በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መካኗ ሴት ሐሴት ታደርጋለች

መካኗ ሴት ሐሴት ታደርጋለች

ምዕራፍ አሥራ አምስት

መካኗ ሴት ሐሴት ታደርጋለች

ኢሳይያስ 54:​1-17

1. ሣራ ልጅ ለመውለድ ትጓጓ የነበረው ለምንድን ነው? በዚህ ረገድ የገጠማት ሁኔታስ ምን ነበር?

ሣራ ልጅ ለመውለድ በጣም ትጓጓ ስለነበረ መካን መሆኗ ከፍተኛ ሐዘን ውስጥ ከቷት ነበር። በዚያ ዘመን መካንነት እንደ አሳፋሪ ነገር ይታይ የነበረ ከመሆኑም በላይ የሣራን ሐዘን ያባባሰ አንድ ሌላ ጉዳይም ነበር። አምላክ የምድር ነገዶች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ ሲል ለባሏ ለአብርሃም የገባው ቃል ሲፈጸም ለማየት ትጓጓ ነበር። (ዘፍጥረት 12:​1-3) ይሁን እንጂ አምላክ ይህን ቃል ከገባ በኋላም ልጅ ሳያገኙ አሥርተ ዓመታት በማለፋቸው ሣራ ልጅ ሳትወልድ አረጀች። በመሆኑም ተስፋ ሳደርግ የኖርኩት እንዲያው በከንቱ ነው ብላ ሳታስብ አልቀረችም። ይሁን እንጂ አንድ ቀን ይህ ሁሉ ሐዘን በደስታ ተተካ!

2. በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 54 ላይ የተመዘገበው ትንቢት ትኩረታችንን ሊስብ የሚገባው ለምንድን ነው?

2 ሣራ ገጥሟት የነበረው አሳዛኝ ሁኔታ በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 54 ላይ የተመዘገበውን ትንቢት ማስተዋል እንድንችል ይረዳናል። በዚህ ምዕራፍ ላይ ኢየሩሳሌም ብዙ ልጆች በመውለድ ሐሴት እንደምታደርግ መካን ሴት ተደርጋ ተገልጻለች። ይሖዋ የጥንት ሕዝቦቹን በቡድን ደረጃ ሚስቱ እንደሆኑ አድርጎ በመግለጽ ለእነሱ ያለውን ጥልቅ ፍቅራዊ ስሜት አሳይቷል። ከዚህም በተጨማሪ ይህ ምዕራፍ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሰውን “ቅዱስ ምሥጢር [NW ]” አንድ በጣም አስፈላጊ የሆነ ገጽታ በሚገባ እንድንገነዘብ ይረዳናል። (ሮሜ 16:​25, 26) የዚህችን ‘ሴት’ ማንነትና የሚገጥሟትን ሁኔታዎች በተመለከተ በትንቢቱ ላይ የሠፈረው ዘገባ በዘመናችን ባለው ንጹሕ አምልኮ ላይ በጣም ጠቃሚ የሆነ ብርሃን ይፈነጥቅልናል።

‘የሴቲቱ’ ማንነት ተለይቶ ታወቀ

3. መካኗ ‘ሴት’ ሐሴት የምታደርገው ለምንድን ነው?

3 ምዕራፍ 54 መግቢያው ላይ የሚከተለውን አስደሳች መግለጫ ይሰጣል:- “አንቺ ያልወለድሽ መካን ሆይ፣ ዘምሪ፤ አንቺ ያላማጥሽ ሆይ፣ እልል በዪ፣ ጩኺም፤ ባል ካላት ይልቅ ፈት የሆነቺቱ ልጆች በዝተዋልና፣ ይላል እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 54:1) ኢሳይያስ ይህን ቃል ሲናገር እጅግ ተደስቶ መሆን አለበት! በተጨማሪም ይህ ቃል ፍጻሜውን ሲያገኝ በባቢሎን በግዞት የሚኖሩት አይሁዶች በእጅጉ እንደሚጽናኑ ጥርጥር የለውም! አይሁዶች በባቢሎን በግዞት በሚኖሩበት ዘመን ሁሉ ኢየሩሳሌም ባድማ ሆና ትቆያለች። በመሆኑም ከሰብዓዊ አመለካከት አንጻር ሲታይ አንዲት መካን ሴት በስተርጅናዋ ልጅ እወልዳለሁ ብላ እንደማትጠብቅ ሁሉ ምድሪቱም እንደገና በሰው ትሞላለች ብሎ ተስፋ ማድረግ አዳጋች ነበር። ይሁን እንጂ ይህች ‘ሴት’ ወላድ የመሆን ትልቅ በረከት ይጠብቃታል። ኢየሩሳሌም እጅግ ሐሴት ታደርጋለች። እንደገና ‘በልጆች’ ወይም በነዋሪዎች ትሞላለች።

4. (ሀ) ሐዋርያው ጳውሎስ ኢሳይያስ ምዕራፍ 54 በ537 ከዘአበ ካገኘው ፍጻሜ በላቀ ሁኔታ እንደሚፈጸም የጠቆመው እንዴት ነው? (ለ) “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” ማን ናት?

4 ኢሳይያስ ላያውቀው ቢችልም የተናገረው ትንቢት ከአንድ ጊዜ በላይ ተፈጻሚነት አለው። ሐዋርያው ጳውሎስ ኢሳይያስ ምዕራፍ 54 ላይ ያለውን ሐሳብ በመጥቀስ ይህች ‘ሴት’ ከምድራዊቷ የኢየሩሳሌም ከተማ የበለጠ ነገርን እንደምታመለክት ገልጿል። “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም ግን በነጻነት የምትኖር ናት እርስዋም እናታችን ናት” ሲል ጽፏል። (ገላትያ 4:26) “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” የተባለችው ማን ናት? በተስፋይቱ ምድር የምትገኘው የኢየሩሳሌም ከተማ እንደማትሆን የታወቀ ነው። ይህች ከተማ የምትገኘው ‘በላይ’ ማለትም በሰማያዊው ዓለም ሳይሆን በምድር ነው። “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” የአምላክ ሰማያዊት ‘ሴት’ ማለትም ኃያላን መንፈሳዊ ፍጥረታትን ያቀፈችው ድርጅቱ ነች።

5. በ⁠ገላትያ 4:​22-31 ላይ በተገለጸው ተምሳሌታዊ ድራማ መሠረት (ሀ) አብርሃም (ለ) ሣራ (ሐ) ይስሐቅ (መ) አጋር (ሠ) እስማኤል ማንን ይወክላሉ?

