በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋ ለራሱ የከበረ ስም ያደርጋል

ይሖዋ ለራሱ የከበረ ስም ያደርጋል

ምዕራፍ ሃያ አራት

ይሖዋ ለራሱ የከበረ ስም ያደርጋል

ኢሳይያስ 63:​1-14

1, 2. (ሀ) መጪው ‘የይሖዋ ቀን’ ለክርስቲያኖች ምን ጥቅም ያስገኝላቸዋል? (ለ) ከመጪው የይሖዋ ቀን ጋር በተያያዘ ከሁሉ የላቀ ግምት የሚሰጠው ጉዳይ ምንድን ነው?

ክርስቲያኖች ለሁለት ሺህ ዓመት ገደማ ‘የእግዚአብሔርን ቀን መምጣት እየጠበቁና እያስቸኮሉ’ ኖረዋል። (2 ጴጥሮስ 3:​11፤ ቲቶ 2:​13) ያን ቀን በጉጉት መጠባበቃቸው ምንም አያስደንቅም። ያ ቀን ሲመጣ አለፍጽምና ካስከተለባቸው መዘዝ ወደሚገላገሉበት አዲስ ሥርዓት ይሸጋገራሉ። (ሮሜ 8:​22) በተጨማሪም በዚህ “የሚያስጨንቅ ዘመን” ከሚደርስባቸው ተጽዕኖ ሁሉ ይላቀቃሉ።​—⁠2 ጢሞቴዎስ 3:​1

2 ይሁን እንጂ ይህ የይሖዋ ቀን ለጻድቃን እፎይታ የሚያስገኝ ቢሆንም ‘እግዚአብሔርን በማያውቁና ለጌታችን ለኢየሱስ ወንጌል በማይታዘዙት’ ሰዎች ላይ ጥፋት ያስከትላል። (2 ተሰሎንቄ 1:​7, 8) ይህ በጥሞና ሊታሰብበት የሚገባ ጉዳይ ነው። በእርግጥ አምላክ ክፉዎችን የሚያጠፋው ሕዝቦቹን አስጨናቂ ከሆኑ ሁኔታዎች ለማላቀቅ ብቻ ነው? የኢሳይያስ መጽሐፍ 63ኛ ምዕራፍ ይሖዋ ክፉዎችን ለማጥፋት እንዲነሳሳ የሚያደርግ ከዚህ የላቀ ምክንያት እንዳለው ይገልጻል። ይሖዋ ይህን እርምጃ የሚወስደው ስሙን ለማስቀደስ ሲል ነው።

ድል አድራጊው ንጉሥ የሚያደርገው ግስጋሴ

3, 4. (ሀ) በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 63 ላይ የተጠቀሰው ትንቢት ከየትኛው ሁኔታ ጋር የተያያዘ ነው? (ለ) ኢሳይያስ ምን ተመልክቷል? አንዳንድ ምሁራን የተዋጊውን ማንነት በተመለከተ ምን አስተያየት ሰንዝረዋል?

3 በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 62 ላይ የሰፈረው ዘገባ አይሁዳውያን ከባቢሎን ግዞት ነፃ ወጥተው ወደ ትውልድ አገራቸው ስለሚመለሱበት ሁኔታ የሚያትት ነው። በመሆኑም ወደ ትውልድ አገራቸው የተመለሱት አይሁዳውያን ቀሪዎች ከሌሎች ጠላቶቻቸው ጥቃት ሊደርስባቸው እንደሚችል በማሰብ ስጋት ሊያድርባቸው ይገባል? የሚል ጥያቄ መነሳቱ የተገባ ነው። ኢሳይያስ ቀጥሎ ያየው ራእይ ከዚህ ስጋት የሚያሳርፍ ነው። ትንቢቱ እንዲህ በማለት ይጀምራል:- “ይህ ከኤዶምያስ፣ ልብሱም የቀላ ከባሶራ የሚመጣ፣ አለባበሱ ያማረ፣ በጉልበቱ ጽናት የሚራመድ ማን ነው?”​—⁠ኢሳይያስ 63:1ሀ

