በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በጽዮን ጽድቅ ይበቅላል

በጽዮን ጽድቅ ይበቅላል

ምዕራፍ ሃያ ሁለት

በጽዮን ጽድቅ ይበቅላል

ኢሳይያስ 61:​1-11

1, 2. እስራኤል ምን ዓይነት ለውጥ ይጠብቃታል? ይህንን ለውጥ የሚያመጣውስ ማን ነው?

ነፃነት የሚታወጅበት ጊዜ ደርሷል! ይሖዋ ሕዝቡን ነፃ በማውጣት ወደ አባቶቻቸው ምድር ለመመለስ ወስኗል። ካፊያ ዝናብ ከጣለ በኋላ እንደሚበቅል ዘር እውነተኛው አምልኮም ዳግመኛ ያቆጠቁጣል። በዚያን ጊዜ ግዞተኞቹ ከተስፋ መቁረጥ ስሜት ተላቅቀው በታላቅ ደስታ የሚያመሰግኑ ከመሆኑም በላይ በሐዘን ተውጠው አመድ የነሰነሱበት ጭንቅላታቸው በመለኮታዊ ሞገስ አክሊል ያጌጣል።

2 ይህን ዕጹብ ድንቅ የሆነ ለውጥ የሚያመጣው ማን ነው? ከይሖዋ በስተቀር ማንም ሊሆን አይችልም! (መዝሙር 9:​19, 20፤ ኢሳይያስ 40:​25) ነቢዩ ሶፎንያስ በትንቢት የሚከተለውን ትእዛዝ አስተላልፏል:- “የጽዮን ልጅ ሆይ፣ ዘምሪ፤ እስራኤል ሆይ፣ እልል በል፤ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፣ በፍጹም ልብሽ ሐሤት አድርጊ ደስም ይበልሽ። እግዚአብሔር ፍርድሽን አስወግዶአል።” (ሶፎንያስ 3:14, 15) ያ ጊዜ ምንኛ አስደሳች ይሆናል! በ537 ከዘአበ ይሖዋ ቀሪዎቹን ወደ ትውልድ አገራቸው ሲመልሳቸው ሕልማቸው እውን የሆነ ያህል ይሆናል።​—⁠መዝሙር 126:​1

3. በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 61 ላይ የሚገኙት ትንቢታዊ ቃላት ምን ፍጻሜ አላቸው?

3 አይሁዳውያን ወደ ትውልድ አገራቸው እንደሚመለሱ በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 61 ላይ አስቀድሞ ተተንብዮ ነበር። ይሁን እንጂ ትንቢቱ በ537 ከዘአበ ከተፈጸመ ከብዙ መቶ ዘመናት በኋላ በመጀመሪያው መቶ ዘመን በነበሩት በኢየሱስና በተከታዮቹ እንዲሁም በዘመናችን ባሉ የይሖዋ አገልጋዮች ላይ በላቀና ይበልጥ ስፋት ባለው መንገድ ፍጻሜውን አግኝቷል። እንግዲያው እነዚህ በመንፈስ አነሳሽነት የተነገሩ ቃላት ትልቅ ትርጉም አላቸው።

‘ይሖዋ በጎ ፈቃድ የሚያሳይበት ዓመት’

4. በ⁠ኢሳይያስ 61:​1 የመጀመሪያ ፍጻሜ መሠረት ምሥራች የመናገር ተልዕኮ የተሰጠው ለማን ነው? በሁለተኛው ፍጻሜስ?

4 ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ጻፈ:- “የጌታ የእግዚአብሔር መንፈስ በእኔ ላይ ነው፣ ለድሆች የምሥራችን እሰብክ ዘንድ እግዚአብሔር ቀብቶኛልና፤ ልባቸው የተሰበረውን እጠግን ዘንድ፣ ለተማረኩትም ነጻነትን ለታሰሩትም መፈታትን እናገር ዘንድ [“የታሰሩትንም ዓይን እከፍት ዘንድ፣” NW ] ልኮኛል።” (ኢሳይያስ 61:1) ምሥራች የመናገር ተልዕኮ የተሰጠው ማን ነው? በመጀመሪያው የትንቢቱ ፍጻሜ መሠረት ይህ ተልዕኮ የተሰጠው በባቢሎን ለሚገኙት ግዞተኞች በአምላክ መንፈስ አነሳሽነት ምሥራች የዘገበው ነቢዩ ኢሳይያስ መሆን አለበት። ይሁን እንጂ ኢየሱስ ኢሳይያስ የጻፋቸው ቃላት በእሱ ላይ ፍጻሜያቸውን እንደሚያገኙ በተናገረ ጊዜ ትንቢቱ እጅግ የላቀ ፍጻሜ እንዳለው አመልክቷል። (ሉቃስ 4:​16-21) አዎን፣ ኢየሱስ የተላከው ቅን ለሆኑ ሰዎች ምሥራች ለመንገር ሲሆን ይህን ተልዕኮ መወጣት ይችል ዘንድ በተጠመቀበት ወቅት በመንፈስ ቅዱስ ተቀብቷል።​—⁠ማቴዎስ 3:​16, 17

5. ወደ 2, 000 ለሚጠጉ ዓመታት ምሥራቹን ሲሰብኩ የኖሩት እነማን ናቸው?

