በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለአሕዛብ የፈነጠቀ ብርሃን

ለአሕዛብ የፈነጠቀ ብርሃን

ምዕራፍ ሃያ ስምንት

ለአሕዛብ የፈነጠቀ ብርሃን

ኢሳይያስ 66:​15-24

1, 2. ብርሃን በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? በዛሬው ጊዜ ምድርን የሸፈነው ምን ዓይነት ጨለማ ነው?

ይሖዋ “ፀሐይን በቀን የጨረቃንና የከዋክብትን ሥርዓት በሌሊት ብርሃን አድርጎ የሚሰጥ” የብርሃን ምንጭ ነው። (ኤርምያስ 31:​35) ብርሃን ሕይወት በመሆኑ ብቻ እንኳ ይሖዋ የሕይወት ምንጭ መሆኑን አምነን ልንቀበል ይገባል። ምድር የፀሐይን ብርሃንና ሙቀት ያለማቋረጥ ባታገኝ ኖሮ በምድር ላይ መኖር እንደማይቻል የታወቀ ነው። ፕላኔታችን ሕይወት አልባ ትሆን ነበር።

2 ስለዚህ ይሖዋ እኛ የምንኖርበትን ዘመን አሻግሮ በመመልከት የብርሃን ሳይሆን የጨለማ ዘመን እንደሚሆን መተንበዩ ትኩረታችንን በእጅጉ ሊስበው ይገባል። ኢሳይያስ በመንፈስ አነሳሽነት “እነሆ፣ ጨለማ ምድርን ድቅድቅ ጨለማም አሕዛብን ይሸፍናል” ሲል ጽፏል። (ኢሳይያስ 60:2) እነዚህ ቃላት መንፈሳዊውን ጨለማ የሚያመለክቱ ቢሆንም እንኳ ያዘሉትን ቁም ነገር አቅልለን ልንመለከተው አይገባም። የፀሐይ ብርሃን የማያገኙ ሰዎች መኖር እንደማይችሉ ሁሉ መንፈሳዊ ብርሃን የማያገኙ ሰዎችም ውሎ አድሮ ከሕልውና ውጪ መሆናቸው አይቀርም።

3. በዚህ የጨለማ ዘመን ብርሃን ልናገኝ የምንችለው ከማን ነው?

3 በዚህ የጨለማ ዘመን ውስጥ ይሖዋ የሚሰጠንን መንፈሳዊ ብርሃን ቸል ብንል ለአደጋ እንጋለጣለን። መጽሐፍ ቅዱስን በተቻለ መጠን በየዕለቱ በማንበብ የአምላክን ቃል ለመንገዳችን ብርሃን አድርገን መጠቀም ይኖርብናል። (መዝሙር 119:​105) ክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ‘ከጻድቃን መንገድ’ እንዳንወጣ እርስ በርስ ለመበረታታት የሚያስችሉ አጋጣሚዎችን ይፈጥሩልናል። (ምሳሌ 4:​18፤ ዕብራውያን 10:​23-25) ትጋት በተሞላበት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትና ገንቢ በሆነ ክርስቲያናዊ ወዳጅነት አማካኝነት የምናገኘው ጥንካሬ በዚህ ‘የመጨረሻ ዘመን’ ጨለማ እንዳንዋጥ ይረዳናል። ይህ ‘የመጨረሻ ዘመን’ ‘በእግዚአብሔር ታላቅ የቁጣ ቀን’ ይደመደማል። (2 ጢሞቴዎስ 3:​1፤ ሶፎንያስ 2:​3) ያ ቀን በጣም እየቀረበ ነው! በጥንቷ ኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ላይ የጥፋት ቀን እንደመጣ ሁሉ በዚህ ዘመንም በትንቢት የተነገረው የይሖዋ የቁጣ ቀን እንደሚመጣ ምንም ጥርጥር የለውም።

ይሖዋ “ይፈርዳል”

4, 5. (ሀ) ይሖዋ በኢየሩሳሌም ላይ የሚመጣው በምን መንገድ ነው? (ለ) በ607 ከዘአበ በኢየሩሳሌም ላይ ከሚደርሰው ጥፋት የሚተርፉት ሰዎች ቁጥር በአንጻራዊ ሁኔታ ሲታይ አነስተኛ ይሆናል ብለን መደምደም የምንችለው ለምንድን ነው? (የግርጌ ማስታወሻውን ተመልከት።)

4 ይሖዋ እጅግ አስደሳች በሆነው የኢሳይያስ ትንቢት የመደምደሚያ ቁጥሮች ላይ የቁጣው ቀን ሲቃረብ የሚከናወኑትን ነገሮች ቁልጭ አድርጎ ገልጿል። ዘገባው እንዲህ ይላል:- “እግዚአብሔር መዓቱን በቁጣ፣ ዘለፋውንም በእሳት ነበልባል ይመልስ ዘንድ ከእሳት ጋር ይመጣል፣ ሰረገሎቹም እንደ ዐውሎ ነፋስ ይሆናሉ። እግዚአብሔርም በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ በእሳትና በሰይፉ ይፈርዳል፤ በእግዚአብሔርም ተወግተው የሞቱት ይበዛሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 66:15, 16