4 ኢሳይያስ ከፍተኛ ጉልበት ያለውና ድል አድራጊ የሆነ ተዋጊ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገሰግስ ተመልክቷል። ያማረው አለባበሱ በጣም ከፍተኛ ሥልጣን እንዳለው ይጠቁማል። በመምጣት ላይ ያለው እጅግ ታዋቂ ከሆነችው የኤዶም ከተማ ማለትም ከባሶራ ሲሆን ይህም በጠላት ምድር ላይ ታላቅ ድል እንደተቀዳጀ ያመለክታል። ይህ ተዋጊ ማን ሊሆን ይችላል? አንዳንድ ምሁራን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ ይናገራሉ። ሌሎች ደግሞ የአይሁድ ወታደራዊ መሪ የሆነው ጁዳ ማካቢስ ነው የሚል እምነት አላቸው። ይሁን እንጂ ተዋጊው ራሱ ከላይ ለቀረበው ጥያቄ እንደሚከተለው በማለት መልስ በሰጠበት ጊዜ ማንነቱን ግልጽ አድርጓል:- “በጽድቅ የምናገር ለማዳንም የምበረታ እኔ ነኝ።”​—⁠ኢሳይያስ 63:1ለ

5. ኢሳይያስ ያየው ተዋጊ ማን ነው? እንደዚያ ብለህ የመለስከውስ ለምንድን ነው?

5 ይህ ተዋጊ ይሖዋ አምላክ ራሱ እንደሆነ ምንም ጥርጥር የለውም። በሌሎች ጥቅሶች ላይ ይሖዋ ‘ከፍተኛ ኃይል’ እንዳለውና ‘ጽድቅን እንደሚናገር’ ተገልጿል። (ኢሳይያስ 40:​26፤ 45:​19, 23) ተዋጊው የለበሰው ያማረ ልብስ “አቤቱ አምላኬ ሆይ፣ አንተ እጅግ ታላቅ ነህ፤ ክብርንና ግርማን ለበስህ” የሚሉትን የመዝሙራዊው ቃላት ያስታውሰናል። (መዝሙር 104:1) ይሖዋ የፍቅር አምላክ ቢሆንም እንኳ አስፈላጊ በሚሆንበት ጊዜ ተዋጊ እንደሚሆን መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ያሳያል።​—⁠ኢሳይያስ 34:​2፤ 1 ዮሐንስ 4:​16

6. ይሖዋ በኤዶም ውጊያ አድርጎ የተመለሰው ለምንድን ነው?

6 ይሁንና ይሖዋ በኤዶም ውጊያ አድርጎ የተመለሰው ለምንድን ነው? አባታቸው ኤሳው የጠነሰሰውን ጥላቻ ይዘው የኖሩት ኤዶማውያን የአምላክ የቃል ኪዳን ሕዝብ የረጅም ጊዜ ጠላቶች ናቸው። (ዘፍጥረት 25:​24-34፤ ዘኍልቁ 20:​14-21) በተለይ የባቢሎን ወታደሮች ኢየሩሳሌምን ባወደሙበት ጊዜ ኤዶማውያን ከኋላ ሆነው ያበረታቱ ስለነበር ኤዶም ለይሁዳ ምን ያህል ጥላቻ እንደነበራት በግልጽ ታይቷል። (መዝሙር 137:​7) ይሖዋ እንዲህ ያለውን ጥላቻ በእሱ ላይ እንደተፈጸመ በደል አድርጎ ይመለከተዋል። በኤዶም ላይ የበቀል ሰይፉን ለመምዘዝ ቆርጦ መነሳቱ ምንም አያስደንቅም።​—⁠ኢሳይያስ 34:​5-15፤ ኤርምያስ 49:​7-22

7. (ሀ) በኤዶም ላይ የተነገረው ትንቢት የመጀመሪያ ፍጻሜውን ያገኘው እንዴት ነው? (ለ) ኤዶም ማንን ታመለክታለች?

7 በመሆኑም ኢሳይያስ ያየው ራእይ ከኢየሩሳሌም የሚመለሱትን አይሁዶች በእጅጉ የሚያበረታታ ነው። በአዲሱ መኖሪያቸው ከስጋት ነፃ ሆነው መኖር እንደሚችሉ ያረጋግጥላቸዋል። እንዲያውም በነቢዩ ሚልክያስ ዘመን አምላክ የኤዶምን ተራሮች ‘በረሃ ከማድረጉም በላይ ርስቱንም ለምድረ በዳ ቀበሮች አሳልፎ ሰጥቷል።’ (ሚልክያስ 1:​3) ይህ ማለት ታዲያ የኢሳይያስ ትንቢት በሚልክያስ ዘመን ሙሉ ፍጻሜውን አግኝቷል ማለት ነው? እንደዚያ ማለት አይደለም። ኤዶም ብትወድምም እንኳ የፈረሱ ከተሞቿን መልሳ ለመገንባት ቆርጣ ተነስታ የነበረ ከመሆኑም በላይ ሚልክያስም ቢሆን በመቀጠል ኤዶምን “ክፉ ምድር” [አ.መ.ት ] እና “እግዚአብሔር ለዘላለም የተቈጣው ሕዝብ” ሲል ጠርቷታል። * (ሚልክያስ 1:​4, 5) ይሁን እንጂ በትንቢቱ መሠረት ኤዶም የምታመለክተው የኤሳውን ዝርያዎች ብቻ አይደለም። ከዚህ ይልቅ የይሖዋ አምላኪዎች ጠላቶች የሆኑትን ብሔራት በሙሉ ታመለክታለች። የሕዝበ ክርስትና ተከታይ የሆኑ አገሮች ለዚህ ዋነኛ ተጠቃሽ ናቸው። ይህች ዘመናዊት ኤዶም ምን ይደርስባት ይሆን?

