በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“በአለቆች አትታመኑ”

“በአለቆች አትታመኑ”

ምዕራፍ አሥራ አንድ

“በአለቆች አትታመኑ”

ኢሳይያስ 50:​1-11

1, 2. (ሀ) አይሁዳውያን የትኛውን በመንፈስ አነሳሽነት የተጻፈ ምክር ሳይከተሉ ቀርተዋል? ይህስ ምን ውጤት አስከትሏል? (ለ) ይሖዋ “የፍችዋ ጽሕፈት የት አለ” ሲል የጠየቀው ለምንድን ነው?

‘ማዳን በማይችሉ በሰው ልጆችና በአለቆች አትታመኑ። የያዕቆብ አምላክ ረዳቱ የሆነ ተስፋውም ሰማይንና ምድርን በፈጠረ በአምላኩ በእግዚአብሔር የሆነ ሰው ምስጉን ነው።’ (መዝሙር 146:​3-6) በኢሳይያስ ዘመን ይኖሩ የነበሩት አይሁዳውያን የመዝሙራዊውን ምክር ቢሰሙ ኖሮ ምንኛ ይጠቀሙ ነበር! በግብጽ ወይም በሌላ አረማዊ ብሔር ከመታመን ይልቅ በ“ያዕቆብ አምላክ” ቢታመኑ ኖሮ ይሁዳን ጠላቶቿ ሊያጠቋት በሚነሱበት ጊዜ ይሖዋ ሊጠብቃት ይችል ነበር። ይሁን እንጂ ይሁዳ ይሖዋ እንዲረዳት መለመን አልፈለገችም። በዚህም ምክንያት ይሖዋ ኢየሩሳሌምን ከጥፋት ለማዳንም ሆነ ነዋሪዎቿ በባቢሎን እንዳይማረኩ ለመከላከል ምንም ዓይነት እርምጃ አይወስድም።

2 ይሁዳ ለሚደርስባት ጥፋት ከራሷ ሌላ ማንንም ልትወቅስ አትችልም። ጥፋት የመጣባት ይሖዋ ስለከዳት ወይም ከሕዝቡ ጋር የገባውን ቃል ኪዳን ችላ ስላለ እንደሆነ አድርጋ አምላክን ልትወነጅል አትችልም። ፈጣሪ ቃል ኪዳኑን የሚያጥፍ አምላክ አይደለም። (ኤርምያስ 31:​32፤ ዳንኤል 9:​27፤ ራእይ 15:​4) ይሖዋ አይሁዳውያንን እንደሚከተለው ብሎ በመጠየቅ ይህን ሐቅ ጠበቅ አድርጎ ገልጾታል:- “እናታችሁን የፈታሁበት የፍችዋ ጽሕፈት የት አለ?” (ኢሳይያስ 50:​1ሀ) በሙሴ ሕግ አንድ ሰው ሚስቱን በሚፈታበት ጊዜ የፍችዋን ወረቀት የመስጠት ግዴታ ነበረበት። ከዚያ በኋላ ሴቲቱ ሌላ ሰው የማግባት ነፃነት ይኖራታል። (ዘዳግም 24:​1, 2) በምሳሌያዊ ሁኔታ ይሖዋ የይሁዳ እህት ለሆነችው የእስራኤል መንግሥት የፍቺ ወረቀት የሰጣት ቢሆንም ይሁዳን አልፈታትም ነበር። * በዚያም ወቅት ቢሆን ‘ባሏ’ ነበር። (ኤርምያስ 3:​8, 14) በመሆኑም ይሁዳ ከአረማዊ ብሔራት ጋር ለመጎዳኘት የሚያስችል ነፃነት አልነበራትም። ‘ሴሎ [መሲሑ] እስኪመጣ ድረስ’ ይሖዋ ከይሁዳ ጋር ያለው ዝምድና እንዳለ ይቀጥላል።​—⁠ዘፍጥረት 49:​10 የ1980 ትርጉም

3. ይሖዋ ሕዝቡን ‘የሸጠው’ በምን ምክንያት ነው?

3 በተጨማሪም ይሖዋ ይሁዳን እንዲህ ሲል ጠይቋታል:- “እናንተን የሸጥሁ ከአበዳሪዎች ለየትኛው ነው?” (ኢሳይያስ 50:​1ለ) ይሖዋ ዕዳ ውስጥ ገብቶ ከዕዳው ለመውጣት ሲል አይሁዳውያን በባቢሎን እንዲማረኩ አያደርግም። ይሖዋ ዕዳውን ለመክፈል ሲል ልጆቹን ለአበዳሪው ለመሸጥ እንደሚገደድ ድሃ እስራኤላዊ አይደለም። (ዘጸአት 21:​7) ከዚህ ይልቅ ይሖዋ ሕዝቡ በባርነት የሚገዙበት እውነተኛው ምክንያት ምን እንደሆነ ሲገልጽ እንዲህ ብሏል:- “እነሆ፣ ስለ ኃጢአታችሁ ተሸጣችኋል፣ ስለ በደላችሁም እናታችሁ ተፈትታለች [“ተሰድዳለች፣” NW ]።” (ኢሳይያስ 50:1ሐ) ይሖዋን የተዉት ራሳቸው አይሁዳውያን ናቸው እንጂ እሱ አልተዋቸውም።

4, 5. ይሖዋ ለሕዝቡ ያለውን ፍቅር ያሳየው እንዴት ነው? ሆኖም ይሁዳ በአጸፋው ያደረገችው ነገር ምን ነበር?

