በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘አዲስ ስም’

‘አዲስ ስም’

ምዕራፍ ሃያ ሦስት

‘አዲስ ስም’

ኢሳይያስ 62:​1-12

1. በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 62 ላይ ምን ማረጋገጫ ተመዝግቦ ይገኛል?

በባቢሎን ያሉት በጣም ተስፋ የቆረጡ አይሁዳውያን ማበረታቻ፣ ማጽናኛና ወደ ትውልድ አገራቸው እንደሚመለሱ የሚያረጋግጥ ተስፋ ማግኘት ያስፈልጋቸዋል። ኢየሩሳሌምና ቤተ መቅደሷ ከወደሙ በርከት ያሉ አሥርተ ዓመታት አልፈዋል። ከባቢሎን 800 ኪሎ ሜትር ገደማ ርቃ የምትገኘው ይሁዳ ለብዙ ዘመናት ባድማ ሆና ቆይታለች። ይሖዋ አይሁዳውያንን ከናካቴው የረሳቸው ይመስል ነበር። ታዲያ ይህ ያሉበት ሁኔታ እንዴት ሊለወጥ ይችላል? ይሖዋ ወደ ትውልድ አገራቸው እንደሚመልሳቸውና ንጹሑን አምልኮ መልሰው እንዲያቋቁሙ እንደሚያደርጋቸው የገባው ቃል ይህን ያሉበትን ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ሊለውጠው ይችላል። በዚያን ጊዜ “የተተወች” እና “ውድማ” የሚሉት መግለጫዎች የአምላክን ሞገስ እንዳገኙ በሚገልጹ ስያሜዎች ይተካሉ። (ኢሳይያስ 62:​4፤ ዘካርያስ 2:​12) ኢሳይያስ ምዕራፍ 62 እንዲህ ባሉ ተስፋዎች የተሞላ ነው። ይሁን እንጂ እንደ ሌሎች የተሃድሶ ትንቢቶች ሁሉ ይህ ምዕራፍም የሚናገረው በባቢሎን በግዞት ያሉ አይሁዳውያን ስለሚያገኙት ነፃነት ብቻ አይደለም። በትንቢቱ የላቀ ፍጻሜ መሠረት ኢሳይያስ ምዕራፍ 62 የይሖዋ መንፈሳዊ ብሔር ማለትም ‘የእግዚአብሔር እስራኤል’ መዳን እንደሚያገኝ ያረጋግጥልናል።​—⁠ገላትያ 6:​16

ይሖዋ ዝም አይልም

2. ይሖዋ ለጽዮን በድጋሚ ሞገሱን ያሳየው በምን መንገድ ነው?

2 የባቢሎን ኃያል መንግሥት በ539 ከዘአበ ከተገለበጠ በኋላ የፋርሱ ንጉሥ ቂሮስ ፈሪሃ አምላክ ያላቸው አይሁዳውያን ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሰው የይሖዋን አምልኮ መልሰው እንዲያቋቁሙ አዋጅ አስነገረ። (ዕዝራ 1:​2-4) ከግዞት ከሚመለሱት አይሁዳውያን መካከል የመጀመሪያዎቹ በ537 ከዘአበ ወደ ትውልድ አገራቸው ተመለሱ። የይሖዋ ፍቅራዊ ስሜት የተንጸባረቀበት የሚከተለው ትንቢታዊ መግለጫ እንደሚጠቁመው ይሖዋ ለኢየሩሳሌም በድጋሚ ሞገሱን አሳይቷል:- “ስለ ጽዮን ዝም አልልም፣ ስለ ኢየሩሳሌምም ጸጥ አልልም፣ ጽድቅዋ እንደ ጸዳል መዳንዋም እንደሚበራ ፋና እስኪወጣ ድረስ።”​—⁠ኢሳይያስ 62:1

3. (ሀ) ይሖዋ ምድራዊቷን ጽዮን እርግፍ አድርጎ የተዋት ለምንድን ነው? በእሷስ ቦታ ማን ተተክቷል? (ለ) በእውነተኛው ሃይማኖት ላይ ምን ሁኔታ ተከስቷል? ይህ የሆነው መቼ ነው? አሁን የምንኖረውስ በየትኛው ዘመን ውስጥ ነው?