5 እነዚህ ቃላት በኢሳይያስ ዘመን የነበሩት ሰዎች ያሉበትን አሳሳቢ ሁኔታ እንዲገነዘቡ ሊያደርጓቸው ይገባል። ባቢሎናውያን የይሖዋን ፍርድ በኢየሩሳሌም ላይ ለማስፈጸም የሚመጡበት ጊዜ ተቃርቧል። ሰረገሎቻቸው እንደ ዐውሎ ነፋስ አቧራውን እያቦነኑ ወደ ኢየሩሳሌም ይገሰግሳሉ። እንዴት የሚያስፈራ ነው! ይሖዋ ወራሪዎቹን በመጠቀም ከሃዲ በሆኑ “ሥጋ ለባሽ” አይሁዳውያን ሁሉ ላይ እሳታማ ፍርዱን ያስፈጽማል። ይሖዋ ራሱ ሕዝቡን የተዋጋ ያህል ይሆናል። ‘ቁጣው’ አይመለስም። በርካታ አይሁዳውያን ‘በእግዚአብሔር ተወግተው ይሞታሉ።’ በ607 ከዘአበ ይህ ትንቢት ፍጻሜውን አግኝቷል። *

6. ይሁዳ ውስጥ ምን አስከፊ ድርጊቶች ይፈጸማሉ?

6 ይሖዋ በሕዝቡ ላይ ‘መፍረዱ’ ተገቢ ነውን? እንዴታ! የኢሳይያስን መጽሐፍ ስንመረምር በተደጋጋሚ ጊዜያት እንደተመለከትነው አይሁዳውያን ራሳቸውን ለይሖዋ የወሰኑ ሕዝቦች እንደሆኑ ተደርገው ይታዩ የነበረ ቢሆንም እንኳ በሐሰት አምልኮ ተዘፍቀዋል። ይህ ድርጊታቸው ደግሞ ከይሖዋ የተሰወረ አልነበረም። የሚከተሉት የትንቢቱ ቃላትም ይህንኑ ሁኔታ የሚጠቁሙ ናቸው:- “በመካከላቸው ያለውን አንዱን ተከትለው ወደ ገነቱ ይገቡ ዘንድ ሰውነታቸውን የሚቀድሱና የሚያነጹ፣ የእሪያንም ሥጋ አስጸያፊ ነገርንም አይጥንም የሚበሉ በአንድነት ይጠፋሉ፣ ይላል እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 66:17) እነዚህ አይሁዳውያን ‘ሰውነታቸውን የሚቀድሱትና የሚያነጹት’ ራሳቸውን ለንጹሕ አምልኮ ለማዘጋጀት ነውን? በፍጹም። ከዚህ ይልቅ ለየት ባሉ የአትክልት ሥፍራዎች በሚደረጉ የአረማውያን የመንጻት ሥነ ሥርዓቶች መካፈላቸው ነው። ከዚያ በኋላ የእሪያ ሥጋንና በሙሴ ሕግ እንደ ርኩስ የሚቆጠሩ ሌሎች ፍጥረታትን በመስገብገብ ጥርግ አድርገው ይበላሉ።​—⁠ዘሌዋውያን 11:​7, 21-23

7. ሕዝበ ክርስትና ጣዖት አምላኪ ከነበረችው ከይሁዳ ጋር የምትመሳሰለው እንዴት ነው?

7 ከእውነተኛው አምላክ ጋር በቃል ኪዳን የተሳሰረ ሕዝብ እንዲህ ያለ ድርጊት መፈጸሙ ምንኛ አስጸያፊ ነው! ይሁን እንጂ በዛሬው ጊዜ በሕዝበ ክርስትና ሃይማኖቶች ውስጥም ከዚህ የማይተናነስ ጸያፍ ድርጊት እንደሚፈጸም ሊስተዋል ይገባል። የሕዝበ ክርስትና አባላትም አምላክን እናገለግላለን ይላሉ። በተጨማሪም መሪዎቻቸው ለአምላክ ያደሩ መስለው ለመታየት ይሞክራሉ። ይሁንና በአረማዊ ትምህርቶችና ወጎች ራሳቸውን ያረክሳሉ። ይህም ድቅድቅ በሆነ መንፈሳዊ ጨለማ ውስጥ እንዳሉ በግልጽ ያሳያል።​—⁠ማቴዎስ 6:​23፤ ዮሐንስ 3:​19, 20

‘ክብሬን ያያሉ’

8. (ሀ) ይሁዳም ሆነች ሕዝበ ክርስትና ምን ይደርስባቸዋል? (ለ) አሕዛብ ‘የይሖዋን ክብር የሚያዩት’ በምን መንገድ ነው?