4 ይሖዋ ቀጥሎ ያነሳው ጥያቄ ለሕዝቡ ያለውን ፍቅር ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው:- “በመጣሁስ ጊዜ ሰው ስለ ምን አልነበረም? በጠራሁስ ጊዜ የሚመልስ ስለ ምን አልነበረም?” (ኢሳይያስ 50:​2ሀ) ይሖዋ ነቢያቱን በመላክ ሕዝቡ ሙሉ በሙሉ ወደ እሱ እንዲመለሱ ማሳሰቢያ ሲሰጣቸው ቤታቸው ድረስ መጥቶ የለመናቸው ያህል ነበር። ሆኖም ፈቃደኛ ሆኖ የተገኘ አልነበረም። አይሁዳውያን ከሰው እርዳታ መለመን መርጠዋል። ይባስ ብሎም ከግብጽ እርዳታ እስከመለመን ደርሰዋል።​—⁠ኢሳይያስ 30:​2፤ 31:​1-3፤ ኤርምያስ 37:​5-7

5 በግብጽ መታመን የመረጡት ከይሖዋ የበለጠ አስተማማኝ የሆነ የማዳን ኃይል ኖሯት ነውን? እነዚህ ከዳተኛ አይሁዳውያን ከብዙ መቶ ዘመናት በፊት የእስራኤል ሕዝብ ራሱን የቻለ ብሔር ሆኖ እንዲቋቋም ያስቻሉትን ሁኔታዎች የዘነጉ ይመስላል። ይሖዋ የሚከተለውን ጥያቄ አቀረበላቸው:- “መታደግ እንዳትችል እጄ አጭር ሆናለችን? ወይስ ለማዳን ኃይል የለኝምን? እነሆ፣ በገሠጽሁ ጊዜ ባሕርን አደርቃለሁ፣ ወንዞችንም ምድረ በዳ አደርጋቸዋለሁ፤ ውኃም በማጣት ዓሦቻቸው ይገማሉ በጥማትም ይሞታሉ። ሰማያትን ጥቁረት አለብሳቸዋለሁ፣ መጋረጃቸውንም ማቅ አደርጋለሁ።”​—⁠ኢሳይያስ 50:​2ለ, 3

6, 7. ይሖዋ በግብጻውያን ላይ የማዳን ኃይሉን ያሳየው እንዴት ነው?

6 በ1513 ከዘአበ ግብጽ ተስፋ የተጣለባት የአምላክ ሕዝብ ነፃ አውጪ ሳትሆን ጨቋኝ ገዢያቸው ነበረች። እስራኤላውያን በዚያች አረማዊት አገር ውስጥ ባሮች ነበሩ። ይሁን እንጂ ይሖዋ እጅግ በሚያስደንቅ ሁኔታ ከግብጽ ባርነት ነፃ አወጣቸው! በመጀመሪያ በምድሪቱ ላይ አሥር መቅሠፍቶች አመጣ። እጅግ የከፋ ጥፋት ያስከተለው አሥረኛው መቅሠፍት ከደረሰ በኋላ የግብጹ ፈርዖን እስራኤላውያን አገሪቱን ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘ። (ዘጸአት 7:​14 –12:​31) ይሁን እንጂ እስራኤላውያን ግብጽን ለቅቀው ከወጡ በኋላ ብዙም ሳይቆይ ፈርዖን ሐሳቡን ለወጠ። ሠራዊቱን ሰብስቦ እስራኤላውያንን ወደ ግብጽ ለመመለስ ያሳድዳቸው ጀመር። (ዘጸአት 14:​5-9) እስራኤላውያን ከኋላቸው በሚያሳድዷቸው ሥፍር ቁጥር የሌላቸው የግብጽ ወታደሮችና ከፊታቸው ባለው ቀይ ባሕር መካከል ገብተው መፈናፈኛ አጡ! ይሁን እንጂ ይሖዋ ከጎናቸው ነበር።