3 ይሖዋ በ537 ከዘአበ ጽዮንን ወይም ኢየሩሳሌምን ቀድሞ ወደነበረችበት ሁኔታ እንደሚመልሳት የገባውን ቃል ፈጽሟል። ነዋሪዎቿ የይሖዋን መዳን ያገኙ ከመሆኑም በላይ ጽድቃቸው እንደ ጸዳል ደምቆ በርቷል። ይሁን እንጂ ከጊዜ በኋላ ንጹሑን አምልኮ ዳግመኛ ወደ ጎን ገሸሽ አደረጉ። በመጨረሻም የኢየሱስን መሲሕነት ለመቀበል አሻፈረን በማለታቸው ይሖዋ በአንድ ወቅት የመረጣቸውን ሕዝቦቹን እርግፍ አድርጎ ለመተው ተገደደ። (ማቴዎስ 21:​43፤ 23:​38፤ ዮሐንስ 1:​9-13) ይሖዋ አዲስ ብሔር ማለትም ‘የእግዚአብሔር እስራኤል’ እንዲወለድ አደረገ። ይህ አዲስ ብሔር የአምላክ ልዩ ሕዝብ የመሆን መብት ያገኘ ሲሆን በመጀመሪያው መቶ ዘመን የዚህ ብሔር አባላት ምሥራቹን በዘመኑ በነበረው ዓለም በሙሉ በቅንዓት ሰብከዋል። (ገላትያ 6:​16፤ ቆላስይስ 1:​23) የሚያሳዝነው ግን ከሐዋርያት ሞት በኋላ እውነተኛው ሃይማኖት እየከሰመ መጣ። በዚህም ሳቢያ በአሁኑ ጊዜ በሕዝበ ክርስትና ውስጥ የሚታየው ዓይነት የክህደት ክርስትና ብቅ አለ። (ማቴዎስ 13:​24-30, 36-43፤ ሥራ 20:​29, 30) ላለፉት በርካታ መቶ ዘመናት ሕዝበ ክርስትና የይሖዋን ስም በከፍተኛ ደረጃ ስታስነቅፍ ኖራለች። ይሁንና በመጨረሻ ይሖዋ “በጎ ፈቃዱን የሚያሳይበት ዓመት” በ1914 የጀመረ ሲሆን ይህ የኢሳይያስ ትንቢትም የላቀ ፍጻሜውን ማግኘት ጀምሯል።​—⁠ኢሳይያስ 61:​2 NW

4, 5. (ሀ) በዛሬው ጊዜ ጽዮንና ልጆቿ እነማንን ያመለክታሉ? (ለ) ይሖዋ ‘መዳንዋ እንደሚበራ ፋና’ እንዲሆን ለማድረግ ጽዮንን የተጠቀመባት በምን መንገድ ነው?

4 በዘመናችን ይሖዋ ጽዮንን ቀድሞ ወደነበረችበት ሁኔታ ለመመለስ የገባው ቃል ምድር ላይ ባሉት ልጆቿ ማለትም በመንፈስ በተቀቡ ክርስቲያኖች በተወከለችውና “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” በመባል በምትታወቀው ሰማያዊት ድርጅቱ ላይ ፍጻሜውን አግኝቷል። (ገላትያ 4:​26) የይሖዋ ሰማያዊት ድርጅት ለአምላክ ያደረች፣ ንቁ፣ አፍቃሪና ትጉ ረዳት ሆና ታገለግላለች። በ1914 መሲሐዊውን መንግሥት በወለደች ጊዜ ታላቅ ደስታ ሆኖ ነበር! (ራእይ 12:​1-5) በምድር ላይ ያሉት ልጆቿ በተለይ ከ1919 አንስቶ ስለ ጽድቋና ስላገኘችው መዳን ለአሕዛብ ሲሰብኩ ቆይተዋል። ኢሳይያስ አስቀድሞ እንደተናገረው እነዚህ ልጆች ልክ እንደ ፋና ጨለማውን በመግፈፍ ብርሃናቸው ቦግ ብሎ እንዲታይ አድርገዋል።​—⁠ማቴዎስ 5:​15, 16፤ ፊልጵስዩስ 2:​15

5 ይሖዋ ለአምላኪዎቹ በእጅጉ የሚያስብ በመሆኑ ለጽዮንና ለልጆቿ ቃል የገባቸውን ተስፋዎች በሙሉ ሳይፈጽም አያርፍም ወይም ዝም አይልም። ‘የሌሎች በጎች’ አባላት የሆኑትን አጋሮቻቸውን ጨምሮ ቅቡዓን ቀሪዎችም ዝም አይሉም። (ዮሐንስ 10:​16) ብቸኛውን የመዳን መንገድ ለሰዎች መናገራቸውን ይቀጥላሉ።​—⁠ሮሜ 10:​10

ይሖዋ ያወጣው ‘አዲስ ስም’

6. ይሖዋ ለጽዮን ሊያደርገው ያሰበው ነገር ምንድን ነው?

6 ይሖዋ በጥንቷ ኢየሩሳሌም ለተወከለችው ለሰማያዊቷ ‘ሴት’ ለጽዮን ሊያደርገው ያሰበው ነገር ምንድን ነው? እንዲህ ሲል ገለጸ:- “አሕዛብም ጽድቅሽን ነገሥታትም ሁሉ ክብርሽን ያያሉ፤ የእግዚአብሔርም አፍ በሚጠራበት በአዲሱ ስም ትጠሪያለሽ።” (ኢሳይያስ 62:2) አሕዛብ የአምላክ ሕዝቦች የሚፈጽሙትን የጽድቅ ሥራ በትኩረት ለመመልከት ይገደዳሉ። ነገሥታት እንኳ ሳይቀሩ ይሖዋ በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም እየተጠቀመ እንዳለና ማንኛውም ዓይነት ሰብዓዊ አገዛዝ ከይሖዋ መንግሥት ጋር ሲነጻጸር ፋይዳ ቢስ መሆኑን አምነው ለመቀበል ይገደዳሉ።​—⁠ኢሳይያስ 49:​23

7. አዲሱ የጽዮን ስም ምን ያመለክታል?

7 ይሖዋ ለጽዮን አዲስ ስም በማውጣት ያለችበት ሁኔታ እንደ​ሚለወጥ ማረጋገጫ ሰጥቷል። ይህ አዲስ ስም የጽዮን ምድራዊ ልጆች ከ537 ከዘአበ ጀምሮ ያገኙትን በረከትና ክብር ያመለክታል። * ይሖዋ ጽዮንን ንብረቱ አድርጎ እንደተቀበላት ያሳያል። በዛሬው ጊዜ የአምላክ እስራኤል አባላት ይሖዋ የሚደሰትባቸው መሆኑን በማወቃቸው እጅግ ሐሴት አድርገዋል። ሌሎች በጎችም የደስታቸው ተካፋይ ናቸው።

8. ይሖዋ ጽዮንን ያከበራት በምን መንገዶች ነው?