5 ከዚህም በተጨማሪ ኢየሱስ ተከታዮቹን ወንጌላውያን ወይም የምሥራቹ ሰባኪዎች እንዲሆኑ አሠልጥኗቸዋል። በ33 እዘአ በጰንጠቆስጤ ዕለት 120 የሚሆኑ ተከታዮቹ በመንፈስ ቅዱስ ተቀብተው የአምላክ መንፈሳዊ ልጆች ሆነዋል። (ሥራ 2:​1-4, 14 - 42፤ ሮሜ 8:​14-16) እነርሱም ምሥራቹን ቅን ለሆኑና ልባቸው ለተሰበረ ሰዎች የመናገር ተልዕኮ ተሰጥቷቸዋል። እነዚህ 120 የሚሆኑ የክርስቶስ ተከታዮች በዚህ መንገድ ከተቀቡት 144, 000 ሰዎች መካከል የመጀመሪያዎቹ ናቸው። የዚህ ቡድን የመጨረሻዎቹ አባላት በዛሬው ጊዜ በምድር ላይ እያገለገሉ ነው። በመሆኑም የኢየሱስ ቅቡዓን ተከታዮች ወደ 2, 000 ለሚጠጉ ዓመታት “ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን” ሲመሰክሩ ኖረዋል።​—⁠ሥራ 20:​20

6. በጥንት ዘመን ምሥራቹ ሲሰበክላቸው እፎይታ ያገኙት እነማን ናቸው? በዛሬው ጊዜስ?

6 ኢሳይያስ በመንፈስ አነሳሽነት የጻፈው መልእክት በባቢሎን ለነበሩት ንስሐ የገቡ አይሁዶች እፎይታ አስገኝቶላቸዋል። ከዚህም በተጨማሪ ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ በምድር ላይ በኖሩበት ዘመን በእስራኤል ምድር ይፈጸም በነበረው የክፋት ድርጊት ልባቸው ለተሰበረና በአይሁድ እምነት የሐሰት ሃይማኖታዊ ወጎች ታስረው ተስፋ ለቆረጡ አይሁዶች እፎይታ አስገኝቷል። (ማቴዎስ 15:​3-6) በዛሬው ጊዜ በሕዝበ ክርስትና አረማዊ ልማዶችና የአምላክን ክብር ዝቅ በሚያደርጉ ወጎች ተተብትበው የሚገኙ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በዚህ ሃይማኖታዊ ሥርዓት ውስጥ በሚሠራው ርኩሰት ‘እያለቀሱና እየተከዙ’ ነው። (ሕዝቅኤል 9:​4) ምሥራቹን የተቀበሉት ሰዎች ከነበሩበት አሳዛኝ ሁኔታ መላቀቅ ችለዋል። (ማቴዎስ 9:​35-38) ይሖዋን “በመንፈስና በእውነት” ማምለክ እንዳለባቸው ሲማሩ የማስተዋል ዓይኖቻቸው ወለል ብለው ተከፍተዋል።​—⁠ዮሐንስ 4:​24

7, 8. (ሀ) ይሖዋ ‘በጎ ፈቃዱን ያሳየባቸው’ ሁለት የተለያዩ ዓመታት የትኞቹ ናቸው? (ለ) ሁለቱ የይሖዋ ‘የበቀል ቀኖችስ’ የትኞቹ ናቸው?

7 ምሥራቹ የሚሰበክበት የተወሰነ ጊዜ አለው። ኢየሱስና ተከታዮቹ ‘የተወደደችውን የእግዚአብሔርን ዓመት [“ይሖዋ በጎ ፈቃድ የሚያሳይበትን ዓመት፣” NW ] አምላካችንም የሚበቀልበትን ቀን እንዲናገሩና የሚያለቅሱትንም እንዲያጽናኑ’ ተልዕኮ ተሰጥቷቸዋል። (ኢሳይያስ 61:​2) ዓመት ረጅም ጊዜ ቢሆንም እንኳ መጀመሪያና መጨረሻ አለው። ይሖዋ ‘በጎ ፈቃድ በሚያሳይበት ዓመት’ ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች አምላክ ለሚያሳውጀው የነፃነት አዋጅ አዎንታዊ ምላሽ መስጠት የሚችሉበትን አጋጣሚ ያገኛሉ።

8 በመጀመሪያው መቶ ዘመን ይሖዋ ለአይሁድ ሕዝብ በጎ ፈቃድ የሚያሳይበት ዓመት የጀመረው ኢየሱስ ምድራዊ አገልግሎቱን ማከናወን በጀመረበት በ29 እዘአ ነው። ኢየሱስ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” እያለ ለአይሁዳውያን ይሰብክ ነበር። (ማቴዎስ 4:​17) አምላክ በጎ ፈቃዱን ያሳየበት ይህ ዓመት የዘለቀው በ70 እዘአ እስከተደመደመው የይሖዋ ‘የበቀል ቀን’ ድረስ ሲሆን በዚያን ጊዜ የሮም ሠራዊት ኢየሩሳሌምንና ቤተ መቅደሷን ደምስሷል። (ማቴዎስ 24:​3-22) እኛም ዛሬ የምንኖረው ይሖዋ በጎ ፈቃዱን እያሳየ ባለበት ሌላ ዓመት ውስጥ ሲሆን ይህ ዓመት የጀመረው የአምላክ መንግሥት በ1914 በሰማይ በተቋቋመበት ጊዜ ነው። ይሖዋ በጎ ፈቃዱን እያሳየ ያለበት ይህ ዓመት በሌላ እጅግ መጠነ ሰፊ በሆነ የበቀል ቀን ይደመደማል። በዚያን ጊዜ ይሖዋ ‘በታላቁ መከራ’ መላውን የዚህ ዓለም ሥርዓት ይደመስሰዋል።​—⁠ማቴዎስ 24:​21

