በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የይሖዋ እጅ አላጠረችም

የይሖዋ እጅ አላጠረችም

ምዕራፍ ሃያ

የይሖዋ እጅ አላጠረችም

ኢሳይያስ 59:​1-21

1. በይሁዳ የነበረው ሁኔታ ምን ይመስላል? በብዙዎች አእምሮ ውስጥ ምን ጥያቄ ይመላለስ ነበር?

የይሁዳ ሕዝብ ከይሖዋ ጋር በቃል ኪዳን የተሳሰረ እንደሆነ ቢናገርም ምድሪቱ በተለያዩ ችግሮች ታምሳለች። ፍትሕ ከመጥፋቱም በላይ ወንጀልና ጭቆና እጅግ ተስፋፍቷል። ሁኔታዎች ከቀን ወደ ቀን እየተሻሻሉ ይሄዳሉ የሚለው ተስፋም እውን ሊሆን አልቻለም። አንድ ትልቅ ችግር እንዳለ በግልጽ ይታያል። ይሖዋ ሁኔታውን ለማስተካከል አንድ ዓይነት እርምጃ ይወስድ ይሆን የሚለው ጥያቄ በብዙዎች አእምሮ ውስጥ ይመላለሳል። በኢሳይያስ ዘመን የነበረው ሁኔታ ይህን ይመስላል። ይሁን እንጂ ኢሳይያስ ያን ዘመን አስመልክቶ ያሰፈረው ዘገባ በጥንት ዘመን የተፈጸሙ ክንውኖችን በመተረክ ብቻ የሚወሰን አይደለም። ኢሳይያስ ያሰፈራቸው ቃላት አምላክን አመልካለሁ እያሉ ሕጎቹን ችላ የሚሉ ሰዎችን በሙሉ የሚመለከቱ ትንቢታዊ ማስጠንቀቂያዎችም ይዘዋል። ከዚህም በተጨማሪ በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 59 ላይ ተመዝግቦ የሚገኘው በመንፈስ አነሳሽነት የተነገረው ትንቢት አስቸጋሪና አደገኛ በሆነ ዘመን ውስጥ እየኖሩም ይሖዋን ለማገልገል ለሚጥሩ ሰዎች በሙሉ ጥሩ ማበረታቻ ይሰጣል።

ከእውነተኛው አምላክ ራቁ

2, 3. ይሖዋ ይሁዳን የማይጠብቀው ለምንድን ነው?

2 የአምላክ የቃል ኪዳን ሕዝቦች በይሖዋ ላይ ክህደት ፈጽመዋል! ለፈጣሪያቸው ጀርባቸውን በመስጠት ከእሱ ጥበቃ ሥር ወጥተዋል። በዚህም ሳቢያ ከባድ መከራ እየደረሰባቸው ነው። ለገጠማቸው ችግር ተጠያቂው ይሖዋ እንደሆነ ተሰምቷቸው ይሆን? ኢሳይያስ እንዲህ አላቸው:- “እነሆ፣ የእግዚአብሔር እጅ ከማዳን አላጠረችም፣ ጆሮውም ከመስማት አልደነቈረችም፤ ነገር ግን በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፣ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሰውሮታል።”​—⁠ኢሳይያስ 59:1, 2

3 እነዚህ ቃላት እውነታውን በማያሻማ መንገድ ቁልጭ አድርገው የሚገልጹ ናቸው። በዚህም ጊዜ ቢሆን ይሖዋ ማዳን አልተሳነውም። ‘ጸሎትን የሚሰማ’ አምላክ እንደመሆኑ መጠን ታማኝ አገልጋዮቹ የሚያቀርቡትን ጸሎት ይሰማል። (መዝሙር 65:​2) ይሁን እንጂ ኃጢአተኞችን አይባርክም። ከይሖዋ የራቀው ሕዝቡ ራሱ ነው። የገዛ ራሳቸው የክፋት ድርጊት ፊቱን ከእነሱ እንዲሰውር አድርጎታል።

4. ይሁዳ የተወነጀለችው በምንድን ነው?

4 እንደ እውነቱ ከሆነ ይሁዳ እጅግ አስከፊ የሆነ ታሪክ አስመዝግባለች። የኢሳይያስ ትንቢት አይሁዳውያን የተወነጀሉባቸውን አንዳንድ መጥፎ ድርጊቶች ይዘረዝራል:- “እጃችሁ በደም ጣታችሁም በበደል ረክሳለች፣ ከንፈራችሁም ሐሰትን ተናግሮአል፣ ምላሳችሁም ኃጢአትን አሰምቶአል።” (ኢሳይያስ 59:3) ሕዝቡ ይዋሻሉ እንዲሁም ክፉ ነገር ይናገራሉ። “እጃችሁ በደም . . . ረክሳለች” የሚለው መግለጫ አንዳንዶች ነፍስ እስከማጥፋት እንደደረሱ ያመለክታል። እንዲህ ያለው ድርጊት ነፍስ ግድያን ብቻ ሳይሆን ‘ወንድምህን በልብህ መጥላትን’ ጭምር የሚከለክል ሕግ ያወጣውን አምላክ ክብር እጅግ ዝቅ የሚያደርግ ነው! (ዘሌዋውያን 19:​17) የይሁዳ ነዋሪዎች ይፈጽሙት የነበረው መረን የለቀቀ ኃጢአትና ይህ ድርጊታቸው የኋላ ኋላ ያስከተለው መዘዝ በዛሬው ጊዜ እያንዳንዳችን ወደ ኃጢአት ድርጊት የሚገፋፉ አስተሳሰቦችንና ስሜቶችን መቆጣጠር እንደሚያስፈልገን ሊያስተምረን ይገባል። አለዚያ ውሎ አድሮ ከአምላክ ጋር የሚያቆራርጥ የክፋት ድርጊት ልንፈጽም እንችላለን።​—⁠ሮሜ 12:​9፤ ገላትያ 5:​15፤ ያዕቆብ 1:​14, 15