የወይን መጥመቂያው

8, 9. (ሀ) ኢሳይያስ የተመለከተው ተዋጊ በምን ሥራ ተጠምዶ ነበር? (ለ) ምሳሌያዊው የወይን መጥመቂያ የሚረገጠው መቼና እንዴት ነው?

8 ኢሳይያስ ከኤዶም የተመለሰውን ተዋጊ “ቀሚስህ ስለ ምን ቀላ? ልብስህስ በወይን መጥመቂያ እንደሚረግጥ ሰው ልብስ ስለ ምን መሰለ?” ሲል ጠየቀው። ይሖዋም እንዲህ ሲል መለሰ:- “መጥመቂያውን ብቻዬን ረግጫለሁ፣ ከአሕዛብም አንድ ሰው ከእኔ ጋር አልነበረም፤ በቁጣዬ ረገጥኋቸው በመዓቴም ቀጠቀጥኋቸው፤ ደማቸውም በልብሴ ላይ ተረጭቶአል፣ ልብሴንም ሁሉ አሳድፌአለሁ።”​—⁠ኢሳይያስ 63:2, 3

9 ይህ ሕያው የሆነ መግለጫ ከፍተኛ እልቂትን የሚያመለክት ነው። የአምላክ ያማረ ልብስ እንኳ ሳይቀር በወይን መጥመቂያ እንደሚረግጥ ሰው ልብስ ተበክሏል። የወይን መጥመቂያ ይሖዋ አምላክ ጠላቶቹን ለማጥፋት እርምጃ በሚወስድበት ጊዜ የሚገቡበትን ወጥመድ ለመግለጽ የሚያስችል ተስማሚ ተምሳሌት ነው። ይህ ምሳሌያዊ የወይን መጥመቂያ የሚረገጠው መቼ ነው? የኢዩኤልና የሐዋርያው ዮሐንስ ትንቢቶችም ስለ ምሳሌያዊ የወይን መጥመቂያ ይናገራሉ። በእነዚህ ትንቢቶች ላይ የተጠቀሰው የወይን መጥመቂያ የሚረገጠው ይሖዋ ጠላቶቹን በአርማጌዶን በሚያጠፋበት ጊዜ ነው። (ኢዩኤል 3:​13፤ ራእይ 14:​18-20፤ 16:​16) በኢሳይያስ ላይ የተጠቀሰው ትንቢታዊ የወይን መጥመቂያም በዚያን ጊዜ የሚፈጸመውን ሁኔታ የሚያመለክት ነው።

10. ይሖዋ የወይን መጥመቂያውን ብቻውን እንደረገጠ አድርጎ የተናገረው ለምንድን ነው?

10 ይሁንና ይሖዋ ከአሕዛብ አንድ ሰው ሳይኖር የወይን መጥመቂያውን ብቻውን እንደረገጠ የተናገረው ለምንድን ነው? ኢየሱስ ክርስቶስ የአምላክ ወኪል ሆኖ የወይን መጥመቂያውን በግንባር ቀደምትነት ይረግጥ የለምን? (ራእይ 19:​11-16) አዎን፣ ይሁንና ይሖዋ እዚህ ላይ እየተናገረ ያለው ስለ ሰዎች እንጂ ስለ መንፈሳዊ ፍጥረታት አይደለም። ማንኛውም ሰብዓዊ ፍጥረት የሰይጣንን ተከታዮች ከምድረ ገጽ ማጥፋት እንደማይችል ማመልከቱ ነው። (ኢሳይያስ 59:​15, 16) ሙሉ በሙሉ ተጨፍልቀው እስኪጠፉ ድረስ በቁጣው የሚረግጣቸው ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ነው።

11. (ሀ) ይሖዋ ‘የበቀል ቀን’ የሚያመጣው ለምንድን ነው? (ለ) ይሖዋ በጥንት ዘመን ‘የተቤዠው’ እነማንን ነው? በዘመናችንስ?