5 ይሁን እንጂ ይሖዋ ሰማያዊና ምድራዊ የሆኑ ሁለት ምሳሌያዊ ሴቶች እንዴት ሊኖሩት ይችላሉ? ይህ ሐሳብ እርስ በርሱ ይጋጫል ማለት ነውን? በፍጹም። ሐዋርያው ጳውሎስ የአብርሃም ቤተሰብ ትንቢታዊ አምሳያ ይህን ሁኔታ ግልጽ እንደሚያደርገው አመልክቷል። (ገላትያ 4:​22-31፤ በገጽ 218 ላይ የሚገኘውን “የአብርሃም ቤተሰብ​—⁠ትንቢታዊ አምሳያ” የሚለውን ርዕስ ተመልከት።) የአብርሃም ሚስት የሆነችው ‘ነፃይቱ ሴት’ ሣራ መንፈሳዊ ፍጥረታትን ያቀፈችውንና በሚስት የተመሰለችውን የይሖዋን ድርጅት ትወክላለች። የአብርሃም ሁለተኛ ሚስት ወይም ቁባትና ባሪያ የሆነችው አጋር ምድራዊቷን ኢየሩሳሌም ትወክላለች።

6. የአምላክ ሰማያዊት ድርጅት ለረጅም ጊዜ መካን ሆና የቆየችው በምን መንገድ ነው?

6 ይህን እንደ መነሻ ይዘን በ⁠ኢሳይያስ 54:​1 ላይ የሰፈረው ሐሳብ የያዘውን ጥልቅ ትርጉም እንመረምራለን። በርከት ላሉ አሥርተ ዓመታት መካን ሆና የኖረችው ሣራ በ90 ዓመቷ ይስሐቅን ወልዳለች። በተመሳሳይም የይሖዋ ሰማያዊት ድርጅት ለረጅም ዘመን መካን ሆና ቆይታለች። ከብዙ ዘመናት በፊት ይሖዋ “ሴቲቱ” “ዘር” እንደምታፈራ በኤድን ተስፋ ሰጥቶ ነበር። (ዘፍጥረት 3:​15) ከ2, 000 ከሚበልጡ ዓመታት በኋላ ይሖዋ የተስፋውን ዘር አስመልክቶ ከአብርሃም ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። ሆኖም የአምላክ ሰማያዊት ‘ሴት’ ይህን ዘር ለማፍራት ብዙ መቶ ዘመናት መጠበቅ አስፈልጓቷል። ያም ሆኖ በአንድ ወቅት ‘መካን የነበረችው የዚህች ሴት’ ልጆች ከሥጋዊ እስራኤል ልጆች የሚበዙበት ጊዜ ደረሰ። መካን ስለሆነችው ሴት የሚገልጸው ምሳሌ መላእክት አስቀድሞ የተነገረለት ዘር የሚገለጥበትን ጊዜ ለማየት የጓጉት ለምን እንደሆነ እንድንገነዘብ ይረዳናል። (1 ጴጥሮስ 1:​12) ይህ የሆነው መቼ ነው?

7. በ⁠ኢሳይያስ 54:​1 ላይ አስቀድሞ በተነገረው መሠረት ‘ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም’ ሐሴት ያደረገችው መቼ ነው? እንደዚያ ብለህ የመለስከውስ ለምንድን ነው?

7 ኢየሱስ ሰው ሆኖ ሲወለድ መላእክት እጅግ እንደተደሰቱ የታወቀ ነው። (ሉቃስ 2:​9-14) ይሁን እንጂ በ⁠ኢሳይያስ 54:1 ላይ አስቀድሞ የተነገረው ክስተት ይህ አይደለም። ኢየሱስ ‘የላይኛይቱ ኢየሩሳሌም’ መንፈሳዊ ልጅ የሆነው በ29 እዘአ በመንፈስ ቅዱስ በተወለደበትና አምላክ ራሱ “የምወድህ ልጄ አንተ ነህ” ብሎ በይፋ በተቀበለው ጊዜ ነው። (ማርቆስ 1:​10, 11፤ ዕብራውያን 1:​5፤ 5:​4, 5) በ⁠ኢሳይያስ 54:​1 ትንቢት ፍጻሜ መሠረት የአምላክ ሰማያዊት ‘ሴት’ ሐሴት ያደረገችው በዚያን ጊዜ ነበር። ከረጅም ዘመን ቆይታ በኋላ የተስፋውን ዘር ማለትም መሲሑን ወለደች! መካን ሆና የኖረችባቸው በርካታ መቶ ዘመናት አበቁ። ደስታዋ ግን በዚህ ብቻ የሚያበቃ አልነበረም።

መካኗ ሴት ብዙ ልጆች ትወልዳለች

8. የአምላክ ሰማያዊት ‘ሴት’ የተስፋውን ዘር ካፈራች በኋላም ሐሴት ያደረገችው ለምንድን ነው?

8 ኢየሱስ ከሞተና ከተነሳ በኋላ የአምላክ ሰማያዊት ‘ሴት’ ‘ከሙታን በኩር’ የሆነውን ይህን የአምላክ ተወዳጅ ልጅ እንደገና መቀበል በመቻሏ ሐሴት አድርጋለች። (ቆላስይስ 1:​18) ከዚያ በኋላ ተጨማሪ መንፈሳዊ ልጆች ማፍራት ጀመረች። በ33 እዘአ በጰንጠቆስጤ ዕለት 120 የሚሆኑ የኢየሱስ ተከታዮች በመንፈስ ቅዱስ በመቀባት ከክርስቶስ ጋር ተባባሪ ወራሾች ሆኑ። በዚያው ዕለት ትንሽ ቆየት ብሎ ሌሎች 3, 000 የሚሆኑ ሰዎች ተጨመሩ። (ዮሐንስ 1:​12፤ ሥራ 1:​13-15፤ 2:​1-4, 41፤ ሮሜ 8:​14-16) እነዚህን ልጆች ያቀፈው ይህ ቡድን ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ ሄደ። የሕዝበ ክርስትና ክህደት በተስፋፋባቸው በመጀመሪያዎቹ መቶ ዘመናት ይህ እድገት በጣም አዝጋሚ ሆኖ ነበር። ይሁን እንጂ በ20ኛው መቶ ዘመን ይህ ሁኔታ ተለውጧል።

9, 10. በጥንት ዘመን በድንኳን የምትኖር ሴት “የድንኳንሽን ሥፍራ አስፊ” የሚለው መመሪያ ምን ማድረግ ይጠይቅባት ነበር? እንዲህ ያለችው ሴት በዚህ ወቅት በጣም የምትደሰተው ለምንድን ነው?