5. የይሁዳ የሥነ ምግባር አቋም ምን ያህል ተበክሎ ነበር?

5 መላው የይሁዳ ብሔር በኃጢአት ተበክሎ ነበር። ትንቢቱ እንዲህ ሲል ይገልጻል:- “በጽድቅ የሚጠራ በእውነትም የሚፈርድ የለም፤ በምናምንቴ ነገር ታምነዋል ሐሰትንም ተናግረዋል፤ ጉዳትን ፀንሰዋል በደልንም ወልደዋል።” (ኢሳይያስ 59:4) ጽድቅ የሚናገር የለም። ሌላው ቀርቶ በፍርድ ቤቶች እንኳ እምነት የሚጣልበት ወይም ታማኝ የሆነ ሰው ማግኘት አስቸጋሪ ነው። ይሁዳ ጀርባዋን ለይሖዋ በመስጠት ከሌሎች ብሔራት ጋር በፈጠረችው ኅብረት ከመመካቷም በላይ በድን በሆኑ ጣዖታት ታምናለች። እነዚህ ሁሉ “ምናምንቴ” እና ለምንም የማይጠቅሙ ናቸው። (ኢሳይያስ 40:​17, 23፤ 41:​29) በዚህም ምክንያት ብዙ ውይይት ቢደረግም ምንም ውጤት ሊገኝ አልቻለም። የተለያዩ እቅዶች ቢወጠኑም ችግርና ጉዳት ከማስከተል በቀር የፈየዱት ነገር የለም።

6. ሕዝበ ክርስትና ያስመዘገበችው ታሪክ ከይሁዳ ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው?

6 በጥንቷ ይሁዳ ይፈጸም የነበረው ክፋትና ዓመፅ በዛሬው ጊዜ በሕዝበ ክርስትና ውስጥም ሲንጸባረቅ ይታያል። (በገጽ 294 ላይ የሚገኘውን “ከሃዲዋ ኢየሩሳሌም​—⁠የሕዝበ ክርስትና አምሳያ” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።) ክርስቲያን ነን በሚሉ አገሮች ውስጥ አሰቃቂ የሆኑ ሁለት የዓለም ጦርነቶች ተካሂደዋል። የሕዝበ ክርስትና የይስሙላ አምልኮ እስከ አሁንም ድረስ የዘር ማጥፋት ዘመቻዎችንና በገዛ አባሎቿ መካከል የሚካሄደውን የጎሳ ጭፍጭፍ ማስቆም አልቻለም። (2 ጢሞቴዎስ 3:​5) ኢየሱስ ተከታዮቹ በአምላክ መንግሥት እንዲታመኑ ያስተማረ ቢሆንም የሕዝበ ክርስትናን እምነት የሚያራምዱ አገሮች ደህንነትን ማስጠበቅ የሚቻለው በጦር መሣሪያ ክምችትና በፖለቲካ ጥምረት እንደሆነ አድርገው ያምናሉ። (ማቴዎስ 6:​10) እንዲያውም አብዛኞቹ ዋነኛ የጦር መሣሪያ አምራቾች የሚገኙት የሕዝበ ክርስትና ተከታይ በሆኑ አገሮች ውስጥ ነው! አዎን፣ ሕዝበ ክርስትና አስተማማኝ ሕይወት የሚገኘው በሰው ልጆች ጥረትና በሰብዓዊ ተቋማት አማካኝነት ነው የሚል እምነት ያላት በመሆኑ እሷም “በምናምንቴ” ታምናለች።

መራራ ፍሬ ማጨድ

7. የይሁዳ እቅድ ሁሉ ከጉዳት በስተቀር ምንም ጥቅም የማያስገኘው ለምንድን ነው?