8 ይሖዋ ለጽዮን አዲስ ስም ካወጣላት በኋላ የሚከተለውን ተስፋ ሰጠ:- “በእግዚአብሔር እጅ የክብር አክሊል፣ በአምላክሽም እጅ የመንግሥት ዘውድ ትሆኛለሽ።” (ኢሳይያስ 62:3) ይሖዋ ምሳሌያዊት ሚስቱ የሆነችው ሰማያዊቷ ጽዮን በክብር እንድትታይ ከፍ ያደርጋታል። (መዝሙር 48:​2፤ 50:​2) የክብር አክሊልና “የመንግሥት ዘውድ” የሚሉት አገላለጾች ክብርና ሥልጣን እንደምትላበስ ያመለክታሉ። (ዘካርያስ 9:​16) ሰማያዊቷን ጽዮን ወይም ‘ላይኛይቱን ኢየሩሳሌም’ የሚወክለው የአምላክ እስራኤል ድንቅ የይሖዋ እጅ ሥራ ማለትም የኃይሉ መገለጫ ነው። (ገላትያ 4:​26) በይሖዋ እርዳታ ይህ መንፈሳዊ ብሔር እጅግ አስደናቂ የሆነ የጽናትና የታማኝነት ታሪክ አስመዝግቧል። ቅቡዓንንም ሆነ ሌሎች በጎችን ጨምሮ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በጣም አስደናቂ የሆነ እምነትና ፍቅር ለማሳየት የሚያስችል ጥንካሬ አግኝተዋል። በክርስቶስ የሺህ ዓመት ግዛት ወቅት ቅቡዓን ክርስቲያኖች ክብራማውን ሰማያዊ ሽልማት ካገኙ በኋላ ሲቃትት የኖረውን ፍጥረት ሕይወት በማሻሻል የዘላለም ሕይወት እንዲያገኝ ለማድረግ በይሖዋ እጅ ያሉ መሣሪያዎች ሆነው ያገለግላሉ።​—⁠ሮሜ 8:​21, 22፤ ራእይ 22:​2

“እግዚአብሔር በአንቺ ደስ ብሎታል”

9. በጽዮን ላይ የሚከሰተውን ለውጥ ግለጽ።

9 በምድራዊ ልጆቿ ለተወከለችው ሰማያዊቷ ጽዮን አዲስ ስም መሰጠቱ አስደሳች ለውጥ እንደሚጠብቃት የሚያሳይ ነው። ዘገባው እንዲህ ይላል:- “ከእንግዲህ ወዲህ:- የተተወች አትባዪም፤ ምድርሽም ከእንግዲህ ወዲህ:- ውድማ አትባልም፤ ነገር ግን እግዚአብሔር በአንቺ ደስ ብሎታልና፣ ምድርሽም ባል ታገባለችና አንቺ:- ደስታዬ የሚኖርባት ትባያለሽ ምድርሽም:- ባል ያገባች ትባላለች።” (ኢሳይያስ 62:4) ምድራዊቷ ጽዮን በ607 ከዘአበ ከጠፋችበት ጊዜ አንስቶ ውድማ ሆና ቆይታለች። ይሁን እንጂ ይሖዋ የተናገራቸው ቃላት ምድሪቱ ቀድሞ ወደነበረችበት ሁኔታ እንደምትመለስና ዳግመኛ በነዋሪዎች እንደምትሞላ የሚያረጋግጡ ናቸው። በአንድ ወቅት ጠፍታ የነበረችው ጽዮን ዳግመኛ የተተወችና ውድማ አትሆንም። በ537 ከዘአበ ኢየሩሳሌም ቀድሞ ወደነበረችበት ሁኔታ ስትመለስ ባድማ ሆና በቆየችባቸው ጊዜያት የነበረው ሁኔታ ሙሉ በሙሉ ይለወጣል። ይሖዋ ጽዮን “ደስታዬ የሚኖርባት” ተብላ እንደምትጠራና ምድሯም “ባል ያገባች” እንደምትባል ገልጿል።​—⁠ኢሳይያስ 54:​1, 5, 6፤ 66:​8፤ ኤርምያስ 23:​5 - 8፤ 30:​17፤ ገላትያ 4:​27-31

10. (ሀ) በአምላክ እስራኤል ላይ ለውጥ የተከሰተው እንዴት ነው? (ለ) የአምላክ እስራኤል “አገር” ምንድን ነው?

10 ከ1919 አንስቶ በአምላክ እስራኤል ላይ ተመሳሳይ የሆነ ለውጥ ተከስቷል። በመጀመሪያው የዓለም ጦርነት ወቅት ቅቡዓን ክርስቲያኖች አምላክ የተዋቸው ይመስሉ ነበር። ሆኖም በ1919 ቀደም ሲል በአምላክ ፊት የነበራቸውን ሞገስ መልሰው ከማግኘታቸውም በላይ የአምልኮ ሥርዓታቸውን ማጥራት ችለዋል። ይህም በትምህርቶቻቸው፣ በድርጅታቸውና በሥራቸው ላይ ለውጥ አስከትሏል። የአምላክ እስራኤል አባላት ወደ ‘አገራቸው’ ማለትም ወደ መንፈሳዊ ርስታቸው ወይም ወደ ሥራ መስካቸው ተመልሰዋል።​—⁠ኢሳይያስ 66:​7, 8, 20-22

11. አይሁዳውያን እናታቸውን የሚያገቡት እንዴት ነው?