11 ይሖዋ ይህን ሥራ ራሱ የሚያከናውንበትን ምክንያት እንዲህ ሲል አክሎ ገልጿል:- “የምበቀልበት ቀን በልቤ ነውና፣ የምቤዥበትም ዓመት ደርሶአልና።” (ኢሳይያስ 63:4) * ሕዝቡን በሚያጠቁ ሰዎች ላይ የበቀል እርምጃ የመውሰድ መብት ያለው ይሖዋ ብቻ ነው። (ዘዳግም 32:​35) በጥንት ዘመን ይሖዋ ‘የተቤዠው’ በባቢሎናውያን እጅ ወድቀው ብዙ መከራ ያሳለፉትን አይሁዳውያን ነበር። (ኢሳይያስ 35:​10፤ 43:​1፤ 48:​20) በዘመናችን የተቤዠው ደግሞ ቅቡዓን ቀሪዎችን ነው። (ራእይ 12:​17) እንደ ጥንቶቹ የአምላክ ሕዝቦች ቅቡዓን ቀሪዎችም ከሃይማኖታዊ ግዞት ነፃ ወጥተዋል። በተጨማሪም ልክ እንደ አይሁዳውያን ቅቡዓኑም ሆኑ ‘የሌሎች በጎች’ አባላት የሆኑ አጋሮቻቸው ስደትና ተቃውሞ ሲደርስባቸው ቆይቷል። (ዮሐንስ 10:​16) በመሆኑም የኢሳይያስ ትንቢት በዛሬው ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖች አምላክ የወሰነው ጊዜ ሲደርስ እነሱን ለመታደግ ሲል እጁን ጣልቃ አስገብቶ እርምጃ እንደሚወስድ እርግጠኞች እንዲሆኑ ዋስትና ይሰጣቸዋል።

12, 13. (ሀ) ይሖዋን የሚረዳው የማይኖረው በምን መንገድ ነው? (ለ) የይሖዋ ክንድ መዳን የሚያስገኘው እንዴት ነው? ቁጣውስ የሚያግዘው እንዴት ነው?

12 ይሖዋ በመቀጠል እንዲህ አለ:- “ተመለከትሁ፣ የሚረዳም አልተገኘም፤ የሚያግዝም አልነበረምና ተደነቅሁ፤ ስለዚህ የገዛ ክንዴ መድኃኒት አመጣልኝ፣ ቁጣዬም እርሱ አገዘኝ። በቁጣዬም አሕዛብን ረገጥሁ በመዓቴም ቀጠቀጥኋቸው፣ ደማቸውንም ወደ ምድር አፈሰስሁት።”​—⁠ኢሳይያስ 63:5, 6

13 በይሖዋ ታላቅ የበቀል ቀን ይሖዋን እንደረዳ አድርጎ ሊናገር የሚችል ሰው አይኖርም። ይሖዋም ቢሆን ፈቃዱን ለማስፈጸም የማንንም ሰው እርዳታ አይሻም። * እጅግ ኃያልና ብርቱ የሆነው ክንዱ ዓላማውን በሚገባ መፈጸም ይችላል። (መዝሙር 44:​3፤ 98:​1፤ ኤርምያስ 27:​5) ከዚህም በተጨማሪ ቁጣው ያግዘዋል። እንዴት? የአምላክ ቁጣ ከቁጥጥር ውጪ የሆነ ስሜት ሳይሆን የጽድቅ ቁጣ በመሆኑ ነው። ይሖዋ ምንጊዜም ትክክለኛ በሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶች ላይ የተመረኮዘ እርምጃ የሚወስድ በመሆኑ ቁጣው የጠላቶቹን ‘ደም ወደ ምድር በማፍሰስ’ የኀፍረት ማቅና ሽንፈት እንዲያከናንባቸው ያነሳሳዋል እንዲሁም ያግዘዋል።​—⁠መዝሙር 75:​8፤ ኢሳይያስ 25:​10፤ 26:​5

የአምላክ ፍቅራዊ ደግነት

14. ኢሳይያስ ምን ተገቢ የሆኑ ማሳሰቢያዎችን ሰጥቷል?