7 የጣዖት አምልኮና ሸፍጥ በተስፋፋበት ሁኔታ ጤናማ ኅብረተሰብ ሊፈጠር ይችላል ብሎ ማሰብ ዘበት ነው። ከሃዲዎቹ አይሁዳውያን እንዲህ ያሉትን ድርጊቶች በመፈጸማቸው ራሳቸው የዘሩት ዘር ያስከተለውን ችግር መልሰው እያጨዱ ነው። ዘገባው እንዲህ ይላል:- “የእባብን እንቁላል ቀፈቀፉ፣ የሸረሪትንም ድር አደሩ፤ እንቁላላቸውንም የሚበላ ሰው ይሞታል፣ እንቁላሉም ሲሰበር እፉኝት ይወጣል።” (ኢሳይያስ 59:5) ይሁዳ የምታቅዳቸው ነገሮች ሁሉ ከውጥናቸው አንስቶ እስከ ፍጻሜያቸው ድረስ ይሄ ነው የሚባል የተጨበጠ ውጤት አያስገኙም። ከመርዛማ እባብ እንቁላሎች የሚፈለፈሉት መርዛማ እባቦች እንደሆኑ ሁሉ አይሁዳውያንም የተሳሳተ አስተሳሰባቸው ጉዳት ከማስከተልና ሕዝቡን ለመከራ ከመዳረግ በቀር የሚያስገኘው ነገር አይኖርም።

8. የይሁዳ አስተሳሰብ የተዛባ መሆኑን የሚያሳየው ምንድን ነው?

8 አንዳንድ የይሁዳ ነዋሪዎች ራሳቸውን ለመጠበቅ ሲሉ ኃይል መጠቀም ቢጀምሩም አይሳካላቸውም። የሸረሪት ድር እንደ ልብስ ከቅዝቃዜና ከብርድ እንደማያስጥል ሁሉ አንድ ሰው በይሖዋ ካልታመነና የጽድቅ ሥራዎችን ካልሠራ በስተቀር ሊያገኘው የማይችለውን ጥበቃ በራሱ ጉልበት ሊያገኘው አይችልም። ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ገለጸ:- “ድሮቻቸውም ልብስ አይሆኑላቸውም፣ በሥራቸውም አይሸፈኑም፤ ሥራቸውም የበደል ሥራ ነው፣ የግፍም ሥራ በእጃቸው ነው። እግሮቻቸው ወደ ክፋት ይሮጣሉ፣ ንጹሑን ደም ለማፍሰስ ይፈጥናሉ፤ አሳባቸው የኃጢአት አሳብ ነው፣ ጉስቁልናና ቅጥቃጤ በመንገዳቸው አለ።” (ኢሳይያስ 59:6, 7) ይሁዳ አስተሳሰቧ ተዛብቷል። ችግሮቿን በኃይል ለመፍታት በመሞከር አምላክ የማይቀበለውን ዝንባሌ አሳይታለች። በደል የምትፈጽምባቸው ብዙዎቹ ሰዎች ንጹሐን መሆናቸውና አንዳንዶቹ ደግሞ እውነተኛ የአምላክ አገልጋዮች መሆናቸው እንኳ ግድ አልሰጣትም።

9. የሕዝበ ክርስትና መሪዎች እውነተኛ ሰላም ሊያገኙ የማይችሉት ለምንድን ነው?

9 እነዚህ በመንፈስ አነሳሽነት የተጻፉ ቃላት በደም አፍሳሽነት ድርጊት የተሞላውን የሕዝበ ክርስትና ታሪክ እንድናስታውስ ያደርጉናል። ሕዝበ ክርስትና ሰዎች ለክርስትና የተዛባ አመለካከት እንዲኖራቸው በማድረጓ በይሖዋ ፊት ከተጠያቂነት አታመልጥም! በኢሳይያስ ዘመን እንደነበሩት አይሁዳውያን ሕዝበ ክርስትናም መሪዎቿ ብቸኛ አማራጭ አድርገው የወሰዱትን የተጣመመ ጎዳና ተከትላለች። በአንድ በኩል ስለ ሰላም እያወሩ በሌላ በኩል ኢፍትሐዊ የሆነ ድርጊት ይፈጽማሉ። እንዴት ያለ አታላይነት ነው! የሕዝበ ክርስትና መሪዎች ይህን ስልት አሁንም እየተጠቀሙበት በመሆኑ እውነተኛ ሰላም ሊያገኙ አይችሉም። ትንቢቱ በመቀጠል ይህን ሁኔታ እንዲህ ሲል ይገልጸዋል:- “የሰላምን መንገድ አያውቁም፣ በአካሄዳቸውም ፍርድ የለም፤ መንገዳቸውን አጣምመዋል፣ የሚሄድባትም ሁሉ ሰላምን አያውቅም።”​—⁠ኢሳይያስ 59:8

በመንፈሳዊ ጨለማ መደናበር

10. ኢሳይያስ ይሁዳን በመወከል ምን ኑዛዜ አቀረበ?