9 ኢሳይያስ በመቀጠል አስደናቂ እድገት የሚታይበትን ጊዜ አስመልክቶ የሚከተለውን ትንቢት ተናገረ:- “የድንኳንሽን ስፍራ አስፊ፣ መጋረጃዎችሽንም ይዘርጉ፤ አትቈጥቢ፤ አውታሮችሽን አስረዝሚ ካስሞችሽንም አጽኚ። በቀኝና በግራ ትሰፋፊያለሽና፣ ዘርሽም አሕዛብን ይወርሳልና፣ የፈረሱትንም ከተሞች መኖሪያ ያደርጋልና። አታፍሪምና አትፍሪ፤ አትዋረጂምና አትደንግጪ፤ የሕፃንነትሽንም እፍረት ትረሺዋለሽ፣ የመበለትነትሽንም ስድብ ከእንግዲህ ወዲህ አታስቢም።”​—⁠ኢሳይያስ 54:2-4

10 እዚህ ላይ ኢየሩሳሌም ልክ እንደ ሣራ በድንኳን የምትኖር ሚስትና እናት ተደርጋ ተገልጻለች። እንዲህ ያለችው እናት ቤተሰቧ እያደገ ሲሄድ መኖሪያዋን ማስፋት ይኖርባታል። የድንኳኑን ሸራና አውታሮች ማስረዘምና ካስማዎቹን አዲስ ቦታ ላይ አጥብቃ መትከል ያስፈልጋታል። ይህ ለእሷ እጅግ አስደሳች ሥራ ነው። እንዲህ በሥራ በምትወጠርበት ጊዜ የቤተሰቡ የዘር ሃረግ ሳይቋረጥ እንዲቀጥል ማድረግ የሚችሉ ልጆች አገኝ ይሆን እያለች ትጨነቅባቸው የነበሩትን ዓመታት በቀላሉ ልትረሳ ትችላለች።

11. (ሀ) የአምላክ ሰማያዊት ‘ሴት’ በ1914 የተባረከችው እንዴት ነው? (የግርጌ ማስታወሻውን ተመልከት።) (ለ) ከ1919 ወዲህ በምድር ላይ ያሉት ቅቡዓን ምን በረከት አግኝተዋል?

11 ምድራዊቷ ኢየሩሳሌም ከባቢሎን ምርኮ ነፃ ከወጣች በኋላ እንዲህ ባለ የተሃድሶ ዘመን ተባርካ ነበር። “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” ደግሞ ይበልጥ ተባርካለች። * በተለይ ደግሞ ከ1919 ወዲህ ቅቡዓን የሆኑት ‘ዘሮቿ’ መልሰው ባገኙት መንፈሳዊ ሁኔታ በከፍተኛ ደረጃ እየተስፋፉ መጥተዋል። (ኢሳይያስ 61:​4፤ 66:​8) ቅቡዓኑ የዚህ መንፈሳዊ ቤተሰብ አባል መሆን የሚፈልጉ ሰዎችን ለማግኘት ወደ ብዙ አገሮች በመሠራጨታቸው ‘አሕዛብን ወርሰዋል።’ በዚህም ሳቢያ የላይኛይቱን ኢየሩሳሌም ቅቡዓን ልጆች በመሰብሰቡ ሥራ እጅግ ፈጣን የሆነ እድገት ተገኝቷል። የ144, 000ዎቹ አጠቃላይ ቁጥር በ1930ዎቹ አጋማሽ ላይ ተሟልቶ ያበቃ ይመስላል። (ራእይ 14:​3) ከዚያ በኋላ በምሥራቹ ስብከት አማካኝነት ቅቡዓንን የመሰብሰቡ ሥራ ያበቃ ቢሆንም እድገቱ ግን በዚህ አላቆመም።

12. ከቅቡዓኑ በተጨማሪ ከ1930ዎቹ ዓመታት ወዲህ ወደ ክርስቲያን ጉባኤ ሲሰበሰቡ የቆዩት እነማን ናቸው?

12 ኢየሱስ “ታናሽ መንጋ” ከሆኑት ቅቡዓን ወንድሞቹ በተጨማሪ ወደ እውነተኛ ክርስቲያኖች በረት መግባት ያለባቸው “ሌሎች በጎች” እንደሚኖሩት ተናግሯል። (ሉቃስ 12:​32፤ ዮሐንስ 10:​16) እነዚህ የቅቡዓኑ ታማኝ አጋሮች ‘የላይኛይቱ ኢየሩሳሌም’ ቅቡዓን ልጆች ባይሆኑም እንኳ ከረጅም ጊዜ በፊት በትንቢት የተነገረ ትልቅ ቦታ አላቸው። (ዘካርያስ 8:​23) ከ1930ዎቹ ዓመታት አንስቶ አሁን እስካለንበት ዘመን ድረስ “እጅግ ብዙ ሰዎች” የተሰበሰቡ ሲሆን ይህም ከዚህ በፊት ታይቶ የማያውቅ እድገት አስገኝቷል። (ራእይ 7:​9, 10) ዛሬ እነዚህ እጅግ ብዙ ሰዎች በሚልዮን የሚቆጠሩ ሆነዋል። በዚህ እድገት የተነሳም ተጨማሪ የመንግሥት አዳራሾች፣ የትልልቅ ስብሰባ አዳራሾችና ቅርንጫፍ ቢሮዎች መገንባት በጣም አጣዳፊ ሆኗል። የኢሳይያስ ቃላት በዘመናችን ይበልጥ ተስማሚ ሆነው ተገኝተዋል። አስቀድሞ በትንቢት የተነገረው የዚህ እድገት አካል መሆን መቻላችን እንዴት ያለ ታላቅ መብት ነው!

ለዘሮቿ እጅግ የምታስብ እናት

13, 14. (ሀ) የአምላክን ሰማያዊት “ሴት” በተመለከተ የተሰጡት አንዳንድ መግለጫዎች ምን ጥያቄ ሊያስነሱ ይችላሉ? (ለ) አምላክ በቤተሰብ መካከል ያለውን ዝምድና እንደ ምሳሌ በመጠቀም ያስተማረበት መንገድ ምን እንድናስተውል ሊያደርገን ይችላል?

