በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መጻተኞች ወደ አምላክ የጸሎት ቤት ተሰበሰቡ

መጻተኞች ወደ አምላክ የጸሎት ቤት ተሰበሰቡ

ምዕራፍ አሥራ ሰባት

መጻተኞች ወደ አምላክ የጸሎት ቤት ተሰበሰቡ

ኢሳይያስ 56:​1-12

1, 2. በ1935 የተሰጠው አስደሳች መግለጫ ምንድን ነው? ይህስ የየትኛው ትንቢት ፍጻሜ አካል ነው?

አርብ፣ ግንቦት 31, 1935 ጆሴፍ ኤፍ ራዘርፎርድ በዋሽንግተን ዲ ሲ በተካሄደ ትልቅ ስብሰባ ላይ ለተገኙ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተሰብሳቢዎች አንድ ንግግር ሰጥቶ ነበር። ንግግሩ ሐዋርያው ዮሐንስ በራእይ ያያቸውን “እጅግ ብዙ ሰዎች” ማንነት የሚያብራራ ነበር። ወንድም ራዘርፎርድ በንግግሩ መደምደሚያ ላይ “በምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ ያላችሁ ሁሉ እባካችሁ አንድ ጊዜ ብድግ በሉ” ሲል ጠየቀ። በስብሰባው ላይ ተገኝተው ከነበሩት ሰዎች አንዱ “ከተሰብሳቢዎቹ መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ብድግ አሉ” ሲል ተናግሯል። ከዚያም ወንድም ራዘርፎርድ “እነሆ፣ እጅግ ብዙ ሰዎች!” አለ። በቦታው ተገኝታ የነበረች ሌላ ተሰብሳቢ “ለጥቂት ጊዜ ጸጥታ ከሰፈነ በኋላ ተሰብሳቢዎቹ ሁሉ በደስታ ተንጫጩ፤ ለረጅም ጊዜ የቆየ ከፍተኛ ጭብጨባ ተሰማ” ስትል ሁኔታውን ወደ ኋላ መለስ ብላ በማስታወስ ተናግራለች።​—⁠ራእይ 7:​9

2 ያ ጊዜ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 56 ላይ ሰፍሮ በሚገኘውና ከ2, 700 ዓመታት ገደማ በፊት በተጻፈው ትንቢት ፍጻሜ ረገድ ጉልህ ድርሻ የሚሰጠው ወቅት ነው። በሌሎቹ በርካታ የኢሳይያስ ትንቢቶች ላይ እንደታየው ሁሉ ይሄኛውም ትንቢት አጽናኝ ተስፋዎችንና ከባድ ማስጠንቀቂያዎችን አንድ ላይ አጣምሮ የያዘ ነው። ትንቢቱ በመጀመሪያ የተነገረው በኢሳይያስ ዘመን ለነበሩት የአምላክ የቃል ኪዳን ሕዝቦች ቢሆንም ከብዙ መቶ ዘመናት በኋላ እኛ ባለንበት ዘመንም ፍጻሜውን አግኝቷል።

መዳን ለማግኘት ሊወሰዱ የሚገባቸው እርምጃዎች

3. አይሁዳውያን አምላክ እንዲያድናቸው ከፈለጉ ምን ማድረግ አለባቸው?

3 ኢሳይያስ ምዕራፍ 56 ዘገባውን የሚጀምረው ለአይሁዳውያን ጥብቅ ማሳሰቢያ በመስጠት ነው። ይሁን እንጂ ሁሉም እውነተኛ አምላኪዎች ነቢዩ የጻፈውን የሚከተለውን ማሳሰቢያ ልብ ማለት አለባቸው:- “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል:- ማዳኔ ሊመጣ ጽድቄም ሊገለጥ ቀርቦአልና ፍርድን [“ፍትሕን፣” አ.መ.ት ] ጠብቁ ጽድቅንም አድርጉ። ይህን የሚያደርግ ሰው ይህንንም የሚይዝ የሰው ልጅ፣ እንዳያረክሰው ሰንበትንም የሚጠብቅ እጁንም ክፋት ከማድረግ የሚጠብቅ ብፁዕ ነው።” (ኢሳይያስ 56:1, 2) አምላክ እንዲያድናቸው የሚፈልጉ የይሁዳ ነዋሪዎች የሙሴን ሕግ መታዘዝና ፍትሕን መጠበቅ እንዲሁም በዕለታዊ ኑሯቸው የጽድቅን መንገድ መከተል ይጠበቅባቸዋል። ለምን? ምክንያቱም ይሖዋ ራሱ ጻድቅ ነው። ጽድቅ የሆነውን ነገር የሚያደርጉ ሰዎች የይሖዋን ሞገስ ስለሚያገኙ ይደሰታሉ።​—⁠መዝሙር 144:​15

4. እስራኤላውያን የሰንበትን ሕግ መጠበቃቸው ጠቃሚ የሆነው ለምንድን ነው?