10 ይሖዋ ይሁዳ የተከተለችውን ጠማማና ጎጂ የሆነ መንገድ ሊባርክ አይችልም። (መዝሙር 11:​5) ስለዚህ ኢሳይያስ መላውን ሕዝብ በመወከል የይሁዳን ኃጢአት እንደሚከተለው ሲል ተናዘዘ:- “ፍርድ [“ፍትሕ፣” አ.መ.ት ] ከእኛ ዘንድ ርቆአል፣ ጽድቅም አላገኘንም፤ ብርሃንን በተስፋ እንጠባበቅ ነበር፣ እነሆም፣ ጨለማ ሆነ፤ ጸዳልን በተስፋ እንጠባበቅ ነበር፣ ነገር ግን በጨለማ ሄድን። እንደ ዕውሮች ወደ ቅጥሩ ተርመሰመስን፣ ዓይን እንደሌላቸው ተርመሰመስን፤ በቀትር ጊዜ በድግዝግዝታ እንዳለ ሰው ተሰናከልን፣ እንደ ሙታን በጨለማ ስፍራ ነን። ሁላችን እንደ ድቦች እንጮኻለን፣ እንደ ርግብ እንለቃቀሳለን።” (ኢሳይያስ 59:9-11ሀ) አይሁዳውያን የአምላክን ቃል ለእግራቸው መብራት ለመንገዳቸውም ብርሃን አድርገው አልተጠቀሙበትም። (መዝሙር 119:​105) በዚህም ሳቢያ ሁሉ ነገር ሊጨልምባቸው ችሏል። በቀትር ጊዜ እንኳ ልክ ጨለማ ውስጥ እንዳለ ሰው ይደናበራሉ። በድን የሆኑ ያህል ነበር። እፎይታ ለማግኘት ካላቸው ከፍተኛ ፍላጎት የተነሳ እንደተራቡ ወይም እንደቆሰሉ ድቦች ይጮኻሉ። አንዳንዶቹ ደግሞ ብቻቸውን እንደቀሩ ርግቦች ያንቋርራሉ።

11. ይሁዳ ፍትሕና መዳን አገኛለሁ ብላ ተስፋ ማድረጓ ከንቱ የሆነው ለምንድን ነው?

11 ይሁዳ ይህ ሁሉ መከራ የደረሰባት በአምላክ ላይ በማመጿ ምክንያት እንደሆነ ኢሳይያስ ጠንቅቆ ያውቃል። እንዲህ አለ:- “ፍርድን [“ፍትሕን፣” አ.መ.ት ] በተስፋ እንጠባበቅ ነበር እርሱም የለም፤ መዳንም ከእኛ ዘንድ ርቆአል። ዓመፃችን በአንተ ፊት በዝቶአልና፣ ኃጢአታችን መስክሮብናልና፣ ዓመፃችን ከእኛ ጋር ነውና፣ በደላችንን እናውቃለንና። ዐምፀናል፣ ሐሰትን ተናግረናል፣ አምላካችንንም ከመከተል ተመልሰናል፤ ግፍንና ዓመፅንም ተናግረናል፣ የኃጢአት ቃልንም ፀንሰን ከልብ አውጥተናል።” (ኢሳይያስ 59:11ለ-13) የይሁዳ ነዋሪዎች ንስሐ ስላልገቡ ምሕረት አላገኙም። ሕዝቡ ይሖዋን በመተዋቸው ፍትሕ ከምድሪቱ ጠፍቷል። በውሸት ከመሞላታቸውም በላይ በወንድሞቻቸው ላይ ግፍ ይፈጽማሉ። በዛሬው ጊዜ ካሉት የሕዝበ ክርስትና ተከታዮች ጋር በእጅጉ ይመሳሰላሉ! በዘመናችን ብዙዎች ፍትሕን ችላ ከማለታቸውም በተጨማሪ የአምላክን ፈቃድ ለማድረግ በሚጥሩት ታማኝ የይሖዋ ምሥክሮች ላይ ከባድ ስደት ያደርሳሉ።

ይሖዋ ፍርድ ያስፈጽማል

12. በይሁዳ ውስጥ ፍትሕ የማስፈን ኃላፊነት የነበረባቸው ሰዎች ምን ዝንባሌ አሳይተዋል?

12 በይሁዳ ምድር ፍትሕ፣ ጽድቅ ወይም እውነት የሚባል ነገር ጨርሶ ያለ አይመስልም። “ፍርድም [“ፍትሕ፣” አ.መ.ት ] ወደ ኋላ ተመልሶአል፣ ጽድቅም በሩቅ ቆሞአል፤ እውነትም በአደባባይ ላይ ወድቆአልና፣ ቅንነትም ሊገባ አልቻለምና።” (ኢሳይያስ 59:14) በከተማይቱ ደጆች ሽማግሌዎች ሕጋዊ ጉዳዮችን ለመመርመር የሚቀመጡባቸው አደባባዮች አሉ። (ሩት 4:​1, 2, 11) እነዚህ ወንዶች ጉቦ ከመቀበል በመታቀብ በጽድቅ መፍረድና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ መዳኘት ይጠበቅባቸዋል። (ዘዳግም 16:​18-20) ይሁን እንጂ በዚያ ዘመን የነበሩት ሰዎች ይፈርዱ የነበረው የራሳቸውን የግል ጥቅም ግምት ውስጥ በማስገባት ነበር። ይባስ ብሎ ደግሞ ከልባቸው መልካም ለማድረግ የሚጥሩትን ሰዎች ዋነኛ የጥቃት ዒላማ ያደርጓቸው ነበር። ዘገባው እንዲህ ይላል:- “እውነትም ታጥቶአል፣ ከክፋትም የራቀ ሰው ለብዝበዛ ሆኖአል።”​—⁠ኢሳይያስ 59:15ሀ

13. የይሁዳ ፈራጆች ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ባለመወጣታቸው ይሖዋ ምን ያደርጋል?