13 በትንቢቱ የላቀ ፍጻሜ መሠረት ‘ሴቲቱ’ የምታመለክተው የይሖዋን ሰማያዊት ድርጅት እንደሆነ ቀደም ሲል ተመልክተናል። ሆኖም ኢሳይያስ 54:​4ን ካነበብን በኋላ መንፈሳዊ ፍጥረታትን ያቀፈችው ይህች ድርጅት ኃፍረት ወይም ስድብ የደረሰባት እንዴት እንደሆነ ጥያቄ ሊፈጠርብን ይችላል። ቀጥሎ ያሉት ቁጥሮች ይህች የአምላክ “ሴት” እንደምትጣል፣ ችግር እንደሚገጥማትና ለጥቃት እንደምትጋለጥ ይናገራሉ። አልፎ ተርፎም አምላክን ታስቆጣዋለች። ፈጽሞ ኃጢአት ሠርተው የማያውቁ ፍጹም መንፈሳዊ ፍጥረታትን ያቀፈች ድርጅት እንዴት እንዲህ ያለ ነገር ሊገጥማት ይችላል? የቤተሰብ ተፈጥሯዊ ባሕርይ ይህን ሁኔታ ግልጽ ያደርግልናል።

14 ይሖዋ ጥልቀት ያላቸውን መንፈሳዊ እውነቶች ለማስተላለፍ በባልና በሚስት እንዲሁም በእናትና በልጆች መካከል ያለውን ቤተሰባዊ ዝምድና እንደ ምሳሌ አድርጎ ይጠቀማል። ምክንያቱም እንዲህ ያሉት ተምሳሌቶች ለሰው ልጆች ትልቅ ትርጉም አላቸው። በግል ያሳለፍነው የቤተሰብ ሕይወት ምንም ዓይነት መልክ ቢኖረው ጥሩ ትዳር ወይም በወላጅና በልጅ መካከል ያለ ጥሩ ዝምድና ምን ሊመስል እንደሚችል መገመት አያዳግተንም። በመሆኑም ይሖዋ ሥፍር ቁጥር ከሌላቸው መንፈሳዊ አገልጋዮቹ ጋር ፍቅራዊ የሆነና የመተማመን መንፈስ የሰፈነበት የጠበቀ ወዳጅነት እንዳለው ለማስተማር የተጠቀመበት መንገድ እጅግ ሕያው ነው። ከዚህም በተጨማሪ ሰማያዊት ድርጅቱ በምድር ላይ ላሉት በመንፈስ የተቀቡ ዘሮቿ የምታስብ መሆኑን ያስተማረበት መንገድም በጣም የሚያስደንቅ ነው። ሰብዓዊ አገልጋዮቹ ሲሰቃዩ ‘በላይኛይቱ ኢየሩሳሌም’ የታቀፉት ታማኝ ሰማያዊ አገልጋዮቹም ይሰቃያሉ። ኢየሱስ ከዚህ ጋር በሚስማማ ሁኔታ “ከሁሉ ከሚያንሱ ከእነዚህ [በመንፈስ የተቀቡ] ወንድሞቼ ለአንዱ እንኳ ስላደረጋችሁት ለእኔ አደረጋችሁት” ሲል ተናግሯል።​—⁠ማቴዎስ 25:40

15, 16. በ⁠ኢሳይያስ 54:​5, 6 ላይ የተገለጹት ቃላት የመጀመሪያ ፍጻሜያቸው ምንድን ነው? የላቀ ፍጻሜያቸውስ?

15 እንግዲያው ስለ ይሖዋ ሰማያዊት “ሴት” የተነገረው አብዛኛው ነገር በምድራዊ ልጆቿ ላይ የሚደርሰውን ሁኔታ የሚያንጸባርቅ መሆኑ ምንም አያስደንቅም። የሚከተሉትን ቃላት ተመልከት:- “ፈጣሪሽ ባልሽ ነው፣ ስሙም የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ነው፤ የእስራኤልም ቅዱስ ታዳጊሽ ነው፣ እርሱም የምድር ሁሉ አምላክ ይባላል። እግዚአብሔር እንደ ተተወችና እንደ ተበሳጨች በልጅነትዋም እንደ ተጣለች ሚስት ጠርቶሻል፣ ይላል አምላክሽ።”​—⁠ኢሳይያስ 54:5, 6

16 እዚህ ላይ የተጠቀሰችው ሚስት ማን ነች? በመጀመሪያ ፍጻሜው መሠረት የአምላክን ሕዝቦች የምትወክለው ኢየሩሳሌም ነች። የአምላክ ሕዝቦች በባቢሎን በግዞት በሚቆዩባቸው 70 ዓመታት ይሖዋ እንደጣላቸውና ከናካቴው እንደተዋቸው ሆኖ ይሰማቸዋል። በትንቢቱ የላቀ ፍጻሜ መሠረት ደግሞ እነዚህ ቃላት ‘ላይኛይቱን ኢየሩሳሌም’ እና በ⁠ዘፍጥረት 3:​15 ፍጻሜ መሠረት ከረጅም ዘመን በኋላ “ዘር” ያፈራችበትን ሁኔታ ያመለክታሉ።

ጊዜያዊ ቅጣት፣ ዘላለማዊ በረከት

17. (ሀ) ምድራዊቷ ኢየሩሳሌም መለኮታዊ ‘ቁጣ’ የሚወርድባት እንዴት ነው? (ለ) ‘የላይኛይቱ ኢየሩሳሌም’ ልጆች ‘ቁጣ’ የደረሰባቸው እንዴት ነው?

17 ትንቢቱ በመቀጠል እንዲህ ይላል:- “ጥቂት ጊዜ ተውሁሽ፣ በታላቅም ምሕረት እሰበስብሻለሁ። በጥቂት ቁጣ [“እጅግ ስለ ተቆጣሁ፣” አ.መ.ት ] ለቅጽበተ ዓይን ፊቴን ከአንቺ ሰወርሁ፣ በዘላለምም ቸርነት እምርሻለሁ፣ ይላል ታዳጊሽ እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 54:7, 8) የአምላክ ‘ቁጣ’ በምድራዊቷ ኢየሩሳሌም ላይ የወረደው በ607 ከዘአበ የባቢሎን ኃይሎች ጥቃት በሰነዘሩባት ጊዜ ነው። በግዞት ያሳለፈቻቸው 70 ዓመታት ረጅም ሊመስሉ ይችላሉ። ሆኖም እንዲህ ያሉት ፈተናዎች ከቅጣቱ ትምህርት አግኝተው ማስተካከያ የሚያደርጉት ሰዎች ከሚያገኟቸው ዘላለማዊ በረከቶች ጋር ሲነጻጸሩ ‘ለጥቂት ጊዜ’ የሚቆዩ ናቸው። በተመሳሳይም ‘የላይኛይቱ ኢየሩሳሌም’ ቅቡዓን ልጆች ይሖዋ በታላቂቱ ባቢሎን ቆስቋሽነት በፖለቲካ ኃይሎች ጥቃት እንዲሰነዘርባቸው በፈቀደ ጊዜ መለኮታዊ ‘ቁጣ’ እንደወረደባቸው ሆኖ ተሰምቷቸዋል። ይሁን እንጂ ብዙ መንፈሳዊ በረከቶች ካገኙበት ከ1919 ወዲህ ካለው ዘመን ጋር ሲነጻጸር ተግሣጽ ያገኙበት ያ ወቅት በእርግጥም አጭር ነበር!