7 ይሖዋ በግብጻውያንና በእስራኤላውያን መካከል የደመና ዓምድ በማቆም ግብጻውያን ወደፊት እንዳይገሰግሱ አገዳቸው። ግብጻውያን በጨለማ ሲዋጡ እስራኤላውያን ግን በብርሃን ይጓዙ ነበር። (ዘጸአት 14:​20) በዚህ መንገድ ይሖዋ ግብጻውያንን ባሉበት እንዲቆሙ ካደረገ በኋላ “ሌሊቱን ሁሉ ጽኑ የምሥራቅ ነፋስ አምጥቶ ባሕሩን አስወገደው፣ ባሕሩንም አደረቀው።” (ዘጸአት 14:21) ውኃው ለሁለት ሲከፈል ሕዝቡ ሁሉ ይኸውም ወንዶቹ፣ ሴቶቹና ሕፃናቱ በሙሉ ቀይ ባሕርን ያላንዳች ችግር ተሻገሩ። ይሖዋ ሕዝቡ ባሕሩን ተሻግረው ሊጨርሱ ጥቂት ሲቀራቸው ደመናውን አነሳው። ግብጻውያን እስራኤላውያንን አሳድደው ለመያዝ እየተንደረደሩ ወደተከፈለው ባሕር ገቡ። ይሖዋ ሕዝቡ ሙሉ በሙሉ ከተሻገሩ በኋላ ውኃው እንደገና እንዲፈስ በማድረግ ፈርዖንና ሠራዊቱን አሰጠማቸው። በዚህ መንገድ ይሖዋ ለሕዝቡ ተዋጋ። ይህ ዛሬ ላሉ ክርስቲያኖች እንዴት ያለ ግሩም ማበረታቻ ነው!​—⁠ዘጸአት 14:​23-28

8. የይሁዳ ነዋሪዎች የሚማረኩት የትኛውን ማስጠንቀቂያ ቸል በማለታቸው ነው?

8 ይሖዋ ይህን ድል የተቀዳጀው ኢሳይያስ ከኖረበት ዘመን ሰባት መቶ ዓመታት በፊት ነው። ይሁዳ አሁን ራሷን የቻለች ብሔር ሆናለች። እንደ አሦርና ግብጽ ካሉ የውጪ መንግሥታት ጋር ዲፕሎማሲያዊ ስምምነቶች የፈጸመችባቸው ጊዜያት ነበሩ። ይሁን እንጂ የእነዚህ አረማዊ ብሔራት መሪዎች እምነት የሚጣልባቸው አልነበሩም። የግል ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ሲሉ ከይሁዳ ጋር የገቡትን የትኛውንም ቃል ኪዳን ከማፍረስ የማይመለሱ ነበሩ። በይሖዋ ስም ይናገሩ የነበሩት ነቢያት ሕዝቡ እንዲህ ባሉ ሰዎች ላይ እምነቱን እንዳይጥል ቢያስጠነቅቁም ሰሚ ጆሮ አላገኙም። በመሆኑም አይሁዳውያን በባቢሎን ተማርከው ለ70 ዓመታት በባርነት ለመኖር ይገደዳሉ። (ኤርምያስ 25:​11) ይሁን እንጂ ይሖዋ ሕዝቡን በመርሳት ከናካቴው እርግፍ አድርጎ አይተዋቸውም። የወሰነው ጊዜ ሲደርስ ሕዝቡን በማስታወስ ወደ ትውልድ አገራቸው ተመልሰው ንጹሕ አምልኮን ዳግመኛ እንዲያቋቁሙ በሩን ይከፍትላቸዋል። ይህን የሚያደርገው ለምን ዓላማ ነው? አሕዛብ ሁሉ ሊታዘዙለት የሚገባው መሲሕ የሚመጣበትን ጊዜ ዝግጁ ሆነው እንዲጠብቁ ለማድረግ ነው።

ሴሎ መጣ

9. ሴሎ ማን ነው? ምን ዓይነት አስተማሪስ ነው?

9 ብዙ መቶ ዘመናት ካለፉ በኋላ “የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ” መሲሑ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ተወለደ። (ገላትያ 4:​4፤ ዕብራውያን 1:​1, 2) ይሖዋ የቅርብ ረዳቱን ለአይሁዳውያን ቃል አቀባይ አድርጎ መሾሙ ለሕዝቡ ምን ያህል ፍቅር እንዳለው የሚያሳይ ነው። ኢየሱስ ተወዳዳሪ የማይገኝለት ቃል አቀባይ ሆኖ አገልግሏል! ኢየሱስ ቃል አቀባይ ብቻ ሳይሆን ታላቅ አስተማሪም ነው። በማስተማር ችሎታው አቻ ከማይገኝለት ከይሖዋ አምላክ በቀጥታ የተማረ በመሆኑ ታላቅ አስተማሪ መባሉ ምንም አያስደንቅም። (ዮሐንስ 5:​30፤ 6:​45፤ 7:​15, 16, 46፤ 8:​26) ኢየሱስ በኢሳይያስ በኩል የተናገረው ትንቢታዊ ቃል ይህን የሚያረጋግጥ ነው:- “የደከመውን በቃል እንዴት እንደምደግፍ አውቅ ዘንድ ጌታ እግዚአብሔር የተማሩትን ምላስ ሰጥቶኛል፤ ማለዳ ማለዳ ያነቃኛል፣ እንደ ተማሪዎችም ትሰማ ዘንድ ጆሮዬን ያነቃቃል።”​—⁠ኢሳይያስ 50:4 *

10. ኢየሱስ ይሖዋ ለሕዝቡ ያለውን ፍቅር የሚያንጸባርቀው እንዴት ነው? ሕዝቡስ ምን ዓይነት ምላሽ ይሰጣሉ?