8 ይሖዋ ሕዝበ ክርስትና የምትፈጽማቸውን ጸያፍ ድርጊቶችና የምታስተምራቸውን የሐሰት ትምህርቶች ይመለከታልን? ኢሳይያስ የመዘገባቸውን የሚከተሉትን የይሖዋ ቃላት ካነበብክ በኋላ ምን መደምደሚያ ላይ እንደምትደርስ ተመልከት:- “ሥራቸውንና አሳባቸውን አውቄአለሁና፤ አሕዛብንና ልሳናትን ሁሉ የምሰበስብበት ጊዜ ይደርሳል፣ እነርሱም ይመጣሉ ክብሬንም ያያሉ።” (ኢሳይያስ 66:18) ይሖዋ አገልጋዮቹ ነን የሚሉት ሰዎች የሚያደርጉትን ብቻ ሳይሆን የሚያስቡትንም ጭምር የሚያውቅ ከመሆኑም በላይ ፍርድ ለመስጠት ተዘጋጅቷል። ይሁዳ በይሖዋ እንደምታምን ብትናገርም ከጣዖት አምልኮ ጋር በተያያዘ የምትፈጽማቸው ድርጊቶችና ከአረማውያን የወረሰቻቸው ልማዶች ቃል አባይ መሆኗን ያሳያሉ። ነዋሪዎቿ በአረማውያን ሥርዓቶች ራሳቸውን “ለማንጻት” መሞከራቸው ምንም ፋይዳ የለውም። ሕዝቡ ጥፋት የሚጠብቀው ሲሆን የሚደርስበትን ጥፋት ደግሞ በአካባቢው ያሉት ጣዖት አምላኪ አሕዛብ ያያሉ። እነዚህ አሕዛብ በዚያ ወቅት የሚፈጸሙትን ነገሮች ስለሚመለከቱና የይሖዋ ቃል መፈጸሙን አምነው ለመቀበል ስለሚገደዱ ‘የይሖዋን ክብር ያያሉ’ ሊባል ይችላል። ይህ በሕዝበ ክርስትና ላይ ፍጻሜውን የሚያገኘው እንዴት ነው? ጥፋት በሚደርስባት ጊዜ ከቀድሞ ወዳጆቿና የንግድ ሸሪኮቿ መካከል ብዙዎቹ የይሖዋ ቃል ፍጻሜውን ሲያገኝ ከዳር ቆመው ለማየት ይገደዳሉ።​—⁠ኤርምያስ 25:​31-33፤ ራእይ 17:​15-18፤ 18:​9-19

9. ይሖዋ ምን ምሥራች ተናገረ?

9 ኢየሩሳሌም በ607 ከዘአበ ስትጠፋ ይሖዋ በምድር ላይ ያሉትን ምሥክሮቹን በሙሉ ያጣል ማለት ነውን? እንደዚያ ማለት አይደለም። ከአቋማቸው ንቅንቅ ሳይሉ በመጽናት ረገድ ግሩም ምሳሌ የሚሆኑ እንደ ዳንኤልና ሦስቱ ጓደኞቹ ያሉ ሰዎች በባቢሎን ግዞተኞች ከሆኑም በኋላ እንኳ ይሖዋን ማገልገላቸውን አይተዉም። (ዳንኤል 1:​6, 7) አዎን፣ ይሖዋ በቀጣዮቹም ጊዜያት ቢሆን ታማኝ ምሥክሮች የሚኖሩት ሲሆን 70ዎቹ ዓመታት ሲገባደዱ ታማኝ ወንዶችና ሴቶች ባቢሎንን ለቅቀው ወደ ይሁዳ በመመለስ ንጹሑን አምልኮ መልሰው ያቋቁማሉ። ይሖዋም በመቀጠል የጠቆመው ይህንኑ ሐሳብ ነው:- “በመካከላቸውም ምልክት አደርጋለሁ፣ ከእነርሱም የዳኑትን ዝናዬን ወዳልሰሙ፣ ክብሬንም ወዳላዩ ወደ አሕዛብ ወደ ተርሴስ ወደ ፉጥ ወደ ሉድ ወደ ሞሳሕ ወደ ቶቤል ወደ ያዋን በሩቅ ወዳሉ ደሴቶች እልካቸዋለሁ፣ በአሕዛብም መካከል ክብሬንም ይናገራሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 66:19

10. (ሀ) ከባቢሎን ነፃ የሚወጡት ታማኝ አይሁዳውያን ምልክት ሆነው የሚያገለግሉት በምን መንገድ ነው? (ለ) በዛሬው ጊዜ ምልክት ሆነው የሚያገለግሉት እነማን ናቸው?

10 በ537 ከዘአበ ወደ ኢየሩሳሌም የሚመለሱት ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ታማኝ ወንዶችና ሴቶች አስደናቂ ምልክት ማለትም ይሖዋ ሕዝቡን ነፃ እንዳወጣ በግልጽ የሚያሳዩ ጥሩ ማስረጃዎች ይሆናሉ። ግዞተኞቹ አይሁዳውያን አንድ ቀን ነፃ ወጥተው በይሖዋ ቤተ መቅደስ ንጹሕ አምልኮ ያቀርባሉ ብሎ ያሰበ ማን ነበር? በተመሳሳይም በመጀመሪያው መቶ ዘመን ቅቡዓን ክርስቲያኖች “ምልክትና ተአምራት” ሆነው ያገለገሉ ሲሆን ይሖዋን ለማገልገል የሚፈልጉ ቅን ሰዎች ወደ እነዚህ ቅቡዓን ክርስቲያኖች ጎርፈዋል። (ኢሳይያስ 8:​18፤ ዕብራውያን 2:​13) በዛሬው ጊዜ ቅቡዓን ክርስቲያኖች ዳግመኛ በወረሱት ምድር ላይ በመስፋፋት አስደናቂ ምልክት ሆነው ያገለግላሉ። (ኢሳይያስ 66:​8) እነዚህ ክርስቲያኖች የይሖዋ መንፈስ አምላክን ለማገልገል የሚፈልጉ ቅን ልብ ያላቸውን ሰዎች የመሳብ ኃይል እንዳለው የሚያሳዩ ሕያው ማስረጃዎች ናቸው።

11. (ሀ) አይሁዳውያን ቀድሞ ወደነበሩበት ሁኔታ ከተመለሱ በኋላ አሕዛብ ስለ ይሖዋ ማወቅ የሚችሉት እንዴት ነው? (ለ) ዘካርያስ 8:​23 የመጀመሪያ ፍጻሜውን ያገኘው እንዴት ነው?