4 ትንቢቱ ሰንበትን ጎላ አድርጎ የገለጸው የሙሴ ሕግ ዋነኛ ገጽታ ስለነበረ ነው። እንዲያውም የይሁዳ ነዋሪዎች ከጊዜ በኋላ ለግዞት ከተዳረጉባቸው ምክንያቶች አንዱ የሰንበትን ሕግ ችላ ማለታቸው ነው። (ዘሌዋውያን 26:​34, 35፤ 2 ዜና መዋዕል 36:​20, 21) ሰንበት ይሖዋ ከአይሁዳውያን ጋር የመሠረተውን ልዩ ዝምድና የሚያመለክት ሲሆን አይሁዶች የሰንበትን ሕግ ማክበራቸው ይህን ልዩ ዝምድና ከፍ አድርገው እንደሚመለከቱ ያሳያል። (ዘጸአት 31:​13) በተጨማሪም በኢሳይያስ ዘመን የነበሩት ሰዎች የሰንበትን ሕግ መጠበቃቸው ይሖዋ ፈጣሪ መሆኑን እንዲያስታውሱ ያደርጋቸው ነበር። ከዚህም ሌላ ይህን ሕግ ማክበራቸው ይሖዋ ያደረገላቸውን ምሕረት እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል። (ዘጸአት 20:​8-11፤ ዘዳግም 5:​12-15) በመጨረሻም ሰንበትን መጠበቃቸው ለይሖዋ ቋሚና የተደራጀ አምልኮ ለማቅረብ ምቹ ሁኔታ ይፈጥርላቸዋል። የይሁዳ ነዋሪዎች በሳምንት አንድ ጊዜ ከዕለት ተዕለት ሥራቸው ማረፋቸው ለመጸለይ፣ ለማጥናትና ለማሰላሰል የሚያስችል አጋጣሚ እንዲያገኙ ይረዳቸዋል።

5. ክርስቲያኖች የሰንበትን ሕግ የመጠበቅን አስፈላጊነት በተመለከተ የተሰጠውን ምክር በመሠረታዊ ሐሳብ ደረጃ ተግባራዊ ማድረግ የሚችሉት እንዴት ነው?

5 ይሁንና ስለ ክርስቲያኖችስ ምን ለማለት ይቻላል? አይሁዳውያን ሰንበትን እንዲጠብቁ የተሰጠው ማበረታቻ በእነሱም ላይ ይሠራል? ክርስቲያኖች በሙሴ ሕግ ሥር ባለመሆናቸው ሰንበትን ማክበር አይጠበቅባቸውም። በመሆኑም ለአይሁዳውያን የተሰጠው ምክር በእነሱ ላይ ቀጥተኛ የሆነ ተፈጻሚነት የለውም። (ቆላስይስ 2:​16, 17) ያም ሆኖ ሐዋርያው ጳውሎስ ታማኝ ክርስቲያኖች “የሰንበት ዕረፍት” እንዳላቸው ገልጿል። ይህ “የሰንበት ዕረፍት” መዳን ለማግኘት ኢየሱስ በከፈለው ቤዛዊ መሥዋዕት ማመንንና በሥራ ብቻ ከመመካት መቆጠብን የሚጠይቅ ነው። (ዕብራውያን 4:​6-10) በመሆኑም ሰንበትን አስመልክቶ በኢሳይያስ ትንቢት ላይ የሰፈሩት ቃላት በዘመናችን ያሉት የይሖዋ አገልጋዮች አምላክ ሰዎችን ለማዳን ባዘጋጀው ዝግጅት ማመን እጅግ አስፈላጊ መሆኑን እንዲያስታውሱ ያደርጓቸዋል። በተጨማሪም እነዚህ ቃላት ከይሖዋ ጋር የጠበቀ ዝምድና የመመሥረትንና ቋሚና ወጥ የሆነ የአምልኮ ሥርዓት የመከተልን አስፈላጊነት እንዳንዘነጋ የሚያደርጉ ጥሩ ማሳሳቢያዎች ናቸው።

ለመጻተኛውና ለጃንደረባው የተሰጠ ማጽናኛ

6. ይሖዋ በመቀጠል ትኩረቱን ያደረገው በየትኞቹ ሰዎች ላይ ነው?

6 ይሖዋ በመቀጠል እሱን ለማገልገል ቢፈልጉም እንኳ በሙሴ ሕግ መሠረት በአይሁድ ጉባኤ የመገኘት መብት የሌላቸውን ሁለት ዓይነት ሰዎች የሚመለከት ቃል ተናገረ። ዘገባው እንዲህ ይላል:- “ወደ እግዚአብሔርም የተጠጋ መጻተኛ:- በእውነት እግዚአብሔር ከሕዝቡ ይለየኛል አይበል፤ ጃንደረባም:- እነሆ፣ እኔ ደረቅ ዛፍ ነኝ አይበል።” (ኢሳይያስ 56:3) መጻተኛው ከእስራኤል ምድር እወገዳለሁ የሚል ስጋት አለበት። ጃንደረባው ደግሞ ስሙን የሚያቆዩ ልጆች መውለድ አለመቻሉ ያሳስበዋል። ይሁንና ሁለቱም ተስፋ ሊቆርጡ አይገባም። ተስፋ መቁረጥ የማይገባቸው ለምን እንደሆነ ከመመርመራችን በፊት ግን እነዚህ ሰዎች በሙሴ ሕግ መሠረት በእስራኤል ሕዝብ መካከል ምን ቦታ እንዳላቸው እንመልከት።

7. ሕጉ በእስራኤል በሚኖሩ መጻተኞች ላይ ምን ገደቦች አበጅቷል?

