በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋ ኩሩዋን ከተማ ያዋርዳል

ይሖዋ ኩሩዋን ከተማ ያዋርዳል

ምዕራፍ አሥራ አራት

ይሖዋ ኩሩዋን ከተማ ያዋርዳል

ኢሳይያስ 13:​1–14:​23

1. የኢሳይያስ መጽሐፍ ከወዲሁ መቼ የሚሆነውን ነገር ጭምር ይናገራል?

የኢሳይያስ የትንቢት መጽሐፍ የተጻፈው በስምንተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ አሦራውያን የተስፋይቱን ምድር በወረሩበት ወቅት ነበር። ቀደም ባሉት የመጽሐፉ ምዕራፎች ውስጥ እንዳየነው ሁሉ ኢሳይያስ አሁንም ነገሮች የሚከናወኑበትን ትክክለኛ አቅጣጫ በሚያስገርም መንገድ ይተነብያል። ይሁን እንጂ መጽሐፉ የአሦራውያን የበላይነት ከገነነበት ዘመን በኋላ የሚሆነውንም አሻግሮ ይመለከታል። የይሖዋ የቃል ኪዳን ሕዝብ በባቢሎን ያለችውን ሰናዖርን ጨምሮ በግዞት ከነበሩባቸው ብዙ ቦታዎች እንደሚመለሱ ይተነብያል። (ኢሳይያስ 11:​11) በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 13 ላይ አንድ አስገራሚ ትንቢት ተጠቅሶ እናገኛለን። ይህ ትንቢት ፍጻሜውን ሲያገኝ ሕዝቡ ወደ ትውልድ አገሩ የሚመለስበት በር ይከፈትለታል። ትንቢቱ በሚከተሉት ቃላት ይጀምራል:- “የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ያየው ስለ ባቢሎን የተነገረ ሸክም።”​—⁠ኢሳይያስ 13:​1

‘ኩራታቸውን አዋርዳለሁ’

2. (ሀ) ሕዝቅያስ ከባቢሎን ጋር ግንኙነት የፈጠረው እንዴት ነው? (ለ) የሚነሣው “ምልክት” ምንድን ነው?

2 በኢሳይያስ የሕይወት ዘመን ይሁዳ ከባቢሎን ጋር ግንኙነት ፈጥራ ነበር። ንጉሥ ሕዝቅያስ በጠና ታሞ ቆይቶ ገና መዳኑ ነበር። በዚህ ጊዜ ከባቢሎን የተላኩ መልእክተኞች እንኳን አተረፈህ ሊሉት ይመጣሉ። እግረ መንገዳቸውን ግን ከአሦር ጋር በሚያደርጉት ውጊያ ሕዝቅያስ ከጎናቸው እንዲሰለፍ የማግባባት ስውር ዓላማ ይዘው እንደነበር እሙን ነው። በዚህ ጊዜ ንጉሥ ሕዝቅያስ ያለውን ሀብት ሁሉ በማስጎብኘት ጥበብ የጎደለው ነገር አደረገ። ከዚህ የተነሣ ኢሳይያስ ንጉሡ ከሞተ በኋላ ይህ ሁሉ ሃብት ወደ ባቢሎን እንደሚጋዝ ለሕዝቅያስ ነግሮታል። (ኢሳይያስ 39:​1-7) በ607 ከዘአበ ኢየሩሳሌም ስትጠፋና ብሔሩ በግዞት ሲወሰድ ይህ ትንቢት ፍጻሜውን አግኝቷል። ይሁን እንጂ የተመረጠው የአምላክ ሕዝብ እስከ መጨረሻው በባቢሎን ይቀራል ማለት አይደለም። ይሖዋ ወደ ትውልድ አገራቸው የሚመለሱበትን መንገድ እንዴት እንደሚከፍትላቸው አስቀድሞ ተናግሯል። እንዲህ በማለት ይጀምራል:- “ምድረ በዳ በሆነ ተራራ ላይ ምልክትን አቁሙ፣ ድምፅንም ከፍ አድርጉባቸው፤ በአለቆችም ደጆች እንዲገቡ በእጅ ጥቀሱ።” (ኢሳይያስ 13:​2) ይህ ‘ምልክት’ ባቢሎንን ከፍ ካለ ቦታዋ የሚያፈናቅላት ወደፊት የሚነሣ የዓለም ኃይል ነው። የሚነሣው “ምድረ በዳ በሆነ ተራራ ላይ” ስለሆነ ከርቀት ያለምንም ችግር ይታያል። ባቢሎንን ለመቅጣት የተጠራው ይህ አዲስ የዓለም ኃይል “በአለቆች ደጅ” ማለትም በታላቂቷ ከተማ በሮች ገብቶ ድል ይነሣታል።

3. (ሀ) ይሖዋ የሚያስነሳቸው ‘የተቀደሱ’ ወገኖች እነማን ናቸው? (ለ) አረማዊ ሠራዊቶች ‘የተቀደሱ’ ሊባሉ የሚችሉት እንዴት ነው?

3 ቀጥሎ ይሖዋ እንዲህ ይላል:- “ቁጣዬን ይፈጽሙ ዘንድ ቅዱሳኔን አዝዣለሁ፣ እኔ ኃያላኔንና በታላቅነቴ ደስ የሚላቸውን ጠርቻለሁ። በተራሮች ላይ እንደ ታላቅ ሕዝብ ድምፅ የሆነ የብዙ ሰው ድምፅ አለ። የተከማቹት የአሕዛብ መንግሥታት የውካታ ጫጫታ አለ። የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ሠራዊትን ለሰልፍ አሰልፎአል።” (ኢሳይያስ 13:​3, 4) ኩራተኛዋን ባቢሎንን እንዲያዋርዱ የተሾሙት እነዚህ ‘ቅዱሳን’ እነማን ናቸው? እነዚህ ‘የተከማቹ አሕዛብ’ ማለትም ኅብረት የፈጠሩ ብሔራዊ ኃይሎች ናቸው። ርቆ ከሚገኝ ተራራማ አካባቢ በባቢሎን ላይ ይወርዱባታል። “ምድርን ሁሉ ያጠፉአት ዘንድ ከሩቅ አገር ከሰማይ ዳርቻ ይመጣሉ።” (ኢሳይያስ 13:​5) ‘የተቀደሱ’ የሆኑት እንዴት ነው? ቅዱስ ናቸው ለማለት እንዳልሆነ ግልጽ ነው። ይሖዋን የማገልገል ምንም ዓይነት ፍላጎት የሌላቸው አረማዊ ሠራዊት ናቸው። ይሁን እንጂ በዕብራይስጥ ቅዱሳን ጽሑፎች ውስጥ “የተቀደሰ” ማለት “አምላክ ለአንድ ዓላማ እንዲጠቀምበት የተለየ” ማለት ነው። ይሖዋ የአሕዛብን ሠራዊት በመቀደስ የራስ ወዳድነት የሥልጣን ጥማቸውን ተጠቅሞ ቁጣውን ሊገልጽ ይችላል። አሦርን የተጠቀመባት በዚህ መንገድ ነበር። ባቢሎንንም ቢሆን በተመሳሳይ መንገድ ይጠቀምባታል። (ኢሳይያስ 10:​5፤ ኤርምያስ 25:​9) ባቢሎንን ለመቅጣት ደግሞ ሌሎች ብሔራትን ይጠቀማል።