10 ኢየሱስ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት በሰማይ ከአባቱ ጋር ይሠራ ነበር። በአባቱና በልጁ መካከል ያለው የጠበቀ ወዳጅነት በ⁠ምሳሌ 8:​30 ላይ በግጥም መልክ ተገልጿል:- “እኔ [በይሖዋ] ዘንድ ዋና ሠራተኛ ነበርሁ፤ . . . በፊቱም ሁልጊዜ ደስ ይለኝ ነበርሁ።” ኢየሱስ አባቱን መስማቱ ከፍተኛ ደስታ አስገኝቶለታል። አባቱ ያሳየውን ፍቅር እርሱም ‘ለሰው ልጆች’ አሳይቷል። (ምሳሌ 8:​31) ኢየሱስ ወደ ምድር ሲመጣ ‘የደከመውን በቃል ይደግፋል።’ አገልግሎቱን የሚጀምረው በኢሳይያስ ትንቢት ላይ የሚገኘውን የሚከተለውን አጽናኝ ቃል በማንበብ ነው:- “የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው፣ ለድሆች ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ቀብቶኛልና፤ . . . የተጠቁትንም ነጻ አወጣ ዘንድ።” (ሉቃስ 4:18፤ ኢሳይያስ 61:1) ለድሆች የምሥራች ያበስራል! ለደከሙት እረፍትን ይሰጣል! ይህ መግለጫ ሕዝቡን እጅግ ሊያስደስታቸው የሚገባ ቢሆንም መግለጫውን ሲሰሙ የሚደሰቱት ሁሉም አይደሉም። ውሎ አድሮ ብዙዎች ኢየሱስ በይሖዋ የተማረ መሆኑን የሚያሳዩትን ማስረጃዎች አምነው ለመቀበል አሻፈረን ይላሉ።

11. ከኢየሱስ ጋር ቀንበሩን የሚሸከሙት እነማን ናቸው? ይህስ ምን ያስገኝላቸዋል?

11 ይሁን እንጂ አንዳንዶች ይበልጥ ለመማር ልባቸው ይነሳሳል። ኢየሱስ የሚያቀርበውን የሚከተለውን ከልብ የመነጨ ጥሪ በደስታ ይቀበላሉ:- “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፣ ወደ እኔ ኑ፣ እኔም አሳርፋችኋለሁ። ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፣ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፣ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ።” (ማቴዎስ 11:28, 29) ወደ ኢየሱስ ከሚመጡት ሰዎች መካከል አንዳንዶቹ ሐዋርያቱ ይሆናሉ። ከኢየሱስ ጋር ቀንበሩን መሸከማቸው ከባድ ሥራ እንደሚያስከትልባቸው ያውቃሉ። ይህ ሥራ የመንግሥቱን ምሥራች እስከ ምድር ዳር ድረስ መስበክን ይጨምራል። (ማቴዎስ 24:​14) ሐዋርያቱም ሆኑ ሌሎቹ ደቀ መዛሙርት በዚህ ሥራ መሳተፍ ሲጀምሩ በእርግጥም ለነፍሳቸው እረፍት የሚያመጣ መሆኑን ይገነዘባሉ። በዘመናችን ያሉ ታማኝ ክርስቲያኖችም ይህን ሥራ በማከናወን ላይ የሚገኙ ሲሆን በዚህ ሥራ መካፈላቸው ተመሳሳይ የሆነ ደስታ አስገኝቶላቸዋል።

ዓመፀኛ አይደለም

12. ኢየሱስ ለሰማያዊ አባቱ ታዛዥ መሆኑን ያሳየው በምን መንገዶች ነው?

12 ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው የአምላክን ፈቃድ ለመፈጸም መሆኑን ፈጽሞ አይዘነጋም። ኢየሱስ ምን ዓይነት አመለካከት እንደሚኖረው አስቀድሞ ተተንብዮአል:- “ጌታ እግዚአብሔር ጆሮዬን ከፍቶአል፣ እኔም ዓመፀኛ አልነበርሁም ወደ ኋላዬም አልተመለስሁም።” (ኢሳይያስ 50:5) ኢየሱስ ምንጊዜም ለአምላክ ታዛዥ ነው። እንዲያውም እንዲህ ብሎ እስከመናገር ደርሷል:- “አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም።” (ዮሐንስ 5:19) ኢየሱስ ሰው ሆኖ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት ስፍር ቁጥር ለሌላቸው ዓመታት ከአባቱ ጋር ሠርቷል። ወደ ምድር ከመጣ በኋላም የይሖዋን መመሪያዎች ተግባራዊ ማድረጉን ይቀጥላል። ኢየሱስ የይሖዋን መመሪያዎች ይህን ያህል ይከተል ከነበረ ፍጽምና የጎደለን የክርስቶስ ተከታዮች ደግሞ ይሖዋ የሚለንን ሁሉ ለማድረግ ምን ያህል መጠንቀቅ እንዳለብን መገመት አያዳግትም!

13. ኢየሱስ ከፊቱ ምን ይጠብቀዋል? ሆኖም ደፋር መሆኑን የሚያሳየው እንዴት ነው?