13 ብልሹ ሥነ ምግባርን በድፍረት ከማውገዝ ወደ ኋላ ያሉት ሰዎች ይሖዋ ማየት የማይችል፣ እየተፈጸመ ያለውን ነገር የማያውቅ ወይም አንዳች ማድረግ የማይችል አምላክ አለመሆኑን ዘንግተዋል። ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ጻፈ:- “እግዚአብሔርም አየ፣ ፍርድም [“ፍትሕ፣” አ.መ.ት ] ስለሌለ ተከፋ። ሰውም እንደሌለ አየ፣ ወደ እርሱ የሚማልድ እንደሌለ ተረዳ ተደነቀም፤ ስለዚህ የገዛ ክንዱ መድኃኒት አመጣለት፣ ጽድቁም አገዘው።” (ኢሳይያስ 59:15ለ, 16) የተሾሙት ፈራጆች ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ሳይወጡ በመቅረታቸው ይሖዋ በጉዳዩ እጁን ጣልቃ ያስገባል። ጣልቃ በሚገባበት ጊዜ ደግሞ የጽድቅ ሥርዓትን የተከተለ የኃይል እርምጃ ይወስዳል።

14. (ሀ) በዛሬው ጊዜ ብዙዎች ምን ዓይነት አመለካከት አላቸው? (ለ) ይሖዋ እርምጃ ለመውሰድ የተዘጋጀው እንዴት ነው?

14 ዛሬም ያለው ሁኔታ ተመሳሳይ ነው። በዓለም ውስጥ ያሉ ብዙዎቹ ሰዎች ‘ኅሊናቸው ደንዝዟል።’ (ኤፌሶን 4:​19 አ.መ.ት ) አብዛኞቹ ሰዎች ይሖዋ እጁን ጣልቃ በማስገባት ክፋትን ከምድር ላይ ያስወግዳል የሚል እምነት የላቸውም። ይሁን እንጂ የኢሳይያስ ትንቢት ይሖዋ ሰብዓዊ ጉዳዮችን በትኩረት እንደሚከታተል ያመለክታል። የፍርድ ውሳኔዎች የሚያስተላልፍ ከመሆኑም በላይ የወሰነው ጊዜ ሲደርስ ብያኔዎቹን ያስፈጽማል። ፍርዶቹ ፍትሐዊ ናቸውን? ኢሳይያስ ፍትሐዊ እንደሆኑ አመልክቷል። የይሁዳን ሕዝብ ሁኔታ በተመለከተ እንዲህ ሲል ጽፏል:- [ይሖዋ] ጽድቅንም እንደ ጥሩር ለበሰ፣ በራሱም ላይ የማዳንን ራስ ቁር አደረገ፤ የበቀልንም ልብስ ለበሰ፣ በቅንዓትም መጐናጸፊያ ተጐናጸፈ።” (ኢሳይያስ 59:17) እነዚህ ትንቢታዊ ቃላት ይሖዋን ለጦርነት እየታጠቀ እንዳለ ተዋጊ አድርገው ገልጸውታል። ዓላማው ዳር እንዲደርስ በማድረግ ‘መዳን’ ለማስገኘት ቆርጦ ተነስቷል። እንከን በማይወጣለትና ፈጽሞ በማይታበለው ጽድቁ ሙሉ በሙሉ ይተማመናል። የፍርድ ብያኔዎቹንም በከፍተኛ ቅንዓት ይፈጽማል። ጽድቅ ድል እንደሚያደርግ ምንም አያጠራጥርም።

15. (ሀ) ይሖዋ ፍርዱን በሚያስፈጽምበት ጊዜ እውነተኛ ክርስቲያኖች ምን አያደርጉም? (ለ) ስለ ይሖዋ ፍርድ ምን ለማለት ይቻላል?

15 ዛሬ በአንዳንድ አገሮች የእውነት ጠላት የሆኑ ሰዎች ስም የሚያጠፋ የሐሰት ፕሮፓጋንዳ በመንዛት የይሖዋ አገልጋዮች የሚያካሂዱትን ሥራ ለማስተጓጎል ጥረት ያደርጋሉ። እውነተኛ ክርስቲያኖች ከእውነት ጎን ለመቆም የማያመነቱ ቢሆንም በግል ለመበቀል አይሞክሩም። (ሮሜ 12:​19) ይሖዋ በከሃዲዋ ሕዝበ ክርስትና ላይ የበቀል እርምጃ በሚወስድበት ጊዜ እንኳ በምድር ላይ ያሉት አምላኪዎቹ በምንም መንገድ በእሷ ላይ እጃቸውን አያነሱም። በቀል የይሖዋ እንደሆነና ጊዜው ሲደርስ ተገቢውን እርምጃ እንደሚወስድ ይገነዘባሉ። ትንቢቱ የሚከተለውን ዋስትና ይሰጠናል:- “እንደ ሥራቸው መጠን እንዲሁ ቁጣን ለባላጋራዎቹ፣ ፍዳንም ለጠላቶቹ ይከፍላል፤ ለደሴቶችም ፍዳቸውን ይከፍላል።” (ኢሳይያስ 59:18) በኢሳይያስ ዘመን እንደነበረው ሁሉ ዛሬም አምላክ ፍርዱን የሚያስፈጽመው ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ብቻ ሳይሆን በተሟላ ሁኔታ ነው። የቅጣት እርምጃው በሩቅ የሚገኙ ‘ደሴቶችን’ ሳይቀር ያጠቃልላል። ርቀው በሚገኙ የምድር ክፍሎች በመኖራቸው ምክንያት ከይሖዋ የቅጣት እርምጃ የሚያመልጡ ሰዎች አይኖሩም።

16. ይሖዋ ከሚወስደው የቅጣት እርምጃ የሚተርፉት እነማን ናቸው? ይህስ በእነሱ ላይ ምን ውጤት ይኖረዋል?