9. በዘመናችን ይሖዋ በጎ ፈቃዱን እያሳየ ባለበት ዓመት መጠቀም የሚችሉት እነማን ናቸው?

9 በዘመናችን አምላክ በጎ ፈቃዱን እያሳየ ባለበት ዓመት መጠቀም የሚችሉት እነማን ናቸው? መልእክቱን የሚቀበሉ፣ ቅን መሆናቸውን በተግባር የሚያሳዩና የአምላክን መንግሥት “ለአሕዛብ ሁሉ” የማወጁን ሥራ በቅንዓት የሚደግፉ ሰዎች ናቸው። (ማርቆስ 13:​10) እንዲህ ያሉ ሰዎች ምሥራቹ በእጅጉ ያጽናናቸዋል። መልእክቱን የማይቀበሉና ይሖዋ በጎ ፈቃድ እያሳየ ባለበት ዓመት የተከፈተውን አጋጣሚ ለመጠቀም ፈቃደኛ ያልሆኑ ሰዎች ግን በቅርብ ጊዜ ውስጥ የአምላክን የበቀል ቀን ለመጋፈጥ ይገደዳሉ።​—⁠2 ተሰሎንቄ 1:​6-9

አምላክን የሚያስከብር መንፈሳዊ ፍሬ

10. ከባቢሎን የሚመለሱት አይሁዳውያን ይሖዋ ያደረገላቸውን ድንቅ ሥራ ሲመለከቱ ምን ይሰማቸዋል?

10 ከባቢሎን የሚመለሱት አይሁዶች ይሖዋ ድንቅ ሥራ እንዳከናወነላቸው ይገነዘባሉ። ከግዞት ነፃ ስለሚወጡ በባቢሎን ሳሉ ያሰሙት የነበረው ልቅሶ በደስታና በምስጋና ይተካል። በመሆኑም ኢሳይያስ የሚከተለውን ትንቢታዊ ተልዕኮ ይፈጽማል:- “እግዚአብሔር ለክብሩ የተከላቸው [“ትልልቅ፣” NW ] የጽድቅ ዛፎች እንዲባሉ ለጽዮን አልቃሾች አደርግላቸው ዘንድ፣ በአመድ ፋንታ አክሊልን፣ በልቅሶም ፋንታ የደስታን ዘይት፣ በኀዘንም መንፈስ ፋንታ የምስጋናን መጐናጸፊያ እሰጣቸው ዘንድ ልኮኛል።”​—⁠ኢሳይያስ 61:3

11. በመጀመሪያው መቶ ዘመን ይሖዋን ላከናወነው ድንቅ ነገር ለማመስገን የተገፋፉት እነማን ናቸው?

11 በመጀመሪያው መቶ ዘመን ከሐሰት ሃይማኖት ባርነት ነፃ የወጡት አይሁዶችም ላደረገላቸው ድንቅ ነገር አምላክን አመስግነውታል። በመንፈሳዊ ከሞተ ብሔር መካከል ነፃ በወጡ ጊዜ የተደቆሰው መንፈሳቸው ‘በምስጋና መጎናጸፊያ’ ተተክቷል። እንዲህ ያለው ለውጥ በኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ የተከሰተው በክርስቶስ ሞት እጅግ አዝነው ሳለ ከሞት የተነሳው ጌታቸው በመንፈስ ቅዱስ እንዲቀቡ በማድረግ ሐዘናቸውን በደስታ በተካው ጊዜ ነበር። ብዙም ሳይቆይ በመንፈስ ቅዱስ የተቀቡት የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች የሰጡትን ስብከት ሰምተው በ33 እዘአ በተጠመቁት 3, 000 የሚሆኑ ቅን ሰዎችም ላይ ተመሳሳይ የሆነ ለውጥ ተከስቷል። (ሥራ 2:​41) የይሖዋ በረከት እንዳልተለያቸው ማወቃቸው ምንኛ ጠቃሚ ነው! ‘ለጽዮን በማልቀስ’ ፋንታ መንፈስ ቅዱስ ከመቀበላቸውም በላይ የይሖዋን የተትረፈረፈ በረከት ያገኙ ሰዎች የሚሰማቸውን ደስታ የሚወክለውን ‘የደስታ ዘይት’ በመቀባታቸው መንፈሳቸው ታድሷል።​—⁠ዕብራውያን 1:​9

12, 13. (ሀ) በ537 ከዘአበ ወደ ትውልድ አገራቸው በተመለሱት አይሁዶች መካከል የነበሩት “ትልልቅ የጽድቅ ዛፎች” እነማን ናቸው? (ለ) ከ33 እዘአ አንስቶ “ትልልቅ የጽድቅ ዛፎች” የሆኑት እነማን ናቸው?