11 ይሖዋ ሕዝቡ ያገኙትን ልዩ ሞገስ ይበልጥ ጠበቅ አድርጎ በመግለጽ እንዲህ አለ:- “ጉልማሳም ድንግሊቱን እንደሚያገባ፣ እንዲሁ ልጆችሽ ያገቡሻል፤ ሙሽራም በሙሽራይቱ ደስ እንደሚለው፣ እንዲሁ አምላክሽ በአንቺ ደስ ይለዋል።” (ኢሳይያስ 62:5) የጽዮን ‘ልጆች’ የሆኑት አይሁዳውያን እንዴት እናታቸውን ሊያገቡ ይችላሉ? ከባቢሎን ግዞት ነፃ ወጥተው ወደ ጽዮን የሚመለሱት አይሁዶች የቀድሞ መዲናቸውን በመውረስ ዳግመኛ የሚሰፍሩባት በመሆኑ ነው። በዚያን ጊዜ ባድማ ሆና የቆየችው ጽዮን በልጆች ትሞላለች።​—⁠ኤርምያስ 3:​14

12. (ሀ) ይሖዋ ቅቡዓን ክርስቲያኖች ከእርሱ ጋር በጋብቻ የተሳሰረችው ድርጅቱ አካል መሆናቸውን ግልጽ ያደረገው በምን መንገድ ነው? (ለ) ይሖዋ ከሕዝቡ ጋር ያለው ዝምድና በዛሬው ጊዜ ለሚመሠረቱ ትዳሮች ከሁሉ የላቀ ምሳሌ የሚሆነው እንዴት ነው? (ገጽ 342 ላይ ያለውን ሣጥን ተመልከት።)

12 በተመሳሳይ ሁኔታ ከ1919 አንስቶ የሰማያዊቷ ጽዮን ልጆች “ባል ያገባች” የሚል ትንቢታዊ ስያሜ የተሰጣትን ምድራቸውን ወይም መንፈሳዊ ርስታቸውን ወርሰዋል። እነዚህ ቅቡዓን ክርስቲያኖች በምድራቸው ላይ ያከናወኑት ሥራ በእርግጥም ‘ለይሖዋ ስም የሚሆኑ ወገኖች’ እንደሆኑ በግልጽ የሚያሳይ ነው። (ሥራ 15:​14) የመንግሥቱን ፍሬዎች ማፍራታቸውና የይሖዋን ስም ማወጃቸው ይሖዋ በእነዚህ ክርስቲያኖች እንደሚደሰት የሚያሳይ ግልጽ ማስረጃ ነው። በማይበጠስ አንድነት ከእርሱ ጋር የተጣመረው ድርጅት አካል እንደሆኑ ግልጽ አድርጓል። ይሖዋ እነዚህን ክርስቲያኖች በመንፈስ ቅዱስ በመቀባት፣ ከመንፈሳዊ ግዞት ነፃ በማውጣትና የመንግሥቱን ተስፋ ለሰው ልጆች ሁሉ እንዲሰብኩ መሣሪያ አድርጎ በመጠቀም ሙሽራ በሙሽራይቱ ደስ እንደሚለው እሱም በእነሱ እንደሚደሰት አሳይቷል።​—⁠ኤርምያስ 32:​41

“አትረፉ”

13, 14. (ሀ) በጥንት ዘመን ኢየሩሳሌም ጥበቃ የምታስገኝ ከተማ የሆነችው እንዴት ነው? (ለ) በዘመናችን ጽዮን ‘በምድር ላይ ምስጋና’ የሆነችው እንዴት ነው?

13 ይሖዋ ያወጣው አዲስ ምሳሌያዊ ስም ሕዝቡ ትምክህት እንዲያድርባቸው እንዲሁም እንደሚቀበላቸውና ባለቤታቸው እንደሆነ እንዲገነዘቡ ያደርጋል። ይሖዋ በመቀጠል አንድ ለየት ያለ ምሳሌ የተጠቀመ ሲሆን ሕዝቡን እንደተመሸገች ከተማ አድርጎ በመግለጽ እንዲህ አላቸው:- “ኢየሩሳሌም ሆይ፣ ጉበኞችን በቅጥርሽ ላይ አቁሜአለሁ፤ ቀንና ሌሊት ከቶ ዝም አይሉም፤ እናንተ እግዚአብሔርን የምታሳስቡ፣ ኢየሩሳሌምን እስኪያጸና በምድርም ላይ ምስጋና እስኪያደርጋት ድረስ አትረፉ ለእርሱም ዕረፍት አትስጡ።” (ኢሳይያስ 62:6, 7) ይሖዋ የወሰነው ጊዜ ሲደርስ ታማኞቹ ቀሪዎች ከባቢሎን ከተመለሱ በኋላ ኢየሩሳሌም “በምድርም ላይ ምስጋና” ማለትም ለነዋሪዎቿ ጥበቃ የምታስገኝ የተመሸገች ከተማ ትሆናለች። በቅጥሮቿ ላይ የሚቆሙት ጉበኞች የከተማይቱን ደህንነት ለማስጠበቅና ለነዋሪዎቿ ማስጠንቀቂያ ለመስጠት ቀን ከሌት ነቅተው ይጠባበቃሉ።​—⁠ነህምያ 6:​15፤ 7:​3፤ ኢሳይያስ 52:​8