11 ይሁንና በ537 ከዘአበ አይሁዳውያን ወደ ትውልድ አገራቸው ከተመለሱ ይሖዋን የማያውቁ አሕዛብ ስለ ይሖዋ እንዴት ሊሰሙ ይችላሉ? ከባቢሎን ግዞት ነፃ ከወጡ በኋላ ታማኝ ከሆኑት አይሁዳውያን መካከል ወደ ኢየሩሳሌም የማይመለሱ ሰዎች ይኖራሉ። እንደ ዳንኤል ያሉ አንዳንድ ሰዎች እዚያው ባቢሎን ውስጥ ይቀራሉ። ሌሎቹ ደግሞ በአራቱም የምድር ማዕዘናት ይበተናሉ። በአምስተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ አይሁዳውያን በመላው የፋርስ ግዛት ውስጥ ይኖሩ ነበር። (አስቴር 1:​1፤ 3:​8) ከእነዚህ አይሁዳውያን መካከል አንዳንዶቹ አረማውያን ለሆኑት ጎረቤቶቻቸው ስለ ይሖዋ በመናገራቸው በፋርስ ግዛት ውስጥ ይኖሩ ከነበሩት አሕዛብ መካከል ብዙዎች ወደ ይሁዲነት ተለውጠዋል። በመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኑ ደቀ መዝሙር ፊልጶስ የሰበከለት ኢትዮጵያዊው ጃንደረባም ወደ ይሁዲነት ተለውጦ የነበረው በዚህ መንገድ ሊሆን ይችላል። (ሥራ 8:​26-40) ይህ ሁሉ ሁኔታ ነቢዩ ዘካርያስ የተናገራቸው የሚከተሉት ቃላት የመጀመሪያ ፍጻሜያቸውን እንዳገኙ የሚያሳይ ነው:- “በዚያ ዘመን ከአሕዛብ ቋንቋ ሁሉ አሥር ሰዎች የአንዱን አይሁዳዊ ሰው ልብስ ዘርፍ ይዘው:- እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር እንዳለ ሰምተናልና ከእናንተ ጋር እንሂድ ይላሉ።” (ዘካርያስ 8:23) በእርግጥም ይሖዋ ለአሕዛብ ብርሃን ልኳል!​—⁠መዝሙር 43:​3

“ለእግዚአብሔር ስጦታ” ማቅረብ

12, 13. ከ537 ከዘአበ አንስቶ ‘ወንድሞች’ ወደ ኢየሩሳሌም የሚመጡት በምን መንገድ ነው?

12 ኢየሩሳሌም ዳግመኛ ከተገነባች በኋላ ከትውልድ አገራቸው ርቀው በተለያዩ የምድር ክፍሎች ተበትነው የሚገኙ አይሁዳውያን ቀደም ሲል የነበረው የክህነት አገልግሎት እንደገና የሚቋቋምባትን የኢየሩሳሌም ከተማ የንጹሕ አምልኮ ማዕከል አድርገው ይመለከቷታል። ብዙዎቹ በከተማዋ ውስጥ በሚከበሩ ዓመታዊ በዓላት ላይ ለመገኘት ረጅም ጉዞ ያደርጋሉ። ኢሳይያስ በአምላክ መንፈስ አነሳሽነት እንዲህ ሲል ጻፈ:- “የእስራኤል ልጆች ቁርባናቸውን በጥሩ [“በንጹሕ፣” የ1980 ትርጉም ] ዕቃ አድርገው ወደ እግዚአብሔር ቤት እንደሚያመጡ፣ እንዲሁ ለእግዚአብሔር ቁርባን [“ስጦታ፣” የ1980 ትርጉም ] ይሆን ዘንድ ወንድሞቻችሁን ሁሉ፣ በፈረሶችና በሰረገሎች፣ በአልጋዎችና በበቅሎች በጠያር ግመሎችም ላይ አድርገው፣ ከአሕዛብ ሁሉ ወደ ተቀደሰው ተራራዬ ወደ ኢየሩሳሌም ያመጡአቸዋል፣ ይላል እግዚአብሔር። ካህናትና ሌዋውያን እንዲሆኑ ከእነርሱ እወስዳለሁ።”​—⁠ኢሳይያስ 66:20, 21