12 ይሖዋ “ትልልቅ የጽድቅ ዛፎች” በመስጠት ሕዝቡን ባርኳቸዋል። እነዚህ ትልልቅ ዛፎች እነማን ናቸው? ከ537 ከዘአበ አንስቶ በነበሩት ዓመታት የአምላክን ቃል በማጥናትና በቃሉ ላይ በማሰላሰል የይሖዋን የጽድቅ መስፈርቶች ያዳበሩ ግለሰቦች ነበሩ። (መዝሙር 1:​1-3፤ ኢሳይያስ 44:​2-4፤ ኤርምያስ 17:​7, 8) እንደ ዕዝራ፣ ሐጌ፣ ዘካርያስና ሊቀ ካህናቱ ኢያሱ ያሉት ወንዶች ከእውነት ጎን ጸንተው የቆሙና ሕዝቡን ከመንፈሳዊ ብክለት የጠበቁ ጎልተው የሚታዩ ‘ትልልቅ ዛፎች’ ነበሩ።

13 ከ33 እዘአ አንስቶ አምላክ በአዲሱ ብሔር ይኸውም “በእግዚአብሔር እስራኤል” መንፈሳዊ ርስት ላይ ተመሳሳይ የሆኑ “ትልልቅ የጽድቅ ዛፎች” ማለትም ደፋር ቅቡዓን ክርስቲያኖችን ተክሏል። (ገላትያ 6:​16) ባለፉት መቶ ዘመናት እነዚህ “ዛፎች” ቁጥራቸው 144, 000 የደረሰ ሲሆን ይሖዋ አምላክን የሚያስከብር የጽድቅ ፍሬ ያፈራሉ። (ራእይ 14:​3) ከእነዚህ ማራኪ ግርማ ካላቸው “ዛፎች” መካከል የመጨረሻዎቹ ያደጉት ይሖዋ፣ ለጊዜው በድን ሆነው የነበሩትን የአምላክ እስራኤል ቀሪዎች መልሶ ሕያው ካደረገበት ከ1919 በኋላ በነበሩት ዓመታት ውስጥ ነው። ይሖዋ የተትረፈረፈ መንፈሳዊ ውኃ በመስጠት ፍሬ የሚሰጡ እጅግ በርካታ የጽድቅ ዛፎች አብቅሏል ማለት ይቻላል።​—⁠ኢሳይያስ 27:​6

14, 15. ነፃ የወጡት የይሖዋ አምላኪዎች (ሀ) በ537 ከዘአበ (ለ) በ33 እዘአ (ሐ) በ1919 ምን ሥራዎች አከናውነዋል?

14 ኢሳይያስ በመቀጠል እነዚህ “ዛፎች” የሚያከናውኑትን ሥራ እንዲህ ሲል ጎላ አድርጎ ገለጸ:- “ከጥንትም ጀምሮ ባድማ የነበሩትን ይሠራሉ ከቀድሞ የፈረሱትንም ያቆማሉ፤ ባድማ የነበሩትንና ከብዙ ትውልድ በፊት የፈረሱትን ከተሞች እንደ ገና ይሠራሉ።” (ኢሳይያስ 61:4) ከባቢሎን ወደ ትውልድ አገራቸው የተመለሱት ታማኝ አይሁዳውያን የፋርሱ ንጉሥ ቂሮስ ባወጣው አዋጅ መሠረት ለረጅም ጊዜ ባድማ ሆነው የቆዩትን ኢየሩሳሌምንና ቤተ መቅደሷን መልሰው ገንብተዋል። ከ33 እዘአ እና ከ1919 በኋላ በነበሩት ዓመታትም የመልሶ ግንባታ ሥራዎች ተካሂደዋል።

15 በ33 እዘአ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ጌታቸው ተይዞ ችሎት ፊት ከቀረበ በኋላ በመገደሉ ከፍተኛ ሐዘን ላይ ወድቀው ነበር። (ማቴዎስ 26:​31) ይሁን እንጂ ከሞት ተነስቶ ሲገለጥላቸው አመለካከታቸው ተለወጠ። መንፈስ ቅዱስ ከወረደባቸው በኋላ ደግሞ ምሥራቹን “በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ” በመስበኩ ሥራ ተጠመዱ። (ሥራ 1:​8) በዚህ መንገድ ንጹሑን አምልኮ መልሰው መገንባት ጀመሩ። በተመሳሳይም ከ1919 ወዲህ ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ የቀሩት ቅቡዓን ወንድሞቹ “ከብዙ ትውልድ በፊት የፈረሱትን ከተሞች” መልሰው እንዲገነቡ አደረጋቸው። የሕዝበ ክርስትና ቀሳውስት ለብዙ መቶ ዘመናት የይሖዋን እውቀት ማስተማር ሲገባቸው ሰው ሠራሽ ወጎችና ቅዱስ ጽሑፋዊ ያልሆኑ መሠረተ ትምህርቶች ሲያስተምሩ ኖረዋል። ቅቡዓን ክርስቲያኖች እውነተኛውን አምልኮ የመገንባቱ ሥራ በተጠናከረ ሁኔታ እንዲቀጥል ጉባኤዎቻቸውን ከማንኛውም ዓይነት የሐሰት ሃይማኖት ርዝራዥ ሙሉ በሙሉ አጠሩ። ከዚህም በተጨማሪ በዓለም አቀፍ ደረጃ ታይቶ የማይታወቅ ታላቅ የምሥክርነት ዘመቻ ማካሄድ ጀመሩ።​—⁠ማርቆስ 13:​10

16. በመልሶ ግንባታው ሥራ ቅቡዓን ክርስቲያኖችን በመርዳት ላይ ያሉት እነማን ናቸው? ምን ሥራስ ተሰጥቷቸዋል?