14 በቀድሞ ዘመን አይሁዳውያን ይሖዋ ለእነሱ ሲል ላደረጋቸው ነገሮች የነበራቸው አድናቆት የጠፋው ወዲያውኑ ነበር። በመሆኑም ኢሳይያስ ይሖዋ እነዚህን ነገሮች ያደረገላቸው ለምን እንደሆነ መለስ ብለው እንዲያስቡ ማድረጉ የተገባ ነው። ኢሳይያስ እንዲህ አለ:- “እግዚአብሔር እንደ ሰጠን ሁሉ፣ የእግዚአብሔርን ቸርነትና [“ፍቅራዊ ደግነት፣” NW ] የእግዚአብሔርን ምስጋና፣ እንደ ምሕረቱና እንደ ቸርነቱም [“ፍቅራዊ ደግነቱ፣” NW ] ብዛት ለእስራኤል ቤት የሰጠውን ትልቅ በጎነት አሳስባለሁ። እርሱም:- በእውነት ሕዝቤ፣ ሐሰትን የማያደርጉ ልጆች፣ ናቸው አለ፤ መድኃኒትም ሆነላቸው። በጭንቃቸው ሁሉ እርሱ ተጨነቀ፣ የፊቱም መልአክ አዳናቸው፤ በፍቅሩና በርኅራኄውም ተቤዣቸው፣ በቀደመውም ዘመን ሁሉ አንሥቶ ተሸከማቸው።”​—⁠ኢሳይያስ 63:7-9

15. ይሖዋ በግብጽ ለነበሩት የአብርሃም ዘሮች ፍቅራዊ ደግነት ያሳየው እንዴትና ለምንድን ነው?

15 ይሖዋ ፍቅራዊ ደግነት በማሳየት ረገድ ግሩም የሆነ ምሳሌ ትቷል! (መዝሙር 36:​7 NW ፤ መዝ. 62:​12 NW ) ይሖዋ ከአብርሃም ጋር የጠበቀ ወዳጅነት መሥርቶ ነበር። (ሚክያስ 7:​20) በዘሩ የምድር አሕዛብ ሁሉ ራሳቸውን እንደሚባርኩ ለአብርሃም ቃል ገብቶለታል። (ዘፍጥረት 22:​17, 18) ይሖዋ ለእስራኤል ቤት ትልቅ በጎነት በማሳየት ለአብርሃም የገባውን ቃል ጠብቋል። በታማኝነት ቃሉን ጠብቆ ካከናወናቸው ተግባሮች መካከል የአብርሃምን ዘሮች ከግብጽ ባርነት ነፃ በማውጣት የፈጸመው ታላቅ ሥራ በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል።​—⁠ዘጸአት 14:​30

16. (ሀ) ይሖዋ ከእስራኤል ጋር ቃል ኪዳን ሲገባ ምን አመለካከት ነበረው? (ለ) አምላክ ሕዝቡን የሚይዘው በምን መንገድ ነው?

16 ይሖዋ እስራኤላውያንን ከግብጽ ነፃ ካወጣቸው በኋላ ወደ ሲና ተራራ በመውሰድ እንዲህ ሲል ቃል ገባላቸው:- “ቃሌን በእውነት ብትሰሙ ኪዳኔንም ብትጠብቁ፣ . . . የተመረጠ ርስት ትሆኑልኛላችሁ፤ እናንተም የካህናት መንግሥት የተቀደሰም ሕዝብ ትሆኑልኛላችሁ።” (ዘጸአት 19:5, 6) ይሖዋ ይህን ግብዣ ሲያቀርብላቸው እያታለላቸው ነበር? በፍጹም፤ ምክንያቱም ይሖዋ “በእውነት ሕዝቤ፣ ሐሰትን የማያደርጉ ልጆች፣ ናቸው” በማለት እንደተናገረ ኢሳይያስ ገልጿል። አንድ ምሁር የሚከተለውን አስተያየት ሰጥተዋል:- “እዚህ ቦታ ላይ ‘በእውነት’ የሚለው ቃል የገባው ሉዓላዊው ጌታ የደነገገው በመሆኑ ወይም ይሖዋ አስቀድሞ የማወቅ ችሎታ ስላለው አይደለም። ይሖዋ በሕዝቡ ተስፋ ሊያደርግና እምነት ሊጥልባቸው የቻለው በፍቅሩ ተገፋፍቶ ነው።” አዎን፣ ይሖዋ ቃል ኪዳን የገባው ሕዝቡ እንዲሳካላቸው ካለው ቅን ምኞት በመነሳት ነው። በግልጽ የሚታይ ድክመት የነበረባቸው ቢሆንም እንኳ እምነት ጥሎባቸዋል። በአምላኪዎቹ ላይ እንዲህ ያለ እምነት የሚጥልን አምላክ ማምለክ ምንኛ የሚያስደስት ነው! በዛሬው ጊዜ ያሉ ሽማግሌዎችም የአምላክ ሕዝቦች ባላቸው መልካም ጎን ላይ በማተኮርና ልክ እንደ ይሖዋ በእነሱ ላይ እምነት በመጣል በአደራ የተሰጧቸውን የጉባኤው አባላት በእጅጉ ማጠንከር ይችላሉ።​—⁠2 ተሰሎንቄ 3:​4፤ ዕብራውያን 6:​9, 10

17. (ሀ) ይሖዋ ለእስራኤላውያን ያለውን ፍቅር ያሳየው እንዴት ነው? (ለ) በዛሬው ጊዜ ምን ትምክህት ሊያድርብን ይችላል?