18. በሕዝቡ ላይ የሚነድደውን የይሖዋ ቁጣ በተመለከተ ምን መሠረታዊ ሥርዓት መማር እንችላለን? ይህስ በግለሰብ ደረጃ ሊነካን የሚችለው እንዴት ነው?

18 እነዚህ ቁጥሮች አንድ ሌላ ትልቅ እውነትም ያስገነዝቡናል። የአምላክ ቁጣ ቶሎ እንደሚያልፍና ምሕረቱ ግን ለዘላለም እንደሚኖር እንድናስተውል ያደርጉናል። ቁጣው በክፉ ድርጊት ላይ የሚነድድ ቢሆንም እንኳ ምንጊዜም ሚዛኑን የጠበቀና ዓላማ ያለው ነው። ከዚህም በተጨማሪ የይሖዋን ተግሣጽ ተቀብለን የምንስተካከል ከሆነ ቁጣው ‘በጥቂት ጊዜ’ ውስጥ ይበርዳል። በምትኩ ‘ታላቅ ምሕረት’ በማድረግ ይቅር የሚለን ከመሆኑም በላይ ፍቅራዊ ደግነቱን ያሳየናል። እነዚህ ባሕርያት ‘ዘላለማዊ’ ናቸው። እንግዲያው ኃጢአት በምንሠራበት ጊዜ ንስሐ ለመግባትና ከአምላክ ጋር ዕርቅ ለመፍጠር ከመጣር ወደ ኋላ ማለት የለብንም። የሠራነው ኃጢአት ከባድ በሚሆንበት ጊዜ ደግሞ ወዲያውኑ የጉባኤ ሽማግሌዎችን ቀርበን ማነጋገር ይኖርብናል። (ያዕቆብ 5:​14) እርግጥ ነው፣ እንዲህ ማድረጋችን ቅጣት የሚያስከትል ሊሆንና ቅጣቱን መቀበል ደግሞ ሊከብደን ይችላል። (ዕብራውያን 12:​11) ይሁን እንጂ እንዲህ ያለው ቅጣት የይሖዋ አምላክ ይቅርታ ከሚያስገኝልን ዘላለማዊ በረከት ጋር ሲነጻጸር ጊዜያዊ ነው።

19, 20. (ሀ) የቀስተ ደመናው ቃል ኪዳን ምንድን ነው? በባቢሎን ለሚኖሩት ግዞተኞችስ ምን ትርጉም አለው? (ለ) ‘የሰላሙ ቃል ኪዳን’ በዘመናችን ላሉት ቅቡዓን ክርስቲያኖች ምን ዋስትና ይሰጣል?

19 ይሖዋ በመቀጠል ለሕዝቡ አጽናኝ የሆነ ዋስትና ሰጠ:- “ይህ ለእኔ እንደ ኖኅ ውኃ ነው፤ የኖኅ ውኃ ደግሞ በምድር ላይ እንዳያልፍ እንደ ማልሁ፣ እንዲሁ አንቺን እንዳልቈጣ እንዳልዘልፍሽም ምያለሁ። ተራሮች ይፈልሳሉ፣ ኮረብቶችም ይወገዳሉ፤ ቸርነቴ ግን ከአንቺ ዘንድ አይፈልስም የሰላሜም ቃል ኪዳን አይወገድም፣ ይላል መሐሪሽ እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 54:9, 10) በምድር ላይ የጥፋት ውኃ ከደረሰ በኋላ አምላክ ከኖኅና ሕያው ከሆነ ነፍስ ሁሉ ጋር ቃል ኪዳን ገብቷል። ይህ ቃል ኪዳን የቀስተ ደመና ቃል ኪዳን በመባልም ይታወቃል። በዚህ ቃል ኪዳን አማካኝነት ይሖዋ ምድርን ዳግመኛ ዓለም አቀፍ በሆነ የጥፋት ውኃ እንደማያጠፋ ቃል ገብቷል። (ዘፍጥረት 9:​8-17) ይህ ለኢሳይያስና ለሕዝቡ ምን መልእክት የሚያስተላልፍ ነበር?

20 የሚደርስባቸው ቅጣት ማለትም ለ70 ዓመታት በባቢሎን በግዞት የሚያሳልፉት ሕይወት አንዴ ከሆነ በኋላ ዳግመኛ አይከሰትም። ከዚያ በኋላ የአምላክ ‘የሰላም ቃል ኪዳን’ ተግባር ላይ ይውላል። “ሰላም” ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል የጦርነት አለመኖርን ብቻ ሳይሆን የሁሉንም ሰው ደህንነት ጭምር የሚያመለክት ነው። አምላክ ይህን ቃል ኪዳን ፈጽሞ አያጥፍም። ለታማኝ ሕዝቦቹ የሚያሳየው ፍቅራዊ ደግነት ከኮረብቶችና ከተራሮች ይበልጥ የጸና ነው። የሚያሳዝነው ግን ውሎ አድሮ ምድራዊ ሕዝቦቹ ቃል ኪዳኑን ያፈርሳሉ። መሲሑን ለመቀበል አሻፈረን በማለት የገዛ ራሳቸውን ሰላም ያደፈርሳሉ። ‘የላይኛይቱ ኢየሩሳሌም’ ልጆች ግን እንዲህ ያለ ሁኔታ አይገጥማቸውም። ተግሣጽ የሚያገኙበት አስቸጋሪ ዘመን አንዴ ካለፈ በኋላ መለኮታዊ ጥበቃ እንደሚያገኙ ዋስትና ተሰጥቷቸዋል።

የአምላክ ሕዝብ የሚያገኘው መንፈሳዊ ደህንነት

21, 22. (ሀ) “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” እንደምትቸገርና በዐውሎ ነፋስ እንደምትናወጥ ተደርጋ የተገለጸችው ለምንድን ነው? (ለ) የአምላክ ሰማያዊት “ሴት” የምታገኘው በረከት ምድር ስላሉት ‘ዘሮቿ’ ምን ነገር ይጠቁማል?