13 ‘ከአሕዛብ ሁሉ ከመጡት ከእነዚህ ወንድሞች’ መካከል አንዳንዶቹ በጰንጠቆስጤ ዕለት መንፈስ ቅዱስ በኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ላይ በፈሰሰ ጊዜ በቦታው ተገኝተው ነበር። ዘገባው እንዲህ ይላል:- “ከሰማይም በታች ካሉ ሕዝብ ሁሉ በጸሎት የተጉ አይሁድ በኢየሩሳሌም ይኖሩ ነበር።” (ሥራ 2:5) ወደ ኢየሩሳሌም የመጡት በአይሁድ ልማድ መሠረት የአምልኮ ሥርዓት ለመፈጸም ቢሆንም ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚገልጸውን ምሥራች ሲሰሙ ብዙዎቹ በእርሱ በማመን ተጠምቀዋል።

14, 15. (ሀ) ቅቡዓን ክርስቲያኖች ከአንደኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ተጨማሪ መንፈሳዊ ‘ወንድሞቻቸውን’ የሰበሰቡት እንዴት ነው? የተሰበሰቡት ሰዎች ‘በንጹሕ ዕቃ ላይ እንዳለ ስጦታ’ ሆነው ለይሖዋ የቀረቡትስ እንዴት ነው? (ለ) ይሖዋ አንዳንዶችን ‘ካህናት እንዲሆኑ የወሰደው’ በምን መንገድ ነው? (ሐ) መንፈሳዊ ወንድሞቻቸውን በመሰብሰቡ ሥራ ከተካፈሉት ቅቡዓን ክርስቲያኖች መካከል አንዳንዶቹ እነማን ናቸው? (በዚህ ገጽ ላይ ያለውን ሣጥን ተመልከት።)

14 ይህ ትንቢት ዘመናዊ ፍጻሜ አለውን? አዎን፣ አለው። ከአንደኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የይሖዋ ቅቡዓን አገልጋዮች የአምላክ መንግሥት በ1914 በሰማይ መቋቋሙን ከቅዱሳን ጽሑፎች ተረዱ። በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ጥልቀት ያለው ምርምር በማካሄድ ተጨማሪ የመንግሥቱ ወራሾች ወይም ‘ወንድሞች’ እንደሚሰበሰቡ ተገነዘቡ። ልበ ሙሉ የሆኑ አገልጋዮች ሁሉንም ዓይነት የመጓጓዣ መንገድ በመጠቀም የቅቡዓን ቀሪዎች አባላት የሚሆኑ ግለሰቦችን ለማግኘት ‘እስከ ምድር ዳር ድረስ’ የተጓዙ ሲሆን ከተገኙት ሰዎች መካከል አብዛኞቹ የሕዝበ ክርስትናን አብያተ ክርስቲያናት እየጣሉ የወጡ ናቸው። እነዚህ ሰዎች ከተገኙ በኋላ ለይሖዋ እንደ ስጦታ ሆነው ቀርበዋል።​—⁠ሥራ 1:​8

15 ቀደም ባሉት ዓመታት የተሰበሰቡት ቅቡዓን ክርስቲያኖች የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ካወቁ በኋላ በይሖዋ ፊት ተቀባይነት ለማግኘት ለውጥ ማድረግ እንዳለባቸው ተገንዝበዋል። ‘በንጹሕ ዕቃ ያለ ስጦታ’ ወይም ሐዋርያው ጳውሎስ እንደገለጸው ‘ለክርስቶስ ንጽሕት ድንግል’ ሆነው መቅረብ እንዲችሉ ራሳቸውን ከመንፈሳዊና ከሥነ ምግባራዊ ርኩሰቶች ለማንጻት የተለያዩ እርምጃዎችን ወስደዋል። (2 ቆሮንቶስ 11:​2) ቅቡዓን ክርስቲያኖች የተሳሳቱ መሠረተ ትምህርቶችን ከማስወገድ በተጨማሪ ከዚህ ዓለም የፖለቲካ ጉዳዮች ሙሉ በሙሉ ገለልተኛ መሆን የሚቻለው እንዴት እንደሆነ መማር አስፈልጓቸው ነበር። በ1931 አገልጋዮቹ በሚፈለገው ደረጃ ከነጹ በኋላ ይሖዋ በምሕረቱ ተገፋፍቶ የይሖዋ ምሥክሮች ሆነው ስሙን እንዲሸከሙ መብት ሰጥቷቸዋል። (ኢሳይያስ 43:​10-12) ይሁንና ይሖዋ አንዳንዶችን ‘ካህናት እንዲሆኑ የወሰደው’ በምን መንገድ ነው? እነዚህ ቅቡዓን ክርስቲያኖች በቡድን ደረጃ ለአምላክ የምሥጋና መሥዋዕት የሚያቀርቡ ‘የንጉሥ ካህናትና ቅዱስ ሕዝብ’ አባላት ሆነዋል።​—⁠1 ጴጥሮስ 2:​9፤ ኢሳይያስ 54:​1፤ ዕብራውያን 13:​15

የመሰብሰቡ ሥራ ቀጥሏል

16, 17. ‘ዘር’ የሚለው ቃል ከአንደኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ እነማንን ያመለክታል?