14 በዘመናችን ይሖዋ ቅቡዓን ጉበኞቹን መሣሪያ አድርጎ በመጠቀም ከሐሰት ሃይማኖት ባርነት ነፃ መውጣት የሚቻልበትን መንገድ ቅን ለሆኑ ሰዎች አሳይቷል። እነዚህ ሰዎች ከመንፈሳዊ ብክለት፣ መጥፎ ከሆኑ ተጽዕኖዎችና ይሖዋን ከሚያሳዝኑ ድርጊቶች መራቅ ወደሚችሉበት ወደ ይሖዋ ድርጅት እንዲመጡ ግብዣ ሲቀርብላቸው ቆይቷል። (ኤርምያስ 33:​9፤ ሶፎንያስ 3:​19) እንዲህ ያለውን ጥበቃ ያገኙ ዘንድ ጉበኛው ማለትም መንፈሳዊውን ‘ምግብ በጊዜው’ የሚያቀርበው “ታማኝና ልባም ባሪያ” የሚጫወተው ሚና ወሳኝ ነው። (ማቴዎስ 24:​45-47) ‘እጅግ ብዙ ሰዎችም’ ከጉበኛው ክፍል ጋር ተባብረው በመሥራት ጽዮን ‘በምድር ላይ ምስጋና’ እንድትሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታሉ።​—⁠ራእይ 7:​9

15. የጉበኛው ክፍልና አጋሮቻቸው ይሖዋን ያለማቋረጥ በማገልገል ላይ ያሉት እንዴት ነው?

15 የጉበኛው ክፍልና አጋሮቻቸው በሙሉ ነፍስ ማገልገላቸውን ቀጥለዋል! በሚልዮን የሚቆጠሩ ታማኝ ግለሰቦች በተጓዥ የበላይ ተመልካቾችና በሚስቶቻቸው፣ በተለያዩ የቤቴል ቤቶችና የይሖዋ ምሥክሮች የማተሚያ ሕንፃዎች ውስጥ በሚያገለግሉ ፈቃደኛ ሠራተኞች፣ በሚስዮናውያን እንዲሁም በልዩ፣ በዘወትርና በረዳት አቅኚዎች ታግዘው በቅንዓት የሚያከናውኑት ሥራ ለዚህ ጥሩ ማስረጃ ነው። ከዚህም በተጨማሪ አዳዲስ የመንግሥት አዳራሾችን በመገንባት፣ የታመሙትን በመጠየቅ፣ ከሕክምና ጋር በተያያዘ ፈታኝና አስቸጋሪ ሁኔታ የገጠማቸውን ግለሰቦች በመርዳትና የተፈጥሮም ሆነ ሌላ ድንገተኛ አደጋ ለደረሰባቸው ሰዎች አስፈላጊውን እርዳታ በወቅቱ በማድረስ በትጋት ይሠራሉ። የራሳቸውን ጥቅም መሥዋዕት የማድረግ መንፈስ ካላቸው ከእነዚህ ግለሰቦች መካከል ብዙዎቹ ቃል በቃል ‘ሌት ከቀን’ ያገለግላሉ።​—⁠ራእይ 7:​14, 15

16. የይሖዋ አገልጋዮች ‘አምላክን ዕረፍት የማይሰጡት’ በምን መንገድ ነው?

16 የይሖዋ አገልጋዮች ሳያቋርጡ እንዲጸልዩና የአምላክ ‘ፈቃድ በሰማይ እንደ ሆነች እንዲሁ በምድር እንድትሆን’ እንዲለምኑ ምክር ተሰጥቷቸዋል። (ማቴዎስ 6:​9, 10፤ 1 ተሰሎንቄ 5:​17) እውነተኛው አምልኮ ቀድሞ ወደነበረበት ሁኔታ እንዲመለስ ያላቸው ፍላጎትና ተስፋ እስኪፈጸም ድረስ ‘ይሖዋን ዕረፍት እንዳይሰጡት’ ማሳሰቢያ ተሰጥቷቸዋል። ኢየሱስ ተከታዮቹን ‘ቀን ከሌት ወደ አምላክ እንዲጮኹ’ አጥብቆ በማሳሰብ አዘውትሮ የመጸለይን አስፈላጊነት ጎላ አድርጎ ገልጿል።​—⁠ሉቃስ 18:​1-8

አምላክን ማገልገል ወሮታ ያስገኛል

17, 18. (ሀ) የጽዮን ነዋሪዎች የድካማቸውን ፍሬ የሚያገኙት በምን መንገድ ነው? (ለ) በዛሬው ጊዜ ያሉት የይሖዋ ሕዝቦች የድካማቸውን ፍሬ እያገኙ ያሉት እንዴት ነው?