4, 5. (ሀ) ይሖዋ ስለ ባቢሎን ምን ነገር ተንብዮአል? (ለ) በባቢሎን ላይ ጥቃት የሚሠነዝሩ ወገኖች ምን እንቅፋት ማለፍ ይጠብቃቸዋል?

4 በዚህ ጊዜ ባቢሎን ገና የዓለም ኃይል አልሆነችም ነበር። ይሁንና ይሖዋ በኢሳይያስ አማካኝነት ባስነገረው መልእክት ባቢሎን ወደፊት ይህንን ቦታ እንደምትይዝ አስቀድሞ የተመለከተ ሲሆን እንደምትወድቅም ተንብዮአል። እንዲህ ይላል:- “የእግዚአብሔር ቀን ቀርቦአልና፣ አልቅሱ፤ ሁሉን ከሚችል አምላክ ዘንድ እንደሚመጣ ጥፋት ይመጣል።” (ኢሳይያስ 13:​6) አዎን፣ የባቢሎን ኩራት በሐዘን ልቅሶ ይተካል። ለምን? ይሖዋ በእርሷ ላይ ፍርዱን የሚያስፈጽምበት “የእግዚአብሔር ቀን” ስለሚመጣ ነው።

5 ይሁንና ባቢሎን እንዴት ልትጠፋ ትችላለች? ይሖዋ የወሰነው ጊዜ ሲደርስ የከተማዋ ደህንነት አስተማማኝ መስሎ ይታያል። ወራሪው ሠራዊት በመጀመሪያ በከተማዋ መካከል በሚያልፈው የኤፍራጥስ ወንዝ የተገነባውን የተፈጥሮ መከላከያ ለማለፍ ዘዴ መቀየስ ይኖርበታል። ይህ ወንዝ ለመከላከያ በተቆፈረው ቦይ የሚያልፍ ሲሆን የከተማዋም የውኃ ምንጭ ነው። ከዚያ ቀጥሎ ደግሞ ፈጽሞ የሚደፈሩ የማይመስሉት በድርብ የተገነቡት የባቢሎን ግዙፍ ቅጥሮች አሉ። ከዚህም በላይ ከተማዋ በቂ የምግብ ክምችት ይኖራታል። ዴይሊ ባይብል ኢሉስትሬሽንስ የተባለው መጽሐፍ የባቢሎን የመጨረሻ ንጉሥ የነበረው ናቦኒደስ “ከተማዋ የሚያስፈልጋትን ነገር ለማከማቸት እጅግ ደክሟል። ደግሞም ነዋሪዎቿን ለሃያ ዓመታት ያህል ሊመግብ የሚችል [የምግብ] ክምችት እንደነበረ ይታመናል” ብሏል።

6. በባቢሎን ላይ እንደሚፈጸም በትንቢት የተነገረለት ጥቃት ሲሰነዘር ምን ድንገተኛ ነገር ይከሰታል?

6 ይሁን እንጂ ውጫዊ ሁኔታ ሊያታልል ይችላል። ኢሳይያስ እንዲህ ይላል:- “ስለዚህ እጅ ሁሉ ትዝላለች፣ የሰውም ሁሉ ልብ ይቀልጣል። ይደነግጣሉ፤ ምጥና ሕማም ይይዛቸዋል፣ እንደምትወልድ ሴትም ያምጣሉ፤ አንዱም በሌላው ይደነቃል፣ ፊታቸውም የነበልባል ፊት ነው።” (ኢሳይያስ 13:​7, 8) ድል አድራጊው ሠራዊት ከተማዋን ሲከብብ የሕዝቡ ምቾት ምጥ የያዛት ሴት እንደሚሰማት ባለ ድንገተኛና ብርቱ ሕመም ይተካል። ልባቸው በፍርሃት ይቀልጣል። እጃቸው ሁሉ ስለሚዝል መከላከል ያቅታቸዋል። ከወደቀባቸው ፍርሃትና ጭንቀት የተነሳ ፊታቸው ‘እሳት’ ይመስላል። ታላቋ ከተማቸው በመውደቋ ተገርመው እርስ በርሳቸው ይተያያሉ።

7. እየመጣ ያለው “የእግዚአብሔር ቀን” ምንድን ነው? በባቢሎን ላይ የሚያስከትለውስ ውጤት ምን ይሆናል?

7 የሆነ ሆኖ ከተማቸው ትወድቃለች። ባቢሎን አስጨናቂ የሆነውን ‘የእግዚአብሔር ቀን’ ማለትም የፍርድ ቀን ትጋፈጣለች። ታላቁ ዳኛ ቁጣውን በመግለጥ ኃጢአተኛ በሆኑት የባቢሎን ነዋሪዎች ላይ የሚገባቸውን ቅጣት ያመጣል። ትንቢቱ እንዲህ ይላል:- “እነሆ፣ ምድሪቱን ባድማ ሊያደርግ፣ ኃጢአተኞችዋንም ከእርስዋ ዘንድ ሊያጠፋ ጨካኝ ሆኖ በመዓትና በጽኑ ቁጣ ተሞልቶ የእግዚአብሔር ቀን ይመጣል።” (ኢሳይያስ 13:​9) ባቢሎን ከፊቷ የሚጠብቃት ጊዜ የጨለመ ነው። ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት ብርሃናቸውን የነፈጓት ያህል ነው። “የሰማይም ከዋክብትና ሠራዊቱ ብርሃናቸውን አይሰጡም፣ ፀሐይም በወጣች ጊዜ ትጨልማለች፣ ጨረቃም በብርሃኑ አያበራም።”​—⁠ኢሳይያስ 13:​10

8. ይሖዋ ባቢሎን እንድትወድቅ የወሰነው ለምንድን ነው?