16 ትክክል የሆነውን ነገር ለማድረግ የሚጥሩ ሰዎች የይሖዋን የጽድቅ ፍርድ ያገኛሉ። ኢሳይያስ ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ በመላው ምድር የሚኖሩ እንዲህ ያሉ ሰዎች ከጥፋት እንደሚድኑ ተንብዮአል። የይሖዋን ጥበቃ ማግኘታቸው ለእሱ ያላቸውን አምልኮታዊ ፍርሃትና አክብሮት በእጅጉ ያጠነክረዋል። (ሚልክያስ 1:​11) ዘገባው እንዲህ ይላል:- “እርሱ የእግዚአብሔር ነፋስ እንደሚነዳው እንደ ጐርፍ ፈሳሽ ይመጣልና በምዕራብ ያሉት የእግዚአብሔርን ስም፣ በፀሐይ መውጫም ያሉት ክብሩን ይፈራሉ።” (ኢሳይያስ 59:19) ከፊቱ ያለን ኃይለኛ ጎርፍ እያካለበ በመውሰድ ያገኘውን ነገር ሁሉ ጠራርጎ እንደሚያጠፋ አውሎ ነፋስ የይሖዋ መንፈስም ፈቃዱ እንዳይፈጸም እንቅፋት የሚሆኑትን ነገሮች በሙሉ ሙልጭ አድርጎ ያስወግዳል። መንፈሱ ከማንም ሰው ጉልበት የላቀ ኃይል አለው። በሰዎችና በብሔራት ላይ ፍርድ ለማስፈጸም በሚጠቀምበት ጊዜ ያሰበውን ነገር በተሟላና አስተማማኝ በሆነ መንገድ ያከናውንለታል።

ንስሐ የገቡ ሰዎች የሚያገኙት ተስፋና በረከት

17. የጽዮን ታዳጊ ማን ነው? የታደጋትስ መቼ ነው?

17 በሙሴ ሕግ መሠረት ራሱን ለባርነት የሸጠን አንድ እስራኤላዊ ሌላ ሰው ከባርነት ሊቤዠው ይችል ነበር። ቀደም ሲል በትንቢታዊው የኢሳይያስ መጽሐፍ ውስጥ ይሖዋ ንስሐ የገቡ ሰዎችን የሚታደግ አምላክ እንደሆነ ተገልጾ ነበር። (ኢሳይያስ 48:​17) አሁንም በድጋሚ ንስሐ የገቡ ሰዎችን እንደሚታደግ ተገልጿል። ኢሳይያስ፣ ይሖዋ የገባውን ቃል እንዲህ ሲል ዘግቧል:- “ለጽዮን ታዳጊ ይመጣል፣ በያዕቆብም ዘንድ ከኃጢአት ለሚርቁ፣ ይላል እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 59:20) ይህ አጽናኝ ተስፋ በ537 ከዘአበ ተፈጽሟል። ይሁን እንጂ ሌላም ተፈጻሚነት አለው። ሐዋርያው ጳውሎስ እነዚህን ቃላት ከሰፕቱጀንት ትርጉም ላይ በመጥቀስ በክርስቲያኖች ላይ ፍጻሜያቸውን እንደሚያገኙ ጠቁሟል። እንዲህ ሲል ጻፈ:- “እንደዚሁም እስራኤል ሁሉ ይድናል፤ እንዲህ ተብሎ እንደ ተጻፈ:- መድኃኒት ከጽዮን ይወጣል ከያዕቆብም ኃጢአተኛነትን ያስወግዳል። ኃጢአታቸውንም ስወስድላቸው ከእነርሱ ጋር የምገባው ኪዳን ይህ ነው።” (ሮሜ 11:26, 27) በእርግጥም ይህ የኢሳይያስ ትንቢት በዚያ ዘመን ብቻ ተወስኖ አይቀርም። ከዚህ ይልቅ እኛ ባለንበት ዘመንም ሆነ ወደፊት በስፋት ፍጻሜውን ያገኛል። እንዴት?

18. ይሖዋ ‘የእግዚአብሔር እስራኤልን’ ወደ ሕልውና ያመጣው መቼና እንዴት ነው?