17 ይሖዋ ለሕዝቡ የሰጣቸው አዲስ ስም ጥረታቸው ከንቱ ሆኖ እንደማይቀር ያረጋግጥላቸዋል። “እግዚአብሔር:- ከእንግዲህ ወዲህ በእርግጥ ለጠላቶችሽ መብል ይሆን ዘንድ እህልሽን አልሰጥም፣ መጻተኞችም የደከምሽበትን ወይንሽን አይጠጡም፤ ነገር ግን የሰበሰቡት ይበሉታል እግዚአብሔርንም ያመሰግናሉ፣ ያከማቹትም በመቅደሴ አደባባይ ላይ ይጠጡታል ብሎ በቀኙና በኃይሉ ክንድ ምሎአል።” (ኢሳይያስ 62:8, 9) የይሖዋ ቀኝ እጅና ጠንካራ ክንድ ኃይሉንና ብርታቱን ያመለክታሉ። (ዘዳግም 32:​40፤ ሕዝቅኤል 20:​5 አ.መ.ት ) በቀኝ እጁና በክንዱ መማሉ ጽዮን ያለችበትን ሁኔታ ለመለወጥ ቆርጦ መነሳቱን ያሳያል። በ607 ከዘአበ ይሖዋ የጽዮን ጠላቶች እንዲዘርፏትና እንዲበዘብዟት ፈቅዶ ነበር። (ዘዳግም 28:​33, 51) ይሁንና አሁን ያ ሁኔታ ተለውጦ በጽዮን ሀብት የሚጠቀሙት ባለቤቶቹ ብቻ ይሆናሉ።​—⁠ዘዳግም 14:​22-27

18 በዚህ ተስፋ ዘመናዊ ፍጻሜ መሠረት ወደ ቀድሞ ሁኔታቸው የተመለሱት የይሖዋ ሕዝቦች ታላቅ መንፈሳዊ ብልጽግና ያገኛሉ። የድካማቸውን ፍሬ ሙሉ በሙሉ ያገኛሉ። የክርስቲያን ደቀ መዛሙርት ቁጥር የሚጨምር ከመሆኑም በላይ መንፈሳዊ ምግባቸው ይትረፈረፋል። (ኢሳይያስ 55:​1, 2፤ 65:​14) ይሖዋ ሕዝቦቹ ታማኝ በመሆናቸው ጠላቶቻቸው መንፈሳዊ ብልጽግናቸውን እንዲያስተጓጉሉ ወይም በሙሉ ነፍስ በማገልገል ያገኙትን ውጤት እንዲያሳጧቸው አይፈቅድም። በይሖዋ አገልግሎት የሚከናወን ማንኛውም ሥራ ከንቱ ሆኖ አይቀርም።​—⁠ሚልክያስ 3:​10-12፤ ዕብራውያን 6:​10

19, 20. (ሀ) ወደ ኢየሩሳሌም ለሚመለሱት አይሁዶች መንገዱ የተጠረገው እንዴት ነው? (ለ) በዘመናችን ቅን ሰዎች ወደ ይሖዋ ድርጅት እንዲመጡ መንገዱ የተጠረገው እንዴት ነው?

19 በተጨማሪም አዲሱ ስም ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች ወደ ይሖዋ ድርጅት እንዲሳቡ ያደርጋቸዋል። ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ወደ ድርጅቱ የሚጎርፉ ሲሆን በሩ ክፍት ሆኖ ይጠብቃቸዋል። የኢሳይያስ ትንቢት እንዲህ ሲል ይገልጻል:- “እለፉ፣ በበሮች በኩል እለፉ፤ የሕዝቡንም መንገድ ጥረጉ፤ አዘጋጁ፣ ጐዳናውን አዘጋጁ፣ ድንጋዮቹንም አስወግዱ፤ ለአሕዛብም ዓላማ አንሡ።” (ኢሳይያስ 62:10) በመጀመሪያው የትንቢቱ ፍጻሜ መሠረት ይህ መልእክት አይሁዳውያን በባቢሎን ከተሞች በር አልፈው ወደ ኢየሩሳሌም እንዲመለሱ የቀረበ ጥሪ ይመስላል። ወደ ኢየሩሳሌም የሚመለሱት ሰዎች ጉዞው ቀና ይሆን ዘንድ ድንጋዮቹን ማስወገድና መንገዱን የሚጠቁም ዓላማ ወይም ምልክት ማቆም ያስፈልጋቸዋል።​—⁠ኢሳይያስ 11:​12

20 ከ1919 አንስቶ ቅቡዓን ክርስቲያኖች ለመለኮታዊ አገልግሎት የተለዩ ሲሆን ‘በተቀደሰ መንገድ’ በመጓዝ ላይ ናቸው። (ኢሳይያስ 35:​8) ከታላቂቱ ባቢሎን ወጥተው በመንፈሳዊው ጎዳና የተጓዙት የመጀመሪያዎቹ ሰዎች እነሱ ናቸው። (ኢሳይያስ 40:​3፤ 48:​20) አምላክ ድንቅ ሥራዎቹን በማስታወቅና ለሌሎች ጎዳናውን በማሳየት በግንባር ቀደምትነት እንዲያገለግሉ መብት ሰጥቷቸዋል። ድንጋዮቹን ማለትም እንቅፋቶቹን ከመንገዱ ላይ ማስወገዳቸው በዋነኛነት የሚጠቅመው ራሳቸውን ነው። (ኢሳይያስ 57:​14) የአምላክን ዓላማዎችና ትምህርቶች በግልጽ መረዳት አስፈልጓቸው ነበር። የሐሰት እምነቶች ወደ ሕይወት በሚወስደው መንገድ ላይ እንቅፋት የሚሆኑ ድንጋዮች ናቸው። የይሖዋ ቃል ግን “ድንጋዩንም እንደሚያደቅቅ መዶሻ” ነው። ቅቡዓን ክርስቲያኖች የአምላክን ቃል መሣሪያ አድርገው በመጠቀም ይሖዋን ለማገልገል የሚፈልጉ ሰዎችን ሊያሰናክሉ የሚችሉትን እንቅፋት የሆኑ ድንጋዮች አድቅቀዋል።​—⁠ኤርምያስ 23:​29

21, 22. ይሖዋ የሐሰት ሃይማኖትን ለቅቀው ለሚወጡ ሰዎች ያቆመው ምልክት ምንድን ነው? እንዴትስ እናውቃለን?