8 ይህች ኩሩ ከተማ እንዲህ ያለ ዕጣ ፈንታ የገጠማት ለምንድን ነው? ይሖዋ እንዲህ ይላል:- “ዓለሙን ስለ ክፋታቸው ክፉዎቹንም ስለ በደላቸው እቀጣለሁ፤ የትዕቢተኞችንም ኩራት እሽራለሁ፣ የጨካኞቹንም ኩራት አዋርዳለሁ።” (ኢሳይያስ 13:​11) ይሖዋ በባቢሎን ላይ ቁጣውን የሚያወርድባት በአምላክ ሕዝቦች ላይ ስለፈጸመችው ጭካኔ ነው። በባቢሎናውያን ክፋት ምክንያት መላው ምድር ይቀጣል። ከዚህ በኋላ እነዚህ ኩሩና አምባገነኖች ይሖዋን በይፋ አይዳፈሩም!

9. በይሖዋ የፍርድ ቀን ባቢሎን ምን ይጠብቃታል?

9 ይሖዋ እንዲህ ይላል:- “የቀሩትም ከጥሩ ወርቅ ይልቅ የከ⁠በሩ ይሆናሉ፣ ሰውም ከኦፊር ወርቅ ይልቅ የከበረ ይሆናል።” (ኢሳይያስ 13:​12) አዎን፣ ከተማዋ ሰው አልባ ትሆናለች። ይሖዋ እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “ስለዚህ በሠራዊት ጌታ በእግዚአብሔር መዓት በጽኑ ቁጣ ቀንም ሰማያትን አነቃንቃለሁ፣ ምድርም ከስፍራዋ ትናወጣለች።” (ኢሳይያስ 13:​13) የባቢሎን “ሰማያት” ማለትም እጅግ ብዙ ቁጥር ያላቸው ወንዶችና ሴቶች አማልክትዋ ከተማዋን በችግሯ ጊዜ መርዳት ባለመቻላቸው ይነቃነቃሉ። “ምድርም” ማለትም የባቢሎን ግዛት እንደ ሌሎቹ ሁሉ አልፎ በታሪክ ብቻ የሚታወስ ያበቃለት ግዛት ስለሚሆን ከስፍራው ይናወጣል። “እንደ ተባረረም ሚዳቋ፣ ማንም እንደማይሰበስበው እንደ በግ መንጋ፣ ሰው ሁሉ ወደ ወገኑ ይመለሳል፣ ሁሉም ወደ አገሩ ይሸሻል።” (ኢሳይያስ 13:​14) የባቢሎን ደጋፊ የሆኑ ባዕድ አገራት በሙሉ ከድል አድራጊው የዓለም ኃይል ጋር አዲስ ወዳጅነት ለመመሥረት በማሰብ ጥለዋት ይሸሻሉ። በመጨረሻ ባቢሎን በሥልጣን ዘመኗ ብዙዎችን ያጠጣችውን በሌሎች እጅ የመውደቅ የመከራ ጽዋ ራሷም ትጎነጫለች:- “የተገኘ ሁሉ የተወጋ ይሆናል፣ የተያዘም ሁሉ በሰይፍ ይወድቃል። ሕፃናቶቻቸውም በፊታቸው ይጨፈጨፋሉ፣ ቤቶቻቸውም ይበዘበዛሉ፣ ሚስቶቻቸውም ይነወራሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 13:​15, 16

አምላክ ለማጥፋት የሚጠቀምበት መሣሪያ

10. ባቢሎንን ድል ለማድረግ ይሖዋ የሚጠቀመው በማን ነው?

10 ይሖዋ ባቢሎንን ለመጣል የሚጠቀምበት ኃይል የትኛው ይሆን? ከ200 ዓመታት ቀደም ብሎ ይሖዋ መልሱን ሰጥቷል:- “እነሆ፣ ብር የማይሹትን፣ ወርቅም የማያምራቸውን ሜዶናውያንን በላያቸው አስነሣለሁ። ፍላጾቻቸውም ጎበዞችን ይጨፈጭፋሉ፣ የማኅፀንንም ፍሬ አይምሩም፣ ዓይኖቻቸውም ለሕፃናት አይራሩም። እግዚአብሔርም ሰዶምንና ገሞራን ባፈረሰ ጊዜ እንደ ነበረው፣ የመንግሥታት ክብር የከለዳውያንም ትዕቢት ጌጥ ባቢሎን እንዲሁ ትሆናለች።” (ኢሳይያስ 13:​17-19) የተቀማጠለችው ባቢሎን ትወድቃለች። ለይሖዋ እንደ መሣሪያ ሆኖ ይህን የሚያስፈጽመው ደግሞ በሩቅ ካለው የሜዶን ተራራማ አካባቢ የሚመጣ ሠራዊት ይሆናል። * በመጨረሻም ባቢሎን በሥነ ምግባር ብልግና የለየላቸው እንደነበሩት እንደ ሰዶምና ገሞራ ከተሞች ባድማ ትሆናለች።​—⁠ዘፍጥረት 13:​13፤ 19:​13, 24

11, 12. (ሀ) ሜዶን የዓለም ኃይል ለመሆን የበቃችው እንዴት ነው? (ለ) ትንቢቱ ስለ ሜዶን ሠራዊት የሚጠቅሰው እንግዳ የሆነ ባሕርይ ምንድን ነው?

11 በኢሳይያስ ዘመን ሜዶንና ባቢሎን በአሦር የግዛት ቀንበር ሥር ነበሩ። ከአንድ መቶ ዓመት ገደማ በኋላ በ632 ከዘአበ ሜዶንና ባቢሎን ሠራዊታቸውን አስተባብረው የአሦር ዋና ከተማ የነበረችውን ነነዌን ገለበጡ። ይህም ባቢሎን የዓለም ልዕለ ኃያል መንግሥት እንድትሆን በር ከፍቶላታል። ከአንድ መቶ ዓመት ገደማ በኋላ ግን ሜዶን እርሷን ለማጥፋት የምትነሣ ጠላትዋ እንደምትሆን አልተገነዘበችም! ይሁን እንጂ ከይሖዋ አምላክ ሌላ ይህንን ነገር አስቀድሞ ሊያውቅ የሚችል ማን ይኖራል?