16 እነዚህ “የንጉሥ ካህናት” አጠቃላይ ቁጥራቸው 144, 000 ሲሆን እነሱን የመሰብሰቡ ሥራ ከጊዜ በኋላ ተጠናቅቋል። (ራእይ 7:​1-8፤ 14:​1) የመሰብሰቡ ሥራ በዚሁ አበቃ ማለት ነውን? እንደዚያ ማለት አይደለም። የኢሳይያስ ትንቢት በመቀጠል እንዲህ ይላል:- “እኔ የምሠራቸው አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር ከፊቴ ጸንተው እንደሚኖሩ፣ እንዲሁ ዘራችሁና ስማችሁ ጸንተው ይኖራሉ፣ ይላል እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 66:22) በእነዚህ ቃላት የመጀመሪያ ፍጻሜ መሠረት ከባቢሎን ግዞት የሚመለሱት አይሁዳውያን ልጆች ማሳደግ ይጀምራሉ። በመሆኑም ‘በአዲሱ ሰማይ’ ማለትም በአዲሱ የአይሁድ አስተዳደር ሥር የሚኖሩት ‘የአዲሱ ምድር’ አባላት ይኸውም ቀድሞ ወደነበሩበት ሁኔታ የሚመለሱት አይሁዳውያን ቀሪዎች ጸንተው ይኖራሉ። ይሁን እንጂ ትንቢቱ በዘመናችን እጅግ አስደናቂ በሆነ መንገድ ፍጻሜውን አግኝቷል።

17 መንፈሳዊ ወንድሞችን ያቀፈው ሕዝብ የሚያፈራው ‘ዘር’ በምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ ያላቸውን “እጅግ ብዙ ሰዎች” ያመለክታል። እነዚህ ሰዎች “ከሕዝብና ከነገድ ከወገንም ከቋንቋም” ሁሉ የተውጣጡ ሲሆኑ “በዙፋኑና በበጉ ፊት” ይቆማሉ። “ልብሳቸውንም አጥበው በበጉ ደም” ያነጻሉ። (ራእይ 7:​9-14፤ 22:​17) በዛሬው ጊዜ “እጅግ ብዙ ሰዎች” ከመንፈሳዊ ጨለማ ወጥተው ይሖዋ ወደሚሰጠው ብርሃን እየመጡ ነው። በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምኑ ከመሆኑም በላይ እንደ ቅቡዓን ወንድሞቻቸውና እህቶቻቸው መንፈሳዊና ሥነ ምግባራዊ ንጽሕናቸውን ጠብቀው ለመኖር ይጥራሉ። በቡድን ደረጃ በክርስቶስ አመራር ሥር ሆነው የሚያገለግሉ ከመሆኑም በተጨማሪ ለዘላለም “ጸንተው ይኖራሉ”!​—⁠መዝሙር 37:​11, 29

18. (ሀ) የእጅግ ብዙ ሰዎች አባላት ቅቡዓን ወንድሞቻቸው የወሰዱትን ዓይነት እርምጃ የወሰዱት እንዴት ነው? (ለ) ቅቡዓን ክርስቲያኖችና አጋሮቻቸው ይሖዋን “በየመባቻውና በየሰንበቱ” የሚያመልኩት እንዴት ነው?

18 እነዚህ ምድራዊ ተስፋ ያላቸው ትጉህ ወንዶችና ሴቶች ሥነ ምግባራዊና መንፈሳዊ ንጽሕና መጠበቅ በጣም አስፈላጊ ቢሆንም እንኳ ይሖዋን ለማስደሰት ሌላም ሊያደርጉት የሚገባ ነገር እንዳለ ይገነዘባሉ። የመሰብሰቡ ሥራ ገና ያላበቃ በመሆኑ በዚህ ሥራ እነሱም የበኩላቸውን ድርሻ ያበረክታሉ። የራእይ መጽሐፍ እነሱን አስመልክቶ የሚከተለውን ትንቢት ይናገራል:- “በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት አሉ፣ ሌሊትና ቀንም በመቅደሱ ያመልኩታል።” (ራእይ 7:15) እነዚህ ቃላት በኢሳይያስ ትንቢት መገባደጃ ላይ የሚገኘውን የሚከተለውን ጥቅስ ያስታውሱናል:- “እንዲህ ይሆናል፤ በየመባቻውና በየሰንበቱ ሥጋ ለባሽ ሁሉ በፊቴ ይሰግድ ዘንድ ዘወትር ይመጣል፣ ይላል እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 66:23) ይህ በዛሬው ጊዜ በመከናወን ላይ ነው። ቅቡዓን ክርስቲያኖችና አጋሮቻቸው የሆኑት እጅግ ብዙ ሰዎች “በየመባቻውና በየሰንበቱ” ማለትም በእያንዳንዱ ወር በየሳምንቱ ይሖዋን ለማምለክ አንድ ላይ ይሰባሰባሉ። ይህን አምልኮ ለማከናወንም በክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ የሚገኙ ከመሆኑም በላይ ለሕዝብ በሚሰጠው የምሥክርነት ሥራ ይካፈላሉ። አዘውትረው ‘ከሚመጡትና በይሖዋ ፊት ከሚሰግዱት’ መካከል ነህን? የይሖዋ ሕዝቦች ይህን ማድረጋቸው ከፍተኛ ደስታ የሚያስገኝላቸው ሲሆን የእጅግ ብዙ ሰዎች አባላት “ሥጋ ለባሽ ሁሉ” ማለትም ሕያዋን ሰዎች ሁሉ ይሖዋን “በየመባቻውና በየሰንበቱ” ለዘላለም የሚያገለግሉበትን ጊዜ በጉጉት ይጠባበቃሉ።

የአምላክ ጠላቶች ፍጻሜ

19, 20. በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን ገሃነም ለምን ዓላማ ያገለግል ነበር? ምንስ ያመለክታል?