21 ይሖዋ ታማኝ አገልጋዮቹ የሚያገኙትን ደህንነት በተመለከተ የሚከተለውን ትንቢት ተናገረ:- “አንቺ የተቸገርሽ በዐውሎ ነፋስም የተናወጥሽ ያልተጽናናሽም፣ እነሆ፣ ድንጋዮችሽን ሸላልሜ [“በጠንካራ አርማታ፣” NW ] እገነባለሁ፣ በሰንፔርም እመሠርትሻለሁ። የግንብሽንም ጉልላት በቀይ ዕንቁ፣ በሮችሽንም በሚያብረቀርቅ ዕንቁ፣ ዳርቻሽንም ሁሉ በከበሩ ድንጋዮች እሠራለሁ። ልጆችሽም ሁሉ ከእግዚአብሔር የተማሩ ይሆናሉ፣ የልጆችሽም ሰላም ብዙ ይሆናል። በጽድቅ ትታነጺያለሽ፤ ከግፍ ራቂ፣ አትፈሪምም፣ ድንጋጤም ወደ አንቺ አትቀርብም። እነሆ፣ ይሰበሰባሉ፣ ነገር ግን ከእኔ ዘንድ አይሆንም፤ በአንቺም ላይ የሚሰበሰቡ ሁሉ ከአንቺ የተነሣ ይወድቃሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 54:11-15

22 እርግጥ በመንፈሳዊው ዓለም ያለችው የይሖዋ “ሴት” ቀጥተኛ በሆነ መንገድ ችግር አልደረሰባትም ወይም በዐውሎ ነፋስ አልተናወጠችም። ይሁን እንጂ በምድር ላይ ያሉት ቅቡዓን ‘ዘሮቿ’ በተለይ ከ1918-19 ባለው ወቅት በመንፈሳዊ ግዞት በነበሩበት ጊዜ እሷም አብራ ተሠቃይታለች። በአንጻሩም የሰማያዊቷ “ሴት” ከፍ ከፍ መደረግ በምድር ያሉት ዘሮቿም ተመሳሳይ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ የሚያንጸባርቅ ነው። እንግዲያው ‘ላይኛይቱን ኢየሩሳሌም’ አስመልክቶ የተሰጠውን አስደሳች መግለጫ ልብ በል። አንድ የማመሳከሪያ ጽሑፍ እንደገለጸው በሮቿ ላይ ያሉት የከበሩ ድንጋዮች፣ በጣም ውድ የሆነው “ጠንካራ አርማታ፣” መሠረቶቿና አልፎ ተርፎም ዳርቻዎቿ “ውበትን፣ ግርማን፣ ንጽሕናን፣ ብርታትንና ጥንካሬን” ያመለክታሉ። ቅቡዓን ክርስቲያኖች እንዲህ ያለውን በረከትና አስተማማኝ ሁኔታ የሚያስገኝላቸው ነገር ምንድን ነው?

23. (ሀ) በመጨረሻው ዘመን ያሉት ቅቡዓን ክርስቲያኖች “ከእግዚአብሔር የተማሩ” መሆናቸው ምን ውጤት አስገኝቷል? (ለ) የአምላክ ሕዝቦች ‘ከከበሩ ድንጋዮች በተሠሩ ዳርቻዎች’ የተባረኩት እንዴት ነው?

23 ኢሳይያስ ምዕራፍ 54 ቁጥር 13 ሁሉም “ከእግዚአብሔር የተማሩ ይሆናሉ” በማለት መልሱን ይሰጠናል። ኢየሱስ ራሱም እነዚህን ቃላት በመጥቀስ ስለ ቅቡዓን ተከታዮቹ ተናግሯል። (ዮሐንስ 6:​45) ነቢዩ ዳንኤል በዚህ ባለንበት ‘የፍጻሜ ዘመን’ ቅቡዓን ክርስቲያኖች የተትረፈረፈ እውነተኛ እውቀትና መንፈሳዊ ማስተዋል በማግኘት እንደሚባረኩ ተንብዮአል። (ዳንኤል 12:​3, 4) እንዲህ ያለው መንፈሳዊ ማስተዋል መለኮታዊውን ትምህርት በምድር ዙሪያ በማዳረስ በታሪክ ዘመናት ሁሉ ታይቶ የማያውቀውን ታላቅ የትምህርት ዘመቻ በግንባር ቀደምትነት ለመምራት አስችሏቸዋል። (ማቴዎስ 24:​14) ከዚህም በተጨማሪ ይህ መንፈሳዊ ማስተዋል በእውነተኛና በሐሰተኛ ሃይማኖት መካከል ያለውን ልዩነት ማየት እንዲችሉ ረድቷቸዋል። ኢሳይያስ 54:​12 ‘በከበሩ ድንጋዮች ስለሚሠሩ ዳርቻዎች’ ይናገራል። ከ1919 አንስቶ ይሖዋ ቅቡዓን አገልጋዮቹ እነዚህ ዳርቻዎች ማለትም ከሐሰት ሃይማኖትና ለአምላክ ከማይታዘዙት የዚህ ዓለም ክፍሎች የሚለዩአቸው መንፈሳዊ ወሰኖች ከምንጊዜውም ይበልጥ ቁልጭ ብለው እንዲታዩአቸው የሚያደርግ ማስተዋል ሰጥቷቸዋል። (ሕዝቅኤል 44:​23፤ ዮሐንስ 17:​14፤ ያዕቆብ 1:​27) በዚህ መንገድ የአምላክ ሕዝብ ሆነው ተለይተዋል።​—⁠1 ጴጥሮስ 2:​9

24. ከይሖዋ የተማርን መሆን የምንችለው እንዴት ነው?