12 ይሖዋ ለጥፋቱ እንደ መሣሪያ አድርጎ የሚጠቀምበትን ኃይል ማንነት ሲገልጽ የሜዶን ሠራዊት ‘ብር እንደማይሻና ወርቅም እንደማያምረው’ ተናግሯል። የጦርነት አባዜ ከተጠናወታቸው ወታደሮች የማይጠበቅ የሚያስገርም ባሕርይ ነው! የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁር የሆኑት አልበርት ባርነስ እንዲህ ብለዋል:- “ምርኮን ተስፋ አድርጎ የማይነሳ ወራሪ ሠራዊት የለም ለማለት ይቻላል።” የሜዶን ሠራዊት በዚህ ረገድ ይሖዋ እንዳለው ሆኖ ተገኝቷልን? አዎን። በጄ ግሌንትዎርዝ በትለር በተዘጋጀው ዘ ባይብል ዎርክ በተባለው መጽሐፍ ላይ የቀረበውን ይህን አስተያየት ተመልከት:- “እስከ ዛሬ ድረስ ውጊያ ከገጠሙት ብሔራት ሁሉ በተለየ መልኩ ሜዶናውያን በተለይ ደግሞ ፋርሳውያን ከወርቅ ይልቅ የሚያጓጓቸው የሚያገኙት ድልና ክብር ነበር።” * ከዚህ አንፃር ሲታይ የፋርሱ ገዢ ቂሮስ እስራኤላውያንን ከባቢሎን ግዞት ነፃ አውጥቶ በሰደዳቸው ጊዜ ናቡከደነፆር ከኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ የዘረፋቸውን በሺህ የሚቆጠሩ የወርቅና የብር ዕቃዎች ለእስራኤላውያኑ መመለሱ ምንም አያስገርምም።​—⁠ዕዝራ 1:​7-11

13, 14. (ሀ) የሜዶንና የፋርስ ተዋጊዎች ለምርኮ እምብዛም ባይጎመጁም ከፍተኛ ግምት የሚሰጡት ለምን ነገር ነበር? (ለ) ቂሮስ ባቢሎን ትኩራራበት የነበረውን መከላከያ ያለፈው እንዴት ነው?

13 የሜዶንም ሆኑ የፋርስ ተዋጊዎች ለምርኮ ያላቸው ፍቅር እምብዛም ይሁን እንጂ የሥልጣን ጥም ግን ነበራቸው። በዓለም መድረክ ከየትኛውም መንግሥት አንሰው መገኘት አይፈልጉም። ከዚህም በላይ ይሖዋ በልባቸው ‘ጥፋትን’ አስገብቷል። (ኢሳይያስ 13:​6) በመሆኑም የባቢሎናውያን እናቶች የማኅፀን ፍሬ የሆኑትን የጠላት ወታደሮች ‘የሚጨፈጭፉበትን’ ፍላጻ ለማስወንጨፍ በሚጠቀሙበት ጠንካራ ደጋን አማካኝነት ባቢሎንን ለማንበርከክ ቆርጠዋል።

14 የባቢሎን ቅጥሮች የሜዶ ፋርስ ሠራዊት አለቃ የሆነውን ቂሮስን አልገቱትም። በ539 ከዘአበ ጥቅምት 5/6 ምሽት ላይ የኤፍራጥስን ወንዝ አቅጣጫ እንዲያስቀይሩ ትእዛዝ ሰጠ። የውኃው መጠን እየጎደለ ሲመጣ ወራሪዎቹ እስከ ጭናቸው የሚደርሰውን ውኃ አቋርጠው በቀስታ ወደ ከተማዋ ገቡ። የባቢሎን ነዋሪዎች ተዘናግተው እያሉ ተያዙና ባቢሎን ወደቀች። (ዳንኤል 5:​30) ይሖዋ አምላክ ኢሳይያስ እነዚህን ነገሮች እንዲተነብይ በመንፈሱ አነሳስቶታል። ጉዳዩ በይሖዋ እጅ እንደነበር ምንም አያጠራጥርም።

15. ባቢሎን የሚጠብቃት ዕጣ ፈንታ ምንድን ነው?

15 የባቢሎን ጥፋት ምን ያህል መጠነ ሰፊ ይሆናል? ይሖዋ የተናገረውን አዳምጥ:- “ለዘላለም የሚቀመጥባት አይገኝም፣ ከትውልድም እስከ ትውልድ ድረስ ሰው አይኖርባትም፤ ዓረባውያንም ድንኳንን በዚያ አይተክሉም፣ እረኞችም መንጎቻቸውን በዚያ አያሳርፉም። በዚያም የምድረ በዳ አራዊት ያርፋሉ፣ ጉጉቶችም በቤቶቻቸው ይሞላሉ፤ ሰጎኖችም በዚያ ይኖራሉ፣ በዚያም አጋንንት ይዘፍናሉ። ተኩላዎችም በግንቦቻቸው፣ ቀበሮችም በሚያማምሩ አዳራሾቻቸው ይጮኻሉ፤ ጊዜዋም ለመምጣት ቀርቦአል ቀንዋም አይዘገይም።” (ኢሳይያስ 13:​20-22) የከተማዋ ዕጣ ፈንታ ፍጹም ጥፋት ይሆናል።

16. ባቢሎን አሁን ያለችበት ሁኔታ ምን ትምክህት ያሳድርብናል?

16 ይህ ወዲያው በ539 ከዘአበ አልተፈጸመም። ያም ሆኖ ግን ኢሳይያስ ባቢሎንን አስመልክቶ የተናገረው ነገር አንድም ሳይቀር እንደተፈጸመ ዛሬ በግልጽ የሚታይ ሐቅ ነው። አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁር ባቢሎንን በሚመለከት እንዲህ ብለዋል:- “ዛሬም ሆነ ባለፉት ብዙ መቶ ዘመናት ባድማ መሬትና የፍርስራሽ ክምር ነች። ይህንን ትዕይንት ተመልክቶ የኢሳይያስና የኤርምያስ ትንበያዎች እንዴት በትክክል ፍጻሜያቸውን እንዳገኙ ለማስተዋል የሚቸገር ሰው አይኖርም።” በግልጽ መረዳት እንደሚቻለው በኢሳይያስ ዘመን ባቢሎን እንደምትወድቅና በመጨረሻም ባድማ እንደምትሆን ሊተነብይ የሚችል አንድም ሰው አልነበረም። ደግሞም ባቢሎን በሜዶንና በፋርስ እጅ የወደቀችው ኢሳይያስ መጽሐፉን ከጻፈ ከ200 ዓመት በኋላ ነው! ሙሉ በሙሉ የወደመችው ደግሞ ከብዙ መቶ ዓመታት በኋላ ነው። ታዲያ ይህ ነገር መጽሐፍ ቅዱስ የአምላክ ቃል ስለመሆኑ ያለንን እምነት የሚያጠናክር አይደለምን? (2 ጢሞቴዎስ 3:​16) ከዚህም በላይ ይሖዋ ጥንት ትንቢቶች እንዲፈጸሙ እንዳደረገ ሁሉ እስካሁን ፍጻሜያቸውን ያላገኙት የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶችም አምላክ በፈቀደው ጊዜ እንደሚፈጸሙ ትምክህት ሊኖረን ይችላል።

ከመከራ ያሳርፍሃል’

17, 18. የባቢሎን ሽንፈት ለእስራኤል በረከት የሚሆነው እንዴት ነው?