19 በኢሳይያስ መጽሐፍ ላይ ስናደርግ የቆየነውን ጥናት ልናጠናቅቅ የቀረን አንድ ቁጥር ብቻ ነው። መጽሐፉ እንዲህ ሲል ይደመድማል:- “ወጥተውም በእኔ ያመፁብኝን ሰዎች ሬሳቸውን ያያሉ፤ ትላቸው አይሞትምና፣ እሳታቸውም አይጠፋምና፤ ለሥጋ ለባሽም ሁሉ አስጸያፊ ነገር ይሆናሉ።” (ኢሳይያስ 66:24) ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱ ለኑሮ በሚያስፈልጉ መሠረታዊ ነገሮች ብቻ እንዲረኩና የመንግሥቱን ጉዳዮች እንዲያስቀድሙ በመከራቸው ጊዜ ይህን ትንቢት ሳያስታውስ አልቀረም። እንዲህ አላቸው:- “ዓይንህ ብታሰናክልህ አውጣት፤ ሁለት ዓይን ኖሮህ ትላቸው ወደማይሞትበት እሳቱም ወደማይጠፋበት ወደ ገሃነመ እሳት ከመጣል አንዲት ዓይን ኖራህ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት ይሻልሃል።”​—⁠ማርቆስ 9:​47, 48፤ ማቴዎስ 5:​29, 30፤ 6:​33

20 ገሃነም የተባለው ቦታ ምንድን ነው? ከብዙ መቶ ዘመናት በፊት ዴቪድ ኪምሂ የተባሉ አይሁዳዊ ምሁር እንዲህ ሲሉ ጽፈው ነበር:- “በኢየሩሳሌም አቅራቢያ የሚገኝ . . . እጅግ የሚቀፍ ቦታ ሲሆን ቆሻሻና አስከሬን ይጥሉበት ነበር። በተጨማሪም ቆሻሻውንና አፅሞቹን ለማቃጠል ሲሉ ያለማቋረጥ እሳት ያነድዱበት ነበር። በመሆኑም በክፉዎች ላይ የተበየነው ፍርድ በምሳሌያዊ ሁኔታ [ገሃነም] ተብሎ ተጠርቷል።” እኚህ አይሁዳዊ ምሁር እንዳሉት ገሃነም ቆሻሻና በክብር እንዳይቀበሩ የተወሰነባቸው አስከሬኖች የሚጣሉበት ሥፍራ ከነበረ እንዲህ ያለውን ቆሻሻ ለማስወገድ ከእሳት የተሻለ ነገር አይኖርም። ከእሳት የተረፈውን ነገር ትሎቹ ይበሉታል። የአምላክ ጠላቶች በሙሉ በመጨረሻ የሚደርስባቸውን ጥፋት የሚያሳይ እንዴት ያለ ተስማሚ ምሳሌ ነው! *

21. በኢሳይያስ መጽሐፍ መደምደሚያ ላይ የተጠቀሰው ሐሳብ የሚያበረታታው እነማንን ነው? ለምንስ?

21 እጅግ አስደሳች የሆነው የኢሳይያስ ትንቢት መደምደሚያው ላይ እንደ አስከሬን፣ እሳትና ትል ያሉ ነገሮችን መጥቀሱ የመጽሐፉ አጨራረስ በጣም አስፈሪ ነው ሊያሰኘው አይችልምን? የአምላክ ቀንደኛ ጠላቶች እንዲህ ሊሰማቸው እንደሚችል የታወቀ ነው። ይሁን እንጂ ኢሳይያስ በክፉዎች ላይ የሚደርሰውን ዘላለማዊ ጥፋት አስመልክቶ የሰጠው መግለጫ ለአምላክ ወዳጆች የበለጠ ድፍረት የሚሰጥ ነው። የይሖዋ ሕዝቦች ጠላቶቻቸው ዳግመኛ እንደማይሠለጥኑባቸው የሚያረጋግጥ እንዲህ ያለ ዋስትና ማግኘት ያስፈልጋቸዋል። በአምላክ አምላኪዎች ላይ ብዙ መከራ ያደረሱትና በአምላክ ስም ላይ ከፍተኛ ነቀፋ ያመጡት እነዚህ ጠላቶች ለዘላለም ይጠፋሉ። ከዚያ በኋላ “መከራም ሁለተኛ አይነሣም።”​—⁠ናሆም 1:9

22, 23. (ሀ) የኢሳይያስ መጽሐፍን በማጥናትህ ያገኘሃቸውን አንዳንድ ጥቅሞች ግለጽ። (ለ) የኢሳይያስን መጽሐፍ ማጥናት ምን ውሳኔ ላይ እንድትደርስ ረድቶሃል? ምን ተስፋስ አለህ?