24 እንግዲያው እያንዳንዳችን ‘እኔ በግለሰብ ደረጃ ከይሖዋ የተማርኩ ነኝን?’ ብለን ራሳችንን መጠየቅ ይኖርብናል። እንዲህ ያለው ትምህርት እንዲሁ በራሱ የሚመጣ አይደለም። ይህን ትምህርት ለማግኘት ጥረት ማድረግ ያስፈልገናል። የአምላክን ቃል አዘውትረን የምናነብና ባነበብነው ነገር ላይ የምናሰላስል ከሆነ እንዲሁም “ታማኝና ልባም ባሪያ” የሚያዘጋጃቸውን በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረቱ ጽሑፎች በማንበብ፣ ለክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ጥሩ ዝግጅት በማድረግና በስብሰባዎቹ ላይ በመገኘት መመሪያ ለማግኘት የምንጥር ከሆነ በእርግጥም ከይሖዋ የተማርን እንሆናለን። (ማቴዎስ 24:​45-47) የተማርነውን ሥራ ላይ ለማዋል እንዲሁም በመንፈሳዊ ንቁዎችና ትጉዎች ለመሆን ከጣርን መለኮታዊው ትምህርት አምላክን በማይታዘዘው ዓለም ውስጥ ካሉት ሰዎች የተለየን መሆናችንን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል። (1 ጴጥሮስ 5:​8, 9) ከሁሉ በላይ ደግሞ ‘ወደ አምላክ እንድንቀርብ ይረዳናል።’​—⁠ያዕቆብ 1:​22-25፤ 4:​8

25. አምላክ ስለ ሰላም የገባው ቃል በዘመናችን ላሉት ሕዝቦቹ ምን ትርጉም አለው?

25 የኢሳይያስ ትንቢት ቅቡዓን ክርስቲያኖች ከፍተኛ ሰላም በማግኘትም እንደሚባረኩ ያሳያል። ይህ ማለት ምንም ዓይነት ጥቃት አይደርስባቸውም ማለት ነውን? እንደዚያ ማለት አይደለም፤ ሆኖም አምላክ እሱ ራሱ ጥቃት እንዲደርስባቸው እንደማያደርግ እንዲሁም የሚደርስባቸው ጥቃት ግቡን እንዲመታ እንደማይፈቅድ ዋስትና ሰጥቷል። ትንቢቱ እንዲህ ሲል ይገልጻል:- “እነሆ፣ ፍሙን በወናፍ የሚያናፋ ለሥራውም መሣሪያ የሚያወጣ ብረት ሠሪን እኔ ፈጥሬአለሁ፤ የሚያፈርሰውንም እንዲያጠፋ ፈጥሬአለሁ። በአንቺ ላይ የተሠራ መሣሪያ ሁሉ አይከናወንም፤ በፍርድም በሚነሣብሽ ምላስ ሁሉ ትፈርጂበታለሽ። የእግዚአብሔር ባሪያዎች ርስት ይህ ነው፣ ጽድቃቸውም ከእኔ ዘንድ ነው፣ ይላል እግዚአብሔር።”​—⁠ኢሳይያስ 54:16, 17

26. ይሖዋ የሰው ዘር ሁሉ ፈጣሪ መሆኑን ማወቃችን የሚያጽናናን ለምንድን ነው?

26 በዚህ የኢሳይያስ መጽሐፍ ምዕራፍ ውስጥ ይሖዋ ፈጣሪ መሆኑን ለሁለተኛ ጊዜ አገልጋዮቹን አሳስቧቸዋል። ቀደም ሲል ምሳሌያዊት ሚስቱን ‘ፈጣሪዋ’ እንደሆነ አሳስቧት ነበር። አሁን ደግሞ የሰው ዘር ሁሉ ፈጣሪ እንደሆነ ተናገረ። ቁጥር 16 በብረት ማቅለጫው ላይ ያለውን ፍም በወናፍ እያናፋ አጥፊ መሣሪያዎች ስለሚሠራ ብረት ሠሪና ‘ጥፋት ስለሚያደርስ’ ተዋጊ ይናገራል። እንዲህ ያሉ ሰዎች በሰብዓዊ ፍጡራን ላይ ፍርሃት ሊያሳድሩ ይችሉ ይሆናል። ይሁን እንጂ በገዛ ራሳቸው ፈጣሪ ላይ የበላይነት ሊቀዳጁ እንደሚችሉ አድርገው እንዴት ሊያስቡ ይችላሉ? ስለዚህ በዛሬው ጊዜ እጅግ አስፈሪ የሆኑ የዚህ ዓለም ኃይሎች እንኳ በይሖዋ ሕዝቦች ላይ ጥቃት በሚሰነዝሩበት ጊዜ በምንም ዓይነት መንገድ ድል ሊቀዳጁ አይችሉም።

27, 28. በእነዚህ አስቸጋሪ ጊዜያት ስለምን ነገር እርግጠኞች መሆን እንችላለን? ሰይጣን በእኛ ላይ የሚሰነዝረው ጥቃት የማይሰምረውስ ለምንድን ነው?

27 በአምላክ ሕዝቦችም ላይ ሆነ በመንፈስና በእውነት በሚያከናውኑት አምልኮ ላይ ከፍተኛ ጥፋት ያደረሰ ጥቃት የተሰነዘረበት ጊዜ አልፏል። (ዮሐንስ 4:​23, 24) ይሖዋ ታላቂቱ ባቢሎን ጊዜያዊ ስኬት ያስገኘ ጥቃት እንድትፈጽም ፈቅዶላት ነበር። “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” ለአጭር ጊዜ የስብከቱ ሥራ ሙሉ በሙሉ የቆመ እስኪመስል ድረስ በምድር ያሉት ዘሮቿ ድምፃቸው ሲጠፋ ተመልክታ ነበር። ያ ሁኔታ አይደገምም! አሁን በመንፈሳዊ ሁኔታ ፈጽሞ ድል የማይደረጉ በመሆናቸው በልጆቿ ሐሴት ታደርጋለች። (ዮሐንስ 16:​33፤ 1 ዮሐንስ 5:​4) በእነሱ ላይ ጥቃት ለመሰንዘር የተሠሩ አጥፊ መሣሪያዎች ነበሩ፤ ወደፊትም ይሠራሉ። (ራእይ 12:​17) ይሁን እንጂ እነዚህ መሣሪያዎች ከሽፈዋል ወደፊትም ይከሽፋሉ። ሰይጣን የቅቡዓን ክርስቲያኖችንና የአጋሮቻቸውን እምነትና ከፍተኛ ቅንዓት ሊያጠፋ የሚችልበት አንድም መሣሪያ የለውም። ይህ መንፈሳዊ ሰላም “የእግዚአብሔር ባሪያዎች ርስት” በመሆኑ ማንም ሊነጥቃቸው አይችልም።​—⁠መዝሙር 118:​6፤ ሮሜ 8:​38, 39

28 የሰይጣን ዓለም ምንም ነገር ቢያደርግ ራሳቸውን ለአምላክ የወሰኑ የአምላክ አገልጋዮች የሚያከናውኑትን ሥራና ዘላለማዊውን ንጹሕ አምልኮ ሊያስቆም አይችልም። ይህ ዋስትና ‘ለላይኛይቱ ኢየሩሳሌም’ ቅቡዓን ዘሮች ትልቅ ማጽናኛ ሆኖላቸዋል። የእጅግ ብዙ ሰዎች አባላትም በዚህ ዋስትና ይጽናናሉ። ስለ ይሖዋ ሰማያዊት ድርጅትና በምድር ላይ ካሉት አምላኪዎቹ ጋር ስላላት ግንኙነት ይበልጥ እያወቅን በሄድን መጠን እምነታችንም የዚያኑ ያህል እየጠነከረ ይሄዳል። እምነታችን ጠንካራ እስከሆነ ድረስ ደግሞ ሰይጣን እኛን ለማጥቃት የሚጠቀምበት ማንኛውም መሣሪያ ፋይዳ ቢስ ይሆናል!

