማግኘት ያስፈልገዋል። የጥንቷን እስራኤል በተመለከተ ግን ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ተንብዮአል:- “እነሆ፣ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ከኢየሩሳሌምና ከይሁዳ ድጋፍንና ብርታትን፣ የእንጀራን ድጋፍ ሁሉ የውኃውንም ድጋፍ ሁሉ፣ ኃያሉንም፣ ተዋጊውንም፣ ፈራጁንም፣ ነቢዩንም፣ ምዋርተኛውንም፣ ሽማግሌውንም፣ የአምሳ አለቃውንም፣ ከበርቴውንም፣ አማካሪውንም፣ ብልሁንም ሠራተኛ፣ አስማት አዋቂውንም ይነቅላል።” (ኢሳይያስ 3:​1-3) ገና አንድ ፍሬ ልጆች መሳፍንት ይሆኑና ግዛታቸው መያዣ መጨበጫ የሌለው ይሆናል። ሕዝቡን የሚጨቁኑት ገዥዎቹ ብቻ ሳይሆኑ “ሕዝቡም፣ ሰው በሰው ላይ . . . ይገፋፋል፤ ብላቴናውም በሽማግሌው ላይ የተጠቃውም በከበርቴው ላይ ይኮራል [“ይነሣል፣” NW]።” (ኢሳይያስ 3:​4, 5) ብላቴናዎቹ አክብሮት በጎደለው መንገድ በሽማግሌው ላይ ይነሣሉ። የኑሮ ደረጃቸው በጣም ከማሽቆልቆሉ የተነሣ ለመግዛት ምንም ብቃት ለሌላቸው ሰዎች እርስ በርሳቸው “አንተ ልብስ አለህ አለቃም ሁንልን ይህችም ባድማ ከእጅህ በታች ትሁን” ይባባላሉ። (ኢሳይያስ 3:​6) ይሁን እንጂ ግብዣው የቀረበላቸው ሰዎች ጠፍ የሆነውን ምድር ለመፈወስ የሚያስችል ችሎታም ሆነ ለማስተዳደር የሚያበቃ ብልጽግና እንደሌላቸው በመግለጽ ግብዣውን ለመቀበል ፈቃደኛ አይሆኑም። “እኔ በቤቴ ውስጥ እንጀራ ወይም ልብስ የለኝምና ባለ መድኃኒት አልሆንም፤ በሕዝቡም ላይ አለቃ አታደርጉኝም” ይላሉ።​—⁠ኢሳይያስ 3:​7

17. (ሀ) የኢየሩሳሌምና የይሁዳ ኃጢአት ‘እንደ ሰዶም’ የሆነው በምን መንገድ ነው? (ለ) ኢሳይያስ ሕዝቡ ለነበረበት ሁኔታ ተጠያቂ ያደረገው ማንን ነው?

17 ኢሳይያስ እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “የክብሩን ዓይን ያስቈጡ ዘንድ ምላሳቸውና ሥራቸው በእግዚአብሔር ላይ ነውና ኢየሩሳሌም ተፈታች ይሁዳም ወደቀ። የፊታቸውም እፍረት ይመሰክርባቸዋል፤ እንደ ሰዶምም ኃጢአታቸውን ያወራሉ፣ አይሠውሩአትም። በራሳቸው ላይ ክፉ ነገርን ሠርተዋልና ለነፍሳቸው ወዮ!” (ኢሳይያስ 3:​8, 9) የአምላክ ሕዝቦች በቃልም ይሁን በድርጊት በእውነተኛው አምላክ ላይ ዓምፀዋል። ፊታቸው ላይ የሚነበበው እፍረት የለሽነትና ንስሐ ያለመግባት ዝንባሌ እንደ ሰዶም ሰዎች ኃጢአት አጸያፊ የሆነውን ኃጢአታቸውን የሚያጋልጥ ነው። ከይሖዋ አምላክ ጋር ቃል ኪዳን የመሠረቱ ቢሆንም ለእነርሱ ሲል የአቋም ደረጃዎቹን አይቀይርም። “የሥራቸውን ፍሬ ይበላሉና ጻድቁን:- መልካም ይሆንልሃል በሉት። እንደ እጁ ሥራ ፍዳው ይደረግበታልና ለበደለኛ ወዮ! ክፉም ደርሶበታል። ሕዝቤንስ አስገባሪዎቻቸው ይገፍፉአቸዋል፣ አስጨናቂዎችም ይሠለጥኑባቸዋል። ሕዝቤ ሆይ፣ የመሩአችሁ ያስቱአችኋል የምትሄዱበትንም መንገድ ያጠፋሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 3:​10-​12

18. (ሀ) ይሖዋ በኢሳይያስ ዘመን ለነበሩት ሽማግሌዎችና መሳፍንት የሰጠው ፍርድ ምንድን ነው? (ለ) ይሖዋ በሽማግሌዎችና በመሳፍንቱ ላይ ከወሰነው ነገር ምን ትምህርት እናገኛለን?