13 የይሖዋን አንድያ ልጅ ለመቀበል አሻፈረን ከሚሉት ሰዎች መካከል አንዳንዶቹ ኢየሱስን የሚያሳድዱት ሲሆን ይህ እንደሚደርስበትም ቀደም ብሎ ተተንብዮል:- “ጀርባዬን ለገራፊዎች ጉንጬንም ለጠጉር ነጪዎች ሰጠሁ፣ ፊቴንም ከውርደትና ከትፋት አልመለስሁም።” (ኢሳይያስ 50:6) ትንቢቱ እንደሚገልጸው መሲሑ በተቃዋሚዎች እጅ ወድቆ ሥቃይና ውርደት ይደርስበታል። ኢየሱስ ይህን በሚገባ ያውቃል። ይህ ስደት እስከ ምን ደረጃ እንደሚቀጥልም አስቀድሞ ተረድቷል። ምድራዊ ሕይወቱ የሚያበቃበት ጊዜ እየተቃረበ በሚመጣበት ጊዜም እንኳ አንዳች ፍርሃት አያድርበትም። እንደ ባልጩት የጠነከረ ቆራጥ አቋም በመያዝ ሰብዓዊ ሕይወቱ ወደሚያልፍባት የኢየሩሳሌም ከተማ ይወጣል። በመንገድ ላይ ሳሉም ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ ይላቸዋል:- “እነሆ፣ ወደ ኢየሩሳሌም እንወጣለን፣ የሰው ልጅም ለካህናት አለቆችና ለጻፎች አልፎ ይሰጣል፣ የሞት ፍርድም ይፈርዱበታል፣ ለአሕዛብም አሳልፈው ይሰጡታል፣ ይዘብቱበትማል ይተፉበትማል ይገርፉትማል ይገድሉትማል፣ በሦስተኛውም ቀን ይነሣል።” (ማርቆስ 10:33, 34) ይህ ሁሉ ግፍና በደል የሚደርስበት ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን ማስተዋል ይጠበቅባቸው በነበሩ የካህናት አለቆችና ጻፎች ዋና ቆስቋሽነት ነው።

14, 15. ኢሳይያስ ኢየሱስ እንደሚገረፍና ውርደት እንደሚደርስበት የተናገራቸው ቃላት ፍጻሜያቸውን ያገኙት እንዴት ነው?

14 ኒሳን 14, 33 እዘአ ምሽት ላይ ኢየሱስ በጌቴሴማኒ የአትክልት ሥፍራ ሆኖ እየጸለየ ነው። ከተከታዮቹ መካከል አንዳንዶቹ አብረውት አሉ። ለዓመፅ የተነሳሱ ሰዎች በድንገት ወደ አትክልት ሥፍራው በመምጣት ኢየሱስን ያዙት። ሆኖም ኢየሱስ ይሖዋ ከእርሱ ጋር መሆኑን ያውቅ ስለነበረ በሁኔታው አልተሸበረም። አባቱን ቢለምን ከአሥራ ሁለት ጭፍሮች የሚበልጡ መላእክት በመላክ ሊያድነው እንደሚችል በመግለጽ በፍርሃት የተዋጡትን ሐዋርያቱን ካረጋጋቸው በኋላ “እንዲህ ከሆነስ . . . መጻሕፍት እንዴት ይፈጸማሉ?” አላቸው።​—⁠ማቴዎስ 26:​36, 47, 53, 54

15 በመሲሑ ላይ የሚደርሰውን ፈተናና ሞት በተመለከተ የተነገሩት ትንቢቶች በሙሉ ተፈጽመዋል። ኢየሱስ በሳንሄድሪን ፊት ቀርቦ በሐሰት ከተወነጀለ በኋላ ጴንጤናዊው ጲላጦስ የተለያዩ ጥያቄዎችን ያቀረበለት ከመሆኑም በላይ አስገርፎታል። ሮማውያን ወታደሮች “ራሱን በመቃ መቱት ተፉበትም።” በዚህ መንገድ ኢሳይያስ የተናገራቸው ቃላት ፍጻሜያቸውን አግኝተዋል። (ማርቆስ 14:​65፤ 15:​19፤ ማቴዎስ 26:​67, 68) መጽሐፍ ቅዱስ የኢየሱስ ጢም ከፍተኛ ንቀትን በሚያሳይ ሁኔታ ቃል በቃል ስለመነጨቱ የሚናገረው ነገር ባይኖርም እንኳ ኢሳይያስ በተነበየው መሠረት ይህም ድርጊት በኢየሱስ ላይ ተፈጽሞ ሊሆን እንደሚችል ጥርጥር የለውም። *​—⁠ነህምያ 13:​25

16. ኢየሱስ ከባድ ፈተና በደረሰበት ጊዜም እንኳ ምን ሁኔታ ይንጸባረቅበት ነበር? በኀፍረት ያልተሸማቀቀውስ ለምንድን ነው?