16 ይህ መጠነ ሰፊ የሆነ ሥራ ነው። በአንጻራዊ ሁኔታ ሲታይ በጣም ጥቂት የነበሩት የአምላክ እስራኤል ቀሪዎች እንዲህ ያለውን ሥራ እንዴት ሊወጡት ይችላሉ? ይሖዋ በኢሳይያስ በኩል እንዲህ ሲል ገለጸ:- “መጻተኞችም ቆመው በጎቻችሁን ያሰማራሉ፣ ሌሎች ወገኖችም አራሾችና ወይን ጠባቂዎች ይሆኑላችኋል።” (ኢሳይያስ 61:5) ምሳሌያዊዎቹ መጻተኞችና ሌሎች ወገኖች የኢየሱስ “ሌሎች በጎች” አባላት የሆኑት “እጅግ ብዙ ሰዎች” ናቸው። * (ራእይ 7:​9፤ ዮሐንስ 10:​11, 16) እነዚህ ሰዎች ሰማያዊ ውርሻ ያላቸው በመንፈስ ቅዱስ የተቀቡ ክርስቲያኖች አይደሉም። ከዚህ ይልቅ ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ ያላቸው ናቸው። (ራእይ 21:​3, 4) ያም ሆኖ ይሖዋን የሚወድዱ ከመሆናቸውም በላይ መንፈሳዊ የሆነ የእረኝነት፣ የግብርናና የወይን ጠባቂነት ሥራ ተሰጥቷቸዋል። እነዚህ ተግባራት የሚናቁ ሥራዎች አይደሉም። እነዚህ ሠራተኞች በምድር ላይ ባሉት የአምላክ እስራኤል አባላት አመራር ሥር ሆነው ሰዎችን በመጠበቁ፣ በመንከባከቡና በመሰብሰቡ ሥራ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ያበረክታሉ።​—⁠ሉቃስ 10:​2፤ ሥራ 20:​28፤ 1 ጴጥሮስ 5:​2፤ ራእይ 14:​15, 16

17. (ሀ) የአምላክ እስራኤል አባላት ምን ይባላሉ? (ለ) የኃጢአት ይቅርታ ለማግኘት የሚያስፈልገው ብቸኛው መሥዋዕት የትኛው ነው?

17 ስለ አምላክ እስራኤልስ ምን የተገለጸ ነገር አለ? ይሖዋ በኢሳይያስ በኩል እንዲህ ይላቸዋል:- “እናንተ ግን የእግዚአብሔር ካህናት ትባላላችሁ፣ ሰዎቹም የአምላካችን አገልጋዮች ብለው ይጠሩአችኋል፤ የአሕዛብን ሀብት ትበላላችሁ፣ በክብራቸውም ትመካላችሁ።” (ኢሳይያስ 61:6) በጥንቷ እስራኤል ይሖዋ ለሕዝቡም ሆነ ለራሳቸው መሥዋዕት የሚያቀርቡ ሌዋውያን ካህናትን ይሾም ነበር። ይሁን እንጂ በ33 እዘአ ይሖዋ በሌዋውያን የክህነት አገልግሎት መጠቀሙን በመተው ሌላ የተሻለ ዝግጅት እንዲቋቋም አደረገ። ፍጹሙን የኢየሱስ ሕይወት ለሰው ልጆች ኃጢአት መሥዋዕት አድርጎ ተቀበለ። የኢየሱስ መሥዋዕት ለሁልጊዜ የሚያገለግል በመሆኑ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ሌላ ተጨማሪ መሥዋዕት ማቅረብ አላስፈለገም።​—⁠ዮሐንስ 14:​6፤ ቆላስይስ 2:​13, 14፤ ዕብራውያን 9:​11-14, 24

18. የአምላክ እስራኤል አባላት ምን ዓይነት ካህናት ሆነዋል? ተልዕኳቸውስ ምንድን ነው?