7 ያልተገረዙ መጻተኞች ከእስራኤላውያን ጋር በአምልኮ ሥርዓት የመካፈል መብት የላቸውም። ለምሳሌ ያህል በማለፍ በዓል ላይ መካፈል አይችሉም። (ዘጸአት 12:​43) መጻተኞች የአገሪቱን ሕግ በግልጽ እስካልተጻረሩ ድረስ ጥሩ መስተንግዶ ያገኙ የነበረ ከመሆኑም በላይ ምንም ዓይነት አድልዎ አይደረግባቸውም ነበር። ይሁን እንጂ ከሕዝቡ ጋር ቋሚ የሆነ ትስስር መፍጠር አይችሉም። እርግጥ አንዳንዶቹ ሕጉን ሙሉ በሙሉ ይቀበሉ የነበረ ሲሆን ይህንንም ለማሳየት ወንዶቹ ይገረዙ ነበር። በዚህ መንገድ ወደ ይሁዲነት ከተለወጡ በኋላ በይሖዋ ቤት አደባባይ የማምለክ መብት ያገኛሉ፤ እንዲሁም የእስራኤል ጉባኤ አባላት ተደርገው ይቆጠራሉ። (ዘሌዋውያን 17:​10-14፤ 20:​2፤ 24:​22) ይሁንና ወደ ይሁዲነት የተለወጡ ሰዎችም እንኳ ይሖዋ ከእስራኤል ጋር የገባው ቃል ኪዳን ሙሉ ተካፋዮች አይሆኑም። በተስፋይቱ ምድርም የራሳቸው የሆነ ርስት አያገኙም። ሌሎች መጻተኞች ወደ ቤተ መቅደሱ መጥተው መጸለይ ይችሉ የነበረ ሲሆን በካህናቱ አማካኝነት የሕጉን መስፈርት ያሟላ መሥዋዕት ማቅረብ ይችሉ እንደነበረም ከሁኔታው መረዳት ይቻላል። (ዘሌዋውያን 22:​25፤ 1 ነገሥት 8:​41-43) ያም ሆኖ እስራኤላውያን ከእነዚህ ሰዎች ጋር የጠበቀ ዝምድና መመሥረት አይችሉም።

ጃንደረቦች የዘላለም ስም ይሰጣቸዋል

8. (ሀ) ጃንደረባ የሆኑ ሰዎችን በተመለከተ ሕጉ ምን ይላል? (ለ) አረማውያን ብሔራት ጃንደረቦችን ለምን ዓላማ ይጠቀሙባቸው ነበር? “ጃንደረባ” የሚለው ቃል አንዳንድ ጊዜ ምን ሊያመለክት ይችላል?

8 ጃንደረቦች ከአይሁዳውያን ወላጆች የተወለዱ ቢሆኑም እንኳ በእስራኤል ሕዝብ መካከል ሙሉ የአባልነት መብት አያገኙም። * (ዘዳግም 23:​1) በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን አንዳንድ አረማውያን ሕዝቦች ጃንደረቦችን ልዩ ቦታ ይሰጧቸው የነበረ ሲሆን በጦርነት ወቅት ከሚማርኳቸው ልጆች መካከል አንዳንዶቹን የመስለብ ልማድ ነበራቸው። ጃንደረቦች በቤተ መንግሥት ውስጥ ባለ ሥልጣናት ሆነው ይሾሙ ነበር። አንድ ጃንደረባ ‘ሴቶችን የሚጠብቅ፣’ ‘ቁባቶችን የሚጠብቅ’ ወይም የንግሥቲቱ አገልጋይ ሊሆን ይችላል። (አስቴር 2:​3, 12-15፤ 4:​4-6, 9) እስራኤላውያን እንዲህ ዓይነት ልማድ እንደነበራቸው የሚጠቁም ወይም ጃንደረባ የሆኑ ሰዎች እየተመረጡ እስራኤላውያን ነገሥታትን እንዲያገለግሉ ይደረግ እንደነበረ የሚያሳይ ምንም ማስረጃ የለም። *

9. ይሖዋ ቃል በቃል ጃንደረባ ለሆኑ ሰዎች ምን የማጽናኛ ቃል ተናግሯል?

9 በእስራኤል ምድር ቃል በቃል የተሰለቡ ሰዎች የሌላውን ሰው ያህል በእውነተኛው አምልኮ ሙሉ በሙሉ የመካፈል መብት የሌላቸው ከመሆኑም በተጨማሪ የቤተሰባቸውን ስም ሊያስጠሩ የሚችሉ ልጆች መውለድ የማይችሉ መሆናቸው ትልቅ ኃፍረት ያስከትልባቸዋል። ከዚህ አንጻር ሲታይ በትንቢቱ ላይ ቀጥሎ የሰፈሩት ቃላት ምንኛ የሚያጽናኑ ናቸው! ትንቢቱ እንዲህ ይላል:- “እግዚአብሔር ሰንበቴን ስለሚጠብቁ ደስ የሚያሰኘኝንም ነገር ስለሚመርጡ ቃል ኪዳኔንም ስለሚይዙ ጃንደረቦች እንዲህ ይላልና:- በቤቴና በቅጥሬ ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያና ስም እሰጣቸዋለሁ፤ የማይጠፋም የዘላለም ስም እሰጣቸዋለሁ።”​—⁠ኢሳይያስ 56:4, 5

10. ጃንደረቦች ሁኔታቸው የተለወጠው ከመቼ ጀምሮ ነው? ከዚያን ጊዜ አንስቶስ ምን መብት የማግኘት አጋጣሚ ተከፍቶላቸዋል?