21 በ537 ከዘአበ አይሁዳውያን ቀሪዎች ወደ ትውልድ አገራቸው ተመልሰው ቤተ መቅደሱን ዳግመኛ እንዲገነቡ ኢየሩሳሌም ዓላማ ወይም ምልክት ሆና አገልግላለች። (ኢሳይያስ 49:​22) በ1919 ቅቡዓን ክርስቲያኖች ከሐሰት ሃይማኖት ባርነት ነፃ ሲወጡ የሚሄዱበት ጠፍቷቸው አልተቅበዘበዙም። ይሖዋ ምልክት አቁሞላቸው ስለነበር የት መሄድ እንዳለባቸው ያውቁ ነበር። ይህ ምልክት ምንድን ነው? በ⁠ኢሳይያስ 11:​10 ላይ አስቀድሞ የተነገረ ሲሆን ጥቅሱ እንዲህ ይላል:- “በዚያም ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ለአሕዛብ ምልክት ሊሆን የቆመውን የእሴይን ሥር አሕዛብ ይፈልጉታል።” ሐዋርያው ጳውሎስ እነዚህ ቃላት ኢየሱስን እንደሚያመለክቱ ገልጿል። (ሮሜ 15:​8, 12) አዎን፣ ምልክቱ በሰማያዊው የጽዮን ተራራ ላይ ንጉሥ ሆኖ በመግዛት ላይ ያለው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው።​—⁠ዕብራውያን 12:​22፤ ራእይ 14:​1

22 ቅቡዓን ክርስቲያኖችም ሆኑ ሌሎች በጎች አንድ በሚያደርገው የሉዓላዊው አምላክ አምልኮ ለመካፈል በኢየሱስ ክርስቶስ ዙሪያ ተሰባስበዋል። የኢየሱስ አገዛዝ የይሖዋን አጽናፈ ዓለማዊ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥና በምድር ዙሪያ ካሉ ብሔራት የተውጣጡ ቅን ልብ ያላቸውን ሰዎች ለመባረክ መሣሪያ ሆኖ ያገለግላል። ይህ ሁላችንም ይሖዋን እንድናወድስ ሊገፋፋን አይገባምን?

“መድኃኒትሽ ይመጣል”

23, 24. በአምላክ የሚያምኑ ሰዎች መዳን እንዲያገኙ እየተደረገ ያለው እንዴት ነው?

23 ይሖዋ በሚስት ለተመሰለችው ድርጅቱ የሰጠው አዲስ ስም ልጆቿ ከሚያገኙት ዘላለማዊ መዳን ጋር ዝምድና አለው። ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ጻፈ:- “እነሆ፣ እግዚአብሔር ለምድር ዳርቻ አዋጅ እንዲህ ብሎ ነግሮአል:- ለጽዮን ልጅ:- እነሆ፣ መድኃኒትሽ ይመጣል፤ እነሆ፣ ዋጋው ከእርሱ ጋር ሥራውም በፊቱ አለ በሉአት።” (ኢሳይያስ 62:11) አይሁዳውያን ባቢሎን ከወደቀች በኋላ ወደ ትውልድ አገራቸው በተመለሱበት ጊዜ መዳን አግኝተዋል። ይሁን እንጂ እነዚህ ቃላት ሌላ የላቀ ፍጻሜም አላቸው። ይህ የይሖዋ ቃል ዘካርያስ ኢየሩሳሌምን አስመልክቶ የተናገረውን ትንቢት እንድናስታውስ ያደርገናል:- “አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፣ እጅግ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፣ እልል በዪ፤ እነሆ፣ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም፣ በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል።”​—⁠ዘካርያስ 9:9

24 ኢየሱስ በውኃ ከተጠመቀና በአምላክ መንፈስ ከተቀባ ከሦስት ዓመት ተኩል በኋላ በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም በመግባት ቤተ መቅደሱን አጥርቷል። (ማቴዎስ 21:​1-5፤ ዮሐንስ 12:​14-16) በዛሬው ጊዜ በአምላክ ለሚያምኑ ሁሉ የይሖዋን መዳን የሚያስገኘው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በተጨማሪም ኢየሱስ በ1914 በዙፋን ላይ ከተቀመጠበት ጊዜ አንስቶ ይሖዋ ፈራጅና ፍርድ አስፈጻሚ አድርጎ ሾሞታል። ሥልጣን ላይ ከወጣ ከሦስት ዓመት ተኩል በኋላ ማለትም በ1918 በምድር ላይ በቅቡዓን ክርስቲያኖች ጉባኤ የተወከለውን የይሖዋ መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ አጥርቷል። (ሚልክያስ 3:​1-5) ይሖዋ ኢየሱስን ምልክት አድርጎ ካቆመው ጊዜ አንስቶ በምድር ዙሪያ መሲሐዊውን መንግሥት በመደገፍ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ተሰብስበዋል። ልክ በጥንት ዘመን እንደሆነው ሁሉ በ1919ም የአምላክ እስራኤል አባላት ከታላቂቱ ባቢሎን ነፃ ሲወጡ ‘መዳን’ አግኝተዋል። የራሳቸውን ጥቅም መሥዋዕት አድርገው መከሩን በመሰብሰቡ ሥራ የተሰማሩት ሠራተኞች “ዋጋ” ወይም “ዕድል ፈንታ” [አ.መ.ት ] በሰማይ የማይጠፋ ሕይወት አሊያም በምድር ዘላለማዊ ሕይወት ማግኘት ነው። በታማኝነት የሚጸኑ ሁሉ ‘ድካማቸው በጌታ ከንቱ እንደማይሆን’ እርግጠኞች መሆን ይችላሉ።​—⁠1 ቆሮንቶስ 15:​58