18 ታዲያ የአምላክ እስራኤል አባላት “የእግዚአብሔር ካህናት” የሆኑት እንዴት ነው? ሐዋርያው ጴጥሮስ እንደ እሱው ላሉ ቅቡዓን ክርስቲያኖች እንዲህ ሲል ጽፏል:- “እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትነግሩ የተመረጠ ትውልድ፣ የንጉሥ ካህናት፣ ቅዱስ ሕዝብ፣ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ።” (1 ጴጥሮስ 2:9) በመሆኑም ቅቡዓን ክርስቲያኖች በቡድን ደረጃ አንድ ልዩ ተልዕኮ የተሰጣቸው ካህናት ሆነዋል። የይሖዋን ክብር ለአሕዛብ በመናገር ምሥክሮቹ ሆነው ያገለግላሉ። (ኢሳይያስ 43:​10-12) ቅቡዓን ክርስቲያኖች በመጨረሻዎቹ ቀናት ይህን በጣም አስፈላጊ የሆነ ተልዕኮ በታማኝነት ሲያከናውኑ ቆይተዋል። በውጤቱም በአሁኑ ጊዜ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ከጎናቸው ተሰልፈው ስለ ይሖዋ መንግሥት በመመስከር ላይ ይገኛሉ።

19. ቅቡዓን ክርስቲያኖች ምን አገልግሎት የማከናወን መብት ያገኛሉ?

19 ከዚህም በተጨማሪ የአምላክ እስራኤል አባላት በሌላ መንገድ ካህናት ሆኖ የማገልገል መብት ይጠብቃቸዋል። ምድራዊ ሕይወታቸው ካለፈ በኋላ ከሞት ተነስተው በሰማይ የማይጠፋ መንፈሳዊ ሕይወት ያገኛሉ። በዚያም በኢየሱስ መንግሥት ከእርሱ ጋር ገዥዎች ብቻ ሳይሆን የአምላክ ካህናትም ሆነው ያገለግላሉ። (ራእይ 5:​10፤ 20:​6) በምድር ላይ ያሉ ታማኝ የሰው ልጆች የኢየሱስ ቤዛዊ መሥዋዕት የሚያስገኛቸውን ጥቅሞች እንዲቋደሱ ያደርጋሉ። እነዚህ የአምላክ እስራኤል አባላት በራእይ መጽሐፍ 22ኛ ምዕራፍ ላይ ተመዝግቦ በሚገኘው የዮሐንስ ራእይ ላይም በድጋሚ “ዛፎች” ተብለው ተገልጸዋል። በራእዩ ላይ 144, 000ዎቹም “ዛፎች” በሰማይ “በየወሩ እያፈሩ አሥራ ሁለት ፍሬ” ሲሰጡ ታይተዋል። “የዛፎቹም ቅጠሎች ለሕዝብ መፈወሻ [ናቸው]።” (ራእይ 22:​1, 2 NW ) ይህ እንዴት ያለ ድንቅ የክህነት አገልግሎት ነው!

ኃፍረቱና ውርደቱ በታላቅ ደስታ ተተካ

20. ነገሥታትና ካህናት ሆነው የሚያገለግሉት ቅቡዓን ተቃውሞ ቢደርስባቸውም እንኳ ምን በረከት ይጠብቃቸዋል?

20 ይሖዋ በጎ ፈቃዱን ማሳየት ከጀመረበት ከ1914 አንስቶ ነገሥታትና ካህናት ሆነው የሚያገለግሉት ቅቡዓን ከሕዝበ ክርስትና ቀሳውስት ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል። (ራእይ 12:​17) ይሁን እንጂ የምሥራቹን ስብከት ለማስቆም የተደረጉት ጥረቶች ሁሉ በመጨረሻ ከሽፈዋል። የኢሳይያስ ትንቢት ይህን ሁኔታ እንዲህ ሲል አስቀድሞ ተናግሯል:- “በእፍረታችሁ ፋንታ ሁለት እጥፍ ይሆንላችኋል፣ በውርደታችሁም ፋንታ ዕድል ፈንታችሁም ደስ ይላቸዋል፤ ስለዚህ በምድራቸው ሁለት እጥፍ ይገዛሉ፣ የዘላለምም ደስታ ይሆንላቸዋል።”​—⁠ኢሳይያስ 61:7

21. ቅቡዓን ክርስቲያኖች ሁለት እጥፍ በረከት ያገኙት እንዴት ነው?

21 በአንደኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ብሔራዊ ስሜት የተጠናወታት ሕዝበ ክርስትና ቅቡዓን ቀሪዎች ኃፍረትና ውርደት እንዲደርስባቸው አድርጋ ነበር። ብሩክሊን በሚገኘው ዋናው መሥሪያ ቤት ይሠሩ የነበሩትን ስምንት ታማኝ ወንድሞች በመንግሥት ላይ ዓመፅ ለማነሳሳት ሞክራችኋል በሚል በሐሰት ከወነጀሏቸው መካከል አንዳንድ ቀሳውስት ይገኙበታል። እነዚህ ወንድሞች አላግባብ ለዘጠኝ ወራት ታስረዋል። በመጨረሻ ግን በ1919 የጸደይ ወራት ከእስር የወጡ ሲሆን በኋላም የተመሠረቱባቸው ክሶች በሙሉ እንዲነሡ ተደርጓል። በመሆኑም የስብከቱን ሥራ ለማስቆም የተሸረበው ሴራ ከሸፈ። ይሖዋ በአምላኪዎቹ ላይ የደረሰውን ኃፍረት በማስወገድ ነፃ ያወጣቸው ከመሆኑም በላይ ቀድሞ ወደነበሩበት መንፈሳዊ ርስት ማለትም ወደ “ምድራቸው” መልሷቸዋል። በመንፈሳዊ ርስታቸውም ላይ ሁለት እጥፍ በረከት አግኝተዋል። ይህ የይሖዋ በረከት የደረሰባቸውን መከራ አካክሶላቸዋል። በእርግጥም እጅግ መደሰታቸው የተገባ ነው!