17 ያም ሆኖ መዝሙራዊው እስራኤላውያንን አስመልክቶ ሲናገር “ታላቅ ነገርንም በግብጽ . . . ያደረገውን ያዳናቸውንም እግዚአብሔርን ረሱ” ብሏል። (መዝሙር 106:21) ዓመፀኝነታቸውና አንገተ ደንዳናነታቸው ብዙውን ጊዜ ለከፋ አደጋ ይዳርጋቸው ነበር። (ዘዳግም 9:​6) ይሖዋ ለሕዝቡ ፍቅራዊ ደግነት ማሳየቱን አቁሞ ነበርን? በፍጹም፤ ከዚህ ይልቅ ኢሳይያስ እንደገለጸው “በጭንቃቸው ሁሉ እርሱ ተጨነቀ።” ይሖዋ ምንኛ ርኅሩኅ ነው! ልክ እንደ ማንኛውም አፍቃሪ ወላጅ፣ አምላክ ልጆቹ ራሳቸው በፈጸሙት ስህተት ሳቢያም እንኳ መከራ ሲደርስባቸው በእጅጉ ያዝን ነበር። አስቀድሞ በተተነበየው መሠረት በተስፋይቱ ምድር ይመራቸው ዘንድ ‘የፊቱን መልአክ’ በመላክ ፍቅሩን ገልጾላቸዋል። ይህ መልአክ ሰው ሆኖ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት በሰማይ ይኖር የነበረው ኢየሱስ መሆን አለበት። (ዘጸአት 23:​20) በመሆኑም ይሖዋ “ሰው ልጁን እንዲሸከም” ሕዝቡን አንሥቶ ተሸክሟቸዋል። (ዘዳግም 1:​31፤ መዝሙር 106:​10) በተመሳሳይ ሁኔታ በዛሬው ጊዜም ይሖዋ የሚደርስብንን መከራ እንደሚያውቅና ከባድ ችግር በሚገጥመን ጊዜ እንደሚያዝንልን እርግጠኞች መሆን እንችላለን። ‘ስለ እኛ የሚያስብ በመሆኑ የሚያስጨንቀንን ሁሉ በእርሱ ላይ መጣል’ እንችላለን።​—⁠1 ጴጥሮስ 5:​7

አምላክ ጠላት ይሆናል

18. ይሖዋ ለሕዝቡ ጠላት የሆነው ለምንድን ነው?

18 ይሁን እንጂ የአምላክን ፍቅራዊ ደግነት በፍጹም አላግባብ ልንጠቀምበት አይገባም። ኢሳይያስ በመቀጠል እንዲህ አለ:- “እነርሱ ግን ዐመፁ ቅዱስ መንፈሱንም አስመረሩ፤ ስለዚህ ተመልሶ ጠላት ሆናቸው፣ እርሱም ተዋጋቸው።” (ኢሳይያስ 63:10) ይሖዋ መሐሪና አሳቢ አምላክ ቢሆንም እንኳ ‘በደለኛውን ሳይቀጣ ዝም ብሎ እንደማይተው’ [አ.መ.ት ] አስጠንቅቋል። (ዘጸአት 34:​6, 7) እስራኤላውያን በተደጋጋሚ በአምላክ ላይ በማመፅ ራሳቸውን ለቅጣት ዳርገዋል። ሙሴ እንዲህ ሲል አሳስቧቸው ነበር:- “አምላክህን እግዚአብሔርን በምድረ በዳ እንዳስቈጣኸው፤ ከግብፅ አገር ከወጣህበት ቀን ጀምሮ ወደዚህ ስፍራ እስከ መጣችሁ ድረስ በእግዚአብሔር ላይ እንዳመፃችሁ . . . አትርሳ።” (ዘዳግም 9:7) የአምላክ መንፈስ የሚያሳድርባቸውን በጎ ተጽዕኖ ለመቀበል አሻፈረን በማለት መንፈሱን አስመርረዋል ወይም አሳዝነዋል። (ኤፌሶን 4:​30) ይሖዋ ጠላታቸው እንዲሆን አስገድደውታል።​—⁠ዘሌዋውያን 26:​17፤ ዘዳግም 28:​63

19, 20. አይሁዳውያን የሚያስታውሷቸው ነገሮች ምንድን ናቸው? ለምንስ?