22 በኢሳይያስ መጽሐፍ ላይ ስናደርግ የቆየነውን ጥናት ስናጠቃልል የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው ይህ መጽሐፍ ያለፈ ታሪክ ብቻ እንዳልሆነና በዚህ ዘመን ላለነው ሰዎችም የሚሆን መልእክት እንደያዘ እንገነዘባለን። ኢሳይያስ የኖረበትን የጨለማ ዘመን መለስ ብለን ስናስብ ያን ዘመንና እኛ ያለንበትን ዘመን የሚያመሳስሉ ሁኔታዎች እንዳሉ እንረዳለን። የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ ሃይማኖታዊ ግብዝነት፣ የፍትሕ መዛባት እንዲሁም ታማኝና ድሃ በሆኑ ሰዎች ላይ የሚፈጸመው ግፍ በኢሳይያስ ዘመን ጎልተው የሚታዩ ችግሮች እንደነበሩ ሁሉ ዛሬም በእጅጉ ተስፋፍተው ይገኛሉ። በስድስተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ የነበሩት ታማኝ አይሁዳውያን በኢሳይያስ ትንቢት በጣም ተደስተው መሆን አለበት። እኛም በዛሬው ጊዜ ይህን መጽሐፍ ስናጠና በእጅጉ እንጽናናለን።

23 ጨለማ ምድርን ድቅድቅ ጨለማም አሕዛብን በሸፈነበት በዚህ አስጨናቂ ዘመን ይሖዋ በኢሳይያስ በኩል ለመላው የሰው ዘር የሚሆን ብርሃን በመፈንጠቁ በጣም አመስጋኞች ነን! ይህ መንፈሳዊ ብርሃን ዘራቸው ወይም ብሔራቸው ምንም ይሁን ምን በሙሉ ልባቸው ለሚቀበሉት ሰዎች ሁሉ የዘላለም ሕይወት ያስገኛል። (ሥራ 10:​34, 35) እንግዲያው ቃሉን በየዕለቱ በማንበብ፣ በቃሉ ላይ በማሰላሰልና መልእክቱን ከፍ አድርገን በመመልከት የአምላክ ቃል በሚሰጠን ብርሃን መጓዛችንን እንቀጥል። ይህ ለእኛ ዘላለማዊ በረከት ለይሖዋ ቅዱስ ስም ደግሞ ክብር ያመጣል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.5 ኤርምያስ 52:​15 ኢየሩሳሌም በባቢሎናውያን እጅ ከወደቀች በኋላ የነበረውን ሁኔታ አስመልክቶ ሲገልጽ ‘ስለ ሕዝቡ ድሆችና በከተማ ውስጥ ስለቀረው የሕዝቡ ቅሬታ ’ ተናግሯል። ቅዱሳን ጽሑፎችን ጠለቅ ብሎ ማስተዋል (እንግሊዝኛ) የተባለው መጽሐፍ ጥራዝ 1 ገጽ 415 ላይ ይህን በተመለከተ የሚከተለውን አስተያየት ይሰጣል:- “ ‘በከተማ ውስጥ የቀረው’ የሚለው አነጋገር ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ በረሃብ፣ በበሽታ ወይም በእሳት አሊያም በጦርነቱ እንዳለቀ ሊጠቁም ይችላል።”

^ አን.20 በገሃነም የሚቃጠሉት በድን አስከሬኖች እንጂ ሕያዋን ሰዎች ስላልነበሩ ገሃነም ዘላለማዊ ሥቃይን አያመለክትም።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 409 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

ከአሕዛብ ሁሉ የመጡ ለይሖዋ የቀረቡ ቅቡዕ ስጦታዎች

በ1920 ሁዋን ሙንዪስ ከዩናይትድ ስቴትስ ተነስቶ ወደ ስፔን ከዚያም ወደ አርጀንቲና በመጓዝ የቅቡዓን ክርስቲያኖች ጉባኤዎችን አቋቋመ። ሚስዮናዊው ዊልያም አር ብራውን (በአብዛኛው ባይብል ብራውን በሚለው መጠሪያው ይታወቃል) ከ1923 አንስቶ እንደ ሴራሊዮን፣ ጋና፣ ላይቤሪያ፣ ጋምቢያና ናይጄሪያ በመሳሰሉ አገሮች የመንግሥቱን መልእክት በመስበኩ የእውነት ብርሃን በምዕራብ አፍሪካ በሚገኙ ቅን ልብ ባላቸው ሰዎች ላይ ፈንጥቋል። በዚያው ዓመት ካናዳዊው ጆርጅ ያንግ ወደ ብራዚል ከዚያም ወደ አርጀንቲና፣ ኮስታሪካ፣ ፓናማ፣ ቬንዝዌላና አልፎ ተርፎም ወደ ሶቭየት ኅብረት በማቅናት ምሥራቹን ሰብኳል። ኤድዊን ስኪነርም በዚሁ ጊዜ ከእንግሊዝ ወደ ሕንድ በመርከብ በመጓዝ ለበርካታ ዓመታት የመከሩን ሥራ በትጋት ሠርቷል።

[በገጽ 411 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በጰንጠቆስጤ ዕለት የተገኙት አንዳንድ አይሁዳውያን ‘ከአሕዛብ ሁሉ የመጡ ወንድሞች’ ነበሩ

[በገጽ 413 ላይ የሚገኝ ባለ ሙሉ ገጽ ሥዕል]