10 አዎን፣ ቃል በቃል ጃንደረባ የሆነ ሰው ሙሉ ተቀባይነት ያገኘ የይሖዋ አገልጋይ የሚሆንበት ዘመን ይመጣል። ጃንደረቦች ታዛዥ ከሆኑ በይሖዋ ቤት ከወንዶችና ሴቶች ልጆች የሚበልጥ “መታሰቢያ” ወይም ቦታና ስም ያገኛሉ። ይህ የሚሆነው መቼ ነው? ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞተ በኋላ ነው። በዚያን ጊዜ አሮጌው የሕግ ቃል ኪዳን በአዲስ ቃል ኪዳን የተተካ ሲሆን ሥጋዊ እስራኤል ደግሞ “በእግዚአብሔር እስራኤል” ተተክቷል። (ገላትያ 6:​16) ከዚያን ጊዜ አንስቶ ያመኑ ሁሉ ለአምላክ ተቀባይነት ያለው አምልኮ ማቅረብ ችለዋል። አካላዊ ሁኔታ ምንም የሚያመጣው ለውጥ አይኖርም። በታማኝነት የሚጸኑ ሁሉ አካላዊ ሁኔታቸው ምንም ይሁን ምን ‘የማይጠፋ የዘላለም ስም ይሰጣቸዋል።’ ይሖዋ ከቶ አይረሳቸውም። ስማቸው ‘በመታሰቢያ መጽሐፉ’ ላይ የሚጻፍ ሲሆን አምላክ የወሰነው ጊዜ ሲደርስ የዘላለም ሕይወት ያገኛሉ።​—⁠ሚልክያስ 3:​16፤ ምሳሌ 22:​1፤ 1 ዮሐንስ 2:​17

መጻተኞች ከአምላክ ሕዝብ ጋር ያመልካሉ

11. መጻተኞቹ በረከት ማግኘት እንዲችሉ ምን እንዲያደርጉ ተመክረዋል?

11 ስለ መጻተኞቹስ ምን ለማለት ይቻላል? ትንቢቱ እንደገና ስለ መጻተኞቹ መናገር ይጀምራል። ኢሳይያስ ይሖዋ ለእነዚህ መጻተኞች የተናገረውን እጅግ የሚያጽናና ቃል እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ያገለግሉት ዘንድ የእግዚአብሔርንም ስም ይወድዱ ዘንድ ባሪያዎቹም ይሆኑ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር የሚጠጉትንም መጻተኞች፣ እንዳያረክሱት ሰንበትን የሚጠብቁትን ቃል ኪዳኔንም የሚይዙትን ሁሉ፣ ወደ ተቀደሰ ተራራዬ አመጣቸዋለሁ፣ በጸሎቴም ቤት ደስ አሰኛቸዋለሁ፤ ቤቴ ለአሕዛብ ሁሉ የሚሆን የጸሎት ቤት ይባላልና የሚቃጠለውን መሥዋዕታቸውንና ሌላ መሥዋዕታቸውን በመሠዊያዬ ላይ እቀበላለሁ።”​—⁠ኢሳይያስ 56:6, 7

12. ኢየሱስ ስለ “ሌሎች በጎች” የተናገረውን ትንቢት በተመለከተ በአንድ ወቅት ምን የሚል አስተሳሰብ ነበረ?

12 በዘመናችን ‘መጻተኞቹ’ ብቅ ያሉት ቀስ በቀስ ነው። ከአንደኛው የዓለም ጦርነት በፊትም ቢሆን የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች በሰማይ ከኢየሱስ ጋር የመግዛት ተስፋ ካላቸውና በአሁኑ ጊዜ የአምላክ እስራኤል በመባል ከሚታወቁት ሰዎች የበለጠ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ግለሰቦች መዳን እንደሚያገኙ ተገንዝበው ነበር። በ⁠ዮሐንስ 10:​16 ላይ ተመዝግበው የሚገኙትን የሚከተሉትን የኢየሱስ ቃላት ያውቁ ነበር:- “ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፣ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ።” አብዛኞቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች እነዚህ “ሌሎች በጎች” ምድራዊ ተስፋ እንዳላቸው ተገንዝበው የነበረ ቢሆንም ወደ መድረክ ብቅ የሚሉት በኢየሱስ ክርስቶስ የሺህ ዓመት ግዛት እንደሆነ አድርገው ያስቡ ነበር።

13. በ⁠ማቴዎስ ምዕራፍ 25 ላይ የተጠቀሱት በጎች በዚህ ሥርዓት የመደምደሚያ ቀኖች ላይ ብቅ እንደሚሉ የተገለጸው ለምንድን ነው?