17 የባቢሎን መውደቅ ለእስራኤል እፎይታ ነው። ከምርኮ ነፃ ወጥተው ወደ ተስፋይቱ ምድር የመመለስ አጋጣሚ ይከፍትላቸዋል። በመሆኑም ኢሳይያስ እንዲህ ይላል:- “እግዚአብሔርም ያዕቆብን ይምረዋል፣ እስራኤልንም ደግሞ ይመርጠዋል፣ በአገራቸውም ያኖራቸዋል፤ መጻተኛም ከእርሱ ጋር ይተባበራል፣ ከያዕቆብም ቤት ጋር ይጣበቃል። አሕዛብም ይዘው ወደ ስፍራቸው ያመጡአቸዋል፣ የእስራኤልም ቤት በእግዚአብሔር ምድር እንደ ሎሌዎችና እንደ ገረዶች አድርገው ይገዙአቸዋል፤ የማረኩአቸውን ይማርካሉ፣ አስጨናቂዎችንም ይገዛሉ።” (ኢሳይያስ 14:​1, 2) እዚህ ላይ “ያዕቆብ” የሚለው መጠሪያ መላውን የእስራኤል 12 ነገድ የሚያመለክት ነው። ይሖዋ ብሔሩ ወደ ምድሩ እንዲመለስ በማድረግ ‘ለያዕቆብ’ ምሕረቱን ያሳያል። ከእነርሱ ጋር በሺህ የሚቆጠሩ መጻተኞች አብረው የሚሄዱ ሲሆን ብዙዎቹም እስራኤላውያንን በቤተ መቅደስ ያገለግላሉ። እንዲያውም አንዳንድ እስራኤላውያን በቀድሞ ማራኪዎቻቸው ላይ የሚገዙ ባለ ሥልጣናት ይሆናሉ። *

18 በግዞት የነበረው ስቃይና መከራ ያከትማል። በምትኩ ይሖዋ ሕዝቡን ‘ከኀዘናቸውና ከመከራቸው ከተገዙለትም ከጽኑ ባርነት ያሳርፋቸዋል።’ (ኢሳይያስ 14:​3) እስራኤላውያን ከባርነት ቀንበር ነፃ ስለወጡ የሐሰት አማልክትን በሚያገለግሉ ሰዎች መካከል ተቀምጠው ከሚደርስባቸው ኃዘንና መከራ ይገላገላሉ። (ዕዝራ 3:​1፤ ኢሳይያስ 32:​18) ላንድስ ኤንድ ፒፕልስ ኦቭ ዘ ባይብል የተባለው መጽሐፍ በዚህ ጉዳይ ላይ አስተያየቱን ሲሰጥ እንዲህ ይላል:- “ለአንድ ባቢሎናዊ፣ በመጥፎ ምግባር ረገድ ሲመዘኑ አማልክቱ ራሳቸው ከራሱ ከግለሰቡ የተለዩ አልነበሩም። ፈሪዎች፣ ሰካራሞችና ጅላጅል ነበሩ።” እንዲህ ካለ የተበላሸ ሃይማኖታዊ ኅብረተሰብ መገላገል እንዴት ትልቅ እፎይታ ነው!

19. እስራኤል የይሖዋን ይቅርታ ለማግኘት ምን ማድረግ ያስፈልጋት ነበር? እኛስ ከዚህ ምን እንማራለን?

19 ይሁን እንጂ የይሖዋን ምሕረት እንዲሁ ያገኛሉ ማለት አልነበረም። ከአምላክ ዘንድ ከባድ ቅጣት ላስከተለባቸው የክፋት ድርጊታቸው መጸጸታቸውን ሊያሳዩ ይገባ ነበር። (ኤርምያስ 3:​25) ምንም ሳያስቀሩ ከልብ መናዘዝ የይሖዋን ይቅርታ ያስገኝላቸዋል። (ነህምያ 9:​6-37⁠ንና ዳንኤል 9:​5ን ተመልከት።) ይኸው መሠረታዊ ሥርዓት ዛሬም ይሠራል። ‘የማይበድል ሰው ስለሌለ’ ሁላችንም የይሖዋ ምሕረት ያስፈልገናል። (2 ዜና መዋዕል 6:​36) መሐሪ የሆነው አምላክ ይሖዋ ፈውስ እናገኝ ዘንድ ኃጢአታችንን ለእርሱ እንድንናዘዝ፣ ንስሐ እንድንገባ እንዲሁም ክፉ ድርጊታችንን እንድንተው ፍቅራዊ ግብዣ ያቀርብልናል። (ዘዳግም 4:​31፤ ኢሳይያስ 1:​18፤ ያዕቆብ 5:​16) ይህ መልሰን ሞገሱን እንድናገኝ ብቻ ሳይሆን እንድንጽናናም ይረዳናል።​—⁠መዝሙር 51:​1፤ ምሳሌ 28:​13፤ 2 ቆሮንቶስ 2:​7

ስለ ባቢሎን የተነገረ “ምሳሌ”

20, 21. የባቢሎን ጎረቤቶች በእርሷ መውደቅ ደስ የሚላቸው እንዴት ነው?