19 አንዳንድ አይሁዳውያን መከራ እየተቀበሉ በነበረበት ወቅት ወደ ኋላ መለስ ብለው ቀደም ባሉት ዘመናት የተከናወኑትን ነገሮች አስበዋል። ኢሳይያስ እንዲህ አለ:- “እርሱም እንዲህ ብሎ የቀደመውን ዘመን አሰበ:- የበጎቹን እረኛ ከባሕሩ ያወጣው ወዴት ነው ያለ? ቅዱስ መንፈሱንም በመካከላቸው ያኖረ ወዴት ነው ያለ? የከበረውንም ክንድ በሙሴ ቀኝ ያስሄደ፣ ለራሱም የዘላለምን ስም ያደርግ ዘንድ ውኃውን በፊታቸው የከፈለ፣ በምድረ በዳም እንደሚያልፍ ፈረስ፣ በቀላይ ውስጥ ያለ ዕንቅፋት ያሳለፋቸው ወዴት ነው ያለ? ወደ ሸለቆ እንደሚወርዱ ከብቶች፣ እንዲሁ የእግዚአብሔር መንፈስ ወደ ዕረፍት አመጣቸው።”​—⁠ኢሳይያስ 63:11-14ሀ  *

20 አዎን፣ አይሁዳውያን በአምላክ ላይ በማመፃቸው ምክንያት የደረሰባቸው መከራ ይሖዋ ጠላታቸው ሳይሆን አዳኛቸው የነበረባቸውን ጊዜያት መልሰው ለማግኘት እንዲመኙ አድርጓቸዋል። ‘እረኞቻቸው’ የነበሩት ሙሴና አሮን ቀይ ባሕርን ያላንዳች ችግር እንዴት እንዳሻገሯቸው ያስታውሳሉ። (መዝሙር 77:​20፤ ኢሳይያስ 51:​10) የአምላክን መንፈስ ከማሳዘን ይልቅ በሙሴና በሌሎች በይሖዋ የተሾሙ ሽማግሌዎች በኩል የመንፈሱን አመራር ያገኙበትን ጊዜ ያስታውሳሉ። (ዘኍልቁ 11:​16, 17) ከዚህም በተጨማሪ ይሖዋ እነሱን ለመርዳት ሲል በሙሴ በኩል ‘የከበረውን ብርቱ ክንዱን’ የተጠቀመባቸው ጊዜያትም ትዝ ይሏቸዋል። ውሎ አድሮ አምላክ ከታላቁና እጅግ ከሚያስፈራው ምድረ በዳ አውጥቶ የዕረፍት ቦታ ወደሆነችውና ማርና ወተት ወደምታፈስሰው ምድር ወስዷቸዋል። (ዘዳግም 1:​19፤ ኢያሱ 5:​6፤ 22:​4) አሁን ግን እስራኤላውያን ከአምላክ ጋር የነበራቸውን ጥሩ ዝምድና በማጣታቸው ለመከራ ተዳርገዋል።

‘ለራሱ የከበረ ስም ያደርጋል’

21. (ሀ) የእስራኤል ሕዝብ ከአምላክ ስም ጋር በተያያዘ ምን ታላቅ መብት ነበረው? (ለ) አምላክ የአብርሃምን ዝርያዎች ከግብጽ ነፃ ያወጣበት ዋነኛው ምክንያት ምንድን ነው?

21 ያም ሆኖ እስራኤላውያን የደረሰባቸው ቁሳዊ ኪሳራ በገዛ እጃቸው ካጡት መብት ጋር ሲነጻጸር ከቁብ የሚቆጠር አይደለም። የአምላክን ስም በማስከበር ረገድ የነበራቸውን ትልቅ ድርሻ አጥተዋል። ሙሴ ለእስራኤላውያን የሚከተለውን ተስፋ ሰጥቷቸው ነበር:- “የአምላክህን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ብትጠብቅ፣ በመንገዱም ብትሄድ፣ እግዚአብሔር እንደ ማለልህ ለእርሱ የተቀደሰ ሕዝብ አድርጎ ያቆምሃል። የምድር አሕዛብም ሁሉ የእግዚአብሔር ስም በአንተ ላይ እንደ ተጠራ አይተው ይፈሩሃል።” (ዘዳግም 28:9, 10) ይሖዋ የአብርሃም ዝርያዎችን ከግብጽ ባርነት ነፃ በማውጣት የታደጋቸው የተሻለ ወይም አስደሳች ሕይወት እንዲያገኙ ብቻ ብሎ አልነበረም። ከዚህ የላቀ ቦታ ለሚሰጠው ነገር ማለትም ለስሙ ሲል የወሰደው እርምጃ ነው። አዎን፣ ይሖዋ ይህን ያደረገው ስሙ “በምድር ሁሉ ላይ ይነገር ዘንድ” ነው። (ዘጸአት 9:​15, 16) እስራኤላውያን በምድረ በዳ ባመጹበት ጊዜም አምላክ ምሕረት ያደረገላቸው እንዲሁ ስላዘነላቸው ብቻ አልነበረም። ይሖዋ ራሱ “በአሕዛብ ፊት ስሜ እንዳይረክስ ብዬ ስለ ስሜ ሠራሁ” ሲል ተናግሯል።​—⁠ሕዝቅኤል 20:​8-10