13 ከጊዜ በኋላ ከዚህ ነጥብ ጋር በተያያዘ በሌላ ጥቅስ ላይ ሠፍሮ የሚገኘውን ሐሳብ በሚገባ ማስተዋል ቻሉ። በ⁠ማቴዎስ ምዕራፍ 25 ላይ ኢየሱስ ስለ በጎችና ፍየሎች የተናገረው ምሳሌ ይገኛል። በምሳሌው ላይ በጎቹ የኢየሱስን ወንድሞች በመርዳታቸው የዘላለም ሕይወት እንደሚያገኙ ተገልጿል። ከዚህ መረዳት እንደሚቻለው በጎቹ ከክርስቶስ ቅቡዓን ወንድሞች የተለየና ራሱን የቻለ አንድ ቡድን አባላት ናቸው። በ1923 በሎስ አንጀለስ፣ ካሊፎርንያ፣ ዩ ኤስ ኤ ውስጥ በተካሄደው ትልቅ ስብሰባ ላይ እነዚህ በጎች ወደ መድረክ ብቅ የሚሉት በሺህው ዓመት ሳይሆን በዚህ ሥርዓት የመደምደሚያ ቀኖች እንደሆነ ተገለጸ። ለምን? ምክንያቱም ኢየሱስ ምሳሌውን የተናገረው “ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው?” ለሚለው ጥያቄ መልስ በሰጠበት ጊዜ ነው።​—⁠ማቴዎስ 24:​3

14, 15. በፍጻሜው ዘመን ሌሎች በጎች ያላቸው ቦታ ይበልጥ ግልጽ እየሆነ የመጣው እንዴት ነው?

14 በ1920ዎቹ ዓመታት ከመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ጋር የተባበሩ አንዳንድ ግለሰቦች የይሖዋ መንፈስ ሰማያዊ ጥሪ እንዳላቸው አድርጎ እንዳልመሰከረላቸው ተገነዘቡ። ያም ሆኖ ሉዓላዊውን አምላክ በቅንዓት ያገለግሉ ነበር። በ1931 ቪንዲኬሽን የተባለው መጽሐፍ ሲዘጋጅ እነዚህ ሰዎች ያላቸው ቦታ ይበልጥ ግልጽ ሆነ። ይህ ጽሑፍ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘውን የሕዝቅኤል መጽሐፍ ቁጥር በቁጥር ሲተነትን የጸሐፊ ቀለም ቀንድ ስለያዘው “ሰው” የሚናገረውን ራእይ አብራርቷል። (ሕዝቅኤል 9:​1-11) በራእዩ ላይ ይህ “ሰው” በኢየሩሳሌም በሚሠራው ርኩሰት በሚያለቅሱና በሚተክዙ ሰዎች ግንባር ላይ ምልክት እያደረገ በከተማይቱ መካከል ሲያልፍ ታይቷል። ይህ “ሰው” የኢየሱስን ወንድሞች ማለትም የቀድሞዋ ኢየሩሳሌም አምሳያ በሆነችው በሕዝበ ክርስትና ላይ ፍርድ በሚፈጸምበት ዘመን በምድር ላይ የሚኖሩትን የቅቡዓን ክርስቲያኖች አባላት ያመለክታል። ምልክት የተደረገባቸው ሰዎች ደግሞ በዚሁ ዘመን የሚኖሩ ሌሎች በጎች ናቸው። በራእዩ ላይ እነዚህ ሰዎች የይሖዋ ፍርድ አስፈጻሚዎች በከሃዲዋ ከተማ ላይ የበቀል እርምጃ በሚወስዱበት ጊዜ በሕይወት እንደሚተርፉ ተገልጿል።

15 በ1932 የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች የእስራኤል ንጉሥ ስለሆነው ስለ ኢዩና እስራኤላዊ ስላልሆነው ስለ ኢዮናዳብ የሚገልጸውን ትንቢታዊ ድራማ በሚገባ በመገንዘባቸው ኢዩ የበኣል አምልኮን ለማጥፋት በወሰደው እርምጃ ኢዮናዳብ ከጎኑ በመሰለፍ እንደተባበረው ሁሉ ሌሎች በጎችም የክርስቶስ ወንድሞችን እንዴት እንደሚተባበሯቸው ማስተዋል ቻሉ። በመጨረሻም በ1935 በዚህ ሥርዓት የመጨረሻ ዘመን የሚኖሩት ሌሎች በጎች ሐዋርያው ዮሐንስ በራእይ ያያቸው እጅግ ብዙ ሰዎች እንደሆኑ ታወቀ። ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገለጸው ቀደም ሲል በተጠቀሰውና በዋሽንግተን ዲ ሲ በተካሄደው ትልቅ ስብሰባ ላይ ጆሴፍ ኤፍ ራዘርፎርድ የምድራዊ ተስፋ ወራሾችን “እጅግ ብዙ ሰዎች” ብሎ በጠራቸው ጊዜ ነበር።

16. ‘መጻተኞቹ’ ምን መብቶችና ኃላፊነቶች ያገኛሉ?