20 ኢሳይያስ ባቢሎን የዓለም ልዕለ ኃያል ሆና ከመነሳቷ ከ100 ከሚበልጡ ዓመታት በፊት ለእርሷ መውደቅ ዓለም የሚሰጠውን ምላሽ በተመለከተ ተንብዮአል። ከእርሷ ግዞት ነፃ ለወጡት እስራኤላውያን እንዲህ የሚል ትንቢታዊ ትእዛዝ አስተላልፏል:- “ይህንም ምሳሌ በባቢሎን ንጉሥ ላይ ታነሣለህ እንዲህም ትላለህ:- አስጨናቂ እንዴት ዐረፈ! አስገባሪም እንዴት ጸጥ አለ! አሕዛብንም በመዓትና በማያቋርጥ መምታት የመታውን፣ አሕዛብንም ባልተከለከለ መከራ በቁጣው የገዛውን የኀጥኣንን በትር የአለቆችንም ዘንግ እግዚአብሔር ሰብሮአል።” (ኢሳይያስ 14:​4-6) ባቢሎን ድል አድራጊና ነፃውን ሕዝብ በባርነት ቀንበር ሥር የምታስገባ ጨቋኝ ገዥ ነች የሚል ገናና ስም አትርፋ ነበር። እንግዲያው በታላቂቷ ከተማ የክብር ዘመን በሥልጣን ላይ ስለነበረው ማለትም በናቡከደነፆር ተጀምሮ በናቦኒደስና በብልጣሶር ስለተቋጨው የባቢሎን ሥርወ መንግሥት ምሳሌ በመናገር በእርስዋ መውደቅ የተሰማቸውን ደስታ መግለጻቸው ምንኛ ተስማሚ ነበር!

21 የእርሷ መውደቅ ያመጣው ለውጥ እንዴት ታላቅ ነው! “ምድርም ሁሉ ዐርፋ በጸጥታ ተቀምጣለች እልልም ብላለች። ጥድና የሊባኖስ ዝግባ:- አንተ ከተዋረድህ ጀምሮ ማንም ይቈርጠን ዘንድ አልወጣብንም ብለው በአንተ ደስ አላቸው።” (ኢሳይያስ 14:​7, 8) በዙሪያቸው የነበሩት የአሕዛብ ነገሥታት የባቢሎን መሪዎች እየቆረጡ ለራሳቸው ዓላማ እንደሚገለገሉባቸው ዛፎች ሆነው ነበር። አሁን ያ ሁሉ ነገር አክትሟል። የባቢሎናውያን ዛፍ ቆረጣ አብቅቷል!

22. በምሳሌያዊ አገላለጽ የባቢሎናዊው ሥርወ መንግሥት ውድቀት በሲኦል ላይ ተጽዕኖ የነበረው እንዴት ነው?

22 የባቢሎን መውደቅ በጣም አስገራሚ ከመሆኑ የተነሣ መቃብሩ ራሱ ዝም አይልም:- “ሲኦል በመምጣትህ ልትገናኝህ በታች ታወከች፤ የሞቱትንም፣ የምድርን ታላላቆች ሁሉ፣ ለአንተ አንቀሳቀሰች፣ የአሕዛብንም ነገሥታት ሁሉ ከዙፋኖቻቸው አስነሣች። እነዚህ ሁሉ:- አንተ ደግሞ እንደ እኛ ደክመሃልን? እኛንስ መስለሃልን? ጌጥህና የበገናህ ድምፅ ወደ ሲኦል ወረደ፤ በበታችህም ብል ተነጥፎአል፣ ትልም መደረቢያህ ሆኖአል ብለው ይመልሱልሃል።” (ኢሳይያስ 14:​9-11) እንዴት ኃይለኛ የሆነ ምሳሌያዊ አገላለጽ ነው! የሰው ዘር የጋራ መቃብር ከባቢሎናውያን ሥርወ መንግሥት ቀድመው ያንቀላፉትን ነገሥታት ሁሉ ቀስቅሶ አዲሱን እንግዳ እንዲቀበሉት ያደረገ ያህል ነው። በዚህ ጊዜ አንዳች ማድረግ በማይቻለውና ውድ የሆነ ምቹ ማረፊያ ሳይሆን ብል በተነጠፈለት እንዲሁም መደረቢያውም ዋጋው የከበረ የተልባ እግር ሳይሆን ትል በሆነው የባቢሎን የገዥ መደብ ላይ ያፌዙበታል።

‘እንደ ተረገጠ ሬሳ’

23, 24. የባቢሎን ነገሥታት ያሳዩት ከልክ ያለፈ ዕብሪት ምን ይመስላል?

23 ኢሳይያስ ምሳሌውን እንዲህ በማለት ይቀጥላል:- “አንተ የንጋት ልጅ አጥቢያ ኮከብ ሆይ፣ እንዴት ከሰማይ ወደቅህ! አሕዛብንም ያዋረድህ አንተ ሆይ፣ እንዴት እስከ ምድር ድረስ ተቈረጥህ!” (ኢሳይያስ 14:​12) የባቢሎን ነገሥታት በዙሪያቸው ካሉት ሁሉ በላይ ራሳቸውን ከፍ ከፍ እንዲያደርጉ የሚያነሳሳቸው በራስ ወዳድነት ላይ የተመሠረተ ኩራት ነው። ገና ጎህ ከመቅደዱ በፊት ሰማይ ላይ ፍንትው ብሎ እንደሚታይ ኮከብ ኃይልና ሥልጣናቸውን በማናለብኝነት ተጠቅመውበታል። በተለይ ለናቡከደነፆር መኩራራት ምክንያት የሆነው ኢየሩሳሌምን ድል በማድረግ አሦር ልትፈጽመው ያልቻለችውን ጀብድ መፈጸሙ ነበር። ኩሩ የነበረው የባቢሎን ሥርወ መንግሥት እንደሚከተለው ብሎ እንደተናገረ ተደርጎ በምሳሌው ውስጥ ተገልጿል:- “ወደ ሰማይ ዐርጋለሁ፣ ዙፋኔንም ከእግዚአብሔር ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አደርጋለሁ፣ በሰሜንም ዳርቻ በመሰብሰቢያ ተራራ ላይ እቀመጣለሁ፤ ከዳመናዎች ከፍታ በላይ ዐርጋለሁ፣ በልዑልም እመሰላለሁ።” (ኢሳይያስ 14:​13, 14) ከዚህ በላይ ምን ብሎ ሊታበይ ይችላል?