22. (ሀ) አምላክ ወደፊት ለሕዝቡ ዳግመኛ የሚዋጋው ለምንድን ነው? (ለ) ለአምላክ ስም ያለን ፍቅር አኗኗራችንን የሚነካው በምን መንገድ ነው?

22 ኢሳይያስ እንደሚከተለው በማለት ይህን ትንቢት ኃይለኛ መልእክት በሚያስተላልፍ መንገድ ደመደመ:- “ለራስህ የከበረ ስም ታደርግ ዘንድ ሕዝብን መራህ።” (ኢሳይያስ 63:14ለ) ይሖዋ ለሕዝቡ በከፍተኛ ደረጃ የሚዋጋው ለምን እንደሆነ ከዚህ በግልጽ መረዳት ይቻላል። ለራሱ የከበረ ስም ለማድረግ ሲል ነው። በመሆኑም የኢሳይያስ ትንቢት የይሖዋን ስም መሸከም ልዩ መብትና ከፍተኛ ኃላፊነት እንደሆነ አጥብቆ ያሳስበናል። በዛሬው ጊዜ ያሉ እውነተኛ ክርስቲያኖች የይሖዋን ስም ከሕይወታቸው አስበልጠው ይወዱታል። (ኢሳይያስ 56:​6፤ ዕብራውያን 6:​10) በአምላክ ቅዱስ ስም ላይ ነቀፋ ሊያመጣ ከሚችል ነገር ሁሉ ይርቃሉ። ለአምላክ ታማኝ በመሆን እሱ በታማኝነት ላሳያቸው ፍቅር አዎንታዊ ምላሽ ይሰጣሉ። ከዚህም በተጨማሪ የይሖዋን ታላቅ ስም የሚወዱ በመሆናቸው ጠላቶቹን በቁጣው የወይን መጥመቂያ የሚረግጥበትን ቀን ለማየት ይናፍቃሉ። ያን ቀን በጉጉት የሚጠባበቁት ለራሳቸው ጥቅም በማሰብ ሳይሆን የሚወዱት አምላካቸው ስም ሲከበር ለማየት ነው።​—⁠ማቴዎስ 6:​9

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.7 በመጀመሪያው መቶ ዘመን እዘአ ሄሮድስ በሚል ስም ይታወቁ የነበሩት ገዥዎች ኤዶማውያን ነበሩ።

^ አን.11 “የምቤዥበትም ዓመት” የሚለው አገላለጽ ይሖዋ ‘የሚበቀልበትን’ ጊዜ የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። በ⁠ኢሳይያስ 34:​8 ላይም ከዚህ ጋር ተመሳሳይ የሆኑ መግለጫዎች እንዴት ጎን ለጎን እንደተሠራባቸው ተመልከት።

^ አን.13 ይሖዋ የሚረዳው ባለመገኘቱ እንደተደነቀ ገልጿል። ኢየሱስ ከሞተ ወደ 2, 000 ከሚጠጉ ዓመታት በኋላም ኃያላን ሰዎች የአምላክን ፈቃድ የሚቃወሙ መሆናቸው እጅግ የሚያስገርም ሊሆን ይችላል።​—⁠መዝሙር 2:​2-12፤ ኢሳይያስ 59:​16

^ አን.19 ‘እርሱም የቀደመውን ዘመን አሰበ’ የሚለው አገላለጽ የቀድሞውን ዘመን ያሰበው ይሖዋ እንደሆነ ያመለክታል ብሎ መደምደም አይቻልም። ቀጥሎ የሰፈሩት ቃላት የይሖዋን ሳይሆን የአምላክን ሕዝብ ስሜት የሚገልጹ ናቸው። በመሆኑም ሶንሲኖ ቡክስ ኦቭ ዘ ባይብል ይህን አገላለጽ “ሕዝቡም የቀደመውን ዘመን አሰቡ” ሲል ተርጉሞታል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 359 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሖዋ በሕዝቡ ላይ ከፍተኛ እምነት ጥሎ ነበር