22, 23. ቅቡዓን ክርስቲያኖች የይሖዋን ባሕርይ የኮረጁት እንዴት ነው? ይሖዋ ወሮታውን የከፈላቸውስ እንዴት ነው?

22 ይሖዋ በመቀጠል በዛሬው ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖች የሚደሰቱበትን ሌላ ምክንያት ጠቀሰ:- “እኔ እግዚአብሔር ፍርድን [“ፍትሕን፣” አ.መ.ት ] የምወድድ ስርቆትንና በደልን የምጠላ ነኝ፤ ፍዳቸውንም [“ምንዳቸውንም፣” NW ] በእውነት እሰጣቸዋለሁ፣ ከእነርሱም ጋር የዘላለምን ቃል ኪዳን አደርጋለሁ።” (ኢሳይያስ 61:8) ቅቡዓን ቀሪዎች መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናታቸው ፍትሕን እንዲወድዱና ክፋትን እንዲጠሉ አድርጓቸዋል። (ምሳሌ 6:​12-19፤ 11:​20) የሰው ልጆች ከሚያካሂዷቸው ጦርነቶችና ፖለቲካዊ ብጥብጦች ገለልተኞች በመሆን ‘ሰይፋቸውን ወደ ማረሻ’ ለውጠዋል። (ኢሳይያስ 2:​4) በተጨማሪም እንደ ስም ማጥፋት፣ ምንዝር፣ ስርቆትና ስካር ያሉትን አምላክን የማያስከብሩ ልማዶች አስወግደዋል።​—⁠ገላትያ 5:​19-21

23 ቅቡዓን ክርስቲያኖች እንደ ፈጣሪያቸው ፍትሕን የሚወድዱ በመሆናቸው ይሖዋ “ምንዳቸውንም በእውነት” ሰጥቷቸዋል። ይሖዋ ከሰጣቸው ‘ምንዳ’ አንዱ ዘላለማዊ ቃል ኪዳን ማለትም ኢየሱስ ከመሞቱ በፊት ባሳለፈው የመጨረሻ ምሽት ለተከታዮቹ ያስታወቀው አዲሱ ቃል ኪዳን ነው። መንፈሳዊ ብሔር ማለትም የአምላክ ልዩ ሕዝብ የሆኑት በዚህ ቃል ኪዳን ነው። (ኤርምያስ 31:​31-34፤ ሉቃስ 22:​20) ይሖዋ በዚህ ቃል ኪዳን አማካኝነት ቅቡዓንም ሆኑ ሌሎች ታማኝ የሰው ዘሮች በሙሉ በኢየሱስ ቤዛዊ መሥዋዕት በተከፈተው ዝግጅት እንዲጠቀሙ የሚያደርግ ሲሆን ይህም የኃጢአት ይቅርታ ማግኘትን ይጨምራል።

በይሖዋ በረከቶች ሐሴት ማድረግ

24. ከአሕዛብ መካከል ይሖዋ የባረከው “ዘር” የሚሆኑት እነማን ናቸው? “ዘር” የሚሆኑትስ እንዴት ነው?

24 በአሕዛብ መካከል ያሉ አንዳንድ ሰዎች ይሖዋ ሕዝቡን እንደባረከ ተገንዝበዋል። ይሖዋ የሚከተለውን ተስፋ በሰጠ ጊዜ ይህ ሁኔታ እንደሚፈጸም ተንብዮ ነበር:- “ዘራቸውም በአሕዛብ መካከል፣ ልጆቻቸውም በወገኖች መካከል የታወቁ ይሆናሉ፤ ያያቸው ሁሉ እግዚአብሔር የባረካቸው ዘር እንደ ሆኑ ይገነዘባል።” (ኢሳይያስ 61:9) ይሖዋ በጎ ፈቃዱን ባሳየበት ዓመት የአምላክ እስራኤል አባላት ማለትም ቅቡዓን ክርስቲያኖች በአሕዛብ መካከል በትጋት ሲያገለግሉ ቆይተዋል። በዛሬው ጊዜ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ቅቡዓኑ ላከናወኑት አገልግሎት አዎንታዊ ምላሽ ሰጥተዋል። ከአሕዛብ የመጡት ሰዎች ከአምላክ እስራኤል ጎን ተሰልፈው በመሥራት “እግዚአብሔር የባረካቸው ዘር” የመሆን መብት ያገኛሉ። ደስታቸው ለሰው ሁሉ በግልጽ ይታያል።

25, 26. ሁሉም ክርስቲያኖች በ⁠ኢሳይያስ 61:​10 ላይ የተገለጸውን ዓይነት ስሜት የሚያንጸባርቁት እንዴት ነው?