18 ይሖዋ በይሁዳ በሚገኙ ሽማግሌዎችና መሳፍንት ላይ ‘ይበይናል፤’ ‘ወደ ፍርድም ያመጣቸዋል’:- “እግዚአብሔር ለፍርድ ተነሥቶአል በሕዝቡም ላይ ሊፈርድ ቆሞአል። እግዚአብሔር ከሕዝቡ ሽማግሌዎችና ከአለቆቻቸው ጋር ይፋረዳል፤ የወይኑን ቦታ የጨረሳችሁ እናንተ ናችሁ፤ ከድሆች የበዘበዛችሁት በቤታችሁ አለ፤ ሕዝቤንም ለምን ታደቅቁአቸዋላችሁ? የድሆችንስ ፊት ለምን ትፈጫላችሁ? ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 3:​13-​15) መሪዎቹ ለሕዝቡ ደህንነት ከመሥራት ይልቅ በማታለል ድርጊት ተጠላልፈው ነበር። ድሀውንና ችግረኛውን እየቀሙ ራሳቸውን ለማበልጸግ ሥልጣናቸውን አላግባብ ተጠቅመውበታል። ይሁን እንጂ እነዚህ መሪዎች የተጨነቁትን ሰዎች በመጨቆናቸው ለይሖዋ መልስ መስጠት ይጠበቅባቸዋል። ዛሬ በኃላፊነት ቦታ ላይ ላሉት ይህ እንዴት ያለ ማስጠንቀቂያ ነው! ሥልጣናቸውን አላግባብ ላለመጠቀም ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ጠንቃቆች ሊሆኑ ይገባል።

19. ሕዝበ ክርስትና ለየትኛው ጭቆናና ስደት ተጠያቂ ነች?

19 ሕዝበ ክርስትና በተለይ ደግሞ ቀሳውስቶቿና መሪዎቿ እየጨቆኑት ላለውና ወደፊትም ለሚጨቁኑት ሕዝብ ይገባ የነበረውን ብዙ ነገር በማጭበርበር ለራሳቸው አጋብሰዋል። ከዚህም በተጨማሪ የአምላክን ሕዝቦች ደብድባለች፣ አሳድዳለች እንዲሁም አንገላትታለች። በይሖዋ ስምም ላይ ነቀፋ አምጥታለች። ጊዜው ሲደርስ ይሖዋ ወደ ፍርድ ያመጣታል።

“በውበትም ፈንታ ጠባሳ ይሆናል

20. ይሖዋ ‘የጽዮንን ሴት ልጆች’ ያወገዘው ለምንድን ነው?

20 ይሖዋ የመሪዎቹን ስህተት ካወገዘ በኋላ ወደ ጽዮን ወይም ወደ ኢየሩሳሌም ሴቶች ዘወር ብሏል። እንደ ፋሽን ሆኖ ይመስላል ‘የጽዮን ቆነጃጅት’ “ሰንሰለት” እና የሚያቃጭል ድምፅ ያለው የእግር አልቦ ያደርጉ ነበር። ሴቶቹ እርምጃቸውን ቆጥበው በሴት ወይዘሮ ወግ “በቀስታ ይራመዳሉ።” ታዲያ ይህ ምን ስህተት አለበት? ስህተቱ የሴቶቹ ዝንባሌ ነው። ይሖዋ እንዲህ ይላል:- “የጽዮን ቆነጃጅት ኮርተዋልና፣ አንገታቸውን እያሰገጉ በዓይናቸው እያጣቀሱ፣ . . . ይሄዳሉና።” (ኢሳይያስ 3:​16) እንዲህ ያለው ትዕቢት የበቀል ፍርድ ያስከትልባቸዋል።

21. ይሖዋ በኢየሩሳሌም ላይ የወሰደው ፍርድ አይሁዳውያን ሴቶችን የሚነካቸው እንዴት ነው?

21 በመሆኑም የይሖዋ ፍርድ በምድሪቱ ላይ በሚመጣበት ጊዜ እነዚህ የታበዩት “የጽዮን ልጆች” እንደዚያ የተኩራሩበትን ውበት ጨምሮ ያላቸውን ነገር ሁሉ ያጣሉ። ይሖዋ እንዲህ ሲል ተንብዮአል:- “ስለዚህ ጌታ የጽዮንን ቈነጃጅት አናት በቡሀነት ይመታል፣ እግዚአብሔርም ኀፍረተ ሥጋቸውን ይገልጣል። በዚያም ቀን ጌታ የእግር አልቦውን ክብር፣ መርበብንም፣ ጨረቃ የሚመስለውንም ጌጥ፣ የጆሮ እንጥልጥሉንም፣ አንባሩንም፣ መሸፈኛውንም፣ ቀጸላውንም፣ ሰንሰለቱንም፣ መቀነቱንም፣ የሽቱውንም ዕቃ፣ አሸንክታቡንም፣ የእጅና የአፍንጫ ቀለበቱንም፣ የዓመት በዓልንም ልብስ፣ መጐናጸፊያውንም፣ ልግምበገላውንም፣ ከረጢቱንም፣ መስተዋቱንም፣ ከጥሩ በፍታ የተሠራውንም ልብስ፣ ራስ ማሰሪያውንም፣ ዓይነ ርግቡንም ያስወግዳል።” (ኢሳይያስ 3:​17-​23 ) መጨረሻቸው እንዴት የሚያሳዝን ነው!