25. የይሖዋ ሕዝቦች ምን ዋስትና ተሰጥቷቸዋል?

25 የይሖዋ ሰማያዊት ድርጅት፣ በምድር ያሉት ቅቡዓን ወኪሎቿና ከእነሱ ጋር ተባብረው በመሥራት ላይ ያሉት ሰዎች ሁሉ ብሩህ የሆነ ተስፋ ይጠብቃቸዋል። (ዘዳግም 26:​19) ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ተንብዮአል:- “እግዚአብሔር:- የተቤዣቸው፣ የተቀደሰ ሕዝብ ብለው ይጠሩአቸዋል፤ አንቺም:- የተፈለገች ያልተተወችም ከተማ ትባያለሽ።” (ኢሳይያስ 62:12) በአምላክ እስራኤል የተወከለችው “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” በአንድ ወቅት እንደተተወች ሆኖ ተሰምቷት ነበር። ወደፊት ዳግመኛ እንዲህ ያለ ስሜት አያድርባትም። የይሖዋ ሕዝቦች በአምላክ ሞገስ ታቅፈው ለዘላለም የእሱን ጥበቃ እያገኙ ይኖራሉ።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.7 “አዲስ ስም” በመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት መሠረት አዲስ ቦታ ወይም መብት ማግኘትን ሊያመለክት ይችላል።​—⁠ራእይ 2:​17፤ 3:​12

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 342 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

ከሁሉ የላቀ የጋብቻ ተምሳሌት

ሰዎች ትዳር ሲመሠርቱ ከጋብቻቸው የሚጠብቁት ነገር ይኖራል። ይሁን እንጂ አምላክ ከትዳር ጥምረት የሚጠብቀው ነገር ምንድን ነው? ጋብቻን የመሠረተው ይሖዋ እንደመሆኑ መጠን ጋብቻን ያቋቋመበት ዓላማ ምንድን ነው?

አምላክ ይህን በተመለከተ ያለውን አመለካከት ከሚጠቁሙን ነገሮች አንዱ ከእስራኤል ሕዝብ ጋር የነበረው ዝምድና ነው። ኢሳይያስ በይሖዋና በእስራኤል መካከል የነበረውን ዝምድና በጋብቻ መስሎታል። (ኢሳይያስ 62:​1-5) ይሖዋ አምላክ ልክ እንደ አንድ “ባል” ‘ለሙሽራው’ ምን እንደሚያደርግላት ልብ በል። ይጠብቃታል እንዲሁም ይቀድሳታል። (ኢሳይያስ 62:​6, 7, 12) የሚያከብራት ከመሆኑም በላይ ከፍ አድርጎ ይመለከታታል። (ኢሳይያስ 62:​3, 8, 9) ከዚህም በተጨማሪ ያወጣላት አዳዲስ ስሞች እንደሚያመለክቱት በእርስዋ ደስ ይለዋል።​—⁠ኢሳይያስ 62:​4, 5, 12

በክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን ጽሑፎች ውስጥ ጳውሎስ በባልና በሚስት መካከል ያለውን ዝምድና በክርስቶስና በቅቡዓን ክርስቲያኖች ጉባኤ መካከል ካለው ዝምድና ጋር አመሳስሎ በገለጸበት ጊዜ ኢሳይያስ በይሖዋና በእስራኤል መካከል ያለውን ግንኙነት አስመልክቶ የተናገረውን ሐሳብ አንጸባርቋል።​—⁠ኤፌሶን 5:​21-27

ጳውሎስ ክርስቲያኖች በኢየሱስና በጉባኤው መካከል ያለውን ዓይነት ዝምድና በትዳራቸው ውስጥ እንዲያንጸባርቁ መክሯቸዋል። ይሖዋ ለእስራኤል እንዲሁም ክርስቶስ ለጉባኤው ካሳዩት ፍቅር የላቀ የፍቅር ዓይነት ሊኖር አይችልም። እነዚህ ተምሳሌታዊ ዝምድናዎች ክርስቲያኖች ስኬታማና አስደሳች የሆነ ትዳር መመሥረት እንዲችሉ ግሩም ምሳሌዎች ይሆናሉ።​—⁠ኤፌሶን 5:​28-33

[በገጽ 339 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሖዋ ለሰማያዊቷ ጽዮን አዲስ ስም ይሰጣታል

[በገጽ 347 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

በዘመናችን የይሖዋ ጉበኛ ዝም አላለም