16 ኢየሱስ ጲላጦስ ፊት በቀረበ ጊዜ ሕይወቱን እንዲያተርፍለት አልተማጸነውም። ከዚህ ይልቅ ቅዱሳን ጽሑፎች ይፈጸሙ ዘንድ መሞት እንዳለበት በመገንዘብ ዝምታን መርጧል። ሮማዊው ገዥ ሊያስገድለውም ሆነ በነፃ ሊለቀው ሥልጣን እንዳለው በገለጸለት ጊዜ ኢየሱስ ያላንዳች ፍርሃት “ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህ” ሲል መለሰለት። (ዮሐንስ 19:11) የጲላጦስ ወታደሮች በኢየሱስ ላይ ኢሰብዓዊ ድርጊት ቢፈጽሙበትም እንኳ በኀፍረት እንዲሸማቀቅ ሊያደርጉት አልቻሉም። ደግሞስ በኀፍረት የሚሸማቀቅበት ምን ምክንያት ይኖራል? ሊያስቀጣው የሚችል ምንም የሠራው ጥፋት የለም። ይህን ሁሉ መከራ የተቀበለው ለጽድቅ ሲል ነው። በመሆኑም ኢሳይያስ ቀጥሎ የተናገራቸው ትንቢታዊ ቃላት ፍጻሜያቸውን አግኝተዋል:- “ጌታ እግዚአብሔር ይረዳኛልና ስለዚህ አልታወክሁም፤ ስለዚህም ፊቴን እንደ ባልጩት ድንጋይ አድርጌዋለሁ፣ እንዳላፍርም አውቃለሁ።”​—⁠ኢሳይያስ 50:7

17. ይሖዋ በኢየሱስ ምድራዊ አገልግሎት ወቅት ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ከጎኑ የነበረው እንዴት ነው?

17 ኢየሱስ እንዲህ ያለ ድፍረት ሊያሳይ የቻለው ሙሉ በሙሉ በይሖዋ ላይ ይተማመን ስለነበረ ነው። ይታይበት የነበረው ሁኔታ የሚከተሉትን የኢሳይያስ ቃላት ሙሉ በሙሉ የሚያንጸባርቅ ነው:- “የሚያጸድቀኝ ቅርብ ነው፤ ከእኔስ ጋር የሚከራከር ማን ነው? በአንድነት እንቁም፤ የሚከራከረኝ ማን ነው? ወደ እኔ ይቅረብ። እነሆ፣ ጌታ እግዚአብሔር ይረዳኛል፤ ማን ይፈርድብኛል? እነሆ፣ ሁሉ እንደ ልብስ ያረጃሉ ብልም ይበላቸዋል።” (ኢሳይያስ 50:8, 9) ኢየሱስ በተጠመቀበት ዕለት ይሖዋ ይህ የአምላክ መንፈሳዊ ልጅ ጻድቅ መሆኑን አስታውቋል። እንዲያውም በዚያን ወቅት የራሱ የአምላክ ድምፅ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው” ብሎ ሲናገር ተሰምቷል። (ማቴዎስ 3:17) ኢየሱስ በምድራዊ ሕይወቱ መገባደጃ ላይ በጌቴሴማኒ የአትክልት ሥፍራ ውስጥ ተንበርክኮ ሲጸልይ ‘አንድ መልአክ ከሰማይ መጥቶ አበርትቶታል።’ (ሉቃስ 22:​41-43) ስለዚህ ኢየሱስ አባቱ በአኗኗሩ እንደተደሰተ ተገንዝቧል። ይህ ፍጹም የአምላክ ልጅ ምንም ዓይነት ኃጢአት አልሠራም። (1 ጴጥሮስ 2:​22) ጠላቶቹ የሰንበትን ሕግ ይጥሳል፣ ጠጪ ነው እንዲሁም ጋኔን አለበት እያሉ በሐሰት ቢወነጅሉትም ኢየሱስ በዚህ የሐሰት ክስ አልተሸማቀቀም። አምላክ ከጎኑ በመሆኑ ማን ሊቃወመው ይችላል?​—⁠ሉቃስ 7:​34፤ ዮሐንስ 5:​18፤ 7:​20፤ ሮሜ 8:​31፤ ዕብራውያን 12:​3

18, 19. ቅቡዓን ክርስቲያኖች ልክ እንደ ኢየሱስ ምን ደርሶባቸዋል?

18 ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን “እኔን አሳደውኝ እንደ ሆኑ እናንተን ደግሞ ያሳድዱአችኋል” ሲል አስጠንቅቋቸው ነበር። (ዮሐንስ 15:20) ብዙም ሳይቆይ የተከናወኑት ሁኔታዎች ይህን የሚያረጋግጡ ናቸው። በ33 እዘአ በጰንጠቆስጤ ዕለት መንፈስ ቅዱስ በኢየሱስ ታማኝ ደቀ መዛሙርት ላይ በወረደ ጊዜ የክርስቲያን ጉባኤ ተቋቋመ። ወዲያውኑ ማለት ይቻላል፣ የሃይማኖት መሪዎች “የአብርሃም ዘር” አባላት ሆነው ከኢየሱስ ጋር የተባበሩትና የአምላክ መንፈሳዊ ልጆች ሆነው የተዋጁት እነዚህ ታማኝ ወንዶችና ሴቶች የሚያከናውኑትን የስብከት ሥራ ለመግታት ሞክረዋል። (ገላትያ 3:​26, 29፤ 4:​5, 6) ከመጀመሪያው መቶ ዘመን አንስቶ አሁን እስካለንበት ጊዜ ድረስ ቅቡዓን ክርስቲያኖች ለጽድቅ የጸና አቋም በመያዝ የኢየሱስ ጠላቶች የሚነዙባቸውን የሐሰት ፕሮፓጋንዳና የሚያደርሱባቸውን ከባድ ስደት መቋቋም ግድ ሆኖባቸዋል።