24 በዳዊት የንግሥና መስመር የተነሱት ነገሥታት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተገለጹት እንደ ከዋክብት ተደርገው ነው። (ዘኍልቁ 24:​17) ከዳዊት አንስቶ እነዚያ ‘ከዋክብት’ መቀመጫቸውን በጽዮን ተራራ አድርገው ገዝተዋል። ሰሎሞን ቤተ መቅደሱን በኢየሩሳሌም ከገነባ በኋላ ደግሞ ጽዮን የሚለው ስም መላዋን ከተማ የሚያመለክት ሆኗል። በሕጉ ቃል ኪዳን መሠረት እስራኤላውያን ወንዶች በሙሉ በዓመት ሦስት ጊዜ ወደ ጽዮን የመጓዝ ግዴታ ነበረባቸው። ከዚህ የተነሣ ‘መሰብሰቢያ ተራራ’ ሆኖ ነበር። ናቡከደነፆር የይሁዳን ነገሥታት በቁጥጥሩ ሥር አስገብቶ ከዚያ ተራራ ለማስወገድ ቆርጦ መነሳቱ ራሱን ከእነዚያ ‘ከዋክብት’ በላይ ለማድረግ መፈለጉን የሚያሳይ ነው። በእነርሱ ላይ ድል በመቀዳጀቱ ለይሖዋ ክብር አይሰጥም። እንዲያውም በእብሪት ራሱን በይሖዋ ቦታ ያስቀመጠ ያህል ሆኖ ነበር።

25, 26. የባቢሎናውያን ሥርወ መንግሥት መጨረሻው አሳፋሪ የሚሆነው እንዴት ነው?

25 እንግዲያው ኩሩ የሆነው የባቢሎን ሥርወ መንግሥት የሚጠብቀው ነገር ፍጹም የተገላቢጦሽ ነው! ባቢሎን ከአምላክ ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አትልም። ይልቁንም ይሖዋ እንዲህ ይላል:- “ነገር ግን ወደ ሲኦል ወደ ጉድጓዱም ጥልቅ ትወርዳለህ። የሚያዩህ ይመለከቱሃልና:- በውኑ ምድርን ያንቀጠቀጠ፣ መንግሥታትንም ያናወጠ፣ ዓለሙን ባድማ ያደረገ፣ ከተሞችንም ያፈረሰ፣ ምርኮኞቹንም ወደ ቤታቸው ያልሰደደ ሰው ይህ ነውን? ብለው ያስተውሉሃል።” (ኢሳይያስ 14:​15-17) የሥልጣን ጥም የተጠናወተው ሥርወ መንግሥት እንደ አንድ ተራ ሰው ወደ ሔድስ (ሲኦል) ይወርዳል።

26 ታዲያ መንግሥታትን ያንበረከከው፣ ፍሬያማውን ምድር ያወደመውና ስፍር ቁጥር የሌላቸውን ከተሞች የገለበጠው ኃይል የት ይገባል? ምርኮኞችን የሚያግዘውና ወደ ትውልድ አገራቸው እንዳይመለሱ አፍኖ የሚይዘው የዓለም ኃይል የት ይሄዳል? የባቢሎን የዓለም ኃይል ሌላው ቀርቶ በአግባቡ እንኳ የቀብር ሥርዓት አይከናወንለትም! ይሖዋ እንዲህ ይላል:- “የአሕዛብ ነገሥታት ሁሉ በየቤታቸው በክብር አንቀላፍተዋል። አንተ ግን እንደ ተጠላ ቅርንጫፍ ከመቃብርህ ተጥለሃል፤ በሰይፍም የተወጉት፣ ተገድለውም ወደ ጉድጓዱ ድንጋዮች የወረዱት ከድነውሃል፤ እንደ ተረገጠም ሬሳ ሆነሃል። ምድርህን አጥፍተሃልና፣ ሕዝብህንም ገድለሃልና ከእነርሱ ጋር በመቃብር በአንድነት አትሆንም፤ የክፉዎች ዘር ለዘላለም የተጠራ አይሆንም።” (ኢሳይያስ 14:​18-20) በጥንቱ ዓለም አንድ ንጉሥ በሥርዓት ሳይቀበር ቀረ ማለት ትልቅ ውርደት ነበር። ታዲያ ስለ ባቢሎን ንጉሣዊ ሥርወ መንግሥትስ ምን ማለት ይቻላል? በግለሰብ ደረጃ ግብዓተ መሬታቸው በክብር የተከናወነላቸው ነገሥታት ሊኖሩ እንደሚችሉ አይካድም። ይሁን እንጂ ከናቡከደነፆር ጀምሮ የተነሡት ነገሥታት ንጉሠ ነገሥታዊ ሥርወ መንግሥት “እንደ ተጠላ ቅርንጫፍ” ተቆጥሮ ተወግዷል። ሥርወ መንግሥቱ በውጊያ ላይ እንደሞተ እንደ አንድ ተራ እግረኛ ወታደር አስከሬን ምንም ምልክት በሌለው ጉድጓድ ውስጥ የተጣለ ያህል ነበር። እንዴት ያለ ውርደት ነው!

27. የወደፊቶቹ የባቢሎናውያን ትውልዶች በአባቶቻቸው በደል ምክንያት ስቃይ የሚደርስባቸው በምን መንገድ ነው?

27 ምሳሌው የሚደመደመው ለድል አድራጊዎቹ ሜዶንና ፋርስ ቁርጥ ያለ ትእዛዝ በማስተላለፍ ነው:- “እንዳይነሡም፣ ምድርንም እንዳይወርሱ፣ የዓለሙንም ፊት በከተሞች እንዳይሞሉ ስለ አባቶቻቸው በደል ለልጆቹ ሞትን አዘጋጁላቸው።” (ኢሳይያስ 14:​21) የባቢሎን ውድቀት ጊዜያዊ ብቻ አይሆንም። ባቢሎናዊው ሥርወ መንግሥት ከሥሩ ተነቅሎ ይወገዳል። በፍጹም እንደገና አያንሰራራም። ወደፊት የሚመጡት የባቢሎናውያን ትውልዶች ‘በአባቶቻቸው በደል’ ምክንያት መከራን ይቀበላሉ።

28. የባቢሎናውያን ነገሥታት ኃጢአት መሠረቱ ምንድን ነው? ከዚህስ ምን እንማራለን?

28 በባቢሎናዊው ሥርወ መንግሥት ላይ የተላለፈው የፍርድ ውሳኔ ለእኛ ትልቅ ትምህርት ይሆነናል። ለባቢሎናውያን ነገሥታት ኃጢአት መሠረቱ መቋጫ ያልነበረው የሥልጣን ጥማቸው ነው። (ዳንኤል 5:​23) ልባቸው የተሞላው በሥልጣን ምኞት ነበር። በሌሎች ላይ የበላይ መሆን ይፈልጉ ነበር። (ኢሳይያስ 47:​5, 6) ሰዎች ለአምላክ ሊሰጡት የሚገባውን ክብር ለራሳቸው ለማግኘት ቋምጠዋል። (ራእይ 4:​11) ይህ ደግሞ በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ያሉትን ጨምሮ በሥልጣን ላይ ላሉ ሁሉ ትልቅ ማስጠንቀቂያ ነው። የሥልጣን ጥምንና በራስ ወዳድነት ላይ የተመሠረተ ኩራት ይሖዋ በግለሰቦችም ይሁን በብሔራት ላይ ማየት የማይሻቸው ባሕርያት ናቸው።

29. የባቢሎን ገዥዎች ኩራትና የሥልጣን ጥም የምን ነገር ነጸብራቅ ነው?