16 በዚህ መንገድ ‘መጻተኞቹ’ በእነዚህ የመጨረሻ ቀኖች በይሖዋ ዓላማ ውስጥ ትልቅ ሚና እንዳላቸው ቀስ በቀስ ግልጽ እየሆነ መጣ። ይሖዋን ለማምለክ ወደ አምላክ እስራኤል ተሰብስበዋል። (ዘካርያስ 8:​23) ከዚህ መንፈሳዊ ሕዝብ ጋር ሆነው ተቀባይነት ያላቸው መሥዋዕቶችን ለአምላክ የሚያቀርቡ ከመሆኑም በላይ ወደ ሰንበት ዕረፍት ይገባሉ። (ዕብራውያን 13:​15, 16) ከዚህም በተጨማሪ ልክ በኢየሩሳሌም እንደነበረው ቤተ መቅደስ “ለአሕዛብ ሁሉ የጸሎት ቤት” በሆነው የአምላክ መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ ይሖዋን ያመልካሉ። (ማርቆስ 11:​17) ‘ልብሳቸውን አጥበው በበጉ ደም በማንጻት’ ኢየሱስ ክርስቶስ በከፈለው ቤዛዊ መሥዋዕት ላይ እምነት እንዳላቸው ያሳያሉ። እንዲሁም “ቀንና ሌሊት ቅዱስ አገልግሎት” [NW ] በማቅረብ ይሖዋን ዘወትር ያገለግሉታል።​—⁠ራእይ 7:​14, 15

17. ዘመናዊዎቹ መጻተኞች አዲሱን ቃል ኪዳን የሚይዙት በምን መንገድ ነው?

17 እነዚህ ዘመናዊ መጻተኞች አዲሱን ቃል ኪዳን የሚይዙት ከአምላክ እስራኤል ጋር ኅብረት በመፍጠር ሲሆን ይህም በአዲሱ ቃል ኪዳን አማካኝነት የሚመጡትን ጥቅሞችና በረከቶች ያስገኝላቸዋል። የቃል ኪዳኑ ተካፋዮች ባይሆኑም እንኳ ከቃል ኪዳኑ ጋር ዝምድና ያላቸውን ሕጎች ከልባቸው ይታዘዛሉ። የይሖዋ ሕግ በልባቸው ውስጥ ከመሆኑም በላይ ይሖዋ ሰማያዊ አባታቸውና ሉዓላዊ ገዥ እንደሆነ ያውቃሉ።​—⁠ኤርምያስ 31:​33, 34፤ ማቴዎስ 6:​9፤ ዮሐንስ 17:​3

18. በፍጻሜው ዘመን ምን የመሰብሰብ ሥራ ሲከናወን ቆይቷል?

18 የኢሳይያስ ትንቢት በመቀጠል እንዲህ ይላል:- “ከእስራኤል የተበተኑትን የሚሰበስብ ጌታ እግዚአብሔር:- ወደ ተሰበሰቡት ዘንድ ሌሎችን እሰበስብለታለሁ ይላል።” (ኢሳይያስ 56:8) ይሖዋ በፍጻሜው ዘመን “ከእስራኤል የተበተኑትን” ማለትም ቅቡዓን ቀሪዎችን ሰብስቧል። ከዚህም በተጨማሪ ሌሎችን ይኸውም እጅግ ብዙ ሰዎችን እየሰበሰበ ነው። በይሖዋና በዙፋን ላይ ባስቀመጠው ንጉሡ ማለትም በኢየሱስ ክርስቶስ አመራር ሥር አንድ ላይ ሆነው በሰላምና በስምምነት ያመልካሉ። በክርስቶስ ለሚመራው የይሖዋ መስተዳድር ታማኝ በመሆናቸው መልካሙ እረኛ ደስተኛ በሆነ አንድ መንጋ እንዲታቀፉ አድርጓቸዋል።

ዕውር ጉበኞች፣ ዲዳ ውሾች

19. ለምድረ በዳና ለዱር አራዊት ምን ግብዣ ቀርቧል?

19 ይሖዋ ከላይ የተገለጹትን የሚያንጹ ፍቅራዊ ቃላት ከተናገረ በኋላ አስገራሚ ብሎም አስደንጋጭ የሆነ መልእክት አስተላለፈ። ለመጻተኞችና ለጃንደረቦች ምሕረት ለማሳየት የተዘጋጀ ቢሆንም የአምላክ ጉባኤ አባላት ነን የሚሉ ብዙዎች የተወገዙ ከመሆኑም በላይ ፍርድ ይጠብቃቸዋል። ከሁሉ የከፋው ደግሞ በሥርዓት ለመቀበር እንኳ የማይበቁ በመሆናቸው የተራቡ አውሬዎች ያነክቷቸዋል። በመሆኑም ትንቢቱ እንዲህ ይላል:- “እናንተ የምድረ በዳ አራዊት ሁሉ፣ እናንተም የዱር አራዊት ሁሉ፣ ትበሉ ዘንድ ቅረቡ።” (ኢሳይያስ 56:9) እነዚህ የዱር አራዊት የሚበሉት ምንድን ነው? ትንቢቱ በመቀጠል ይገልጸዋል። ይህም አምላክን የሚቃወሙ ሰዎች ሁሉ በቅርቡ በሚካሄደው የአርማጌዶን ጦርነት የሚገጥማቸውን ዕጣ እንድናስታውስ ሊያደርገን ይችላል። አስከሬናቸው ለሰማይ አዕዋፍ እራት ይሆናል።​—⁠ራእይ 19:​17, 18

20, 21. የሃይማኖት መሪዎቹ መንፈሳዊ አመራር ለመስጠት ብቁ እንዳልሆኑ የሚያሳየው ምንድን ነው?