19 ይሁንና ኢየሱስ የተናገራቸውን የሚከተሉትን አበረታች ቃላት ያስታውሳሉ:- “ሲነቅፉአችሁና ሲያሳድዱአችሁ በእኔም ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲናገሩባችሁ ብፁዓን ናችሁ። ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ።” (ማቴዎስ 5:11, 12) በመሆኑም ቅቡዓን ክርስቲያኖች ኃይለኛ ጥቃት በሚሰነዘርባቸው ጊዜም እንኳ አይሸማቀቁም። ተቃዋሚዎቻቸው ምንም አሉ ምን አምላክ ጻድቃን ብሎ እንደጠራቸው ያውቃሉ። በአምላክ ፊት ‘ነውርና ነቀፋ የለባቸውም።’​—⁠ቆላስይስ 1:​21, 22

20. (ሀ) ቅቡዓን ክርስቲያኖችን እየደገፉ ያሉት እነማን ናቸው? ምንስ ደርሶባቸዋል? (ለ) ቅቡዓን ክርስቲያኖችም ሆኑ “ሌሎች በጎች” በተማሩት ሰዎች ምላስ መናገር የሚችሉት እንዴት ነው?

20 በዘመናችን የ“ሌሎች በጎች” አባላት የሆኑ “እጅግ ብዙ ሰዎች” ቅቡዓን ክርስቲያኖችን በመደገፍ ላይ ናቸው። እጅግ ብዙ ሰዎችም ለጽድቅ የጸና አቋም ይዘዋል። በዚህም ምክንያት ከቅቡዓን ወንድሞቻቸው ጋር መከራ የደረሰባቸው ከመሆኑም በላይ ‘ልብሳቸውን አጥበው በበጉ ደም አንጽተዋል።’ ይሖዋ እነዚህ ሰዎች ‘ታላቁን መከራ’ በሕይወት የሚያልፉ ጻድቃን እንደሆኑ ተናግሯል። (ራእይ 7:​9, 14, 15፤ ዮሐንስ 10:​16፤ ያዕቆብ 2:​23) በአሁኑ ጊዜ ተቃዋሚዎቻቸው የማይበገሩ መስለው ቢታዩም እንኳ አምላክ የወሰነው ጊዜ ሲደርስ እነዚህ ተቃዋሚዎች ከመጣል በቀር ለምንም እንደማይረባ ብል የበላው ልብስ እንደሚሆኑ የኢሳይያስ ትንቢት ያመለክታል። እስከዚያው ጊዜ ድረስ ግን ቅቡዓን ክርስቲያኖችም ሆኑ “ሌሎች በጎች” ዘወትር በመጸለይ፣ የአምላክን ቃል በማጥናትና ይሖዋን በአንድነት ተሰብስበው በማምለክ አቋማቸውን ጠብቀው ይኖራሉ። በዚህ መንገድ ከይሖዋ የተማሩ ይሆናሉ፤ እንዲሁም በተማሩት ሰዎች ምላስ ይናገራሉ።

በይሖዋ ስም ታመኑ

21. (ሀ) በብርሃን የሚጓዙት እነማን ናቸው? ምን ውጤትስ ያገኛሉ? (ለ) በጨለማ የሚጓዙ ምን ይደርስባቸዋል?