22. የኢየሩሳሌም ሴቶች ያጡት ጌጣቸውን ብቻ ሳይሆን ምንንም ጭምር ነው?

22 ትንቢታዊው መልእክት እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “በሽቱ ፋንታ ግማት፣ በመታጠቂያውም ፋንታ ገመድ፣ ጠጉርንም በመንቀስ ፋንታ ቡሀነት፣ በመጎናጸፊያ ፋንታ ማቅ፣ በውበትም ፋንታ ጠባሳ ይሆናል።” (ኢሳይያስ 3:​24) በ607 ከዘአበ ኩራተኞቹ የኢየሩሳሌም ሴቶች ከብልጽግና ወደ ድህነት አሽቆልቁለዋል። ነፃነታቸውን ተነፍገው በምትኩ የባርነት ምልክት የሆነ ጠባሳ ተደርጎላቸዋል።

‘ባዶዋን ትቀራለች’

23. ይሖዋ ኢየሩሳሌምን በሚመለከት ምን ነገር ተናግሯል?

23 ይሖዋ ቀጥሎ ስለ ኢየሩሳሌም ከተማ ሲናገር እንዲህ ብሏል:- “ጎልማሶችሽ በሰይፍ፣ ኃያላንሽም በውጊያ ይወድቃሉ። በሮችዋ ያዝናሉ ያለቅሱማል፤ እርስዋም ብቻዋን [“ባዶዋን ትቀራለች፣” NW] በምድር ላይ ትቀመጣለች።” (ኢሳይያስ 3:​25, 26) የኢየሩሳሌም ወንዶች ኃያላኑ ሳይቀሩ በውጊያ ይወድቃሉ። ከተማዋ እንዳልነበረች ትሆናለች። “በሮችዋ” ‘የሚያዝኑበትና የሚያለቅሱበት’ ጊዜ ይሆናል። ኢየሩሳሌም ‘ባዶዋን ትቀራለች’ በሌላ አባባል ባድማ ትሆናለች።

24. ወንዶች በሰይፍ መውደቃቸው በኢየሩሳሌም ሴቶች ላይ ምን ከባድ ችግር አስከትሏል?

24 ወንዶቹ በሰይፍ መውደቃቸው በኢየሩሳሌም ሴቶች ላይ የሚያስከትለው መዘዝ ቀላል አይሆንም። ኢሳይያስ ይህንን የትንቢቱን ክፍል ሲደመድም እንዲህ ብሏል:- “በዚያም ቀን ሰባት ሴቶች:- የገዛ እንጀራችንን እንበላለን የገዛ ልብሳችንንም እንለብሳለን፤ ስምህ ብቻ በእኛ ላይ ይጠራ፣ መሰደባችንንም አርቅ ብለው አንዱን ወንድ ይይዙታል።” (ኢሳይያስ 4:​1) ለትዳር የሚሆኑ በቂ ወንዶች አለመኖራቸው ከባድ ችግር ከመሆኑ የተነሣ በርካታ ሴቶች ባል የላቸውም ከሚለው ነቀፋ ነፃ ለመሆንና በአንዱ ሰው ስም ለመጠራት ማለትም የእርሱ ሚስት ተብለው ለመታወቅ ሲሉ አንዱን ወንድ ይከተላሉ። የሙሴ ሕግ አንድ ባል ሚስቱን የመመገብና የማልበስ ግዴታ እንዳለበት ይገልጻል። (ዘጸአት 21:​10) ይሁን እንጂ እነዚህ ሴቶች ‘የገዛ እንጀራቸውን ሊበሉና የገዛ ልብሳቸውን ሊለብሱ’ በመስማማት ሰውዬውን ከሕጋዊ ግዴታዎች ነፃ ለማድረግ ፈቃደኞች ሆነዋል። በአንድ ወቅት እጅግ ኩራተኛ ለነበሩት “የጽዮን ልጆች” ይህ እንዴት ያለ አሳዛኝ ሁኔታ ነው!

25. ራሳቸውን ከፍ ከፍ የሚያደርጉ ሰዎች መጨረሻቸው ምንድን ነው?

25 ይሖዋ ራሳቸውን ከፍ ከፍ የሚያደርጉትን ያዋርዳል። በእርግጥም በ607 ከዘአበ የተመረጠ ሕዝቡን ትዕቢት ‘አዋርዷል፣ ኩራታቸውንም ጥሏል።’ እውነተኛ ክርስቲያኖችም ‘ይሖዋ ትዕቢተኞችን እንደሚቃወምና ለትሑታን ግን ጸጋን እንደሚሰጥ ዘወትር ያስታውሱ’።​—⁠ያዕቆብ 4:​6

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 50 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ጣዖታት፣ ቁሳዊ ንብረትና ወታደራዊ ጀብድ ኢየሩሳሌምን ከይሖዋ ፍርድ ሊታደጓት አይችሉም

[በገጽ 55 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

‘በይሖዋ ቀን’ የዓለም የሐሰት ሃይማኖት ግዛት ትጠፋለች