20 ትንቢቱ በመቀጠል እንዲህ ይላል:- “ጉበኞቹ ዕውሮች ናቸው፣ ሁሉ ያለ እውቀት ናቸው፤ ሁሉም ዲዳ የሆኑ ውሾች ናቸው ይጮኹም ዘንድ አይችሉም፤ ሕልምን ያልማሉ፤ ይተኛሉ፤ ማንቀላፋትንም ይወድዳሉ። መብል ወዳጆች ከቶ የማይጠግቡ ውሾች ናቸው፣ እነርሱም ያስተውሉ ዘንድ የማይችሉ እረኞች ናቸው፤ ሁሉ ወደ መንገዳቸው፣ ከፊተኛው እስከ ኋለኛው ድረስ ሁሉ፣ እያንዳንዳቸው ወደ ጥቅማቸው ዘወር ብለዋል። ኑ የወይን ጠጅ እንውሰድ፣ በሚያሰክርም መጠጥ እንርካ፤ ዛሬም እንደ ሆነ እንዲሁ ነገ ይሆናል፣ ከዛሬም ይልቅ እጅግ ይበልጣል ይላሉ።”​—⁠ኢሳይያስ 56:10-12

21 የይሁዳ የሃይማኖት መሪዎች ይሖዋን እናመልካለን ይላሉ። “ጉበኞቹ” እንደሆኑ ይናገራሉ። ይሁን እንጂ በመንፈሳዊ ዕውሮች፣ ዲዳዎችና እንቅልፋሞች ናቸው። ነቅተው የማይጠብቁና አደጋ ሲመጣ የማያስጠነቅቁ ከሆነ ጥቅማቸው ምኑ ላይ ነው? እንዲህ ያሉ ሃይማኖታዊ ጉበኞች ማስተዋል የጎደላቸው ናቸው። በግ መሰል ለሆኑ ሰዎች መንፈሳዊ አመራር ለመስጠት የሚያስችል ብቃት የላቸውም። ከዚህም በተጨማሪ ምግባረ ብልሹ ናቸው። በራስ ወዳድነት ላይ የተመሠረተውን ፍላጎታቸውን በቀላሉ ማርካት አይችሉም። የይሖዋን አመራር ከመከተል ይልቅ በራሳቸው መንገድ ይሄዳሉ፣ አግባብ ያልሆነ ጥቅም ለማግኘት ይሯሯጣሉ፣ የሚያሰክር መጠጥ ከልክ በላይ ይጠጣሉ፣ ሌሎችም የእነሱን ፈለግ እንዲከተሉ ይገፋፋሉ። አምላክ ፍርዱን የሚያስፈጽምበት ጊዜ እየቀረበ እንዳለ ካለማስተዋላቸው የተነሳ ምንም ችግር እንደማይመጣ አድርገው ይናገራሉ።

22. በኢየሱስ ዘመን የነበሩት ሃይማኖታዊ መሪዎች በጥንቷ ይሁዳ ከነበሩት ጋር ተመሳሳይ የሆኑት እንዴት ነው?

22 ቀደም ሲል ኢሳይያስ በትንቢቱ ላይ ተመሳሳይ የሆነ ምሳሌያዊ አነጋገር በመጠቀም ከሃዲ የሆኑት የይሁዳ ሃይማኖታዊ መሪዎች መንፈሳዊ ስካርና ድብታ እንደተጠናወታቸውና ማስተዋል እንደጎደላቸው ገልጾ ነበር። በሕዝቡ ላይ የሰው ወግና ሥርዓት ከመጫናቸውም በላይ የሐሰት ሃይማኖታዊ ትምህርቶችን ያስተምሩ ነበር። ከዚህም በተጨማሪ የአምላክን እርዳታ መጠየቅ ሲገባቸው በአሦር ታምነዋል። (2 ነገሥት 16:​5-9፤ ኢሳይያስ 29:​1, 9-14) ከስህተታቸው መማር እንዳልቻሉ በግልጽ መረዳት ይቻላል። የሚያሳዝነው በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩት የሃይማኖት መሪዎችም እንዲሁ ነበሩ። የራሱ የአምላክ ልጅ ያመጣላቸውን ምሥራች ከመቀበል ይልቅ ኢየሱስን ገሸሽ በማድረግ ለማስገደል አሲረውበታል። ኢየሱስ በግልጽ ‘ዕውር መሪዎች’ ብሎ የጠራቸው ሲሆን “ዕውርም ዕውርን ቢመራው ሁለቱም ወደ ጉድጓድ ይወድቃሉ” ሲል አክሎ ተናግሯል።​—⁠ማቴዎስ 15:​14

በዘመናችን ያሉ ጉበኞች

23. ጴጥሮስ ሃይማኖታዊ መሪዎችን አስመልክቶ የተናገረው የትኛው ትንቢት ፍጻሜውን አግኝቷል?