18 በመጀመሪያው መቶ ዘመን ጥቂት የእስራኤል ሕዝብ ቀሪዎች የኢየሱስን መሲሕነት አምነው ተቀበሉ። (ሮሜ 9:​27፤ 11:​5) በ33 እዘአ በጰንጠቆስጤ ዕለት ይሖዋ 120 በሚሆኑ አማኞች ላይ ቅዱስ መንፈሱን በማፍሰስ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በተገባው አዲስ ቃል ኪዳን እንዲታቀፉ አደረጋቸው። (ኤርምያስ 31:​31-33፤ ዕብራውያን 9:​15) በዚያ ዕለት አዲስ ብሔር ማለትም ‘የእግዚአብሔር እስራኤል’ ተወለደ። የዚህ ብሔር አባላት የአብርሃም ሥጋዊ ዘሮች ሳይሆኑ በአምላክ መንፈስ የተወለዱ ናቸው። (ገላትያ 6:​16) ይህ አዲስ ብሔር ቆርኔሌዎስ ወደ ክርስትና ከተለወጠበት ጊዜ አንስቶ ካልተገረዙ አሕዛብ የተውጣጡ ሰዎችን ያቀፈ ሆኗል። (ሥራ 10:​24-48፤ ራእይ 5:​9, 10) በዚህ መንገድ ይሖዋ እነዚህን ሰዎች የዋጃቸው ሲሆን ከኢየሱስ ጋር አብረው የሚወርሱ መንፈሳዊ ልጆቹ ሆነዋል።​—⁠ሮሜ 8:​16, 17

19. ይሖዋ ከአምላክ እስራኤል ጋር ምን ቃል ኪዳን ገብቷል?

19 በመቀጠል ይሖዋ ከአምላክ እስራኤል ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። ዘገባው እንዲህ ይላል:- “ከእነርሱ ጋር ያለው ቃል ኪዳኔ ይህ ነው ይላል እግዚአብሔር፤ በአንተ ላይ ያለው መንፈሴ በአፍህም ውስጥ ያደረግሁት ቃሌ ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም ድረስ ከአፍህ ከዘርህም አፍ ከዘር ዘርህም አፍ አያልፍም፣ ይላል እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 59:21) እነዚህ ቃላት በራሱ በኢሳይያስ ላይ ተፈጻሚነታቸውን አገኙም አላገኙ ‘ዘሩን እንደሚያይ’ ዋስትና ተሰጥቶት በነበረው በኢየሱስ ላይ ፍጻሜያቸውን እንዳገኙ ጥርጥር የለውም። (ኢሳይያስ 53:​10) ኢየሱስ ከይሖዋ የተማረውን ቃል ያስተማረ ሲሆን የይሖዋ መንፈስ በላዩ ነበረ። (ዮሐንስ 1:​18፤ 7:​16) የአምላክ እስራኤል አባላት የሆኑትና ከእርሱ ጋር አብረው የሚወርሱት ወንድሞቹም የይሖዋን ቅዱስ መንፈስ ተቀብለው ሰማያዊ አባታቸው ያስተማራቸውን ቃል መስበካቸው የተገባ ነው። ሁሉም “ከእግዚአብሔር የተማሩ” ናቸው። (ኢሳይያስ 54:​13፤ ሉቃስ 12:​12፤ ሥራ 2:​38) ይሖዋ በሌላ እንደማይተካቸውና ለዘላለም ምሥክሮቹ አድርጎ እንደሚጠቀምባቸው በኢሳይያስ አማካኝነት አሊያም ኢሳይያስ ትንቢታዊ አምሳያ በሆነለት በኢየሱስ በኩል ቃል ገብቷል። (ኢሳይያስ 43:​10) ይሁንና በዚህ ቃል ኪዳን የሚጠቀሙት ‘ዘሮቻቸው’ እነማን ናቸው?

20. ይሖዋ ለአብርሃም የገባው ቃል በመጀመሪያው መቶ ዘመን የተፈጸመው እንዴት ነው?

20 በጥንት ዘመን ይሖዋ ለአብርሃም “የምድር አሕዛብ ሁሉም በዘርህ ይባረካሉ [“ራሳቸውን ይባርካሉ፣” NW ]” ሲል ቃል ገብቶለት ነበር። (ዘፍጥረት 22:18) በዚህ መሠረት መሲሑን የተቀበሉ ጥቂት ሥጋዊ እስራኤላውያን ቀሪዎች ወደ ብዙ አሕዛብ በመሄድ ስለ ክርስቶስ የሚናገረውን ምሥራች ሰበኩ። ከቆርኔሌዎስ አንስቶ ብዙ ያልተገረዙ አሕዛብ የአብርሃም ዘር በሆነው በኢየሱስ ‘ራሳቸውን ባርከዋል።’ የአምላክ እስራኤል አባልና የአብርሃም ዘር ሁለተኛ ክፍል ሆነዋል። እነዚህ ሰዎች የይሖዋ “ቅዱስ ሕዝብ” አካል ሲሆኑ ‘ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራቸውን የእርሱን በጎነት የመናገር’ ተልዕኮ ተሰጥቷቸዋል።​—⁠1 ጴጥሮስ 2:​9፤ ገላትያ 3:​7-9, 14, 26-29

21. (ሀ) በዘመናችን የአምላክ እስራኤል አባላት ምን “ዘር” አፍርተዋል? (ለ) እነዚህ ‘ዘሮች’ ይሖዋ ከአምላክ እስራኤል ጋር በገባው ቃል ኪዳን ወይም ውል የሚበረታቱት እንዴት ነው?