21 አሁን ደግሞ የሚከተለውን የጎላ ልዩነት ተመልከት:- “ከእናንተ እግዚአብሔርን የሚፈራ፣ የባሪያውንም ቃል የሚሰማ ማን ነው? ያ ሰው በጨለማ የሚሄድ ከሆነና፣ ብርሃንም ከሌለው፣ በእግዚአብሔር [ስም ] ይታመን፤ በአምላኩም ይደገፍ።” (ኢሳይያስ 50:10 አ.መ.ት ) የአምላክ አገልጋይ የሆነውን የኢየሱስ ክርስቶስን ድምፅ የሚሰሙ ሁሉ በብርሃን ይጓዛሉ። (ዮሐንስ 3:​21) ይሖዋ የሚለውን መለኮታዊ ስም መጠቀም ብቻ ሳይሆን የዚህ ስም ባለቤት በሆነው አምላክ ላይ ይታመናሉ። በአንድ ወቅት በጨለማ ይጓዙ የነበረ ቢሆን እንኳ አሁን ሰውን አይፈሩም። በአምላካቸው ላይ ይደገፋሉ። በጨለማ መጓዛቸውን የሚቀጥሉ ሰዎች ግን ሰውን ይፈራሉ። ጴንጤናዊው ጲላጦስ እንዲህ ዓይነት ሰው ነበር። ኢየሱስ ከተመሠረቱበት የሐሰት ክሶች በሙሉ ነፃ መሆኑን ቢገነዘብም እንኳ ይህ ሮማዊ ባለሥልጣን ሰውን በመፍራቱ ኢየሱስን ሊለቅቀው አልደፈረም። የሮም ወታደሮች የአምላክን ልጅ ቢገድሉትም ይሖዋ ከሞት በማስነሳት የግርማና የክብር አክሊል አጎናጽፎታል። ጲላጦስስ የደረሰበት ሁኔታ ምን ነበር? ፍላቪየስ ጆሴፈስ የተባለው አይሁዳዊ ታሪክ ጸሐፊ እንደዘገበው ኢየሱስ በሞተ በአራት ዓመት ጊዜ ውስጥ ጲላጦስ በሌላ ሮማዊ ገዥ እንዲተካ ከመደረጉም በተጨማሪ ወደ ሮም ተመልሶ ለተመሠረቱበት ከባድ ክሶች መልስ እንዲሰጥ ታዝዟል። ኢየሱስን ያስገደሉት አይሁዶችስ ምን ደረሰባቸው? አራት አሥርተ ዓመታት በማይሞላ ጊዜ ውስጥ የሮም ሠራዊት ኢየሩሳሌምን በማውደም ነዋሪዎቿን ከመጨፍጨፉም በላይ ከሞት የተረፉትን ለባርነት ዳርጓቸዋል። ጨለማን የመረጡ ሁሉ መጨረሻቸው አያምርም።​—⁠ዮሐንስ 3:​19

22. ሰዎች ያድኑናል ብሎ ተስፋ ማድረግ ትልቅ ሞኝነት የሆነው ለምንድን ነው?

22 ሰዎች ያድኑናል ብሎ ተስፋ ማድረግ ትልቅ ሞኝነት ነው። የኢሳይያስ ትንቢት ምክንያቱን ሲገልጽ እንዲህ ይላል:- “እነሆ፣ እሳት የምታነድዱ የእሳትንም ወላፈን የምትታጠቁ ሁላችሁ፣ በእሳታችሁ ነበልባል ባነደዳችሁትም ወላፈን ሂዱ፤ ይህ ከእጄ ይሆንባችኋል፤ በኀዘን ትተኛላችሁ።” (ኢሳይያስ 50:11) ሰብዓዊ መሪዎች ይሾማሉ ይሻራሉ። አንድ ልዩ ግርማ ሞገስ ያለው መሪ ለተወሰነ ጊዜ የሕዝቡን ቀልብ መሳብ ይችል ይሆናል። ይሁን እንጂ አንድ ሰው ምንም ያህል ቅን አስተሳሰብ ቢኖረው ሊያደርገው የሚችለው ነገር በጣም ውስን ነው። ደጋፊዎቹ በደንብ የሚንቀለቀል እሳት ያነድልናል ብለው ሲጠብቁ እሳቱ አነስተኛ ብርሃንና ሙቀት ሰጥቶ ወዲያው እልም የሚል ትንሽ ‘የእሳት ነበልባል’ ሆኖ ሊቀር ይችላል። በሴሎ ማለትም በመሲሑ የሚታመኑ ሰዎች ግን እንደጠበቁት ሳይሆን ቀርቶ ለሐዘን አይዳረጉም።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.2 ይሖዋ በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 50 የመጀመሪያ ሦስት ቁጥሮች ላይ የይሁዳን ብሔር በጥቅሉ እንደ ሚስቱ ነዋሪዎቿን ደግሞ በግለሰብ ደረጃ እንደ ልጆቿ አድርጎ ገልጿቸዋል።

^ አን.9 ጸሐፊው ከ⁠ኢሳ. 50 ቁጥር 4-11 ጀምሮ እስከ ምዕራፉ መጨረሻ ድረስ ባሉት ቁጥሮች ላይ ስለራሱ እየተናገረ ያለ ይመስላል። ኢሳይያስ በእነዚህ ቁጥሮች ላይ ከተጠቀሱት ፈተናዎች መካከል አንዳንዶቹ በራሱ ላይ ደርሰውበት ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ ትንቢቱ ሙሉ በሙሉ ፍጻሜውን ያገኘው በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ነው።

^ አን.15ሰፕቱጀንት ትርጉም ኢሳይያስ 50:​6ን “ጀርባዬን ለጅራፍ ጉንጬንም ለጥፊ አሳልፌ ሰጠሁ” ሲል ተርጉሞታል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 155 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

አይሁዳውያን ከይሖዋ ይልቅ የሰብዓዊ ገዥዎችን እርዳታ መርጠዋል

[በገጽ 156, 157 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሖዋ በእስራኤላውያንና በግብጻውያን መካከል የደመና አምድ በማቆም ሕዝቡን ጠብቋል