25 ሁሉም ክርስቲያኖች ማለትም ቅቡዓንም ሆኑ ሌሎች በጎች ይሖዋን ለዘላለም የሚያወድሱበትን ጊዜ በጉጉት ይጠባበቃሉ። በመንፈስ አነሳሽነት እንዲህ ሲል የተናገረው ነቢዩ ኢሳይያስ የተሰማው ዓይነት ስሜት ይሰማቸዋል:- “አክሊልን እንደ ለበሰ ሙሽራ፣ በጌጥ ሽልማትዋም እንዳጌጠች ሙሽራ፣ የማዳንን ልብስ አልብሶኛልና፣ የጽድቅንም መጐናጸፊያ ደርቦልኛልና በእግዚአብሔር እጅግ ደስ ይለኛል፣ ነፍሴም በአምላኬ ሐሤት ታደርጋለች።”​—⁠ኢሳይያስ 61:10

26 ቅቡዓን ክርስቲያኖች ‘የጽድቅን መጎናጸፊያ’ በመልበስ በይሖዋ ፊት የጠሩና ንጹሕ ሆነው ለመኖር ቁርጥ ውሳኔ አድርገዋል። (2 ቆሮንቶስ 11:​1, 2) በይሖዋ ፊት ጻድቅ ተብለው ሰማያዊ ሕይወት የመውረስ ተስፋ ያገኙ በመሆናቸው ነፃ ከመውጣታቸው በፊት ወደነበሩበትና ባድማ ወደሆነው የታላቂቱ ባቢሎን ርስት ዳግመኛ አይመለሱም። (ሮሜ 5:​9፤ 8:​30) የተሰጣቸው የመዳን ልብስ በምንም ነገር ሊለወጥ የማይችል ውድ ሀብት ነው። አጋሮቻቸው የሆኑት ሌሎች በጎችም ይሖዋ አምላክ ያወጣቸውን ከፍ ያሉ የእውነተኛ አምልኮ መስፈርቶች ለመጠበቅ ቁርጥ ውሳኔ አድርገዋል። ‘ልብሳቸውን አጥበው በበጉ ደም በማንጻታቸው’ የጸደቁ ሲሆን “ከታላቁ መከራ” ይተርፋሉ። (ራእይ 7:​14፤ ያዕቆብ 2:​23, 25) እስከዚያው ጊዜ ድረስ የቅቡዓን አጋሮቻቸውን ምሳሌ በመኮረጅ ከታላቂቱ ባቢሎን ጋር ማንኛውንም ዓይነት ንክኪ ከመፍጠር ይቆጠባሉ።

27. (ሀ) በሺህው ዓመት ግዛት ምን ለየት ያለ ነገር ‘ይበቅላል?’ (ለ) በአሁኑ ጊዜም እንኳ ጽድቅ በሰው ልጆች መካከል እየበቀለ ያለው እንዴት ነው?

27 በዘመናችን የይሖዋ አምላኪዎች በመንፈሳዊ ገነት ውስጥ በመሆናቸው እጅግ ደስተኞች ናቸው። በቅርቡ ደግሞ ቃል በቃል ምድራዊቷን ገነት ይወርሳሉ። በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 61 የመደምደሚያ ቃላት ቁልጭ ብሎ የተገለጸውን ያን ጊዜ በታላቅ ጉጉት እንጠባበቃለን:- “ምድርም ቡቃያዋን እንደምታወጣ፣ ገነትም ዘሩን እንደሚያበቅል፣ እንዲሁ ጌታ እግዚአብሔር ጽድቅንና ምስጋናን በአሕዛብ ሁሉ ፊት ያበቅላል።” (ኢሳይያስ 61:11) በክርስቶስ የሺህ ዓመት ግዛት ወቅት ምድር ‘ጽድቅን ታበቅላለች።’ የሰው ልጆች በታላቅ ደስታ እልል ይላሉ። ጽድቅ በምድር ሁሉ ላይ ይሰፍናል። (ኢሳይያስ 26:​9) ይሁንና ይሖዋን በአሕዛብ ሁሉ ፊት ለማመስገን ያን ታላቅ ቀን መጠበቅ አያስፈልገንም። በአሁኑ ጊዜ ለሰማያዊው አምላክ ክብር በመስጠትና ስለ መንግሥቱ የምሥራች በመናገር ላይ ባሉ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች መካከል ጽድቅ እየበቀለ ነው። አሁን ባለንበት ዘመንም እንኳ እምነታችንና ተስፋችን አምላካችን በሚያፈስሳቸው በረከቶች እንድንደሰት ያደርገናል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.16 አይሁዳውያን ያልሆኑ ሰዎች ከአይሁዳውያን ጋር ወደ ኢየሩሳሌም የተመለሱ ከመሆኑም በላይ ምድሪቱን መልሶ በመገንባቱ ሥራ እንደተባበሯቸው የሚታመን በመሆኑ ኢሳይያስ 61:​5 በጥንት ዘመንም ፍጻሜውን አግኝቶ ሊሆን ይችላል። (ዕዝራ 2:​43-58) ይሁን እንጂ ከቁጥር 6 አንስቶ ያለው ትንቢት የአምላክ እስራኤልን ብቻ የሚያመለክት ይመስላል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 323 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ኢሳይያስ ለአይሁዳውያን ግዞተኞች ምሥራች አብስሯል

[በገጽ 331 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ከ33 እዘአ አንስቶ ይሖዋ 144, 000 “ትልልቅ የጽድቅ ዛፎች” ተክሏል

[በገጽ 334 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ምድር ጽድቅን ታበቅላለች