21 በዛሬው ጊዜ የአምላክ እስራኤል አባላት ሙሉ በሙሉ እንደተሰበሰቡ ካሉት ሁኔታዎች በግልጽ መረዳት ይቻላል። ያም ሆኖ አሕዛብ በከፍተኛ ደረጃ እየተባረኩ ነው። እንዴት? የአምላክ እስራኤል አባላት “ዘር” ማለትም ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ ያላቸውን የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በማፍራታቸው ነው። (መዝሙር 37:​11, 29) እነዚህ ‘ዘሮችም’ ከይሖዋ የተማሩና በመንገዱ የሚሄዱ ናቸው። (ኢሳይያስ 2:​2-4) በመንፈስ ቅዱስ የተጠመቁ ወይም የአዲሱ ቃል ኪዳን ተካፋዮች ተደርገው የማይቆጠሩ ቢሆንም እንኳ ሰይጣን የስብከት ሥራቸውን ለማደናቀፍ የሚፈጥራቸውን እንቅፋቶች ሁሉ መወጣት እንዲችሉ ይሖዋ ቅዱስ መንፈሱን በመስጠት ያጠነክራቸዋል። (ኢሳይያስ 40:​28-31) እነዚህ ሰዎች በአሁኑ ጊዜ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሲሆኑ እነሱም በተራቸው የራሳቸውን ዘር እያፈሩ በሄዱ መጠን ቁጥራቸው እያደገ ይሄዳል። ይሖዋ ከቅቡዓን ክርስቲያኖች ጋር የገባው ቃል ኪዳን ወይም ውል እነዚህ ‘ዘሮች’ ይሖዋ እነሱንም ለዘላለም ቃል አቀባዮቹ አድርጎ እንደሚጠቀምባቸው እንዲተማመኑ ያደርጋቸዋል።​—⁠ራእይ 21:​3, 4, 7

22. በይሖዋ ላይ ምን ትምክህት ሊያድርብን ይችላል? ይህስ ለምን ነገር ሊያነሳሳን ይገባል?

22 እንግዲያው ሁላችንም በይሖዋ ላይ ያለንን እምነት ጠብቀን እንኑር። ይሖዋ ለማዳን ዝግጁ ከመሆኑም በላይ ይህን ለማድረግ የሚያስችል ኃይል አለው! እጁ መቼም ቢሆን አታጥርም። ታማኝ አገልጋዮቹን ከማዳን ወደኋላ የሚልበት ጊዜ አይኖርም። በእሱ የሚታመኑ ሁሉ የአምላክን መልካም ቃል “ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም ድረስ” ከአፋቸው አይለዩም።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 294 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

ከሃዲዋ ኢየሩሳሌም​—⁠የሕዝበ ክርስትና አምሳያ

አምላክ የመረጠው ሕዝብ መዲና የነበረችው ኢየሩሳሌም መንፈሳዊ ፍጥረታትን ያቀፈችውን የአምላክ ሰማያዊት ድርጅት እንዲሁም ሰማያዊ ትንሣኤ ያገኙትን ቅቡዓን ክርስቲያኖች አቅፋ የያዘችውን የክርስቶስ ሙሽራ ትወክላለች። (ገላትያ 4:​25, 26፤ ራእይ 21:​2) ይሁን እንጂ የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች በተደጋጋሚ ጊዜያት ለይሖዋ ታማኝ ሆነው ባለመገኘታቸው ከተማዋ ጋለሞታና አመንዝራ ተብላ ተጠርታለች። (ሕዝቅኤል 16:​3, 15, 30-42) ከዚህ አንጻር ሲታይ ኢየሩሳሌም ለከሃዲዋ ሕዝበ ክርስትና ተስማሚ ተምሳሌት ነች።

ኢየሱስ ኢየሩሳሌምን “ነቢያትን የምትገድል ወደ እርስዋ የተላኩትንም የምትወግር” ብሏታል። (ሉቃስ 13:​34፤ ማቴዎስ 16:​21) ልክ እንደ ከዳተኛዋ ኢየሩሳሌም ሕዝበ ክርስትናም እውነተኛውን አምላክ እንደምታገለግል የምትናገር ቢሆንም ከጽድቅ መንገዶቹ በእጅጉ ርቃለች። ይሖዋ በከሃዲዋ ኢየሩሳሌም ላይ የፍርድ እርምጃ ለመውሰድ የተጠቀመባቸውን የጽድቅ መስፈርቶች በመጠቀም በሕዝበ ክርስትናም ላይ እንደሚፈርድ እርግጠኞች መሆን እንችላለን።

[በገጽ 296 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

አንድ ፈራጅ ጉቦ ከመቀበል በመታቀብ በጽድቅ መፍረድና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ መዳኘት ይኖርበታል

[በገጽ 298 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የይሖዋ የፍርድ ውሳኔዎች ፈቃዱ እንዳይከናወን እንቅፋት የሚፈጥሩትን ነገሮች በሙሉ ልክ እንደ ጎርፍ ጠራርገው ያስወግዷቸዋል

[በገጽ 302 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሖዋ ሕዝቡ ምሥክሮቹ ሆነው የማገልገል መብታቸውን እንደማያጡ ቃል ገብቷል