23 ሐዋርያው ጴጥሮስ ክርስቲያኖችን ለማሳት ሐሰተኛ አስተማሪዎች እንደሚነሱ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል። እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ሐሰተኞች ነቢያት ደግሞ በሕዝቡ [በእስራኤል ሕዝብ] መካከል ነበሩ እንዲሁም በመካከላችሁ ደግሞ ሐሰተኞች አስተማሪዎች ይሆናሉ፤ እነርሱም የዋጃቸውን ጌታ እንኳ ክደው የሚፈጥንን ጥፋት በራሳቸው ላይ እየሳቡ የሚያጠፋ ኑፋቄን አሹልከው ያገባሉ።” (2 ጴጥሮስ 2:1) እንዲህ ያሉ የሐሰት አስተማሪዎች ያስተማሩት የሐሰት ትምህርትና ኑፋቄ ምን ውጤት አስከትሏል? ሕዝበ ክርስትና እንድትቋቋም ያደረገ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ የሕዝበ ክርስትና ሃይማኖታዊ መሪዎች አምላክ ፖለቲካዊ ወዳጆቻቸውን እንዲባርክ በመጸለይ የተሻለ ጊዜ እንደሚመጣ ሲናገሩ ይደመጣል። የሕዝበ ክርስትና ሃይማኖታዊ መሪዎች በመንፈሳዊ ሁኔታ ዕውሮች፣ ዲዳዎችና እንቅልፋሞች እንደሆኑ በግልጽ ታይቷል።

24. በመንፈሳዊ እስራኤልና በመጻተኞቹ መካከል ምን ዓይነት አንድነት አለ?

24 ይሁን እንጂ ይሖዋ ከመጨረሻዎቹ የአምላክ እስራኤል አባላት ጋር በታላቁ መንፈሳዊ የጸሎት ቤቱ እንዲያመልኩት በሚልዮን የሚቆጠሩ መጻተኞችን እየሰበሰበ ነው። እነዚህ መጻተኞች ከተለያዩ ብሔራት፣ ዘሮችና ቋንቋዎች የተውጣጡ ቢሆኑም እርስ በርሳቸውም ሆነ ከአምላክ እስራኤል ጋር አንድነት አላቸው። መዳን ሊገኝ የሚችለው በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ከይሖዋ አምላክ ብቻ እንደሆነ በሚገባ ያምናሉ። ለይሖዋ ባላቸው ፍቅር ተገፋፍተው ከክርስቶስ ወንድሞች ጋር ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ስለ እምነታቸው ይመሰክራሉ። በተጨማሪም ሐዋርያው በመንፈስ ተነሳስቶ “ኢየሱስ ጌታ እንደ ሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳነሣው በልብህ ብታምን ትድናለህ” ሲል የጻፋቸው ቃላት በእጅጉ ያጽናኗቸዋል።​—⁠ሮሜ 10:9

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.8 “ጃንደረባ” የሚለው ቃል ያልተሰለበ የቤተ መንግሥት ባለ ሥልጣንን ለማመልከትም ተሠርቶበታል። ፊልጶስ ያጠመቀው ኢትዮጵያዊ ወደ ይሁዲነት የተለወጠ ሳይሆን አይቀርም። ይህ ሰው የተጠመቀው ምሥራቹ አይሁዳውያን ላልሆኑ ያልተገረዙ ሰዎች መነገር ከመጀመሩ በፊት ስለሆነ ጃንደረባ የተባለው የቤተ መንግሥት ባለ ሥልጣን መሆኑን ለማመልከት ነው።​—⁠ሥራ 8:​27-39

^ አን.8 ኤርምያስን የረዳውና ከንጉሥ ሴዴቅያስ ጋር በቀጥታ የመነጋገር መብት የነበረው አቤሜሌክ ጃንደረባ ተብሏል። ጃንደረባ ተብሎ የተጠራው የተሰለበ ሰው ነው ለማለት ሳይሆን የቤተ መንግሥት ባለ ሥልጣን መሆኑን ለማመልከት እንደሆነ መገመት ይቻላል።​—⁠ኤርምያስ 38:​7-13

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 250 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሰንበት ለመጸለይ፣ ለማጥናትና ለማሰላሰል የሚያስችል ምቹ አጋጣሚ ይፈጥር ነበር

[በገጽ 256 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

በ1935 በዋሽንግተን ዲ ሲ በተካሄደው ትልቅ ስብሰባ ላይ ሌሎች በጎች ያላቸው ቦታ በግልጽ ተብራርቷል (ከታች፣ የጥምቀት ሥነ ሥርዓት፤ በስተቀኝ፣ የስብሰባው ፕሮግራም)

[በገጽ 259 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የዱር አራዊት ግብዣ ቀርቦላቸዋል

[በገጽ 261 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

መጻተኞቹና የአምላክ እስራኤል አንድነት አላቸው