29 የባቢሎን ገዥዎች ኩራት “የዚህ ዓለም አምላክ” የሆነውን የሰይጣን ዲያብሎስ መንፈስ ያንጸባረቀ ነበር። (2 ቆሮንቶስ 4:​4) እርሱም እንዲሁ ሥልጣን ለማግኘት ከመቋመጡም ሌላ ራሱን ከይሖዋ አምላክ በላይ ለማድረግ ፈልጓል። የባቢሎን ንጉሥና በእርሱ አገዛዝ ሥር የነበሩት ሰዎች ከገጠማቸው ነገር ጋር በሚመሳሰል መንገድ የሰይጣን ርኩስ ምኞት በመላው የሰው ዘር ላይ ለደረሰው መከራና ስቃይ ምክንያት ሆኗል።

30. በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሰችው ሌላዋ ባቢሎን የትኛዋ ነች? ያሳየችውስ መንፈስ ምን ዓይነት ነው?

30 ከዚህም በተጨማሪ በራእይ መጽሐፍ ውስጥ ስለ ሌላ ባቢሎን ማለትም ስለ “ታላቂቱ ባቢሎን” ተጠቅሶ እናገኛለን። (ራእይ 18:​2) ይህቺ የዓለም የሐሰት ሃይማኖት ድርጅትም በኩራት የተሞላች፣ የጭቆናና የጭካኔ መንፈስ የሚንጸባረቅባት ነች። ከዚህ የተነሣ እርሷም አምላክ በቀጠረው ጊዜ ‘የይሖዋን ቀን’ ለመቅመስ ትገደዳለች። (ኢሳይያስ 13:​6) ከ1919 ወዲህ “ታላቂቱ ባቢሎን ወደቀች” የሚለው መልእክት በምድር ሁሉ አስተጋብቷል። (ራእይ 14:​8) የወደቀችው የአምላክን ሕዝቦች በግዞት መያዟ ባከተመ ጊዜ ነው። በቅርቡ ደግሞ ሙሉ በሙሉ ትጠፋለች። የጥንቷን ባቢሎን በሚመለከት ይሖዋ እንደሚከተለው የሚል ትእዛዝ ሰጥቶ ነበር:- “በእስራኤል ቅዱስ ላይ በእግዚአብሔር ላይ ኰርታለችና እንደ ሥራዋ መጠን መልሱላት፣ እንዳደረገችም ሁሉ አድርጉባት።” (ኤርምያስ 50:​29፤ ያዕቆብ 2:​13) ታላቂቱ ባቢሎንም ተመሳሳይ ፍርድ ይጠብቃታል።

31. ታላቂቱ ባቢሎን በቅርቡ ምን ይገጥማታል?

31 በመሆኑም ይሖዋ በኢሳይያስ መጽሐፍ ውስጥ በሚገኘው በዚህ ትንቢት መጨረሻ ላይ የተናገረው ሐሳብ የሚሠራው ለጥንቷ ባቢሎን ብቻ ሳይሆን ለታላቂቱ ባቢሎንም ጭምር ነው:- “በእነርሱ ላይ እነሣለሁ . . . ከባቢሎን ስምንና ቅሬታን፣ ዘርንና ትውልድንም እቈርጣለሁ . . . የጃርት መኖርያ የውኃም መቋሚያ አደርጋታለሁ፤ በጥፋትም መጥረጊያ እጠርጋታለሁ።” (ኢሳይያስ 14:​22, 23) የጠፋችው የጥንቷ ባቢሎን ፍርስራሽ ይሖዋ በቅርቡ በታላቂቱ ባቢሎን ላይ ምን እንደሚያደርግባት የሚያመለክት ነው። እውነተኛውን አምልኮ ለሚያፈቅሩ ሁሉ እንዴት ያለ ማጽናኛ ነው! እንደ ኩራት፣ ዕብሪት ወይም ጭካኔ ያሉት የሰይጣን ባሕርያት በውስጣችን እንዳያቆጠቁጡ እንድንታገል የሚያነሳሳ እንዴት ያለ ጥሩ ማበረታቻ ነው!

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.10 ኢሳይያስ በስም የጠቀሰው ሜዶንን ብቻ ነው። ይሁን እንጂ በባቢሎን ላይ አብረው የሚነሱት ነገሥታት በርከት ያሉ ሲሆኑ እነርሱም ሜዶን፣ ፋርስ፣ ኤላም እና ሌሎችም ትናንሽ ብሔራት ናቸው። (ኤርምያስ 50:​9፤ 51:​24, 27, 28) በአካባቢው የነበሩት አገሮች ሜዶንንና ፋርስን የሚጠሯቸው “ሜዶን” ብለው ነበር። ደግሞም በኢሳይያስ ዘመን ገናና ኃይል የነበረችው ሜዶን ናት። ፋርስ ኃያል ሆና ብቅ ያለችው በቂሮስ የግዛት ዘመን ነው።

^ አን.12 ይሁን እንጂ ከጊዜ በኋላ ሜዶናውያንና ፋርሳውያን ከፍተኛ የቅንጦት ፍቅር ያደረባቸው ይመስላል።​—⁠አስቴር 1:​1-7

^ አን.17 ለምሳሌ ያህል ዳንኤል በሜዶንና ፋርስ መንግሥት ሥር የባቢሎን ከፍተኛ ባለ ሥልጣን ሆኖ ተሾሞ ነበር። ከ60 ዓመታት ገደማ በኋላ ደግሞ አስቴር የፋርሱ ንጉሥ የአሕሻዊሮስ ንግሥት ሆና የነበረ ሲሆን መርዶክዮስ በመላው የፋርስ ግዛት ላይ ጠቅላይ ሚንስትር ሆኖ ተሾሞ ነበር።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 178 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የወደቀችው ባቢሎን የምድረ በዳ ፍጥረታት መፈንጫ ትሆናለች

[በገጽ 186 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

እንደ ጥንቷ ባቢሎን ሁሉ ታላቂቱ ባቢሎንም የፍርስራሽ ክምር ትሆናለች