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.11 ራእይ 12:​1-17 እንደሚገልጸው የአምላክ “ሴት” አንድ በጣም አስፈላጊ የሆነ “ዘር” ይኸውም አንድ መንፈሳዊ ልጅ ሳይሆን ሰማያዊውን መሲሐዊ መንግሥት በመውለድ በእጅጉ ተባርካለች። ይህን ዘር የወለደችው በ1914 ነው። (ራእይ ​—⁠ታላቁ መደምደሚያው ደርሷል! የተባለውን መጽሐፍ ገጽ 177-86 ተመልከት።) የኢሳይያስ ትንቢት ይበልጥ የሚያተኩረው አምላክ በምድር ባሉት ቅቡዓን ልጆቿ ላይ ባፈሰሰው በረከት የተነሳ በምታገኘው ደስታ ላይ ነው።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 218, 219 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

የአብርሃም ቤተሰብ ​—⁠ትንቢታዊ አምሳያ

ሐዋርያው ጳውሎስ የአብርሃም ቤተሰብ ተምሳሌታዊ ድራማ ማለትም ይሖዋ ከሰማያዊት ድርጅቱና በሙሴ ቃል ኪዳን ሥር ከነበረው ምድራዊው የእስራኤል ሕዝብ ጋር ያለውን ዝምድና የሚወክል ትንቢታዊ አምሳያ እንደሆነ ገልጿል።​—⁠ገላትያ 4:​22-31

አብርሃም የቤተሰብ ራስ እንደመሆኑ መጠን ይሖዋ አምላክን ይወክላል። አብርሃም ውድ ልጁን ይስሐቅን መሥዋዕት አድርጎ ለማቅረብ ፈቃደኛ መሆኑ ይሖዋ ተወዳጅ ልጁን ለሰው ልጆች ኃጢአት መሥዋዕት አድርጎ ለማቅረብ ያሳየውን ፈቃደኝነት ያመለክታል።​—⁠ዘፍጥረት 22:​1-13፤ ዮሐንስ 3:​16

ሣራ የአምላክን ሰማያዊት “ሚስት” ማለትም መንፈሳዊ ፍጥረታትን ያቀፈችውን ድርጅቱን ትወክላለች። ይህች ሰማያዊት ድርጅት ከይሖዋ ጋር የተቀራረበ ዝምድና ስላላት፣ ለአምላክ የራስነት ሥልጣን ስለምትገዛና ዓላማዎቹ ዳር እንዲደርሱ ሙሉ ትብብር ስለምታደርግ የይሖዋ ሚስት ተደርጋ መገለጿ የተገባ ነው። “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” ተብላም ትጠራለች። (ገላትያ 4:​26) ይህችው “ሴት” በ⁠ዘፍጥረት 3:​15 ላይም የተጠቀሰች ሲሆን በ⁠ራእይ 12:​1-6, 13-17 ላይ ደግሞ በራእይ ተገልጻለች።

ይስሐቅ የአምላክን ሴት መንፈሳዊ ዘር ይወክላል። ይህ ዘር በዋነኛነት የሚያመለክተው ኢየሱስ ክርስቶስን ቢሆንም መንፈሳዊ ልጆች ሆነው የተዋጁትንና ከክርስቶስ ጋር ተባባሪ ወራሾች የሆኑትን ቅቡዓን ወንድሞቹንም ያካትታል።​—⁠ሮሜ 8:​15-17፤ ገላትያ 3:​16, 29

አጋር የአብርሃም ሁለተኛ ሚስት ወይም ቁባት የነበረች ከመሆኑም በላይ ባሪያ ነበረች። አጋር በሙሴ ሕግ ሥር የነበረችውን ምድራዊቷን ኢየሩሳሌም የምትወክል ሲሆን ይህ ሕግ በሥሩ የነበሩት ሰዎች በሙሉ የኃጢአትና የሞት ባሪያዎች መሆናቸውን በግልጽ አሳይቷል። የሕጉ ቃል ኪዳን የተቋቋመው በሲና ምድር በመሆኑ ጳውሎስ “አጋር በዓረብ ምድር ያለችው ደብረ ሲና ናት” ሲል ተናግሯል።​—⁠ገላትያ 3:​10, 13፤ 4:​25

እስማኤል የአጋር ልጅ ሲሆን ከሙሴ ሕግ ባርነት ያልተላቀቁትን በመጀመሪያው መቶ ዘመን ይኖሩ የነበሩ አይሁዳውያንን ማለትም የኢየሩሳሌም ልጆችን ይወክላል። እስማኤል ይስሐቅን እንዳሳደደው ሁሉ እነዚህ አይሁዳውያንም ክርስቲያኖችን ይኸውም በሣራ የተመሰለችውን ‘የላይኛይቱን ኢየሩሳሌም’ ቅቡዓን ልጆች አሳድደዋል። በተጨማሪም አብርሃም አጋርንና እስማኤልን እንደሰደዳቸው ሁሉ ይሖዋም በመጨረሻ ኢየሩሳሌምንና ዓመፀኛ ልጆቿን እርግፍ አድርጎ ትቷቸዋል።​—⁠ማቴዎስ 23:​37, 38

[በገጽ 220 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ በመንፈስ ቅዱስ የተቀባ ሲሆን ኢሳይያስ 54:​1 ከዚያን ጊዜ አንስቶ የላቀ ፍጻሜውን ማግኘት ጀምሯል

[በገጽ 225 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሖዋ “ለቅጽበተ ዓይን” ፊቱን ከኢየሩሳሌም ሰውሮ ነበር

[በገጽ 231 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

ተዋጊውና ብረት ሠሪው በፈጣሪያቸው ላይ የበላይነት ሊቀዳጁ ይችላሉን ?